የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

@simakonem


ያየነውን እንመሰክራለን የሰማነውን እንናገራለን!

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

15 Oct, 11:49


የፀሐይ ብርሃን በጠቢባን ጥበብ ይሰፈራል፤ የጨረቃም ውበት ይመጠናል፤ ሰማይና ምድር በአድማስ፣ ባሕርም በናጌብ ይወሰናል። የእመቤታችንን ክብር ግን መመጠንና መወሰን ይቅርና ማን ሊመረምረው ይቻለዋል? ''ሊቁ መኑ ዘይክል ነቢበ ዕበይኪ" እንዳለ ገናንነትሽን ማን ይናገራል እያልን ስለ እሷ የተነገረውን ሁሉ በመደነቅ እናነባለን። ሊቃውንቱ ለእመቤታችን ውዳሴ በመጽሐፍ የሚያኖሩት ለኀሊና ማቅኛ እንዲሆን ነው እንጅ ከዚያ በኋላስ ኅሊና አስቦ ወደማይደርስበት ጥልቅ ባሕረ ውዳሴ መግባት ነው።የአበቦችን ውበት በምድረ በዳ፣ ከዋክብትን በሰማይ ላይ በጥበቡ የገለጠ አምላክ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንም በሊቃውንት አንደበት ይገልጣታል። ቅዱስ ኤፍሬምን አፈ በረከት ቅዱስ ዮሐንስን አፈ ወርቅ ያሰኛቸው የድንግል እመቤታችን ውዳሴ ነው። እስከ ዕለተ ምጽአት የሚነሣው ትውልድ እንዲያመሰግናት በትንቢት የተነገረላት ሉቃ 1:48 ይፈጸም ዘንድ ዛሬ ባሉ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት አንደበትም በጉባኤ፣ በማኅሌት፣ በቤተ መቅደስ ትመሰገናለች።

ርእሰ ሊቃውንት አባ ገብረ ኪዳን እመቤታችን “ያስተበፅዑኒ ኩሉ ትውልድ" ብላ ከተናገረችላቸው አንዱ ናቸው። ለዚህም ምስክሬ ትምህርታቸው ነው። በዐውደ ምሕረት "የምድር ጌጥ" ይሏታል። በጉባኤ ቤት "ብርሃንኪ የዐቢ እምብርሃነ ፀሐይ” ይሏታል። በበዐታቸው "ሰአሊ ለነ ቅድስት" ይሏታል። ዛሬ ደግሞ ተነቦ የማይጠገብ ውዳሴዋን በመጽሐፍ አቅርበውልናል።

ይሄ መጽሐፍ በትውፊት የምናወርሰው፥ ነገር ግን እያየነው የተደረሰ አዲሱ አርጋኖን ነው። ቅድመ ዓለም በአምላክ ኅሊና ከታሰበው ድኅረ ዓለም በነቢያት እስከተነገረው፥ በመላእክት ከተዘመረው በሐዋርያት እስከተሰበከው ሊጠቀስ የሚገባው ተጠቅሷል። የእመቤታችን ነገር ሐረግ ነው፤ በነካነው ጊዜ ሁሉ ብሉያትን ሐዲሳትን ሊቃውንትን ያንቀሳቅሳል።

ርእሰ ሊቃውንት እንደ ሐረግ ሳቢ አንድ ጥቅስ በመዘዙ ጊዜ የመጻሕፍት ሁለንተናቸው ይንቀሳቀሳል። ከብሉይ ኪዳን ጀምሮ በእግዚአብሔር መንፈስ የተጻፈ መጽሐፍ ሁሉ እመቤታችን የሌለችበት መጽሐፍ አይገኝም።ይህን መጽሐፍ ባነበባችሁ ጊዜ ይህንን እውነት ትረዱታላችሁ። "አሐቲ ድንግል" አንድ መጽሐፍ ብቻ አደለም። ትርጓሜ፤ ድርሳን፤ ምዕላድ፤ ውዳሴም ነው። ሁልጊዜ የርእሰ ሊቃውንት አባ ገብረ ኪዳንን ስብከት ስሰማ የምመኘው ይህንን መጽሐፍ ነበር። አንዳንዴ ስብከት መሆኑን ረስቼ መጽሐፍ የሚያነቡልኝ ይመስለኝ ነበርና። እነሆ የተመኘሁት መጽሐፍ በብራና ተጠቅሎ በቤተ መጻሕፍት ተጥሎ አገኘነው። ከእኔ ጋራ የተወለደውን የመጻሕፍት ንጉሥ ታዩ ዘንድ ኑ!

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ የ፬ቱ ጉባኤያተ መጻሕፍት ምስክር መምህር

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

14 Oct, 04:59


አብረን እንሰደድ
___||___
[ዘሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ]

ጌታ ከተወለደ ሁለት ዓመት ሞላው። ንጉሥ አልባዋ ቤተ አይሁድ ንጉሥ ተወለደላት። ትንቢቱ መሥዋዕቱ የዚህን ሕጻን ልደት ፍለጋ የተደረገ ደጅ ጥናት ነበረ። አብርሃም ከሀገሩ የወጣው ከዘመዶቹ የተለየው፤ ይሥሐቅ በአባቱ እጅ የተሠዋው፤ ያዕቆብ በላባ ቤት የበግ እረኛ ሁኖ የተቀጠረው እዚህ ለመድረስ ነበር። ነገር ግን ይህን ሁሉ ልብ ያለው የለም።

ሁለት ዓመት ሲሞላው ሰብአ ሰገል ወርቅ እጣን ከርቤ ገበሩለት። ነገሥታቱ እጅ መንሻ አቅርበው ከተመለሱ በኋላ መልአኩ ገብርኤል መጥቶ ለዮሴፍ "ሔሮድስ ሕጻኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ሕጻኑንና እናቱን ይዘህ ሽሽ" ብሎ ነገረው።

ሰብአ ሰገል ከጌታ ጋር አብረው እንዲሰደዱ ወይም ጌታን ይዘው ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ አልተፈቀደላቸውም። በሳጥናቸው ወርቅ ይዘው መጥተው ወርቅ የሆነች ሃይማኖት በልባቸው ይዘው ተመለሱ። የነሱን እጅ መንሻ ከተቀበለ በኋላ ሳይውል ሳያድር ተሰደደ።

ከዮሴፍ እና ከሰሎሜ በቀር አብሮ ለመሰደድ የተፈቀደለት የለም።
፨ ጌታ ባደረበት ለማደር በዋለበት ለመዋል አብሮ መሰደድ ምንኛ መልካም ነው!?
ዮሴፍ ሆይ በገሊላ ከቀሩ ሰዎች ይልቅ አንተ ብፁዕ ነህ፤ ጌታ ከሌለባት ከተማ ጌታ ያለባት ምድረ በዳ ትበልጣለችና።
አረጋዊ ሆይ በግብፅ ምድረ በዳ ያገለገልኸው መላእክት በሰማይ የሚያገለግሉትን ነው።
ዮሴፍ ሆይ ሕጻኑና እናቱ በተሰደዱበት ምድረ በዳ ከዓለት ላይ ውኃ ፈሰሰ። ሕጻኑን ካሳደደችው ከተማ ግን ደም እንደ ጎርፍ ፈሰሰ። የሕጻናቱ ደም በግፍ ሲፈስ ዓይኖችህ እንዳያዩ ሊሠውርህ አብረህ ተሰደድህ።
አረጋዊ ዮሴፍ ሆይ ኢሳይያስ ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ሁኖ በራዕይ ያየውን ጌታ አንተ በገሊላዊቷ ብላቴና ጀርባ ታዝሎ አየኸው።
አረጋዊ ሆይ ነቢዩ ዳዊት "እነሆ በኤፍራታ ሰማነው በዱርም መካከል አገኘነው" ብሎ በመንፈስ የዘመረለትን ሕጻን በግብፅ በረሃ መጓዝ ተስኖት እናቱ እንድታዝለው አንጋጦ እየለመነ ሲያለቅስ ሰማኸው።
ኦ ወዮ እንደ ምን ያለ ድንቅ ነው!?
በአርያም የሚያድር ጌታ በግብፅ ምድረ በዳ አደረ። ከሰው ሁሉ ተመርጠው ከሱ ጋር በምድረ በዳ ያደሩ ሰዎች ምንኛ የታደሉ ናቸው?!
እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ በዱር እያደሩ በምድረ በዳ እየኖሩ ከሱ ጋር በልባቸው የሚሰደዱ ቅዱሳን ብዙ ናቸው።
እኛም አብረን እንሰደድ።

ከድንግል ጋር አብረን እናልቅስ።
ኑ! እሾኽ ሲወጋት እንቅፋት ሲመታት ተመልክተን እናንባ።
ኑ! ለልጇ የምታጠጣው እፍኝ ውኃ የቸገራትን ሴት እመቤታችንን እንያት።
ኑ! የልጇን ጫማ ሽፍቶች የወሰዱባትን ሴት ተመልከቷት።
ኑ! መላኩ ፋኑኤል የመገባትን ብላቴና በግብፅ ከበርቴዎች በር ቆማ ስትለምን ስሟት።
ኑ! የኪሩቤል ክንፍ የሚጋርዳትን እመቤት ግብፃዊቷ ስትመታት ልጇንም ከጇ ነጥቃ ከዓለት ላይ ስትጥልባት ተመልከቱ።
ይህን ግፍ ታዩ ዘንድ ኑ! በነፍስሽ ሰይፍ ያልፋል የተባለው ሊፈጸምባት ልቧ እጅግ አዘነ። ኮቲባ መሬት ላይ የጣለችው ልጇን ለማንሣት ብክንክን ስትል እናያት ዘንድ ኑ! ክርስቲያኖች ሆይ !
"እነሆ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅን ትወልጃለሽ ብሎ ያበሠረኝ መልአክ ወዴት አለ" እያለች በግብፅ ጎዳና ወድቃ የምታለቅሰዋን ብላቴና ታረጋጓት ዘንድ ኑ።

ከወደዳችኋትማ አብረናት እንሰደድ። ባለ በገናው ዳዊት፣ ባለ መሰንቆው ዕዝራ ወዴት አሉ? ያዘነች የተከዘች እመቤታችንን ለማጽናናት ይምጡ።
በቤተ መቅደስ ያረጋጓት መላእክት ወዴት ሄዱ በግብፅ ቆላ ፀሐይ እንዳያቃጥላት ክንፋቸውን ይዘርጉላት።

፨አብረን እንሰደድ።
የዮሴፍ በትሮች ሲለመልሙና በግብፅ አሸዋ ላይ ተተክለው ትልቅ ዛፍ ሲሆኑ እናያለን።
አብረን እንሰደድ፦ ሰሎሜ እንዳዘለችው እኛም በዘባነ ልቡናችን በእምነት እናዝለዋለን።
አብረን እንሰደድ፦ እንደ ሔሮድስ ከመቀሰፍ እንድናለን።
አብረን እንሰደድ፦ በመከራው ከተሳተፍነው በክብሩ ሲገለጥ ከእርሱ ጋር እንነግሣለን።
አብረን እንሰደድ፦ በከተማ ከዘገየው ከዮሳ ጋር እንዳይፈረድብን።
አብረን እንሰደድ፦ አብረን እንመለሳለን።

