አብሰራ ገብርኤል ለማርያም

@enatachn_mareyam


እኔ #በእግዚአብሔር_ፊት የምቆመው #ገብርኤል_ነኝ

በቻናላናችን የሚሰጡ ነገሮች
መንፈሳዊ ትምህርቶች
መንፈሳዊ ምክሮች
መንፈሳዊ መዝሙር
መንፈሳዊ ጥያቄዎች
መንፈሳዊ ስዕልዎች
በየለቱ ስንክሳር

አስተያየት ካላቹ 👇👇👇
https://t.me/Enatemareyam21
https://t.me/Enatemareyam21

አብሰራ ገብርኤል ለማርያም

23 Oct, 13:12


                          †                          

[    🕊    ገ ድ ለ   ቅ ዱ ሳ ን   🕊     ]

▬▬▬▬▬▬   †    ▬▬▬▬▬▬

[  የአባታችን የቅዱስ መቃርዮስ የተጋድሎ ሕይወቱና ትምህርቱ  ]

[                ክፍል  ሃያ ስድስት                 ]

💛

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

[  እግዚአብሔር የአባ መቃርዮስን ጩኸት እንደ መለሰለት  ]

                         🕊                         

❝ በአንድ ወቅት ታላቁ አባ መቃርዮስ ከአስቄጥስ ወደ ግብፅ እየሄደ ሳለ ትንሽ ቅርጫቶች ተሸክሞ ነበር፡፡ እርሱም በደከመው ጊዜ ቁጭ አለ፡፡ ዓይኖቹን ወደ ሰማይ አቅንቶ ፦ " ጌታ ሆይ ፣ ምን ያህል እንደ ደከመኝና እንደዛልኩ የምታይ አንተ ነህ " አለ፡፡ ይህን ካለ በኋላ ወዲያውኑ ራሱን ከቅርጫቶቹ ጋር በዓባይ ወንዝ ዳር ላይ ደርሶ አገኘው፡፡

የቅዱስ መቃርዮስ ደቀ መዝሙር የነበረው አባ በብኑዳ እንዲህ አለ ፦ " አንድ ቀን ቅዱስ መቃርዮስ ቆሞ ሲጸልይ ሳለ እግዚአብሔር እንዲህ ሲል ተናገረው ፦ ' መቃራ ሆይ ፣ እገሌ በምትባል ሀገር ያለማቋረጥ በትጋት የሚያገለግለኝንና የሚያመሰግነኝን አንድ ገበሬ ምሰል፡፡ ' ይህን በሰማ ጊዜ ከመጀመሪያዎቹ አርድእት አንዱ የሆንኩትን እኔን በብኑዳን ፦ ' ተነሥና ምርኩዝህን ይዘህ ከእኛ ጋር እገሌ ወደምትባል ሀገር እንሂድ ' አለኝ፡፡ ወደዚያ ሄደን ከወንዙ ሐይቅ ዳር ደረስን ፣ የሚያሻግረን በፈለግን ጊዜ አላገኘንም ነበርና ስፋቱን እየተመለከትን ሁላችንም ዝም ብለን በዚያ ተቀምጠን ነበር፡፡ ቅዱስ መቃርዮስ ግን በተመሥጦ ሆኖ ራእይን እያየ ነበር፡፡

እኔም አባታችን ፣ እግዚአብሔር ጸሎትህን እንደሚሰማ አውቃለሁና ይረዳን ዘንድ ጸልይ አልኩት፡፡ ያን ጊዜም እየማለደ ጸለየ፡፡ ወዲያውኑ ታላቅ አዞ ከባሕሩ ወጣ ፤ ቅዱሱም ' እግዚአብሔር ከወደደና አዝዞህ ከሆነ አሻግረን ' አለው፡፡ ያ አዞም ተሸከመንና ወደ ማዶ አሻገረን፡፡ ቅዱስ መቃርዮስም ያንን አዞ ' እግዚአብሔር ዋጋህን እስከሚሰጥህ ድረስ ወደ ውኃው ግባ ' አለው፡፡ እርሱም እራሱን ወደ ውኃው አጠለቀ፡፡

