ይህ ጾም ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ከርሰቶስ በተወለደ በ 30 ዓመቱ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንሰ እጅ ጥር 11 ቀን በዮርዳኖስ ከተጠመቀ በኋላ ከጥር 12 ቀን እስከ የካቲት 21 ቀን ድረስ 40 መዓልትና ሌሊት ከቆመ ሳያርፍ ከዘረጋ ሳያጥፍ በትኅርምት በገዳመ ቆሮንጦስ የጾመው ጾም በመሆኑ ዐቢይ ተብሏል፡፡ [ማቴ. 4.1]፡፡ ጾሙ የተለየ፣ የከበረ፣ የተቀደሰ፣ የጸና፣ የተከለከለ እና እነዚህን የመሰሉ ተቀጽላ ስሞችን ያገኛል፡፡ እኛም ጌታ የጾመውን ለማስታወስ በረከቱን ለማግኘት በግብር እርሱን ለመምሰል የሥጋ ፈቃዳችንን ለነፍስ ፈቃዳችን ለማስገዛት እንጾመዋለን፡፡ ጌታችን የጾመው እቀደስ እከብር ወይም እነፃ ብሎ ሳይሆን ለእኛ አርአያ ለመሆን ነው፡፡
❖ ለምን ጾሙን አርባ ቀንና አርባ ሌሊት አደረገው?
✓ እግዚአብሔር አምላካችን የፈጠረውን የሰው ልጆችን አባት አዳምን በልጅነት አክብሮ ገነት ያስገባው በፈጠረው በአርባ ቀኑ ነው፡፡ "ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ እግዚአብሔር ዘገብሮ ለአዳም" አዳምን የፈጠረ እግዚአብሔር ቅዱስ ነው እያሉ እያመሰገነ መላእክት ወደ ገነት አስገብተውታል፡፡ [ቀሌ 4]
✓ ለአዳም አርባ ቀን ከተፈጸመለት በኋላ ወደ ገነት አስገባው፡፡ ሔዋንንም በኹለት አርባ ማለትም በሰማኒያ ቀኑዋ ወደ ገነት አስገባት፡፡ [ኩፋ. 4:12]፡፡
✓ በተጨማሪም አዳም ትእዛዘ እግዚአብሔርን ካፈረሰ በኋላ ዲያቢሎስ በአቋራጭ መጥቶ አስወጣው እንጂ ሱባኤ የገባው ለአርባ ቀናት ነበር፡፡ ይህን አርባ ቀን የሰው ልጆች ከስሕተት በኋላ በቀንም ሆነ በዓመት ለጾም፣ ለሱባኤ፣ ከዚያ አልፎ ለመትነት አገልግሏል፡፡
✓ በኦሪት ዘፍጥረት እንደምናነበው የሰው ልጅ በንፍር ውኃ የተቀጣው አርባ መአልትና ሌሊት ነበር፡፡ "አርባ ቀንና አርባ ሌሊት በምድር ላይ ዝናብ አዘንባለሁና የፈጠርሁትንም ፍጥረት በምድር ላይ አጠፋለሁና፡፡" [ዘፍ. 7:12]፡፡ የሰማይ መስኮቶች ተከፈቱ ዝናቡም አርባ መአልትና አርባ ሌሊት በምድር ላይ ሆነ፡፡ [ዘፍ. 7:12]፡፡
✓ በዚህ ዓይነት አርባ ቀን እግዚአብሔር ሰውን እንደ ቀጣበት እናያለን፤ መቅጣት ብቻ ሳይሆን በዚህ የአርባ መአልትና የአርባ ሌሊት ምድር በዛበት ርኲሰት አጥቧታል፡፡ ምክንያቱም የጥምቀት ምሳሌ ነውና፡፡ ማየ አይህ (የጥፋት ውኃ የጥምታት ምሳሌ ለመሆኑ ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ በማለት ጽፏል "ጥቂቶች ማለት ስምንት ነፍሳት በውኃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኅ ዘመን በቆየ ጊዜ ቀድሞ አልታዘዙም ይህም ውኃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡" [2ኛጴጥ.3.20 ና 21]፤ አሁንም ከዚሁ ሳንርቅ የመርከቧ መስኮቶች የተከፈቱት በአርባ ቀን መሆኑን ይገልጻል፡፡ "ከአርባ ቀን በኋላ ኖኅ የሠራውን የመርከቢቱን መስኮት ከፈተ" [ዘፍ. 8.6]፡፡ መርከቧ የቤተክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡ እስራኤል ወደ ምድረ ርስት ያደረጉት ጉዞ አርባ ዓመት እንደ ፈጀ ተጽፏል፡፡ ይህም መንገድ ደግሞ የአርባ ቀን መንገድ ነበር፤ በእግዚአብሔር ቁጣ ወደ አርባ ዓመታት ተለወጠ እንጂ፡፡ "በሙሴ ተመርተው ከግብጽ የወጡ ሁሉ አይደሉምን? አርባ ዓመትም የተቆጣባቸው እነማን ነበሩ? ሬሳቸው በምድረ በዳ የወደቀ" [ዕብ. 3.7-19] ሲል ቅዱስ ጳውሎስ ጽፎታል፡፡
