ዕድሜ ዘመኑን ለኢትዮጵያ ጉድጓድ ሲምስ የኖረው፥ ኢትዮጵያን በስም ለመጥራት ጥዩፍ መሆኑን በአደባባይ ሲናገር ክብር የሚሰማው፥ ኢትዮጵያዊ ለመሆን ''እንደራደራለን'' እያለ ሲናገር የከረመው፥ 'አሮጊቷ' ሲልም ሊያንቋሽሻትና ሊያሳንሳት የሚታትረው የዘረኛውና የጽንፈኛው ካምፕ ሰሞኑን 'ከእኛ በላይ ኢትዮጵያዊ ላሳር' ዓይነት ጨዋታ ጀምሯል። ኢትዮጵያዊነት ሲበርደው የሚለብሳት ሲሞቀው የሚያወልቃት ማንነቱ ያልሆነችለት፥ በየትኛውም ዘመን፥ በየትኛው ክፉ ጊዜ ከጎኗ ሆኖ ሲታደጋት የኖረው፥ ከጎሳና ከብሄር ማንነቱ በላይ ኢትዮጵያዊነቱን አስቀድሞ ሲዋደቅላት የሰነበተው፥ ዛሬም የህልውና አደጋ በገጠማት ዘመን የትኛውንም ዋጋ ከፍሎ ሊያድናት ዝግጁ የሆነው ልጇ በእነዚህ ጎጠኞችና መንደርተኞች 'ባንዳ' የሚል ታርጋ ተለጥፎበት ስንሰማ 'ጊዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል' የሚለውን ተረት አስታውሶናል። የኢትዮጵያዊነት ካራንት ለኪና መዛኝ እነሱ መሆናቸው በእርግጥም ዓለም ቲያትር ናት የሚያሰኝ ነው።
በቅድሚያ ግን ከአንገት በላይ ቢሆንም እንኳን 'ኢትዮጵያን' በስም ለመጥራት አበቃችሁ። እንኳን ደህና መጣችሁ - ለማለት እንፈልጋለን።
በተረፈ በዚህ ዘመን ከግብጽ የበለጠ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ደህንነት ብርቱ ስጋት አብይ አህመድ ነው። ከሶማሊያ ልቆ የኢትዮጵያን ህልውና ከገደል አፋፍ ላይ ያስቀመጠው አቶ አያልቅበት አህመድ ነው። ከኤርትራ በላይ ኢትዮጵያን ሊያፈራርሳት ወገቡን ታጥቆ የተነሳው 7ኛው ንጉስ የሚል ቅዥት ውስጥ ገብቶ የሚዳክረው ሰውዬ ነው። ይህ ሀቅ ነው። በቁልል ውሸት የማይሸፈን፥ በፕሮፖጋንዳ መዓት የማይደበቅ፥ ግዙፍ እውነት። ከየትኛውም ውጪያዊና ውስጣዊ ሃይል በላይ የኢትዮጵያን ሉዋላዊነት ያስደፈረው ግለሰብ በጠራው 'የሉዋላዊነት ቀን ድግስ' ላይ አብሮ መታየት በራሱ የኢትዮጵያን ክብር ዝቅ የሚያደርግ ብቻ ሳይሆን በክህደት ወንጀል የሚያስጠይቅም ነው።
@Ankermedia