‹‹፡ በዘመቻ ቻቻና፣ በወረት ከበርቻቻ ካልሆነ በስተቀር በራሱ ጊዜ እንቦጭን ለመንቀል የሚተጋ አንድ ሰው የለም፡፡ የካሮት አትክልትን ባየበት ቦታ ሁሉ ለመንቀል የሚቋምጥ ግን መአት ነው፡፡በሚንረል ምልዖቱ ፣ በንጥረ- ምግብ ይዘቱ ተወዳጅና ተመራጭ ነውና፡፡
ሙጃ በቅሎ፣ እዛው አፍርቶ እዛው ደርቆ እዛው ባለበት እስኪበሰብስ የሚያጭደው ቀርቶ የሚነካው የለም፡፡ ስንዴን ወይም ጤፍን ወይም ገብስን ግን ገና ከማሸቱ ማጭዱን ይዞ የመድረቂያውን ቀን የሚጠባበቀው ብዙ ነው፡፡የረሀብ ጌታ፣የምጣኔው አለኝታ፤ የጎታው ነጭ ወርቅ፣የዋድያቱ ነጭ አዝሙድ፣ የምጣዱ ላይ ነፍስ አድን ነውና፡፡
ቅንጭብ ላይ ድንጋይ የሚወረውር የለም፡፡ የብርትኳን ወይም የማንጎ ወይም የእንኮይ ዛፍ ላይ ግን ሁሉም ድንጋይ ይወረውራል፡፡ ጣፋጭ ፍሬ ስለሚያፈራ፡፡ ቅንጭብና ቁልቋል ላይ መጥረቢያ የሚያነሳ ሰው የለም፡፡ ዝግባ ጥድና ባህርዛፍ ላይ ግን መጥረቢያውም ዶዘሩም ያጓራል፤ ለቤቱ ካስማ ለድልድዩ ጋድማ፣ ለህንጻው ማማ ናቸውና፡፡››
ሰዉን ናሰው ምዕራፍ 2