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

27 Sep, 03:58


ቦታውን ማወቅ የቻለ ማንም አልነበረም። አይሁድ እንዳይገኝ አድርገው አጥፍተውት ነበርና ዓለም የሚጠቅማትን የምትመርጥበት እውቀት ቢኖራት ኖሮ በርባንን አድንልን አትልም ነበር፤ ከሞት የማያድነውንና የምድረ በዳውን መና የበሉ እስራኤል ከሰማይ የወረደውንና ሕይወት የሚሰጠውን መና ኢየሱስ ክርስቶስን ለመብላት ባላንጎራጎሩም ነበር ዮሐ. 6፥። የመስቀሉም ነገር እንዲሁ ነው። ከፀሐይ በላይ እስከ ሲኦል ድረስ የሚደርስ ብርሃን ያለውን የሕይወት ብርሃን የተሸከመውን የብርሃን መቅረዝ አፈር ሲደፉበት አላፈሩም። በእርግጥ “ወደ ወገኖቹ መጣ ወገኖቹም አልተቀበሉትም” ዮሐ. 1፥11 ተብሎ የተነገረባቸው መሆናቸውን እናውቃለን። የሚጠቅማቸውን ለማወቅ የመንፈስ ቅዱስ እርዳታ ያስፈልግ ነበር መንፈስ ቅዱስ ካደረበት ሰው በቀር ኢየሱስ ክርስቶስን አምላክ ነው ብሎ መቀበል እንደማይችል ሁሉ ቅዱስ መስቀሉንም የሕይወት ዛፍ ነው ብሎ ለመቀበል አይችልም። ለዚህ ነው ከሦስት መቶ ዓመታት ለሚበልጥ ጊዜ በመሬት ውስጥ እንዲኖር ያደረጉት።
ነገር ግን ከመሬት በታች ቢኖርም በምዕመናን ልብ አልተረሳም ነበርና ጊዜው ሲደርስ ዕሌኒ በሱባኤዋ ጊዜ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መላክ መጥቶ የመስቀሉን ነገር ነገራት ቅዱስ ያሬድ “ትቤሎ ዕሌኒ ለመልአክ ንግረኒ በእንተ መስቀሉ ለክርስቶስ፤ ዕሌኒ መልአኩን ስለክርስቶስ መስቀል ንገረኝ” አለችው ብሎ የዘመረው በሱባኤዋ ጊዜ የተገለጸላትን መልአክ ነው። ከመልአኩ የተረዳችውን ከኢየሩሳሌም ሽማግሌዎች የሰማችውን መሠረት አድርጋ መስከረም አሥራ ሰባት ቀን የተቀበረበትን ተራራ ማስቆፈር ጀመረች። እስከ መጋቢት አሥር ቀን ድረስ የቀጠለው ቁፋሮ የጌታን መስቀል ማስገኘት የቻለ ነው።
በጎ ነገር የተመኘ ማን አጥቶ ያውቃል? ከምድር በታች ያለውንስ ቢሆን እግዚአብሔር የሚጠቅመንና ደስ የሚያሰኝ ነገር ከሆነ የማይከለክለን መሆኑን በዕሌኒ ማወቅ እንችላለን። ተቆፍሮ እስኪወጣ ድረስ ናፈቀች፤ መጋቢት አሥር ንግሥት ዕሌኒ በዙፋኗ ላይ ተቀምጣ በአጃቢዎቿ ተከባ መስቀሉን ለማውጣት ከሚቆፈርበት ስፍራ አጠገብ ተቀምጣ ይህ መስቀል ከሰማይ ይበልጣል፤ ሰማይ ላይ ካለችው ፀሐይ ይልቅ በብርሃኑ ጨለማችንን ያራቀልንን እውነተኛ ፀሐይ ኢየሱስ ክርስቶስን የተሸከመ መስቀል እንዴት ከሰማይ አይበልጥ? ይህ መስቀል ከያዕቆብ መሰላል ጋር አንድ ነው፤ በላዩ ንጉሥ ወልደ እግዚአብሔር ተቀምጦበታልና። ያዕቆብ በሕልሙ ያየውን የወርቅ መሰላል ላየው ነው። እያለች በልቧ ታወጣ ታወርድ ነበር። ያሰበችው ተሳካ ቆፋሪዎቹ መስቀሉን አገኙት፤ የመስቀሉን ብርሃን በመቃብርም ውስጥ ሆኖ አዩት ስለዚህም ይሄዋ ብለው ወስደው ለንግሥቲቱ አስረከቡ። ንግሥቲቱ የተመኘችውን አገኘችው፤ የጓጓችለትን አየችው።
መስከረም አሥራ ስድስት ደመራ ደምረን የምናከብረው ለምንድነው?
ዛሬ በመላው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ባለችበት ቦታ ሁሉ መስከረም አሥራ ስድስት ንግሥት ዕሌኒ ደመራ ደምራ ሰንድሮስ የሚባል ነጭ ዕጣን ያጠነችበትን በዓል ያከብራሉ። ይህ ዕለት መስከረም አሥራ ሰባት ቀን የመስቀሉ ቁፋሮ ከመጀመሩ በፊት ንግሥቲቱ መልአኩ በነገራት መሠረት ደመራ ደምራ ያቃጠለችበት ዕለት ነው። በኋላም በቅዱስ መስቀል ስም ቤተ ክርስቲያን በጎልጎታ አንጻ ቅዳሴ ቤቱን ያከበረችው በዚህ ቀን ነበር። የሕይወት ዛፍ ወደ ተተከለበት ስፍራ ያደረሰን አምላካችን ስሙ የተመሰገነ ይሁን!

#ከበረከተ_መስቀሉ_ያሳትፈን

#እንኳን_ለብርሃነ_መስቀሉ_በሰላም_አደረሰን_አደረሳችሁ!

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

27 Sep, 03:58


የሕይወት ዛፍ፦ በሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ
__//____
በገነት ውስጥ ያለችውን የሕይወት ዛፍ መኖሯን የሰማነው አዳም ከገነት በተሰደደበት ጊዜ ነበር። ሞትን የሚያስፈርደውን ዛፍ በልቷልና እጁን እንዳይሰድና ከሕይወትም ዛፍ እንዳይበላ ወደ ሕይወት ዛፍ የሚወስደው መንገድ የምትገለባበጥ የእሳት ሰይፍ በእጃቸው የያዙ መላእክት ይጠብቋት ነበር። ዘፍ. 3፥22 ይህችን የሕይወት ዛፍ ፍሬዋን እንበላ ዘንድ ተመልሰን ገነት እስከምንገባ ድረስ እግዚአብሔር አልተወንም። እኛ ወደ ገነት የምንገባው በአካለ ነፍስ እንጅ በአካለ ሥጋ ባለመሆኑ በገነት ያለችውን የሕይወት ዛፍ ፍሬዋን ለመብላት የምትችለው ሥጋችን በመቃብር ውስጥ ታድራለች። ነፍሳችንም ከሥጋችን ተለይታ ወደ ተዘጋጀላት ገነት ትገባለች። እግዚአብሔር ቸር ነውና የሕይወትን ዛፍ ሳናያት ፍሬዋንም ሳንመገብ እንዳንቀር በመካከላችን አምጥቶ ተከለልን ያችም የሕይወት ዛፍ በመካከላችን የበቀለው ቅዱስ መስቀል ነው። አባ ጊዮርጊስ በውዳሴ መስቀል መጽሐፉ ቅዱስ መስቀልን የሕይወት ዛፍ ብሎ ነው የሚጠራው። ለመዳን ያበቃንንን የሕይወት ፍሬ ኢየሱስ ክርስቶስን የተመገብነው በመስቀል ላይ አግኝተነው ስለሆነ ነው። በገነት ሳለን ያልተመገብነው ይህ የሕይወት ምግብ በገነት ሳለን ከበላነው የሞት ፍሬ ይልቅ በእጅጉ ጠቀመን። እግዚአብሔር ያዘጋጀልንን የሕይወት ዛፍ ፍሬዋን በስንፍናችን ምክንያት ሳንበላት ለሥጋችን አድልተን የበለስን ፍሬ በላን። እግዚአብሔር ክፉዎች አይሁድ የሕይወትን ዛፍ እንዲተክሉት አደረገ። ሲተክሉት ፍሬው ዓለምን እንደሚያድን ቢያውቁ ኖሮ ባልተከሉትም ነበር። እግዚአብሔር ባወቀ ዕፀ መስቀል ተተከለ፤ ፍሬውም የክርስቶስ ሥጋና ደም ሆነ።

#የሕይወት_ማዕድ
ነቢዩ ዳዊት “ወሠራእከ ማዕደ በቅድሜየ፤ በፊቴ ማዕድን አዘጋጀህልኝ በጠላቶቼ ፊት ራሴን በዘይት ቀባህ” መዝ. 23፥5 በሚለው መዝሙሩ ውስጥ ማዕድ ብሎ የጠራው ቅዱስ መስቀልን ነው። የዘለዓለም ምግብ ክርስቶስን የተመገብንበት ይህ ቅዱስ መስቀል ሁልጊዜም በቤተ ክርስቲያን ፊት እንደተዘረጋ ይኖራል። አይሁድ ያቀረቡት የሞት ምልክት አድርገው ነበር፤ እግዚአብሔር ግን የሕይወት ምልክት አደረገው። ጠላቶቻችን ሲሆኑ ይህንን የከበረ ማዕድ በፊታችን አቀረቡልን። ቅዱስ ዳዊት “በዱር መካከል አገኘነው” መዝ. 132፥6 ብሎ በሌላ መዝሙር የዘመረለት የጌታ መስቀል በዘመናት ሁሉ ስንፈልገው የነበረ መድኃኒት ነው። ለቁስለኛ ከመድኃኒት በቀር ምን ያስፈልገዋል? ለተራበ ሰውስ ከምግብ ውጭ ምን እንዲያቀርቡለት ይሻል? እነሆ ቅዱስ መስቀል ለሕሙማን ፈውስ ለተራቡትም ምግብን ይዞ በዱር መካከል ካሉ ዕፀዋት ተለይቶ የሕይወትን ፍሬ አፍርቶ አገኘነው። እንደ አብርሃም ያለ ቅድስና ሳይኖረን አብርሃም በጉን ታስሮ ያገኘበትን ዕፀ ሳቤቅ ከነበጉ አገኘነው ዘፍ. 22፥13። አብርሃም ያቀረበውን በግ ዛሬም በፊታችን ቀርቦ እንመገበዋለን፤ የአብርሃም በግ በይስሐቅ ፋንታ ተሠዋ፤ እኛ ያገኘነው የእግዚአብሔር በግ ክርስቶስ ግን ስለ ዓለም ሁሉ ተሠዋ። አብርሃም ያቀረበው በግ የታሰረበት ዕፀ ሳቤቅ ጌታ የተሰቀለበት የቅዱስ መስቀል ምሳሌ ነበር። የሀገራችን ሊቅ ቅዱስ ያሬድ “ዕፀ ሳቤቅ ብሂል ዕፀ ሥርየት መስቀል፤ ዕፀ ሳቤቅ የተባለ የሥርየት እንጨት መስቀል ነው” ብሎ እንደተረጎመው።

#የመስቀሉ_መጥፋት
ለቁስላችን ፈውስን፤ ለረሀባችን ምግብን፤ ለድካማችን ኃይልን ያገኘንበትን መስቀል ጌታ ካረገ በኋላ አይሁድ ከፊታችን አጠፉብን። እነሱ ያሰቡት በእንጨት ተሰቅሎ የሞተ ሁሉ የተረገመ ነው ስለተባለ ክብር ይግባውና በፊታችን ክርስቶስ እንደተረገመ ሰው እንዲቆጠር ነበር። ነገር ግን ከሰዎች ሁሉ እርግማንን የሚያርቅ ሆነ። በገነት ካሉ ዕፀዋት መካከል የምንታረቅበትን ፍሬ ይዞ የተገኘ ዛፍ የለም። በቀራንዮ የተተከለው መስቀል ግን ከእግዚአብሔር ጋር የምንታረቅበትን ፍሬ ያስገኘ በመሆኑ በገነት ካሉት ዛፎች ይልቅ የጠቀመን ይህ ነው። በገነት ሳለን የሰማነውን እርግማን ያስወገደልን የክርስቶስ መስቀል ነው። አይሁድ እና አጋንንት ይህንን አላሰቡም። ለሰው ልጅ ጥቅም ይሰጣል ብለው ሳያስቡ ለሰዎች ጠቅሞ ቢያገኙት መልሰው በቆሻሻ መድፊያ ቦታ ጣሉትና ሁሉም ሰው የቤት ጥራጊ እንዲደፋበት አዘዙ። ለሦስት መቶ ዓመታት ቅዱስ መስቀል ከምዕመናን ፊት ተሠውሮ ነበር። መጀመሪያ “በክርስቶስ ያመነ ሁሉ ከምኩራብ ይሰደድ” ዮሐ. 9፥22 ብለው ዐዋጅ እንደነገሩ አሁንም በመስቀሉ ላይ ቤቱን ጠርጎ ያልደፋ ይቀጣል ብለው ዐዋጅ ስለነገሩ መስቀሉ በጎልጎታ ተቀብሯል። ቅዱስ ያሬድ “በጎልጎታ ዘደፈኑ አይሁድ ዮም ተረክበ ዕፀ መስቀል፤ በጎልጎታ አይሁድ የቀበሩት ዕፀ መስቀል ዛሬ ተገኘ” ብሎ በዘመረው ዝማሬ የትና ማን እንደቀበረው አስረጂ ነው።

#ሐዋርያት ሲቀበር ለምን ዝም አሉ? ፈጥነው ከተቀበረበት ያላወጡትስ ለምንድነው?
በዘመኑ ሐዋርያት ወንጌልን ለማዳረስ በየሀገሩ ሁሉ እስከ ዓለም ዳርቻ ይዞሩ ስለነበር መስቀሉን ፍለጋ ወደ ኢየሩሳሌም አልተመለሱም። የሚድኑ ነፍሳትን ፍለጋ ከሮማ ነገሥታትና ከአጋንንትም ጋር ጦርነት ላይ ስለነበሩ ሰዎችን ከኃጢአት ነጻ ለማውጣት እንጅ መስቀሉን ከተቀበረበት ለማውጣት ሳይሞክሩ በሰማዕትነት በየሀገረ ስብከታቸው አረፉ። በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዘመነ ሰማዕታት ሲያልፍና ቤተ ክርስቲያንም ከነገሥታት እስራትና ግድያ ስታርፍ መስቀሉን የሚፈልግ ትውልድ ተነሣ። ቤተ ክርስቲያን በዘመነ ሰላምና በዘመነ ሰማዕታት ልትሠራው የሚገባትን ለይታ ካላወቀች ዓለምን አሸንፋ መቀጠል አትችልም። በዘመነ መከራ ወንጌል ወደ መስበክ ምዕመናንን በክህደት በኃጢአት እንዳይያዙ የመጠበቅ ሥራ ላይ ትኩረት ማድረግ አለባት። በሰላም ዘመን ዳግሞ ማለትም አብያተ ክርስቲያናት ተከፍተው፣ ሃይማኖቱ የቀና ምግባሩ የጸና ንጉሥ አንግሠው በትምህርቱ መናፍቃንን የሚገሥጽ በትሩፋቱ ምዕመናንን የሚያንጽ ጳጳስ አግኝተው በተቀመጡበት ሰዓት የቤተ መቅደስ ሕንጻ ብትገነባና ሌሎችንም ምዕመናንን ከመጠበቅ ወንጌልን ከማስፋት ተጨማሪ የሆኑ ሥራዎችን ብፀራ አያስነቅፋትም። ለዚህ ነው በሐዋርያት ዘመን መስቀሉን የመፈለግ ሥራ ያልተጀመረው የሚቀድም ሥራ ስለነበረ ነው።