ወደ ሀገሩ በወጣንና ወደዚያ በደረስን ጊዜ በሀገረ ገዢው እርሻ ላይ ተሰማርተው የሚሠሩ ብዙ ገበሬዎችን አገኘን፡፡ አረጋዊው መቃራም እነዚያን ገበሬዎች እያንዳንዳቸውን እየተመለከተ በበሩ አንጻር ተቀመጠ፡፡ እግዚአብሔር ስለ እርሱ ያመለከተው ያ ገበሬ በመጣ ጊዜ በዙሪያው ከብባው ያለችውን ጸጋ እግዚአብሔር ተመለከተ ፣ በትዕግሥት የተከደነ መሆኑንም አየ፡፡ ሰላምታ ሰጥቶ የተቀደሰች መሳምን ሳመው፡፡ ከዚያም እርሱን ይዞ ለብቻው ገለል አደረገውና ፦ 'እግዚአብሔርን የምታገለግልበት ሥርዓተ ተልእኮህ ምንድን ነው ? ' አለው፡፡ ያ ገበሬም ፦ ' እኔ በዚህ ዓለም ለቀሲስ [ ለካህን ] እላላካለሁ ፣ ጌታዬ ሰማያዊ ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስም ዋጋዬን ይሰጠኛል፡፡ ስለዚህም ይህን ያህል ዘመን ሁሉ ዘወትር አገለግላለሁ ፣ እኔም ልቤ የቀና ነው ' አለው፡፡

መቃርዮስም ፦ ' ይህን ሃሳብ ከየት አገኘኸው?' አለው፡፡ እርሱም ፦ " ሠራተኞቹን አምጧቸውና ደመወዛቸውን ስጧቸው " ካለው ከጌታ ቃል ነው ' አለው፡፡ ቅዱስ መቃርዮስም ይህን ነገር ከእርሱ በሰማ ጊዜ ሳመውና መከረው ፣ በላዩም ላይ ማሕየዊ በሆነ በትዕምርተ መስቀል ባረከው፡፡ ከዚያም ሲመለስ ነፍሱን ፦ ' መቃራ ሆይ ወዮልህ ፣ የዚህን ዓለማዊ ወንድም ያህል እንኳን አእምሮ የለህም ፣ ብታውቅበትና በምግባርህ እግዚአብሔርን ብታገለግል እርሱ ዋጋህን ይሰጥሃል' እያለ በመንገድ ላይ ሁሉ ታላቅ ለቅሶን ያለቅስ ነበር፡፡ "

" ወደ ወንዙ በደረስን ጊዜ የሚያሻግረን ስላጣን አባት መቃርዮስ በዚያ ጸለየ፡፡ እኛንም ፦ ' ልጆቼ ሆይ እግዚአብሔር እስኪረዳን ድረስ ተቀመጡ ' አለን፡፡ እኔም በዚያ ትንሽ ተኛሁና በነቃሁ ጊዜ እኔና እርሱን በበኣታችን በር ፊት ቆመን አገኘሁት፡፡ እኔም 'ይህ ነገር እንዴት ሆነ? አልኩት፡፡ እርሱም ፦ 'ልጄ ሆይ ነቢዩ እንባቆምን ከይሁዳ ምድር ወስዶ  ባቢሎን ከነቢዩ ዳንኤል ዘንድ እንደ ዓይን ጥቅሻ አድርሶ እንደ ገና ወደ ቦታው የመለሰው እርሱ ነውና እግዚአብሔርን አመስግን ፤ እኛንም ከዚህ ያደረሰን እርሱ ነው' አለው፡፡ ❞

የአባታችን የቅዱስ መቃርዮስ ምልጃና ጸሎቱ አይለየን፡፡

ይቆየን !