✓ እስራኤል አርባ ዘመን መና ከደመና እየወረደላቸው ተመግበዋል፤ ውኃ ከዐለት እየፈለቀላቸው ጠጥተዋል፡፡ ሲያምጹም ተቀጥተዋል፡፡ ሙሴ ወንድሞቹን እስራኤልን ለመጎብኘት የመጣው በአርባ ዓመት ነበር "በዚያም ወራት እንዲህ ሆነ ሙሴ ጎበዝ በሆነ ጊዜ ወንድሞቹ ወጣ የሥራቸውን መከራ ተመለከተ" [ዘጸ. 3:11፤ ሐዋ. 7:23] የተሰደደውም በዚሁ ዕድሜው ነው፡፡ በምድያም በግ በመጠበቅ አርባ ዘመን ኖሯል፡፡ እንደገና እስራኤል ከግብጽ ባርነት ነጻ እንዲያወጣ እግዚአብሔር የላከው በአርባ ዘመን ነበር፡፡ "አርባ ዓመትም ሲሞላ የጌታ መልአክ በሲና ተራራ ምድረ በዳ ታየው፡፡" [ዘጸ. 3:30]፡፡
✓ ይህም ብቻ አይደለም ሙሴ ለዚህ አገልግሎት በተመረጠበት ጊዜ በሲና ተራራ አርባ ቀንና ሌሊት ጾሟል "ሙሴም ወደ ደመናው ውስጥ ገባ ወደ ተራራውም ወጣ ሙሴም በተራራው ላይ አርባ ቀን አርባ ሌሊት ቆየ" [ዘጸ. 24.19] ዝም ብሎ ሥራ ፈትቶ አይደለም የቆየው፤ ሥራውም ጾም ነው፡፡ "እግዚአብሔርም ሙሴን በእነዚህ ቃሎች መጠን ከአንተና ከእስራኤል ጋር ቃል ኪዳን አድርጌያለሁና እነዚህን ቃሎች ጻፍ አለው በዚያም አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ከእግዚአብሔር ጋር ነበር አልበላም አልጠጣም" [ዘጸ. 34፡27] እየጾመ ነበር ማለት ነው፡፡ በዚህ ጾሙ ሙሴ የቃል ኪዳኑን ጽላቶች ተቀብሎአል፡፡ ከዚህ የምንረዳው ከንቱ ሳይሆን ዋጋ ያለው እንደኾነ ነው፡፡ የኤልያስ ጉዞ አርባ ቀን አርባ ሌሊት እንደ ነበረ ተጽፏል፡፡ "የእግዚአብሔር መልአክ ደግሞ ኹለተኛ ጊዜ መጥቶ ዳሰሰውና የምትሄደበት መንገድ ሩቅ ነውና ተነሥተህ ብላ አለው፤ ተነሥቶም በላ ጠጣ፤ በዚያም ምግብ ኃይል እስከ እግዚአብሔር ተራራ ኮሬብ ድረስ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ሄደ" [ዘጸ.19፡4-8]፡፡
✓ ሕዝቅኤል አርባ ቀን ጾሞ 600 ሙታን አስነሥቷል፡፡ ዕዝራ ሱቱኤል አርባ ቀን ጾሞ የጠፋ መጻሕፍትን መልሷል፤ አብረው የነበሩ ዐምስት ሰዎች ቀን ቀን ይጽፋሉ ማታ ማታ ጥቂት እህል ውኃ ይቀምሱ ነበር፡፡ [ዕዝ.ሱቱ. 13፡23-25] ጌታችን በተወለደ በአርባ ቀኑ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቷል፡፡ [ሉቃ. 2፡22]: ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አርባ መአልትና ሌሊት ጾመ [ማቴ. 4፡2]፡፡ በተነሣ በአርባኛው ቀን ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ [ሐዋ. 11.10]፡፡ ሰው በተፀነሰ በአርባ ቀኑ ተስዕሎተ መልክዕ ይፈጸምለታል፡፡ "በአርባ ቀን ትሾመዋለህ" እንዲል ቅዱስ አትናቴዎስ ወንድ በተወለደ በአርባ ቀኑ ሴት በተወለደች በ80 ቀኗ ኹለት አርባ ክርስትና ይነሣል፡፡ ሰው በአፈር በአርባ ቀኑ ጸሎተ ፍትሐት ይደረስለታል፡፡ ሰው በአርባ ቀኑ ጸሎተ ተክሊል ይደረስለታል፡፡ [ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 24 ገጽ 322]
አርባ ቀን ይህን ያህል ምስጢር ያለው ቀኑ ነው ጌታችን ለምን? አርባ ቀን ጾመ ስንል ከላይ ያየናቸውን አበው ነቢያት ብዙውን ጊዜ የጾሙት አርባ ቀን ነው፡፡ ቢቀንስ አጎደለ ከፍ ቢያደርግ አበዛ ብለው አይሁድ የነቢያትን ሕግ አፈረሰ በማለት ትምህርቱን አንቀበልም ባሉ ነበርና ይህንን ምክንያት በማንሣት አርባ መአልትና ሌሊትን ጾመ፡፡ እስራኤል 40 ዓመት ተጉዘው ምድረ ርስት ገብተዋል፡፡ እናንተም 40 ቀን ብትጾሙ ገነት መንግሥተ ሰማያት ትገባላቹ ሲለን ነው፡፡ ከላይ እንደ ተመለከትነው የጥፋት ውኃ አርባ ቀንና ሌሊት ዘነበ፤ ምድር ጸዳች ሰው አርባ ቀንና ሌሊት ቢጾም ርስት መንግሥተ ሰማያት ይወርሳል ሲለን ነው፡፡ ጾም ሲርስት ለመንግሥተ ሰማያት የሚያበቃ ከኃጢአት የሚያነጻ እንደሆነ ሊያስተምረን በኦሪት በተጾመው ቊጥር ጾም ሥርዓትን ሰጥቶናል፡፡
መላካም ጾም ይሁንላችሁ።