#የዕሌኒ_መነሣት
ንግሥት ዕሌኒ በክርስቶስ ፍቅር ልቧ የታሰረች ሴት ነበረች። የመስቀሉ ዜና በምድር ላይ ጠፍቶ ስለነበረ ወደ እግዚአብሔር ለማመልከት ሱባኤ ገብታለች። የዓለም ነገር አይገርማችሁም? መስቀሉ በተተከለበት ስፍራ የተቀበሩ ብዙዎቹ ሙታን ተነሥተዋል፤ መስቀሉ ከቆመበት አካባቢ የነበሩ መቃብሮች ተከፍተዋል፤ መስቀሉ ቀራንዮ ላይ ከቆመ በኋላ የቤተ መቅደስ መጋረጃ ተቀዷል፤ በዚህ መስቀል ላይ የተሰቀለው ክርስቶስ ከሞተ በኋላ ጎኑን ቢወጉት ከጎኑ ውኃና ደም ሲፈስ ታይቷል። ይህ የሕይወት ውኃ የፈለቀበት ምንጭ ቅዱስ መስቀል ሲጠፋ ከሥሩ የተነሡ ሙታን እንዴት ዝም አሉ? ጌታ በተሰቀለ ጊዜ ጎኑን የወጋው ወታደር የጠፋች ዐይኑ የበራችለት የመስቀሉ ጥላ ሲያርፍበት የጌታም ከጎኑ የፈሰሰ ደሙ ሲረጭበት ነበር ይህ ዓይኑ የበራችለት ሰው ስለመስቀሉ መጥፋተ እንዴት አልጠየቀም? ለመስቀሉ ቤት ሠርቶ ሊያኖር የሞከረ ሰው እንዴት አልተገኘም? ዓለም ምን እንደሚፈልግ ተመልከቱ። የሚጠቅመውን አያውቅም። ለሚጠቅመው ነገር ስፍራ አያዘጋጅም። ያ ሁሉ ተአምራት የተደረገበትን መስቀል በማይገባ ስፍራ ጣሉት፤ ከዐይናችን ሰወሩት። ዕሌኒ ሱባኤ እስከገባች ድረስ ስለመስቀሉ በትክክል

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

25 Dec, 17:35


"ምዕመናን ሆይ ወዴት ናችሁ?"

የክርስቶስ ወደ ዓለም መምጣት ምክንያቱ ግዛት ጠቦት ሊያሰፋ ሠራዊት አንሶት ሊመለምል አይደለም። የጠፉ ምዕመናንን ፍለጋ ነው እንጅ።

ሰውን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመመለስ ነው እንጅ የሐዋርያት በየሀገሩ መበተን ለሌላ ለምንድነው? መንፈስ ቅዱስ እየረዳቸው የተበተኑትን ሰበሰቡ የጠፉትን ፈልገው አገኙ። ሐዋርያት የሰበሰቧትም ምዕመን አሐቲ ጉባኤ ̱ˉ ቤተ ክርስቲያን ተባለች።

ሐዋርያት የሰበኳቸው ከተሞች ዛሬ በክርስትና የሉም። ይህ ከላይ የምትመለከቱት ቤተ ክርስቲያን በስቶክሆልም ከተማ የሚገኝ የጥንት ካቴድራል ነው።

ዛሬከሕንጻው በቀር ምንም ሰው በውስጡ የለም። ይህን ባየሁ ጊዜ ልቤ በብዙ ከተሞች ተመላለሰ። ሮም ብሄድ ፌቤንን አገኛት ይሆን? ደጋጎቹ ባልና ሚስት አቂላና ጵርስቅላ በቤታቸው ላለችው ቤተክርስቲያን ሰላምታ የተጻፈላት ትዝ አሉኝ ጢሮፊሞስ፣ ጠርሲዳና ሌሎችም የጌታ ደቀ መዛሙርት ይኖሩ ይሆን? አልሁ የት አለች ገላትያ? የት ገባች ቁስጥንጥንያ? ወዴት ናት ያች የሊቃውንት መዲና አንጾኪያ? እውነት ነው ማለት ነው በሀገሬ ሳለሁ የሰማሁት? የያዕቆብ ጉባኤ ንጽቢን ፈርሳለች? የአፈ ወርቅ መንበር ቁስጥንጥንያ ረክሳለች?

አግናጥዮስን ከሞት ሊያድኑት የተከተሉት የሰሜርኔስ ምዕመናን ዛሬ የት አሉ? ፈለግሁ አላገኘሁም። ሰይጣን ለተለያየ ሥራ ተካፍሎ አዲሱን ትውልድ ወስዶታል። ይህንን ሳይ አገሬ አሳዘነችኝ የነገ ዕጣ ፈንታዋ አስለቀሰኝ። አውሮፓ ምዕመናንን ያጣችው ከሰማይ በመጣ መቅሰፍት አይደለም። የካህናቱ ሐዋርያትን መስሎ አለመኖር ያመጣው ነው። እኛም አገር ከሕዝቡ በፊት ዓለማዊነት ያጠቃቸው ካህናት፣ መነኮሳት፣ ሰባክያን የሉም? በሌላ የተደረገው በኛ ሳይደረግ ቀድመን እንሥራ። በኋላ ብንጠራው አቤት የሚል ትውልድ የለም። ዛሬ ምዕመናንን እንፈልጋቸው

የሮም ቤት ክርስቲያን የሥልጣን ጥማት አብያተ ክርስቲያናትን የምዕራብና የምሥራቅ ተብለው እንዲከፈሉ አደረገ። በኬልቄዶን ጉባኤ የነበረው ትልቁ በሽታ የሮም ቤተ ክርስቲያን የበላይነቷን ለማስከበር ባደረገችው ጥረት ከምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ለመለያየት መነሻ ሆናት። በኋላም ገንዘብ ወዳድነቷ ለፕሮቴስታንት መፈጠር ምክንያት ሆነ። የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ዓለማውያን ከሆኑ ዓለምን የሚያሸንፉበት መንፈሳዊ ጥበብን ያጣሉ። ያን ጊዜ አዲሱን ትውልድ በሥጋ ትምህርት ይነጠቃሉ።

ዛሬ ለአውሮፓ አብያተ ክርስቲያናት አዲሱን ትውልድ የማግኘት ዕድል የላቸውም። እንስሳዊ ኑሮን ተለማምዶ ይበላል ይጠጣል ይተኛል ይነሣል ተንቀሳቃሽ ሮቦት ሆኗል። በአደንዛዥ ዕጸዋት አደነዘዙት፣ በኳስ አስፈነጠዙት በመጨረሻ ሰዶማዊ አደረጉት። በእርግጥ የመጨረሻው ምን እንደሚሆን አይታወቅም የሚመጣው ጥፋት ከባድ ነው። ሃይማኖት የሌለውን ትውልድ ሰው አድርጎ ማኖር አይቻልም። እኛም ዛሬ ካልሠራን ነገ የሚሰማን የለም። የሠራነው ቤተ መቅደስ ባዶ ሲሆን ቆመን አናይም። አዲሱ ትውልድ ያሳዝናል ሰይጣን በመንግሥት ተደራጅቶ እየተዋጋው የሚገኝ ትውልድ ነው። መድረስ የሚገባን ዛሬ ነው። አምሳ ዓመት አልሞላውም የአውሮፓ ቤት መቅደስ ባዶ ሲሆን። ሩቅ እንዳይመስላችሁ ሰይጣን በደጅ ነው።

ምዕመናኑም ልጆቻቸውን አውሮፓ ወስደው ቢያዝናኗቸው፣ ልዩ ምልክት ያለው ልብስ ቢገዙላቸው፣ ከፍተኛ ክፍያ ያለበት ትምህርት ቤት ወስደው ቢያስተምሯቸው ከሚጠቅሟቸው በላይ ሃይማኖታቸውን እንዲያውቁ ማንነታቸውን እንዲጠነቅቁ ቢያደርጓቸው መልካም ነው። ተስፋ የሌለው ዘመን እየመጣ ነው። አብያተ ክርስቲያናት በራቸውን ከፍተው እየተጣሩ ነው

"ምዕመናን ሆይ ወዴት ናችሁ?"

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

04 Dec, 18:58


የኢትዮጵያ የሕግ ሥርዓት ሜታ ሞደርኒዝም( በተዋሕዶ ከበረ) መሆን አለበት!
=====================================
አቅራቢው ዳዊት በዛብህ( ደራሲ፣ የሕግ ባለሙያና የዩኒቨርስቲ መምሕር) የኢትዮጵያ የሕግ ሥርዓት ከዘመናዊነት አንጻር" በሚል ርእስ ግሩም ገለጻ(presentation) አቅርቦ ቆንጆ ውይይት ተካሄዷል!
==============
ዳዊት በዛብህ የኢትዮጵያን ከቅድመ ዘመናዊነት እስከ ዛሬ ያለውን የመሠልጠን ብያኔ ካሄሰ በኋላ ኢትዮጵያ ከራሷ የሚነሳ የራሷን የዝማኔን ብያኔ መሥጠት አለባት በማለት ገልጿል አክሎም ከዘመናዊነት ፣ ከድሕረ ዘመናዊነትና ከድህረ - ድህረ ዘመናዊነት በኋላ የመጣውን አዲሱን ሜታ ሞደርኒዝም( በይነ ዘመናዊነትን) የዶ/ር እጓለን የተዋሕዶ ከበረ ጽንሰ ሀሳብን በመከተል ከጥንት ጀምሮ ያሉንን መልካም የሕግ ሥርዓት ከአሁኑ ጋር በማዋሃድ አዲስ የኢትዮጵያ የሕግ ሥርዓት መቀመር አለብን ብሏል። ይሁንና ከዐውደ ፋጎስ የውይይት ክበብ አባላት ከፍተኛ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ተሰጥተውበታል !
እጅግ ያማረ ገለጻና ውይይት ነበር !

ምሥጋና
=========
---አዳራሹን ለፈቀደልን:-ለኢትዮጵያ ብሔራዊ መዛግብትና ቤተመጻሕፍት (ወመዘክር)
-- የቪዲዮ ቀረጻውን በነጻ ለቀረጸልን:- ዋካ የምስል ፕሮዳክሽን ( ለፍቅረሥላሴ አስፋው)
---- ጥናቱን ላቀረበልን ለዳዊት በዛብህ

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

03 Dec, 21:43


በወንጌል ታሪኩ የተጻፈውን ባለ አህያውን ሰው አግኝተነዋል፡− የ donkey tyube መሥራች እሸቱ መለሰ ነው። አብረውት የሚሠሩ መምህራንና መዘምራንም “ከዚህ በላይ የምታወጣውን ሁሉ እኔ ስመለስ እከፍልሃለሁ” የተባለውን የጌታን ቃል ተስፋ አድርገው የሚሠሩ ናቸው። ጌታ እስኪመጣ ድረስ የቆሰለውን ዓለም ለማዳን የተላኩ መልዕክተኞች ናቸው። ሉቃ 10፥25−37

ሊቀ ሊቃውንት ስምዓ ኮነ መልአክ የዐራቱ ጉባኤያት መምህር

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

03 Dec, 21:43


ባለ አህያው ሰው
ኀዳር 24 2016 ዓ/ም
(በሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ)

ደግነት ላልተሰጠው ሰው የአሚናዳብ ሠረገላ ቢኖረውም ምንም ታሪክ አይኖረውም።
ባሕርዩን በደግነት ቅኝት ቃኝቶ ለሚኖር ሰው ደግሞ አህያም ቢሆን ባለው ነገር ያገለግላል እንጅ የአሚናዳብ ሠረገላ እስኪሰጠው ድረስ አይጠብቅም። እግዚአብሔር እንደ ፈርዖን በየዕለቱ የምንጠፈጥፈውን ጡብ ካልሞላችሁ ብሎ አስገባሪዎችን ልኮ አያስገርፈንም።

የምንችለውን ብንሠራ ደግሞ ከሠራነው በላይ ከፍ ከፍ ያደርገናል። ምንም እንኳን ያላገለገሉትን የማያስጨንቅ፤ የሠሩትን በጸጋ የሚያከብር አምላክ መሆኑን ብናውቅም የኛን መምጣት የሚጠብቁ አገልግሎቶች በመንገዳችን ላይ አሉ። ምናልባትም ከኛ ቀድመው በዚያ መንገድ ያለፉ ሰዎች አይተው ቸል ብለው ያለፏቸው አገልግሎቶች ሊሆኑ ይችላሉ። እኛም ቢሆን ለዚያ ብለን በዚያ መንገድ ላይ መራመድ አልጀመርንም ግን እግዚአብሔር በዚያ መንገድ ላይ እግረ መንገዳችንን ወደ መንግሥተ ሰማያት የምናቀናበትን ዕድል ፈጠረልን።

የያዝነው መሣሪያ፣ የጫንነው አህያ፣ የቋጠርነው ስንቅ፣ የመቀነታችን ወርቅ፣ የማሰሯችን ዘይት፣ የከረጢታችን ዱቄት ከኛ አልፎ ለሌላ አይተርፍም ብለን አስበን ይሆናል − ከቤታችን የወጣነው። ድንገት ግን፥ ፊታችን ላይ ካለን ነገር ልናካፍለው የሚገባን ሰው ያጋጥማል። ሽፍቶች የጨከኑበት፤ መንገዱን ያሰናከሉበት፤ ዓላማ የነበረው፤ ነገር ግን ለዓላማው መሳካት በሚያደርገው ትግል ላይ ሳለ ድንገት ላይነሣ የወደቀ ሰው ታገኙና የእናንተ እርዳታ ሊያስፈልገው ይችላል። ደግፋችሁ እንዳታቆሙት መቆም አይችልም። ወይም የያዛችሁት ሠረገላ እንደ ባኮስ ሠረገላ ለሱም ለእናንተም የሚበቃ ሆኖ ወጥቶ ከእናንተ ጋር እንዲቀመጥ አታደርጉት፤ አስቸጋሪ ነገር ነው ሥራ 8፥31።
ደጉ ሣምራዊ ይሄ ሁሉ አይፈትነውም፤ ከአህያው ወርዶ በቁስሉ ላይ ዘይቱን አፍስሶ ያነሣዋል እንጅ ከዚህ በፊት እንደመጡት ሰዎች አልፎት አይሄድም። ይህንን ሰው አይቶ ቸል ብሎ ማለፍ ከደበደቡት እና ካቆሰሉት ሽፍቶች በምን ይለያል?