†                       †                         †
💖                    🕊                     💖

አብሰራ ገብርኤል ለማርያም

23 Oct, 10:53


🕊                        💖                       🕊   

[   🕊  የሥነ-ሥዕል ዐውደ ርእይ   🕊   ]

    ▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬

       [           በእንተ ሉቃስ          ]

- ከጥቅምት ፲፯ - ፳፬ [ 17 - 24 ]


የላፍቶ ፥ ፈለገ ብርሃን : ቅድስት ሥላሴ እና ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት የአቅሌሲያ ሕፃናት ሥነ-ሥዕል ክፍል

            [       ተጋብዛችኋል !       ]

[ ሳሪስ 58 ኪዳነ ምሕረት ጠበል 100 ሜትር ገባ ብሎ ]


🕊                        💖                       🕊

አብሰራ ገብርኤል ለማርያም

23 Oct, 04:58


የሚያሳድዷችሁን መርቁ . . . ደስ ከሚላቸው ጋር ደስ ይበላችሁ ከሚያለቅሱም ጋር አልቅሱ
እርስ በርሳችሁ በአንድ አሳብ ተስማሙ ። የትዕቢትን ነገር አታስቡ ። ነገር ግን የትሕትናን ነገር ለመሥራት ትጉ ። (ሮሜ. ፲፪፥፲፬-፲፮)

        
#_ሰናይ__ቀን🙏

አጫጭር ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቶች
      •➢ 👇  ለማግኘት // 👇

@Enatachn_mareyam  
@Enatachn_mareyam

አብሰራ ገብርኤል ለማርያም

22 Oct, 21:22


በነዚህ ዓመታት ሁሉ ይህ አካሉ የተለወጠ ሕጻን ቅዱስ ዘካርያስ መሆኑን ያወቀ የለም:: እንዲህ የቆሰለውም አሲድነት ካለው የጉድጉዋድ ውሃ ውስጥ ሰጥሞ ለ፵ [40] ቀናት በመጸለዩ ነው::

በመጨረሻ ግን አባቱ በምልክት ለይቶት አለቀሰ:: "ልጄ! አንተ ለእኔ አባቴ ነህ" ብሎታል:: አበው መነኮሳትም ተሰብስበው እጅ ነስተውታል:: በ፯ [7] ዓመቱ የመነነው አባ ዘካርያስ በ፶፪ [52] ዓመቱ በዚህች ቀን ዐርፎ በክብር ተቀብሯል::

አምላከ አፈ ወርቅ ዮሐንስ የድንግል እመ ብርሃንን ፍቅሯንና ውዳሴዋን ይግለጽልን:: ከአባቶቻችን ክብርና በረከትንም ያሳትፈን::

[  † ጥቅምት ፲፫ [ 13 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት   ]

፩. ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ
፪. አባ ዘካርያስ ገዳማዊ
፫. አባ ማርዳሪ ጻድቅ
፬. ቅዱስ አብጥማዎስ ሰማዕት

[    †  ወርኀዊ በዓላት    ]

፩. እግዚአብሔር አብ
፪. ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላዕክት
፫. ፺፩ "99ኙ" ነገደ መላዕክት
፬. ቅዱስ አስከናፍር
፭. ፲፫ "13ቱ" ግኁሳን አባቶች
፮. ቅዱስ አርሳንዮስ ጠቢብ ገዳማዊ
፯. አቡነ ዘርዐ ቡሩክ

" እናንተ የምድር ጨው ናችሁ . . . እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ:: በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሠወር አይቻላትም:: መብራትንም አብርተው በዕንቅብ በታች አይደለም እንጂ በመቅረዙ ላይ ያናሩታል:: በቤት ላሉት ሁሉም ያበራል:: መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ::" [ማቴ.፭፥፲፫-፲፮] (5:13-16)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖

አብሰራ ገብርኤል ለማርያም

22 Oct, 21:22


 🕊

✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞

❖ ጥቅምት ፲፫ [ 13 ] ❖

[  ✞ እንኩዋን ለዓለም ሁሉ መምሕር "ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ" እና ለአባ "ዘካርያስ ገዳማዊ" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞  ]

†   🕊  ዮሐንስ አፈ ወርቅ  🕊   †

ለቤተ ክርስቲያን የብርሃን ምሰሶ ስለሆነላት ስለ ታላቁ ሐዋርያዊ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ምን እላለሁ? ምንስ እናገራለሁ? እንደ እኔ ያለ ኃጥእ: ለባሴ ሥጋና ገባሬ ንስሃ ስለሱ ሊናገር አይቻለውምና:: አባቶቻችን እንደ ነገሩን ስለ አፈ ወርቅ ለመናገር "አፈ ወርቅ" መሆን ያስፈልጋል:: እስኪ በቅዱሱ አባት ምልጃ ጥቂት ልሞክር::

ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ማን ነው?

ነገዱ ከሶርያ: የተወለደው በ፫፻፵፯ [347] ዓ/ም በእስክንድርያ ሲሆን አባቱ አስፋኒዶስ እናቱ ደግሞ አትናስያ ይባላሉ:: እነርሱ ደግ ቢሆኑ ይህንን እንቁ ልጅ እግዚአብሔር ሰጣቸው:: ዮሐንስ ለክርስቲያን እንደሚገባ በትምሕርትና በጥበብ አደገ:: ገና በሕጻንነቱ ወደ ግሪክ ሔዶ የዘመኑን ሳይንስ [ፍልስፍና] ከአፉ እስከ ገደፉ ተምሮ ተመልሷል::

ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅን ለየት ከሚያደርጉት ነገሮችም አንዱ ይሔው ነው:: በዘመናዊም ሆነ በመንፈሳዊ ትምሕርት ይህ ቀረህ የማይሉት ሊቅ የሆነው ገና በ፲፭ [15] ዓመቱ ነበር:: በ፪ [2] ወገን የተሳለ ሰይፍ በመሆኑ ስንኩዋን በሕይወተ ሥጋ እያለ ዛሬም ለንፉቃን ትልቅ የራስ ምታት ነው::

ቅዱሱ ገና በ፲፮ [16] ዓመቱ ሃብት: ንብረት: ውበት: ክብርና እውቀት የሞላለት ቢሆንም ያለውን ሁሉ ለነዳያን ሰጥቶ መጻሕፍትን ብቻ ሰብስቦ ከባልንጀራው ቅዱስ ባስልዮስ ጋር በርሃ ገባ:: ሰውነቱን በጾምና በጸሎት እየቀጣ በበርሃ ሲኖር ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስና ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ዼጥሮስ ወደ እርሱ መጡ:: ሊቀ ሐዋርያት የመንግስተ ሰማያትን መክፈቻ ስልጣን ቅዱስ ዮሐንስ ደግሞ ወንጌሉን ሰጥተው ተሰወሩት::

ከዚህች እለት በሁዋላ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ባሕረ ምስጢራት ሆነ:: ብሉይ ከሐዲስ: ከኦሪት ዘፍጥረት እስከ ራዕየ ዮሐንስ ድረስ በአንድምታ ትርጉዋሜ ተነተናቸው:: በተለይ ሐዲስ ኪዳንን እየመላለሰ አመሰጠረው:: ቅዱስ ሕሊናው ሳይታክት: ንጹሕ እጆቹ ሳይዝሉ የጻፋቸው ድርሳናት: መልዕክታትና ትርጉዋሜያት ቢቆጠሩ አሥር ሺህ ሞሉ:: በእውነት ለዚህ አንክሮ ይገባል! የሚገርመው ይህን ሁሉ ሲሰራ እድሜው ገና ለጋ: ማዕርጉም ዲቁና ነበር::