ለማንኛውም ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ የሚወርደው ደጉ ሣምራዊ በሕይወት አጋጣሚ አንዳንድ ጊዜ የሚያጋጥም ነው እንጅ ሁልጊዜ በመካከላችን አይኖርም። በዝተው ዕለት ዕለት የምናገኛቸው፥ ከፍ ሲል፡− በገዛ የሕይወት መንገዳችን ደርሰው ራስ ራሳችንን የሚቀጠቅጡን ሽፍቶችን ነው። ዝቅ ሲል ደግሞ፡− መቀጥቀጣችንን መጎዳታችንን እያዩ ቸል ብለው የሚያልፉንን ሌዋዊውንና ካህኑን ነው። አንተ የምትጠቀምበትን መንገድ ለመዝጋት ሲያስቡ እጃቸው ላይ ያለውን ሕግ ጠቅሰው ያሰናክሉሃል፤ ማቴ 12፥2። በግል ሕይወታቸው ግን ሕጉን ያውቁታል እንጅ ሕጉን ስለማይኖሩበት “የሚጠላህን ሰው አህያ ከሸክሙ በታች ወድቆ ብታየው አትተወው ነገር ግን ከእርሱ ጋር አንሣው” ዘጸ 23፥5 የምትል ሕግ እያስተማሩ እንኳን ለአህያው ለሰው የማይራሩ ጨካኞች ናቸው።

እኛ ግን እነሆ ባለ አህያውን ሰው አግኝተነዋል! ደጉ ሣምራዊ በዘመናችን ከዚህ ሌላ እንዴት ሆኖ ሊመጣ ይችላል? ሽፍቶች የቀጠቀጡትን ልባችንን በቁስሉ ላይ ከዘይቱ አፍስሶ ጥዝጣዜውን አራቀለት። ከአህያው ላይ ወርዶ በአህያው ላይ ጭኖ ወደ ባለምድኃኒት ያመጣቸው ብዙ ናቸው። መጀመሪያ በአሜሪካ ያየነውን ደግነቱን ይሄው ዛሬ ደግሞ በዐረቡ ምድር ደገመው። ተስፋ መቁረጥ የሚሉት ሽፍታ ላደቀቀው ሕዝብ እንዲህ ያለ ደግነት ከወዴት ይገኛል? ለዚህ ሕዝብ ከቤተ ክርስቲያን በላይ ዘይትና መድኃኒት ከየት ይገኝለታል? የቆሰሉ ሰዎች የሚጫኑባት ይህች donkey የተባረከች ትሁን። ለካ ለአዲሱ ትውልድ እግዚአብሔር አዲስ የጽድቅ መንገድ ያዘጋጃል? በእውነት እኔ አዝን ነበር ይሄ የዘመናችን ሰው እንግዶችን በእግዚአብሔር ስም ተቀብሎ በቤቱ እንዳያስተናግድ ለራሱና ለእንግዶች የሚበቃ ቤት የለው፥ በዚያውም ላይ እንደ አባቶቻችን ዘመን እንግዶችን ወደ ቤታችን ወስደን ለማሳደር ብዙ አስቸጋሪ ነገሮች አሉብን፥ እንኳን የማናውቃቸውን ይቅርና የምናውቃቸውንም ወስደን ለማሳደር የምንቸገርባቸው ብዙ ዘመን ያመጣቸው ጉዳዮች መኖራቸው ግልጽ ነው። በዚህ ምክንያት ይሄ የኔ ዘመን ጎጆውን የተቀማ ትውልድ “እንግዳ ብሆን አልተቀበላችሁኝም” ተብሎ ይፈረድበት ይሆን? ብየ አዝን ነበር። እግዚአብሔር ለካ ሌላ የጽድቅ መንገድ አዘጋጅቷል። ሰይጣን የጽድቅ መንገዶችን ሲያጠብብን እግዚአብሔር በሌላ በኩል አሰፋልን።

አሁን ዓለም በወንበዴዎች እጅ ወድቋል፤ ምሕረት በሌላቸው ኃያላን በትር ተመትቶ ደቋል፤ ቀድመው የከፍታ ቦታውን የያዙ ኃያላን አዲሱን ትውልድ መውጫ መግቢያ አሳጥተውታል። ትምህርቱን፣ ጉርብትናውን፣ ትዳሩን፣ ንግዱን፣ ኑሮውን፣ መዝናናቱን እና ሌላውንም ሞራል አልባ አድርገውታል። ቤተ ክርስቲያን የምታስፈልገው ትውልድ ከቀድሞው ይልቅ ያሁኑ ይመስለኛል። ለቀደሙት ሰዎች የምታስፈልገው ለክርስቲያኑ ወይም የሚመጣውን ሕይወት ተስፋ ለሚያደርጉት ነበረ። አሁን ግን በምድር ለሚኖር ፍጥረት ሁሉ ታስፈልጋለች። የኖኅ መርከብ የምታስፈልገው ለኖኅና ቤተ ሰቡ ብቻ እንዳልሆነ ታውቃላችሁ።

ባሕርይዋ የማይለወጥ ቤተ ክርስቲያናችን ጠባዩን ለለወጠው ዓለም ታስፈልገዋለች። አንዳንድ ሰዎች አሜሪካ ውስጥ ገዳም መሥራት ምን ያደርግልናል ሲሉ እንሰማ ነበር እኛ ኢትዮጵያውያን አሜሪካን በሃይማኖት ነው እንጅ በሌላ በምን ልንረዳት እንችላለን? ያጣችው ሃይማኖት ነው እንጅ ሌላውማ አላት። ወረርሽኝ በበዛበት አካባቢ የጤና ኬላ አብዝቶ ማቋቋም የሚድኑትን ያበዛል እንጅ ጉዳት የለም። የሠለጠነውን ዐለም ያኽል በዲያብሎስ የጥርስ ንክሻ የገባ ያለ አይመስለኝም ስለዚህ ገዳማት አድባራትን በውስጣቸው ብንሠራ ኪዳኑ፣ ቅዳሴው፣ ዕጣኑ መሥዋዕቱ ከጠላት ንክሻ ሊታደጋቸው ይቻለዋል።

ቤተ ክርስቲያን ካልደረሰችለት ዓለም ለጥፋት እየተቃረበ ነው። ወንበዴዎች ቀጥቅጠው በጎዳና ጥለው ልብሱን ገፈው ጥለውት ሲሄዱ እያየን ነው። በዶንኪ ቲዩብ እየተሠራ ያለው መልካም ሥራ የደጉ ሣምራዊን ሥራ የሚመስል ነው። ባለቤቱም እንደ ደጉ ሣምራዊ ነው። ከአህያው ወርዶ ማለትም ራሱን ከመጥቀም ወጥቶ ምዕመናን መጽናኛ የሚያገኙበት ቤተ ክርስቲያን በኳታር እንዲሠራ ማድረጉ የሚደነቅ ሣምራዊነት ነው። በዓለም ሁሉ ያሉትን ሰዎች ለበጎ ነገር ማነቃቃት መታደል ነው። በዚህ ስፍራ እግዚአብሔርን አግኝተው ንስሐ ገብተው ኃዘንተኛ የነበሩት ተጽናንተው ስታይ እንዴት ልብህ ትደሰት ይሆን? አንተ ደግ ሣምራዊ ያንተ ደስታ ማንም የማይቀማህ ደስታ ነው።

አንተ የምትደሰተው ጠላቶቻቸውን በዘመናዊ መሣሪያ አጥፍተው እንደሚደሰቱ የዓለም ኃያላን መንግሥታት አይደለም ከምዕመናን ጠላቶቻቸው አጋንንት ጠፍተውላቸው በማየትህ ነው እንጅ። ዓለም ሕዝቦቿን ስደተኛ እያደረገች ባለችበት በዚህ ዘመን ለስደተኞቹ ምዕመናን መኖሪያ የሚሆን የእግዚአብሔር ቤት ነው ብሎ አስቦ መሥራት እንዴት ያለ መታደል ነው? አወ ከዚህ በኋላ መዕመናን ልባቸው በዚያ ያድራልና ማደሪያ አልባዎች አይሆኑም። ዓለም በራሷ እጅ የሠራቻቸውን ከተሞች በራሷ እጅ እያጠፋች ባለችበት ወቅት የሰዎችን ተስፋ መገንባት መታደል ነውና ለታደልኸው ላንተ በተቀደሰ ሰላምታ ሰላም ብያለሁ። የደረስህላቸው ገዳማት ስላንተ ቀኑን ሙሉ እጃቸውን ዘርግተው ጸሎት እንደሚያደርሱ አንዳንዶችን ከቦታው ሂጀ አይቻለሁ።

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

27 Nov, 14:24


በትግል የምትኖሩ ሁሉ እግዚአብሔር በትግል ውስጥ ለምን እንዳኖራችሁ ትግላችሁ ውስጥ እግዚአብሔር እየሠራ ያለውን መልካም ነገር መርምሩና ድረሱበት። ምናልባትም በእናንተ ትግል ውስጥ ፈታኞቻችሁን እየቀጣላችሁ ይሆናል። የእስራኤል መቆየት ለግብጽ ቅጣት ነበር እንጅ ጥቅም አልነበረም።

ግብጽ በውኃ ፋንታ ደም የቀዳችው፣ ምድሯ በቅማልና በጓጉንቸር የተሞላው፣ ለሦስት ቀናት ብርሃን ከማየት የተከለከለችው፣ ከንጉሡ ቤት ጀምሮ በሁሉም ግብጻውያን ቤት ውስጥ በማለዳ ሬሳ የተገኘው በእስራኤል መቆየት ነው። እስራኤልን መልቀቅ ጥቅሙ ለእስራኤል ብቻ ሳይሆን ለግብጻውያንም ነበር። ፈርዖን ግን ይህንን አላወቀም።

ሰላም የነሡን ሰዎች ሰላም ቢሰጡን ዕዳ ቆልለው የሚያስጨንቁን ሰዎች ባያስጨንቁን ዕረፍቱ ለሁላችንም ከእግዚአብሑእር ዘንድ ይሆንልን ነበር ግን አስገባሪዎቻችን ይህ አይገባቸውም። እኛማ እግዚአብሔር የፈቀደው ቀን ሲደርስ ከዚህ መውጣታችን አይቀርም። ምክንያቱም በትግል ውስጥ እንድናልፍ ፈቃዱ ቢሆንም በዚያው ውስጥ ሳለን እጃችንን ለሞት እንደንሰጥ ግን አያደርገንም።

ዳዊት ከተቀባ በኋላ በሳዖል መሳደዱ ዱር ለዱር መንከራተቱ አያስደንቅም? በእግዚአብሔር ፈቃድ ለንጉሥነት የተመረጠው ዳዊት ከዕለታት አንድ ቀን የሚበላው አጥቶ ያልተፈቀደለትን እንጀራ እስከ መብላት ደርሷል። ይህ ሁሉ መሆኑ የዳዊት መንግሥት የጌታ ፈቃድ ባይሆን ነውን? አይደለም! ጨለማውም የሚመጣው በጌታ ፈቃድ ነው። ብርሃንም የሚሆነው በጌታ ፈቃድ ነው። “ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉም” ዮሐ 15፥5 ማለቱን አስተውሉ!