ከዚህ በሁዋላ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ቅስና ተሹሞ በስብከተ ወንጌል ብዙ ቦታዎችን አዳረሰ:: በቅድስናው ወደውታልና የቁስጥንጥንያ ፓትርያርክ አድርገው ሾሙት:: አፈ ወርቅ ሲናገርም ሆነ ሲያስተምር እንኩዋን የሚያወራ ኮሽ የሚል የለም:: ከጣዕመ ትምሕርቱ የተነሳ ሕዝቡ በተደሞ ይሰሙት ነበር:: ሲያስተምር ምድራዊው ሰው ይቅርና ልዑላኑ መላእክት ተሰብስበው ያደንቁት ነበር:: አንዴም እመቤታችን በሕዝብ መካከል "አፈ ወርቅ" ብላ ጠርታዋለች:: ለዛም ነው "አፈ ወርቅ" የሚባለው:: ቅዱሱ በሥልጣነ ቃሉ መልዐከ ሞትን ገስፆ ፲ [10] ዓመት አቁሞታል::

ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ለሰው ፊት አያደላም:: በርሱ ዘንድ ንጉሥና ደሃ ነዳይ እኩል ነው:: ለሞት ያበቃውም ይሔው ነበር:: ምክንያቱም የወቅቱ ንግስት አውዶክስያ ያንዲት ድሃ መበለትን መሬት ቀምታ "አልመልስም" በማለቷ መክሮ አወገዛት:: እርሷ ግን ከኃጥአንና መናፍቃን ጋር መክራ 2 ጊዜ አጋዘችው:: በተሰደደበት ሃገር ፍሬ አፍርቶ: አስተምሮና አሳምኖ በ፬፻፯ [407] ዓ/ም አርፏል:: ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን ሳይጠግቡት እንደናፈቁት በ፷ [60] ዓመቱ አጡት:: በወቅቱ ታላቅ ሐዘንና ለቅሶ ተደረገ::

ከዕረፍቱ አስቀድሞ አንድ ቀን የዘመኑ ደግ ንጉሥ
አርቃድዮስ ግብር አገባ:: [ግብዣ አዘጋጀ]

በዚያች ሌሊት ደግሞ ቅዱሱ ሊቅ ታጥቆ ሲጸልይ ሳለ: አባ ማርዳሪ የሚባል ጻድቅ ደግሞ ከሰማይ ፲፪ [12] ቱ ሊቃነ መላእክት [እነ ቅዱስ ሚካኤል] ከሰማይ በግርማ ሲወርዱ ተመለከተ::

ደንግጦ "ወዴት ናችሁ ጌቶቼ" ቢላቸው "ቁስጥንጥንያ: ወደ ዮሐንስ አፈ ወርቅ እንሔዳለን:: እርሱ እመቤታችንን እንደሚያመሰግናት ጌታ ነግሮናልና" አሉት:: "እባካችሁ እኔም የአፈ ወርቅ ምስጋናው እንገለጥልኝ መርቁኝ" አላቸው:: ሊቃነ መላእክቱም መርቀውት ጐዳናቸውን ቀጠሉ::

በማግስቱ በቤተ መንግስት ውስጥ ሊቃውንቱ: መሳፍንቱ: ዻዻሳቱ: ሕዝቡ ሁሉ ተሰብስበው ከድግሱ በሉ:: ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ግን በመንበሩ ተቀምጦ ነበር እንጂ አልበላም:: ድግሱ ሲጠናቀቅ ንጉሡ አርቃድዮስ ሊቁን "ጥያቄ አለኝ" ብሎ በጉባኤ መካከል ጠየቀው::

"ምነው ወንጌላዊ ማቴዎስ 'ኢያዕመራ ዮሴፍ እስከ አመ ወለደት ወለደ ዘበኩራ-የበኩር ልጇን እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም' ማለቱ [ማቴ.፩፥፳፭] (1:25) ስለ ምን ነው?" ቢለው ቅዱሱ ተነስቶ: በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ይተረጉምለት ጀመር::

"ድንግል ማርያም ንጹሕ ብርሌን ትመስላለች:: ብርሌ የተለያየ ቀለም ያለው ፈሳሽ ቢያስገቡበት ቀለሙ አብሮ ይቀያየራል:: እመቤታችንም ጌታን ጸንሳለችና ሕብረ መለኮቱ ሲለዋወጥ መልኩዋ አብሮ ሲለዋወጥ እያየ ዮሴፍ ይደነግጥ ነበር::

'እርሷ ማን ናት? በማሕጸኗ ያለውስ ማን ነው?' እያለ ይጨነቅ ነበር:: ጌታን ከወለደች በሁዋላ ግን አንድ ሕብረ መልክ ሆናለችና:: አስቀድሞ ማን እንደ ነበረች አላወቀም::

አሁን ግን ልጇ አምላክ ዘበአማን: እርሷም ወላዲተ አምላክ መሆኗን አወቀ ማለት ነው" እያለ ሲተረጉም ሰምተው ሁሉም ሲያደንቁ በዚያ የነበረች ስዕለ አድኅኖ "አፈ ወርቅ! ልሳነ ወርቅ! አፈ በረከት!" ስትል ተናገረች::

ያን ጊዜ አርቃድዮስ የወርቅ ልሳን በሊቁና በስዕሏ ላይ አደረገ:: አፈ ወርቅ ግን ባጭር ታጥቆ "እሰግድ ለኪ! እሰግድ ለኪ! ወእዌድሰኪ . . ." ብሎ ዛሬ በተአምረ ማርያም የምናውቀውን ምስጋና ሰተት አድርጐ አደረሰላት:: ይህንን ምስጋናም ሊቃነ መላእክቱ ሰምተው እያደነቁ ወደ ሰማይ ወጥተዋል::

ቅዱሱ ሲጠራ እንዲሕ ነው :-

¤ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ
¤ አፈ በረከት
¤ አፈ መዐር [ማር]
¤ አፈ ሶከር [ስኩዋር]
¤ አፈ አፈው [ሽቱ]
¤ ልሳነ ወርቅ
¤ የዓለም ሁሉ መምሕር
¤ ርዕሰ ሊቃውንት
¤ ዓምደ ብርሃን [የብርሃን ምሰሶ]
¤ ሐዲስ ዳንኤል
¤ ሊቀ ዻዻሳት ዘበርትዕ [እውነተኛው]
¤ መምሕር ወመገስጽ ዘኢያደሉ ለገጽ
¤ ጥዑመ ቃል - - -


†  🕊  አባ ዘካርያስ ገዳማዊ  🕊  †

ይህ ታላቅ ጻድቅ ባለ ጥዑም ዜና ነው:: ወላጆቹ እሱንና አንዲት ሴትን ከወለዱ በሁዋላ አባቱ መንኖ ገዳም ገባ:: ከዘመናት በሁዋላ ረሃብ በሃገሩ ሲገባ እናቱ ወስዳ ለአባቱ ሰጠችው:: ይህን ጊዜ ዕድሜው ፯ [7] ዓመት ነበር::

በገዳም ከአባቱ ጋር ሲኖር ከመልኩ ማማር የተነሳ አባቶች መነኮሳት "ይህ ልጅ ይህን መልክ ይዞ እንዴት መናኝ መሆን ይችላል!" ሲሉ ሰማ:: በሌሊትም ተነስቶ በሕጻን አንደበቱ "ጌታየ! መልኬ ካንተ ፍቅር ከሚለየኝ መልኬን አጠፋዋለሁ" አለ:: ከገዳሙም ጠፋ::

አባትም በጣም አዘነ:: ከ፵ [40] ቀናት በሁዋላ ግን ሊያዩት የሚያሰቅቅ: አካሉ ሁሉ የቆሳሰለ አንድ ነዳይ ሕጻን መጥቶ ወደ ገዳሙ ተጠጋ:: ይህ ሕጻን በጾም: በጸሎትና በትሕትና ተጠምዶ ለ፵፭ [45] ዓመታት አገለገለ::

አብሰራ ገብርኤል ለማርያም

22 Oct, 15:37


                          †                          

💖  [    የትሕርምት ሕይወት !    ]  💖

🕊                       💖                      🕊


[      ❝ አገልግሎትን በተመለከተ ! ❞     ]

❝ ተወዳጆች ሆይ ! ጅማሬአችሁን መልካም እንዳደረጋችሁ እንዲሁ የዕርጅና ዘመናችሁን በደስታ ልትፈጽሙ ይገባችኋል። ብርሃናችሁም በዝቶ ለዓለም እንዲያበራ በቅድስና ሕይወት ተመላለሱ፡፡