ማስታወሻ:- ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ የአራቱ ጉባኤያት መምህርና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ ሲሆን የመጻሕፍት ደራሲም ናቸው:: ሊቅ ሊቃውንት የጃንደረባው ሚዲያ ዐምደኛ ሲሆኑ ጽሑፎቻቸው ዘወትር ሰኞ የሚነበቡ ይሆናል::

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

27 Nov, 14:24


“እግዚአብሔር ባይፈቅድ ነው”

| ጃንደረባው ሚድያ | ኅዳር 2016 ዓ.ም.|

✍🏽 ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ እንደጻፉት

ካለፉት ቀናት መካከል አንደኛው ቀን የትምህርት ቤት ወንድሜን ለመጠየቅ የሄድሁበት ቀን ነበር። ከተገናኘን ብዙ ቀን ሆኖን ስለነበር ለእግርህ ውኃ ላሙቅልህ፣ ምግብ ይቅረብልህ አላለኝም። እንዲሁ ያለፈውን ዘመናችንን በዛሬ ዐይናችን እያየን በዛሬ ሚዛን እየመዘንን በሚያስቀው ስንስቅ በሚያስጸጽተው ስንጸጸት ቆይተን ለእንግድነቴ የሚገባው ግብዣ ከተደረገልኝ በኋላ ዛሬአችንን ወደ መገምገም ተመለስን።

የቆሎ ተማሪ አፈር ላይ ተኝቶ ይማራል እንጅ “አፈር ፈጭተን ውኃ ተራጭተን” ይሉት ጨዋታ አያውቅምና ያ አፈር ላይ ተኝቶ አብሮኝ ይማር የነበረው ጓደኛዬ ዛሬ የአንድ ድርጅት ባለቤት ሆኗል። የሚኖሩበት ቤት ፀሐይ ሳትወጣ ብትዘገይ የሚያሞቅ፣ የተመኙትን ነፋስ የሚያነፍስ መሣሪያ የተገጠመለት ዘመናዊ ድንኳን ነው። በመጨረሻ የጠየቅሁት ጥያቄና የመለሰልኝ መልስ ነው ዛሬ ለምጽፍላችሁ ደብዳቤ መነሻ የሆነኝ። “ዜማ ቤት እያለን ማኅሌት በጣም ትወድ እንደነበር አውቃለሁ እንዲያውም ትዝ ካለህ ከማኅሌት ስትመለስ የመጀመሪያ ሥራህ የነበረው ተኝተው ያደሩ ተማሪዎች ላይ ውኃ መድፋት ነበር ዛሬስ እንዴት ነህ?” አልሁት ትንሽ እንደማፈር ሲል አየሁት።

ትንሽ እንደማሰብ አደረገና “እኔማ አገልግሎት ምን ያኽል እንደምወድ አንተም ታውቃለህ ነገር ግን የምወደውን አገልግሎት ሰዎች አስጠሉኝና ተውሁት። ለጥቂት ቀናት እንዳልሄድ አለመፈለጋቸውን እያወቅሁ ተጋፍቸ ሄድሁ፤ አንድ ቀን መኪናዬን ያልተገባ ነገር አደረጉብኝ ሌላም ልነግርህ የማልፈልገውን አደረጉብኝ፤ ሲሰለቸኝ መቼስ ሰው ይደለሁ? በቃ ማገልገሌን እግዚአብሔር ባይፈቅድልኝ ነው ብየ እርግፍ አድርጌ ተውሁት ይሄው አራት ዓመቴ ማኅሌቱን ከተውሁት አለኝ”።

እንዲህ አይነት መወሰኛ ቃል እየተጠቀምን ነገሮችን ሁሉ በጅምር የምናስቀር ብዙ ሰዎች መኖራችንን ባሰብሁ ጊዜ እንድጽፍ ተገደድሁ። ብዙ ሰዎች ብትጠይቋቸው ያላገቡት እግዚአብሔር ስላልፈቀደ ነው። ያልቆረቡት እግዚአብሔር ስላልፈቀደ ነው። ሥራቸው ስኬት ያላመጣላቸው እግዚአብሔር ስላልፈቀደ ነው። የጀመሩትን ነገር ሁሉ ያልጨረሱት እግዚአብሔር ስላልፈቀደ ነው። ሩቅ አስበው ከቅርብ የተመለሱት እግዚአብሔር ስላልፈቀደ ነው። እንዲህ እያሉ ይቀጥላሉ። ሁሉንም ነገር እግዚአብሔር ስላልፈቀደ ብለው ነው የሚተዉት።

ለአንዳንዶቹ የሚመስላቸው እግዚአብሔር ከፈቀደ ያለምንም ትግል ነገሮች ሁሉ የሚከናወኑ ይመስላቸዋል። እግዚአብሔር ከፈቀደ ነገሮች ሁሉ “ለይኩን” በሚል ትዕዛዝ እንዲፈጸሙላቸው ይፈልጋሉ። እግዚአብሔር የፈቀደልንን ሕይወት ለመኖር ሲባል እኮ ነው ይሄ ሁሉ ተጋድሎ፤ የሰማዕታት ተጋድሏቸው፣ የጻድቃን ምናኔአቸ፣ የደናግል የመነኮሳት ትዕግሥታቸው፣ የሰብአ ዓለም ሕግ መጠበቃቸው፣ የካህናት ትጋታቸው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማስቀየር የሚደረግ ይመስላችኋል? ይሄ ሁሉ ሩጫ እግዚአብሔር የፈቀደልንን ሕይወት እንዳናጣ ለመሆን ነው።

ሐዋርያትን “ሑሩ ወመሀሩ” ብሎ ያዘዘ ማነው? ቅዱስ ጳውሎስን “ንዋየ ኅሩየ ረሰይኩከ” ብሎ ያከበረ ማነው? ኃጥአንን ለንስሐ የጠራ ማነው? ነገር ግን በፈቀደላቸው መንገድ ሲጓዙ የሚገጥማቸውን ተጋድሎ ተመልከቱ። ዓለም ሳይፈጠር ጀምሮ መንግሥተ ሰማያት ለሰው የተዘጋጀች ስጦታ ናት ቢሆንም ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀልንን ስጦታ ዓለምን ካላሸነፍን አናገኘውም ማቴ 25፥34፣ 1ዮሐ 5፥5
የእስራኤል ከግብጽ መውጣት ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቆረጠ ነገር ነበር። “በግብፅ ያለውን የሕዝቤን መከራ በእውነት አየሁ፥ ከአስገባሪዎቻቸውም የተነሣ ጩኸታቸውን ሰማሁ፤ ስቃያቸውንም አውቄአለሁ፤ ከግብፃውያንም እጅ አድናቸው ዘንድ፥ ከዚያችም አገር ወተትና ማር ወደምታፈሰው ወደ መልካሚቱና ወደ ሰፊይቱ አገር ወደ ከነአናውያንም ወደ ኬጢያውያንም ወደ አሞራውያንም ወደ ፌርዜወናውያንም ወደ ኤዊያውያንም ወደ ኢያቡሳውያንም ስፍራ አወጣቸው ዘንድ ወረድሁ” ዘፀ 3፥7 ብሎ መውጣታቸው ፈቃዱ መሆኑን ገልጿል።

ዳሩ ግን እስራኤል የእግዚአብሔር ፈቃድ ስለሆነ ያለምንም ሰልፍ ግብጽን ለቀው መውጣት አልቻሉም። እግዚአብሔር ለእስራኤል መውጣትን እንደፈቀደ ሁሉ የፈርዖንን ልብ እንደሚያጸናም “እኔም የፈርዖንን ልብ አጸናለሁ” ዘጸ 4፥21። ብሏል። ምን አይነት ነገር ነው? በአንድ በኩል ፈቅጃለሁ እስራኤል ይውጡ ይላል በሌላ በኩል የፈርዖንን ልብ አጸናለሁ ይላል።

ተመልከተው! የእግዚአብሔር ፈቃድ ታግለህ እንድታሸንፍ ነው እንጅ ለይኩን ተብሎ በቃል በተፈጠረ ዓለም ውስጥ በቃል እንደማዘዝ ቀላል በሆነ መንገድ እንድትጓዝ አይደለም። እግዚአብሔር ከፈቀደልህም በኋላ አስማተኞች ይፈታተኑሃል፤ ፈርዖን ፍርድ ያጠብቅብሃል፤ አስገባሪዎች ግብር ይጭኑብሃል፤ አንዳንዴም ለጸሎት ለዝማሬ ወደ ቤተ እግዚአብሔር ስታቀና ባዩ ጊዜ እንደ ሥራ ፈት ይቆጥሩህና ለማሰናከያ የሚሆን ሽልማት ያለው ሥራ ለምስጋና በተመደበው ጊዜ ያዘጋጁልሃል። እና አንዳንዴ እንዲያውም በቃ የጀመርሁት ጸሎት፣ ሱባኤ፣ ቅዳሴ፣ ቁርባን፣ ኪዳን የበለጠ ፈተናዬን ስላበዛብኝ ከሰይጣን ጋር እልህ ከምጋባ አርፌ ብቀመጥ ይሻለኛል እንድትል ያደርግሃል። እስራኤልም ያሉት እንዲሁ ነበር “በፈርዖንና በሠራዊቱ ፊት ሽታችንን አግምታችኋል፥ ይገድሉንም ዘንድ ሰይፍ በእጃቸው ሰጥታችኋልና እግዚአብሔር ይመልከታችሁ ይፍረድባችሁም” ዘጸ 5፤21 ብለው ሊያድኗቸው ከተላኩ አገልጋዮቻቸው ጋር መጣላት ጀመሩ። የተፈቀደልህ ቦታ እስከምትደርስ ድረስ ላንተ ነጻ መውጣት ከተላኩ ካህናት መነኮሳት ጋር ሳይቀር የሚያጋጭ ፈተና ያጋጥምሃል።

በአንድ በኩል እግዚአብሔር የላካቸው ሰዎች “እኔ እግዚአብሔር ነኝ ከባርነት ነጻ አወጣችኋለሁ፤ ከተገዥነትም አድናችኋለሁ በተዘረጋ ክንድ በታላቅ ፍርድም እታደጋችኋለሁ ለእኔም ሕዝብ እንድትሆኑ እቀበላችኋለሁ” ዘጸ 6፥6 ብሏል ብለው ይነግሩናል። ግን እግዚአብሔር በሕይወታችን ውስጥ ወዴት አለ? በሥራችን የረዳን፣ መከራችን ያቀለልን፣ ባርነታችንን ያስቀረልን መቼ ነው? እንላለን አይደል? አወ ይቀላል ስንል መከራው እየበዛ ሲሄድ፤ በምንረግጠው ጭቃ ውስጥ የልጆቻችን ደም ተቀላቅሎ ስናይ፤ በከተማው የሚሰማ የገራፊዎች ጅራፍ ድምጽ ብቻ ሲሆን፤ እስራኤል በደሙ ጭቃ አቡክቶ በሚገነባው ፒራሚድ ግብጻዊ ሲያጌጥበት ስናይ ከዚህ ሌላ ስሜት ሊኖረን እንደማይችል ይታወቃል።

ነገር ግን እውነቱን ከመጽሐፍ ቅዱስ ተረዱት። እግዚአብሔር “ኃይሌን ባንተ አሳይ ዘንድ ስሜም በምድር ሁሉ ይነገር ዘንድ ለዚህ አሰነሣሁህ” ሮሜ 9፥17 ብሎ የኃይ መገለጫ አድርጎታል። እኛ በፈርዖን ላይ የሚገለጠውን ኃይሉን እንጠባበቃለን እንጅ እግዚአብሔር እኛን ለማዳን አልፈቀደም ብለን አናንጎራጉርም።

የጌታ ፈቃድ እስኪሆን እስኪደረግ ድረስ በብርቱ ትግል ውስጥ እናልፋለን። ከዚህ አስጨናቂ ሕይወት መውጣታችንን ቢወድም ኃይሉን በጠላቶቻችን ላይ እንዲያሳይ የኛ ትዕግሥት ያስፈልጋል። የእግዚአብሔርን ማዳን ገና በሰፊው ስትደረግልን በሕይወታችን ውስጥ እናያለን። ከተፈቀደልን ሕይወት የምንደርሰው በትዕግሥት ነው።

ከማንጎራጎር ወጥተን በእኛ ላይ የወደደውን ለማድረግ ሥልጣን ያለውን ጌታ የሚያደርገውን ሁሉ በማስተዋል መመልከት ነው። ሸክላ ሠሪ የወደደውን ሊሠራበት በእጁ ያለውን ጭቃ ሥልጣን የለውምን? እግዚአብሒርም በእኛ ላይ የወደደውን የሚያደርግበት ሥልጣን አለው።

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

20 Nov, 14:18


ወደ እግዚአብሔር ፊታችሁን እንድትመልሱ ወንጌል የሰበኩላችሁና የዘመሩላችሁ ሰዎች ዛሬ የጫወታ ማድመቂያዎቻችሁ ናቸው።

ለሕመማችሁ ቅዱስ ቊርባንን መድኃኒት ማድረጋችሁ መልካም ነበር፥ ነገር ግን እንደ ቆረበ ሰው የኖራችሁት ኑሮ ወዴት አለ? ያለ ልክ ትናገራላችሁ፤ ሰክራችሁ ትታያላችሁ፤ አድማ ትሠራላችሁ፤ ሰውን ትጠላላችሁ። ታዲያ እንዴት በቊርባኑ ትጠቀማላችሁ? አንድ ሐኪም ባዘዘው መሠረት ያልተወሰደ መድኃኒት በሽታ የመከላከል ዕድል ሊኖረው ይችላልን?