ተወዳጆች ሆይ ! ከእናታችሁ ማሕፀን ኃጢአት የሚስማማው ባሕርይን ገንዘባችሁ አድርጋችሁ ተወልዳችሁ ነበር። በኃጢአት ሕይወትም ተመላልሳችሁ ነበር፡፡ ስለዚህ በጽድቅ ሥራ ስለመጽናትና እግዚአብሔርን ወደ መምሰል በማደግ ራሳችሁን ጽኑ በሆነ መሠረት ላይ ትመሠረቱ ዘንድ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቃችሁ አዲሱን ሰው ክርስቶስን ለብሳችሁታል፡፡

ስለዚህ ወንድሞች ሆይ ከሁሉ በላይ በጻድቃን የሚመሰገነውን እግዚአብሔር አምላካችሁን በመፍራት ተመላለሱ፡፡

ተወዳጆች ሆይ ! ትሑት የሆነውና እናንተን ከልጅነት ጀምሮ በጥበብ ያሳደጋችሁ እርሱ አምላካችሁ እስትንፋችሁ እንክትቋረጥ ድረስ የሚተዋችሁ አምላክ አይደለም፡፡

ከታዳጊነት ዕድሜአችሁ ጀምሮ የእርሱ ምርጥ ዕቃ ትሆኑ ዘንድ ለራሱ ካጫችኹ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምስጋናን ትቀበሉና በእናንተ ምክንያት ሰዎች እርሱን እንዲያከብሩ ፍጻሜ ዘመናችሁን በቅድስና ፈጽሙ፡፡

እርሱ ሁሉ የእርሱ ሲሆን እኛን ባለጠጎች ሊያደርገን ደሀ ሆነ፡፡ ስለዚህ ተወዳጆች ሆይ ! ለነፍሳችሁ ዕረፍትን ታገኙ ዘንድ ራሳችሁን ከእርሱ ቀንበር በታች አኑሩ። “ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳልና።” [ሉቃ.፲፬፥፲፩] ብሎ ጌታችን አስተምሮአልና በትሕትና ሆነን እንመላለስ፡፡

ለእርሱ ክብር ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡ ❞

[  ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ  ]


🕊                       💖                   🕊

አብሰራ ገብርኤል ለማርያም

22 Oct, 12:36


                          †                          

[    🕊    ገ ድ ለ   ቅ ዱ ሳ ን   🕊     ]

▬▬▬▬▬▬   †    ▬▬▬▬▬▬

[  የአባታችን የቅዱስ መቃርዮስ የተጋድሎ ሕይወቱና ትምህርቱ  ]

[                ክፍል  ሃያ አምስት                 ]

💛

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

[  አጋንንት ቅዱስ መቃርዮስን አብዝተው እንደ ተዋጉት  ] [ - ፪ - ]

                         🕊                         

❝ በአንድ ወቅት ከአኃው ጋር የውኃ ጉድጓድ እየቆፈሩ እያለ በእኩለ ቀን ላይ የፀሐይ ቃጠሎ ስለ ጸናባቸው ያርፉ ዘንድ በሄዱ ጊዜ ቅዱስ መቃርዮስ እጁን ለመታጠብ ብቻውን ወደ ኋላ ቀርቶ ነበር፡፡ ያን ጊዜ ሰይጣናት ወደ ውኃ ጉድጓድ ውስጥ ወረወሩት፡፡ አኃው በጉድጓዱ ዙሪያ አንጸዋቸው የነበሩትን ድንጋዮች ሁሉ እያነሡ ወደ እርሱ ወረወሩበት ፣ ድንጋዩም እስከ ግማሽ ሰውነቱ ያህል ሸፈነው፡፡