ችግራችሁን ለመፍታት ካህናትን ማማከራችሁ መልካም ነበር “የማይፈታውን እንፈታ ዘንድ ሥልጣንን የሰጠኸን....” ብለው በመጽሐፈ ኪዳን ሲጸልዩ የሰማናቸው ካህናት ካልፈቱት ችግራችንን ማን ሊፈታው ይችላል። ነገር ግን ስህተታችሁ ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ከእውነተኞች መምህራን ትምህርት ይልቅ እንደ ሥነ ልቡና ባለሙያ ትችላለህ፤ ሕልም አለህ፤ የጌታ ልጅ ስለሆንህ ሁሉ ያንተ ነው፤ ጠላትህ የተወጋ ይሁን፤ ዐይነ ጥላ ተደርጎብሀል፤ ድግምት ተደግሞብሀል ወዘተ የሚሏችሁን ትከተላላችሁ። እውነተኛ ትምህርት ከመስማት ፈቀቅ ብላችኋል። የአጥማቂ፣ የነገር አዋቂ፣ የጎሳ፣ የጎጥ የምናምን አምላኪ ትሆናላችሁ። ክህነት በዘር ይወርድ ይመስል ከብሔሩ ውጭ በሆነ ካህን መባረክ የማይፈልግ ምዕመን እንዴት ብሎ ነው ከፈተና መውጣት የሚችለው? ምን ቢሆን ነው እግዚአብሔር ምሕረቱን ለሰው ሊሰጥ የሚችለው?

ለማንኛውም የፈተናው ምንጭ ራሳችን ከሆንን ራሳችንን እናስተካክል። ክርስቶስን ብለን የጀመርነውን ክርስትና በተለያየ ምክንያት የምንፈተንበት እንዳይሆን ከዐላማችን ፈቀቅ ልንል አይገባንም። ዐላማችን ክርስቶስን ተከትለን ወደ ቀራንዮ መድረስ ነው። ዮሐንስ ይህንን ሁሉ ፈተና መልስ ሳይሰጥ ስላለፈው ነው እንጅ ሌሊቱ ነግቶ በቀራንዮ ያየነው ዝም ብሎ እንዳይመስላችሁ። ድካም ካዩባችሁ ፈታኞቻችሁ ብዙ ናቸው። እንደ ዮሐንስ እያለፋችሁ መሄድን ልመዱ። ቀራንዮ ላይ በረከት ይጠብቃችኋል። ክርስቶስ ከምድር ከፍ ብሎ ታገኙታላችሁ። ማርያምን በእናትነት ትቀበላላችሁ። በገነት ለመኖር ዕድል ታገኛላችሁ። ለፈተና አሳልፈው የሰጡንን ድክመቶቻችንን ካወቅን ፈተናውን ማለፍ እንችላለን።

አቤቱ ወደ ፈተና ከሚወስዱ ክፉ ሀሳቦች አድነን!

በቴሌግራም https://t.me/simakonem

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

20 Nov, 14:18


በፈተና ላሉት

✍🏽 ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ እንደጻፉት

ይሄ ፈተና ከምን መጣ? ፈተናው ከእኛ ጋር ካሉት ይልቅ በእኛ ላይ ለምን በዛ? ምንጭ የሌለው ፈተና ባይኖርም ምንጩን ሳናውቀው በመጣ ፈተና ነፍሳችን ደከመች። ሰውነታችን ኑሮን ሰለቸች። ፈተናው አስመርሮናል፤ መከራው ከብዶናል ነገር ግን የፈተናውን ምክንያት ሳናውቅና ሳንመረምር ከፈተና ወደ ፈተና ስንሸጋገር እንኖራለን። በመጀመሪያው ማስቆም ሲቻል የመጀመሪያው ፈተና ይኸው ለቀጣይ ፈተና አሳልፎ ሰጥቶን በፈተና እንናወጣለን። በዚህ መንገድ አልፈው ብዙዎቹ ለሚፈልጉት ስኬት ደርሰዋል እኛ ግን አቃተን። በኛ ዘንድ ምናኔም ፈተና ሆኖብናል፤ ትዳርም ፈተና ሆኖብናል። ለምን?
ትዳር በእኛ አልተጀመረም። ከሴት ጋር መኖር ለብዙዎች በረከት ነው። መጽሐፍም “መወደዷ ከወርቅ ይመረጣልና ብልህና ደግ የሆነች ሴትን አትጥላ” ሲራ 7፥19 ብሎ ከቀይ ወርቅ ይልቅ የተወደደ ጸጋ ያላት መሆኑን ይናገራል። ቢሆንም እኛ ዘንድ ሲመጣ ፈተና ያልሆነብን ምን ነገር አለ? ቅዱሳን ሐዋርያት “በጌታ ዘንድ ሴት ያለ ወንድ፤ ወንድም ያለ ሴት አይሆንም” 1ቆሮ 11፥11 ብለው እያስተማሩን እኛ ግን ከዚያ ውጭ በሆነ ሕይወት መኖር እንደነበረብን እያሰብን ነው ያለነው።

የፈተናዬ ምንጭ እሷ ናት ወይም እሱ ነው እየተባባሉ የሚኖሩ ብዙዎች ናቸው። ባል ሚስቱን፤ ሚስትም ባሏን፤ ወንድም ወንድሙን ወይም አንዱ በሌላው ምክንያት ይህ ፈተና እንደመጣበት ሊያስብ ይችል ይሆናል። ዳሩ ግን የፈተና ምክንያት ብዙ ጊዜ በክርስትና ወጣንያን በሆኑ ሰዎች ሕይወት ውስጥ የራሳችን ፍላጎት እንጅ ከሰው ወይም ከሰይጣን የሚመጣ ፈተና እምብዛም የለብንም።

ከዕለታት በአንድ ቀን ጴጥሮስና ዮሐንስ ክርስቶስን ተከትለው ወደ አንድ ስፍራ ተጓዙ። ደብረ ታቦር ወይም ደብረ ዘይት ተከትሎ እንደመሄድ ያለ ቀላል መንገድ ግን አልነበረም። የሰው ገጠመኙ ብዙ አይደል? መንገዶች ሁሉ ወስደው፣ ወስደው የሚያጋፍጡን የሕይወት ግጥሚያ የተለያየ ነው። የነዚህም ቅዱሳን ሰዎች ጉዞ ከዚህ በፊት ከእርሱ ጋር ሲያደርጉት እንደነበረው ያለ ቀና መንገድ አልሆነላቸውም። እስካሁን በተጓዙባቸው ቦታዎች ሁሉ መለያየት አልታየባቸውም ነበር፤ በሁሉም መንገዶቻቸው ዕኩል ተጉዘው አብረው በደስታ ይመለሱ ነበር። ለሌላው የማይነግሩት ድንቅ ምሥጢር ተገልፆላቸው ይመለሱ ነበር። የዛሬው ግን ይለያል። አንዱን ከአንዱ የለየ ታሪክ የተስተናገደበት፤ ወንድማማቾች አብሮ ጀምሮ አብሮ መጨረስ ያልቻሉበት ፈታኝ ጉዞ ነበር። የጸና ብቻ ካልሆነ የተጓዘ ሁሉ የማያሸንፍበት መንገድ።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተያዘባት ሌሊት ከደቀ መዛሙርቱ መበተን በኋላ ከመበተን ተርፈው ሁለቱ ጴጥሮስና ዮሐንስ ብቻ እስከ ሊቀ ካህናቱ ግቢ ተከትለው መሄዳቸውን ቅዱስ ዮሐንስ በጻፈው ወንጌል ላይ ተጽፏል ዮሐ 18፥15 የጴጥሮስ መከተል በተናገረው ቃል መሠረት ነው ሉቃ 22፥33። የዮሐንስ ግን የሚደንቅ ነው። በአፉ ሳይናገር ሠርቶ የሚያሳይ ሰው እንዴት የታደለ ነው። ስላልነገሩን፣ ስላልጻፉልን፣ የጻፍነውን like share ስላላደረጉልን እንጅ በልባቸው የሚወዱን ስንት ሰዎች አሉ መሰላችሁ።

ከጴጥሮስ ቀድሞ በልቡ ከክርስቶስ ጋር ለመሞትም ሆነ ለእስራት ሊሄድ በልቡ ቃል የገባ ዮሐንስ ነው ነገር ግን በጉባኤ መካከል ከመናገር ተቆጥቦ ጉባኤው ከተፈታ በኋላ ሲያደርገው ታየ። ሕዝብ ሲሰበሰብ፣ ጉባኤው ሲሰፋ ማያደርጉትን ሚቀባጥሩ፤ እጃቸው ላይ የሌለውን ዘር ሊዘሩ የሚሞክሩ፤ በራበው ሕዝብ መሳለቅ ልምድ ሆኖባቸው ሊጎርስ አፉን ለከፈተ ሕዝብ እንጀራ ያልጠቀለሉበትን እጃቸውን የሚዘረጉ፤ የሕዝቡ መሰብሰብ ብቻ ገፋፍቶ የማያውቁትን የሚያናግራቸው፤ ከመናገራቸው በፊት ያላሰቡትን ተናግረው የሚያስቡ ሰዎች ይገርሙኛል። እንደ ዮሐንስ ያሉት ክርስቲያኖች ግን ሁሉን ነገር በጊዜውና በቦታው ካልሆነ አያደርጉትም። የቅዱስ ጴጥሮስ ፈተና የሚጀምረው ከዚህ ነው − የማያደርጉትን ከመናገር።

የማትፈጽሙትን ቃል ኪዳን አትግቡ። ከባድ ፈተና በሕይወታችሁ ይዞ ይመጣና ሕይወታችሁን ይበጠብጣል። ቃል ኪዳናችሁ ከመፈጸም ዐቅማችሁ በላይ ሊሆን አይገባም።
ለማንኛውም የጴጥሮስ ፈተና ቀጠለ። እስከ ሊቀ ካህናቱ ግቢ በር ድረስ አብሮ ቢመጣም ክርስቶስ በገባበት የመከራ በር አብሮ መግባት ከበደው። ለነፍሱ ሳስቶ ከበር ውጭ ቆሞ ቀረ። በሰዎቹ ዘንድ በመታወቅ ቢሆን ኖሮ ከዮሐንስ የሚበልጥ እሱን የሚያውቀው አልነበረም። “በሊቀ ካህናቱም ዘንድ የታወቀ ነበረ” ተብሎ የተጻፈው ለዮሐንስ ነውና። ግን ዮሐንስ በልቡ ጨክኖ ስለነበር ከክርስቶስ ፍቅር የሚለየው ምንም ነገር አልነበረም። ጴጥሮስ ገና ለዚህ መዐርግ አልደረሰም። የበረታው ዮሐንስ ያልበረታውን ወንድሙን ሊያበረታ ወደ ውጭ ወጥቶ ለበረኛይቱ እንድታስገባው ነገረለትና ገባ።

የበረታ ባልንጀራ ማለት ወንድሙን አንድ እርምጃ ወደ ክርስቶስ ማቅረብ የቻለ ነው። ግን አሁንም ሁኔታዎቹ ለጴጥሮስ ምቹ አልነበሩም። ቀኑ በጣም ውርጭ ነበርና የመጣበትን የክርስቶስን ነገር ረስቶ እሳት አንድደው ከሚሞቁ የሊቃነ ካህናቱ በለሟሎች ጋር ተሰልፎ ነፍሱን ለጊዜው ከሚደርስባት ጭንቅ ማዳን ፈለገ። የእሳቱ ወጋገን በገለጠላቸው ብርሃን ተመርተው ሂደው እየተመላለሱ መላልሰው ሃይማኖቱን አስካዱት። ያሳዝናል! በጥቂቱ የተጀመረ ፈተና አሁን ይኸው እዚህ ደረሰ። በትንሹ ያላጠፋነው ኃጢአት ለትልቅ ኀጢአት አሳልፎ ይሰጣል።

አሁን በሕይወታችን ለገጠመን ለዚህ ሁሉ ፈተና መነሻ የሆነውን ነገር እንዳትረሱ፤ ያ በመጀመሪያ ከልብ ጨክነን የማንፈጽመውን ቃል መግባታችን ነው። ብዙዎች ጥሩ ባለትዳር ሊሆኑ ሲችሉ ወደ ምንኩስና ገብተው ራሳቸውን ፈተኑ። አንዳንዶቹ ደግሞ ጥሩ መነኮሳት ሊሆኑ ሲችሉ ወደ ትዳር ገብተው ለራሳቸውም ለትዳር አጋራቸውም ፈተና ሆኑ። አንዳንዶቹ አለቅነት አልተሰጣቸውም። ለአለቅነት መሐላ ሲፈጽሙ ተዉ የሚላቸው ጠፍቶ ነው እንጅ ዛሬ እንዲህ የማይወጡት ፈተና ውስጥ ወድቀው አይቀሩም ነበር። ይሄን ሁሉ የትዕቢት፣ የፍቅረ ንዋይ፣ ድሆችን የመጥላት፣ ያለ ጊዜ መብላት መጠጣት እና ሌሎችም ፈተናዎች ከወዴት መጡ? ከምንችለው በላይ ማሰባችን፣ የማይገባ ንግግራችን የሚያመጣብን ፈተና ነው። ከቆንምለት ዐላማ መዛነፋችን፣ መንገዳችንን መሳታችን፣ ጅማሬአችንን ከፍጻሜችን የተለየ አድርጎታል።