ይህን ነገርም ከአኃው አንዱ ባወቀ ጊዜ ወደ ጉድጓዱ ሲመጣ ቅዱስ መቃርዮስ ዙሪያውን በድንጋይ ተከቦ አየው ፤ ነገር ግን ከዚያ ሰይጣናት ከጣሉበት ጉድጓድ ውስጥ ያወጣው ዘንድ አልቻለም፡፡ ከመምጣት በዘገየ ጊዜ አኃው ወደዚያ ሲሄዱ ቅዱስ መቃርዮስ በድንጋይና በጭቃ ተከቦ ፣ የሠሩትም ሥራም ፈርሶ ድካማቸው ሁሉ ከንቱ ሆኖ አገኙት፡፡

አኃው እርስ በእርሳቸው " አባታችንን ዛሬ ምን አገኘው " አሉ፡፡ " ቅዱስ አባታችን ሆይ ይህን ያደረገብህ ማነው ? " አሉት፡፡ እርሱም ፈገግ አለና ፦ " ከዚህ ጉድጓድ አውጡኝ " አላቸው፡፡ እነርሱም አወጡት ፤ ከዚያም የሆነውን ነገር ሁሉ ነገራቸው፡፡ ከዚያ በኋላም ከበፊቱ የበለጠ ጥልቅ የሆነ ጉድጓድ ቆፈሩ፡፡ እንዲህ እያደረጉ አኃው ብዙ ጉድጓዶችን ቆፈሩ፡፡ በዚያ ሰይጣናት እርሱን በጣሉበት የውኃ ጉድጓድም ከዕረፍቱ በኋላ እግዚአብሔር ብዙ ተአምራትን በዚያ የጉድጓድ ውኃ አማካኝነት አደረገ፡፡

በሌላ ጊዜም ቅዱስ መቃርዮስ ብቻውን ቁጭ ብሎ እያለ ኪሩባዊው ተገለጠለት ፣ እርሱም ባየው ጊዜ እጅግ ፈራ፡፡ ኪሩባዊውም ፦ "በተጋድሎህ ጽና ፣ በሰይጣናት ጥላቻና ተንኮል ላይ በርታባቸው እንጂ እንዳትዘናጋ ተጠንቀቅ ፣ በሰዎች ላይ በምታደርገው ነገር ሁሉ እግዚአብሔርን አመስግን እንጂ ራስህን ከፍ ከፍ እንዳታደርግ ተጠበቅ " አለው፡፡ ቅዱስ መቃርዮስም ፦ " እነሆ ሰይጣናት ነፍስና ሥጋዬን እያስጨነቁኝና እያሰቃዩኝ ምኑን እታበየዋለሁ ፤ ከጌታዬ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ረዳት የለኝም ፣ ፈውስን የምታደርግልኝ ጸጋው ናትና" አለው፡፡ ኪሩባዊውም ፦ " የምታደርጋቸውን ድካምህንና ተጋድሎህን መከራህንና ችግርህን ሁሉ ከአንተ ዘንድ ያሉትን ታልፋቸዋለህ " አለው፡፡ ❞

የአባታችን የቅዱስ መቃርዮስ ምልጃና ጸሎቱ አይለየን፡፡

ይቆየን !


†                       †                         †
💖                    🕊                     💖

አብሰራ ገብርኤል ለማርያም

22 Oct, 05:58


#ሚካኤል_ሆይ በጠላት ተማርከው
ለሚጨነቁትና ለሚሰቃዩት ዋስ
ጠበቃቸው አንተ ነህና በእኔ ለይ
የሚተበትቡትን የጠላቶቼን የምክር
መረብ በጣጥሰህ ጣልልኝ ነፍሴንም
ስጋዬንም ለአንተ አደራ ሰጥቼሀለሁና።

#ኃያሉ_ሚካኤል_ሆይ ኃይልህን የሰው
ኃይል ሊተካከለው አይችልምና
እንግደለው እናጥፋው የሚሉትን
ጠላቶቼን ጭጋግ በቀላቀለ በዓዉሎ
ንፋስ በትናቸው።

        
#ሰናይ__ቀን 🙏

ለመቀላቀል
@Enatachn_mareyam  
@Enatachn_mareyam