ብዙዎቻችን አሁን በምንኖረው ሕይወት የጠበቅነውን ኑሮ ማግኘት አልቻልንም። ከዓለም ወጥተን ወደ ቤተ ክርስቲያን መጠጋታችን፤ ከመሸታ ቤቶች ይልቅ ቤተ ክርስቲያን አካባቢ ለማምሸት መምጣታችን፤ በችግራችን ሁሉ ካህናትን ለማማከር መወሰናችን፤ ለሕመማችን ቅዱስ ቊርባንን እንደ መፍትሔ ማሰባችን አሁን የደረሰብን ፈተና እንዳይደርስብን በመስጋት ነበር። ነገር ግን ካሰብነው በተቃራኒ ሆነ። ፈተናው መልኩን ቀይሮ መጣ። ለምን? አንዳንዶቻችን የፈተናው ምንጭ ራሳችሁ መሆናችሁን ላስረዳችሁ።

ከዓለማዊነት ወጥታችሁ ቤተ ክርስቲያን አዘውታሮች መሆናችሁ መልካም ነበር፤ ነገር ግን ትንሽ ከቆያችሁ በኋላ ለድኅነት ብላችሁ በተጠጋችኋት ቤተ ክርስቲያን ከድኅነቱ ድኽነቱ ይቅደም ብላችሁ BUSINESS መሥራት ጀመራችሁ። ዛሬ ለናንተ የታቦት መውጣት በጉጉት የምትጠብቁት የገቢ ምንጭ ሆኗል። ከመሸታ ቤት መውጣታችሁ መልካም ነበር፤ ነገር ግን አሁንም መጠጡ ነው እንጅ የቀረው የመሸታ ቤቱን ወሬ ይዛችሁት ቤተ ክርስቲያን ገብታችኋል። አዳራሽ ውስጥ በተቀመጣችሁ ጊዜ የምታወሩት ፌዝና ቧልት ከመሸታ ቤት ሰዎች በምን ይለያል? ያኔ

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

13 Nov, 18:40


በርተሎሜዎሶቻችንም ሰውን ተክለው ያጸድቁታል ብለን ተስፋ ስናደርግ ሰፊ እርሻ ከመንግሥት ተቀብለው አትክልት እየተከሉ እንደሆነ ሰማን እንግዲህ በዚህ ሰዓት የቀረን ብቸኛ ተስፋ ያንች መመለስ ነውና ርግቢቱ ሆይ! እባክሽ ተመየጢ?

ከመጣሽማ እንኳን ሰዎች መላእክት ይወርዳሉ። “ወሰላም በምድር” የሚለው ቅዳሴአችንም እውነት ይሆንልናል። ከመጣሽማ አባ ሕርያቆስም ለከንቱ ውዳሴ ሳይሆን በማብዛት ያይደለ በማሳነስ፤ በማስረዘም ያይደለ በማሳጠር ምስጋናሽን ያቀርባል። አድማጭ ሲኖር ዜማ የሚያስረዝሙ አድማጭ እንደሌለ ካወቁ ምስጋናሽን አስታጉለው የሚወጡ እነዚህን አናገኛቸውም ነበር።

ከመጣሽልንማ እንዚራ ስብሐቱን፣ አርጋኖኑን፣ ሰዓታቱን፣ ኆኅተ ብርሃኑን፣ ማኅሌተ ጽጌውን፣ አንቀጸ ብርሃኑን በስምሽ የሚደርሱልሽ አዲሶቹ አባ ጊዮርጊሶች፣ ቅዱስ ያሬዶች ይነሡልን ነበር። ይሄው አዲስ ድርሰት አዲስ ምስጋና የሚያሰማን አጥተን ስንት ጊዜ ሆነን። የዳዊት የሰሎሞን ርግብ ድንግል ማርያም ሆይ ተመየጢ ተመየጢ? እናይሽ ዘንድ ተመለሺ::

ማስታወሻ:- ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ የአራቱ ጉባኤያት መምህርና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ ሲሆን የመጻሕፍት ደራሲም ናቸው:: ሊቅ ሊቃውንት የጃንደረባው ሚዲያ ዐምደኛ ሲሆኑ ጽሑፎቻቸው ዘወትር ሰኞ የሚነበቡ ይሆናል::

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

13 Nov, 18:40


ተመየጢ ተመየጢ

ጃንደረባው ሚድያ | ኅዳር 2016 ዓ.ም.

✍🏽 ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ እንደጻፉት

“አንቺ ሱላማጢስ ሆይ ተመለሽ ተመለሽ፤ እናይሽ ዘንድ ተመለሽ ተመለሽ” መኃ 7፥1 በኖኅ መርከብ ውስጥ ሆኖ ዐይኖቹ አሻግሮ ማየት የማይፈልግ ማን አለ? ከዚያ ሁሉ ጥፋት በኋላ ምድርን መልሶ ማየት ያጓጓል። ለዐርባ ቀናት ከሰማይ የወረደውና ከምድር የገነፈለው ትኩስ ውኃ የተራሮችን ራስ ሳይቀር የሚገሽር ትኩሳት የነበረው ውኃ ነው።

ማንም ቢሆን ለአንድ መቶ ሃምሳ ቀናት ምድርን ይዟት የቆየውን ውኃ መጉደል አለመጉደሉን በልቡ ማውጣት ማውረዱ አይቀርም። በዚህ መካከል የምድሪቱን ዕጣ ፋንታ ሊያሳውቅ የሚችል ታማኝ መልዕክተኛ ማግኘት እንዴት መታደል ነው? መዓቱ ቆሟል፤ በመርከቧ ውስጥ የሚኖሩት ሁሉ የምድሩን ፊት ማየት ይፈልጋሉ። በዚህ ጊዜ ነው ኖኅ ርግብን ምድሩን አይታ እንድትመለስ የላካት። መጀመሪያ ሄደች ለእግሯ ማረፊያ ስላላገኘች ተመልሳ መጣች፤ ምድሩ በውኃ ተሞልቶ ነበርና። ዳግመኛ ላካት የውኃውን መድረቅ ለማመልከት የወይራ ዝንጣፊ ይዛ ተመለሰች ከሰባት ቀን በኋላ መልሶ ላካት አልተመለሰችም። ኖኅም ምድር ከጥፋት ውኃ ማረፏን በዚህ አወቀና ከመርከቡ ወጣ።

ርግቢቱን ወደ ዓለም ልኮ ኖኀ ከመርከብ ወጣ። ለጥፋት ውኃ መምጣት ምክንያት የሆነው ኃጢአት መጉደሉን የምትናገረዋ ርግብ እመቤታችን እስከትመጣ ድረስ የዚህችኛዋ ርግብ አገልግሎት እስከዚህ ድረስ ስለነበረ ነው − መመለሷን ሳይጠብቅ ከመርከብ የወጣው። የኖኅ ርግብ ሳትመለስ በዚያው መቅረቷ እንደ ቁራ የምድሩ ነገር ስቧት አይደለም፤ እውነተኛው ሰላም የሚሰበክበት፣ የጥፋት ውኃ በሚጎድልበት ሳይሆን የሰው ልጅ ከኃጢአት የሚያርፍበት ዘመን እስኪመጣ ድረስ ርግቢቱ አትመለስም።

ከዚያ በኋላ የተነሡ ነቢያት ይህንን ስለሚያውቁ ነው እንደ ኖኅ ዘመን ከሚበሩት አእዋፍ መካከል የሆነችውን ርግብ ሳይሆን ከሰዎች መካከል አንዷ የሆነችውን ርግብ ተመየጢ ተመየጢ ሲሉ የኖሩት። ከጥፋት ውኃ ሳይሆን ከኃጢአት መውጫ ጊዜው መድረሱን የምታበሥራቸውን ርግብ በሕይወተ ሥጋ መቆየት እስከቻሉበት ዘመን ድረስ ተመየጢ ተመየጢ እያሉ ደጅ ይጠኗታል። ርግቧ ካልተመለሰች ሰላም በምድር ላይ መታወጁን ማን ይናገራል? ቁራም አልተመለሰም። ሌላ መልዕክተኛም አልተገኘም።

መጥቀው ከሚበሩ ንስሮች ይልቅ ለሰላም አብሣሪነት የተመረጠች ይህች ርግብ እንዴት ያለች የተመረጠች ናት? ይህች ርግብ የእመቤታችን ምሳሌ ናት ብለው ሊቃውንት ተርጉመዋል። በሰሎሞን መኃልይ ላይ “ርግቤ መደምደሚያዬ” መኃ 5፥2 ተብላ የተጠራች እመቤታችንን ቅዱስ ኤፍሬም “ተፈሥሒ ኦ ማርያም ርግብ ሠናይት፤ በጎ ርግብ እመቤታችን ደስ ይበልሽ” ብሎ አመስግኗታል። ከዚህ አያይዞ የመልክአ ውዳሴ ደራሲ ደግሞ “ርግበ ገነት ጽባሓዊ፤ በምሥራቅ በኩል የተተከለችው የገነት ርግብ” ብሏታል። ከእመቤታችን ቀድመው ለእናትነት ቀድመው የተመረጡ ብዙ ቢሆኑም የሰላም አለቃ ክርስቶስን ለመውለድ ግን አልተቻላቸውም። በቅድስና የተመረጡ የታወቁ ሴቶችም ነበሩ የእመቤታችንን ያኽል በሰውና በእግዚአብሔር ዘንድ የታመነ የሰላም መልዕክተኛ ግን አልተገኘም።

በምድር ላይ የሚኖር ፍጥረት ሁሉ መምጣቷን እያሰበ ሲናፍቅ ነው የኖረው። በርግጥም በመጣች ጊዜ ክርስቶስን ይዛ በመገኘቷ መላእክት በምድር ላይ ለሚኖሩ ሁሉ “ለግዚአብሔር ምስጋና በሰማይ ይሁን በምድርም ሰላም” ሉቃ 2፥14 እያሉ አዋጅ ነገሩ። ስትጠበቅ የነበረችው የኖኅ ርግብ መጣችና ሰላምን ወለደችልን። ሰላም ከማንም ዘንድ የሆነችለን አይደለም፤ ሰላምን ተወልዳ ነው ያገኘናት ያውም ከሌላ አይደለም − ከእመቤታችን ነው።

ዛሬም የኖኅ ርግብ ሆይ! ተመየጢ ተመየጢ እንላለን።
ምድር እንደዚያን ጊዜው ሁሉ ሰላም የላትም። የሰላም ወሬ ሊያወራን የሚችል ማንም የለም። በያንዳንዱ ቀን ማለዳ መስኮታችንን ከፍተን የጥፋት ውኃ መጉደሉን የሚነግረን ሰው እንፈልጋለን ነገር ግን እስካሁን የነገረን የለምና ርግቢቱ እመቤታችን ሆይ እባክሽ ተመየጢ?

ይሆናል ብለን የላክነው ቁራ የምድርን በሬሳ መሞላት እንደ መልካም ነገር ሆኖለት ፊቱን ወደ እኛ አልመለሰም። ከኛ ጋር በነበረ ጊዜ በፊታችን ላይ ያየውን ጭንቀት ከኛ ተለይቶ ከወጣ በኋላ ረስቶት ሰላሙን ሊያበሥረን ወደኛ መመለስ አልፈለገም። ዛሬም የኛን ተሰብስቦ በአንድ ስፍራ መቀመጥ እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ዓለምን እንደፈለገ ብቻውን ከወዲያ ወዲህ ይመላልስባታል። ነገሮችን ሁሉ ለብቻው ሊጠቀምባቸው ወደደ። የመርከቧ ነዋሪዎች ተጨንቀዋልና ርግቢቱ ድንግል ማርያም ሆይ እባክሽ ተመየጢ?

ወይናችን እንዲያፈራ፤ አበባም በምድራችን ላይ እንዲታይ በመርከቧ ውስጥ ያለን እኛ ልጆችሽ ምድርን እንድንወርሳት ሱላማጢስ ሆይ ተመለሽ።

ሔሮድስ ሞቷል፣ አርኬላዎስ ነግሷል አልልሽም፤ እንዳልሞተ ታውቂአለሽ። አርኬላዎስ ብለን የሾምናቸው ሁሉ ሔሮድስ እየሆኑብን ተቸገርን። በኛ ዘመን በዳዊት ዙፋን የሚቀመጥልን፤ በልቡ እግዚአብሔርን መፈለግ ደስ የሚያሰኘው ንጉሥ እንኳን ባናገኝ በሔሮድስ ፋንታ ለይሁዳ የምንሾመው አርኬላዎስ ብንፈልግ አላገኘንም። የሕጻኑን ነፍስ የሚሿት ዛሬም አሉ አልሞቱም ግን ቢሆንም ተመየጢ!

ምድር የሞላት በግፍ የፈሰሰው የገሊላ አውራጃ ሕጻናት ደም ስለቆመ አይደለም ተመየጢ የምንልሽ ግፋችንን እንድታይልን ነው እንጅ። በኛ ዘንድ ስለልጆቿ የምታለቅስ ራሔል አሁንም እያለቀሰች ነው። ለቅሶም በራማ እየተሰማ ነው። ዋይታ በየደጁ አለ። ከሔሮድስ ቃል ተገብቶላቸው በገደሉት ሰው ልክ ሽልማት ሊቀበሉ የወጡት ገና አልተመለሱም። ግን ምን እናድርግ? ሰለ አባታሽ ስለ ኢያቄም፣ ስለ እናትሽ ስለ ሐና ብለሽ እመቤቴ ሆይ ተመየጢ?

ካልተመለስሽማ በመንፈስ ቅዱስ የሚመራ ደራሲ፤ “ወእቀውም ዮም በትሕትና ወበፍቅር” ብሎ የሚቀድስ፤ እንደ ዘካርያስ የሚያጥን፤ እንደ ሙሴ ቅብዐ ክህነት የሚቀባን ካህን ከወዴት እናገኛለን? ስለዚህ ነው ተመየጢ የምንልሽ። እመቤቴ ሆይ! አባቶቻችንን እንደ ጥንቱ የልብሳቸውን ዘርፍ ዳስሰን መፈወስ አምሮናል፤ ጥላውን ሲጥልብን የሚፈውስ ካህን ያስፈልገናል፤ ጋኔን ማውጣትም በገንዘብ ሆነ፥ እኛን ድሆችሽን ከአጋንንት እስራት ማን ነጻ ያውጣን? ተአምራት ማድረግም ትንቢት መናገርም ለግያዝ ሆነ።

ገንዘብ ሳይቀበሉ ከለምጻችን የሚያነጹን እነ ኤልሳዕ ቢፈለጉ አይገኙም። ስለሌሉ ሳይሆን ቅብዝብዝነታችንና ምልክት ፈላጊነታችን ካጠገባችን አርቋቸው ይኸው ባጠገባችን የሉም። ግሩም በሆነው በቊርባኑ ፊት በቆመ ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ “ጎሥዐ” ብሎ የሚያመሰግን ካህን ዐይናችን ፈለገ፤ ልባችን ተመኘ፤ ነገር ግን በምስጋና እና በውዳሴ “ጎሥዐ” ማለትን ትተው በልሳነ ሥጋ “ጎሳ” የሚሉት በዝተውብን እየተጨነቅን ነውና ተመየጢ?

የጴጥሮስ ጥላ የጳውሎስ ሰበኑ እመቤቴ ሆይ ቀራጩ ማቴዎስ ወንጌላዊ ተብሎ የተጠራው፣ ዐሣ አጥማጆቹ ወንድማማቾች ሰውን ወደ ማጥመድ የተለወጡት፣ ገበሬው ታዴዎስ፣ አትክልተኛው በርተሎሜዎስ ለዚህ መዐርግ የበቁት ባንች ነው። ሿሚውን ወለድሽላቸው፤ ታሪካቸውን የሚለውጠውን ወደ ዓለም አመጣሽላቸው። በእኛ ዘንድ ግን ነገሮች ሁሉ ተገለባብጠውብናል። ዓሣ አስጋሪ የነበሩት እነዚያ ወንድማማቾችም እንደገና መረብና መርከባቸውን ይዘው ወደ ገሊላ ባሕር ገብተዋል። ማቴዎስም ወደ ቀራጭነቱ ተመልሷል፤ ታዴዎስም ወንጌልን በገበሬ ዘር መስሎ ያስተምረናል ብለን ስንጠብቅ ዘር ወደ መዝራት ተመልሶ ዘሩን እየዘራ ነው።

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

10 Nov, 17:12


✍️ሊቀሊቃውንት ስምዓኮነ መልአክ

"የቅዱስ ዳዊት ታሪክ የእግዚአብሔርን ምሕረትና ፍቅር ለመረዳት እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ በታናሽነታችን ወራት እግዚአብሔር እንደሚያስበንና በታላቅነታችንም ወቅት ብናጠፋ እንደሚገሥጸን ከእረኛው ዳዊት ታሪክ እንማራለን፡፡

ዳዊት እግዚአብሔር ባከበረው ጊዜ የሚደሰት ባዋረደው ጊዜ የሚያንጎራጉር ሰው አይደለም፡፡ ተግሣጹንም በምስጋና የሚቀበል ሰው ነው። የእስራኤል ቆነጃጅት "ዳዊት ዕልፍ ገደለ" ብለው በዘመሩለት ጊዜ እንዳልተቃወመ ሳሚ ወልደ ጌራ ከኋላ እየተከተለ በሰደበውም ጊዜ አልተቃወመም፡፡

በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ባለሟልነትን ለምትሻ ነፍስ የዳዊት ታሪክ እንዲህ ባለ ሁኔታ ተዘጋጅቶ መቅረቡ እጅግ መልካም ነገር ነው፡፡ ምክንያቱም በልዕልና ስንኖር ድቀት እንደሚገጥመን፣ በድቀትም ውስጥ ብንሆን ተስፋ መቁረጥ እንዳያገኘን የሚያስገነዝቡ ብዙ ገጠመኞች በዚህ ቅዱስ ነቢይ ታሪክ ውስጥ ያሉ ስለሆነ ነው።

ከእረኝነት ወደ ንጉሥነት ከመጣበት መንገድ ይልቅ ለኔ ከኀጢአት ወደ ጽድቅ የመጣበት የንስሐ መንገድ ያስደንቀኛል። ከታናሽነት ወደ ታላቅነትማ የመጡ ብዙ ናቸው ከታላቅነት በኋላ በንስሐ ተዋርደው ክብራቸውን ያስመለሱ ግን ጥቂቶች ናቸው፡፡

ዳዊት ነቢዩ የእግዚአብሔርን ተግሣጽ ሰምቶ ባደረገው መመለስ ለምድራውያን ነገሥታት ብቻ ሳይሆን ለሰማያዊው ንጉሥ ለኢየሱስ ክርስቶስም አባት ሆነው᎓᎓ የማትጠፋ መንግሥት ባለቤት መሆን እንዴት ያለ መታደል ነው። ዲያቆን ኤልያስ የደከመች ነፍስን የሚያበረታ ታሪክ አንሥቶ በመጻፉ እጅግ ሊመሰገን ይገባዋል።

እኛም በእግዚአብሔር ዘንድ የሚረሳ ታናሽ፣ በእግዚአብሔር ፊት የማይቀጣ ታላቅ እንደሌለ አውቀን በምድር ብቻ ሳይሆን በሰማይም ታላቅ ለመሆን ይህን መጽሐፍ ብንመለከት መልካም ነው እላለሁ።"

የሊቀሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ጽሑፎች

09 Nov, 16:23


መልእክት ቀዳማዊ ኀበ ሰብአ ስቶክሆልም
[ወደ ስቶክሆልም ሰዎች የተላከ የመጀመሪያ መልእክት]
__________
ስለተቀደሰች ሃይማኖታችሁ፣ ግብዝነት ስለሌለባት ፍቅራችሁ ይህን እጽፍላችሁ ዘንድ ኅሊናዬ ግድ አለኝ። ከጎናችሁ የተኛ ትውልድ አለ፤ እናንተ ግን ንቃታችሁ የሚያስደንቅ ነው። ካጠገባችሁ ሃይማኖትን በታሪክ እንጅ በተግባር የማያውቁት ሕዝቦች አሉ፤ እናንተ ግን በሃይማኖት ውስጥ እየኖራችሁ ታሪክ ትሠራላችሁ። ሃይማኖቱ በሞተበት ሕዝብ መካከል ሆኖ በሃይማኖት መኖር ምንኛ አስጨናቂ ነው?
ለናንተ ግን ቀላል ነው። በዝማኔ ውስጥ ባለች ከተማ እየኖሩ የመነኑ አባት፣ እንደ ነፍሳቸው ለናንተ የሚሳሱ ካህናት አሏችሁና።

በከተማዋ መንገዶች መሐል ስንመላለስ የአባ ገብረ ጊዮርጊስ ልብሰ ምንኩስና የሚያስደነግጣቸው አንዳንድ ሰዎችን ሳይ የእግዚአብሔርን ሥራ ሳደንቅ ነበር።
በጳውሎስ ልብስ ይደነግጡ የነበሩ አጋንንት ዛሬም ባሉ ካህናት ልብስ መደንገጣቸው ቢያስገርመኝ ነው ሥራ 19:11
ባጠቃላይ ሃይማኖቷን ባልቀየረች ከተማ ውስጥ ሃይማኖታቸውን የለወጡ ሰዎች ናቸው ያሉት።
አገሪቱ ገና ከነ ሃይማኖቷ ናት። እዩት ባንዲራዋን፤ መስቀል ነው። (እኛ እንኳን ያላደረግነውን)
በዐደባባዮቿ ተመላለሱ እዚህም እዚያም መቅደስ ነው።
እዩልኝ ስም አወጣጧን፤ Mariatorget - ማርያቶሬት የሚባል ዐደባባይ አላት። የማርያም ዐደባባይ አላቸው። በማርያም እናትነት አያምኑም።
ግቡ ወደ መርከቧ፤ Exit Mariehamn የሚል ወደብ ታገኛላችሁ። ሰው የላትም እንጅ
አገሪቱማ ከነሃይማኖቷ ናት።

አለን አደል እንዴ እኛ አቡነ አኖሬዎስን ኑር ሁሴን፣ ሀገረ ማርያምን ቡሌ ሆራ ወዘተ ብለን ካልጠራን ብለን ሰልፍ የምንወጣ፥ ጸረ ሃይማኖት የሆነ ሀሳባቸውን በብሔር ነጻ መውጣት ስም ሲፈጽሙብን ሳንመረምር የተቀበልን። ምንም ዓይነት ሃይማኖታዊ ምልክት በምድሪቱ እንዳይገኝ ከሚሠሩት ጋር አብረን የተሰለፍን።
እናንተ ግን የማይቀድሱበትን መቅደስ ከሚንከባከቡ ሰዎች መካከል ናችሁ።
የማያምኑትን መስቀል ከከተማዋ አናት ላይ ሰቅለው ይንከባከባሉ።

ይሄ መቅደስ ድሮ አልነበራቸውም። በኋላ የነቅዱስ ጳውሎስ ጉዞ ያፈራቸው ምዕመናን በዘሩት ወንጌል የበቀሉ ሰዎች ያነጹት ነው። በመካከል አባቶቻቸው ከሠሩላቸው መቅደስ ወጥተው ያልሠሩላቸውን ከተማ መሥራት ጀመሩ።
ከተሞቻቸውን ገንብተው ሲጨርሱ በልባቸው የነበረች ሃይማኖታቸውን አጧት።
ስለዚህ በተሠራ ከተማ ውስጥ የፈረሰ ሃይማኖት ይዘው ያለ ተስፋ ይኖሩ ጀመር።

ይህን ሁሉ እያየሁ ከተማዋን በጎበኘሁ ጊዜ ስለናንተ እግዚአብሔርን አመሰገንሁት።
በዝቶ በሚፈሰው የኃጢአት ፈሳሽ እንዳትወሰዱ ጠብቋችኋልና።
ቤተ መቅደስ እያላቸው ጭፈራ ቤት ከሚያድሩ ሕዝቦች መካከል እየኖራችሁ ቤተ መቅደስ ሳይኖራችሁ ለሃይማኖት እንድትተጉ አድርጓችኋልና።
የእግዚአብሔር መቅደስ እናንተ ናችሁ። ምናልባትም ከኢትዮጵያ በቀር የሰው እጅ የሠራው ቤተ መቅደስ ከአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በፊት አልነበረም። የሮማ ነገሥታት በቤተክርስቲያን ላይ ከሚያደርሱት ጭካኔ የተነሣ ክፉዎች በሚገዟቸው ከተሞች ቤተ መቅደስ ሳይገነባ ለብዙ ዘመናት ክርስትናችን ቀጥሏል።
አሁንም እናንተ ካላችሁ ሌላውን ትሠሩታላችሁ። የተዘጉትንም ትከፍታላችሁ።
__________
ይህን እየጻፍኩ ቆይቼ ቀና ስል ከአገሬ ሰማይ ሥር መሆኔን የሚያሳይ ካርታ ተመለከትሁ። ወደ መስኮቱ አንገቴን ዘወር ሳደርገው አገሬ ነግቶላታል። በምሥራቅ ያሉ ተራሮችን ለማለፍ የምትታገል ፀሐይ ከሩቅ ወጋገኗን ማሳየት ጀምራለች። በደምብ እያየሁት ነው አገሬ በንጋት ውስጥ ትታያለች። ወደ መሬት ስወርድ የጨለማ ሥራ የከበባቸው ሰዎች ካልገጠሙኝ ከላይ ስመለከተው ነግቷል።
ኤርፖርት ላደረሳችሁኝ በሙሉ!
በመንገዴ አንድም ጊዜ አልረሳኋችሁም፤ ፍቅራችሁን ዐይናችሁ ላይ አየው ነበር። ሳትለዩኝ ተለያችሁኝ፤ ሳልለያችሁ ተለየኋችሁ።
አሁን ደመና በተረገረገበት የኢትዮጵያ ሰማይ ላይ ሆኜ እጽፍላችኋለሁ አባ፣ ዳንኤል፣ ሣራ፣ መቅደስ፣ ኤልያስ፣ ማካል ወርቅነህ እና ሰላም (አቤት አትሉም እንዴ) በሰላም ገብቻለሁ።

የእግዚአብሔር ጸጋ የወልድ ፍቅር የመንፈስ ቅዱስ ሰላም ከእናንተ ጋር ይሁን!!