ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia) @ethbiblica Channel on Telegram

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

@ethbiblica


ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia) (Amharic)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia) ከኢትዮጵያ አማርኛ ታሪክ ገጽን ድረገጽ ነው ብሎ ሲመጣ፣ ይህ ማለት አሁን ዓረፈችው መሳሪያ ውስጥ ስለተነገረኝ ነው። እናም ደግሞ ስለ ወቅታዊ መጽሐፍና የጽሑፍ ጽሑፍ ምንም ያህል አይነት አገኘውኩት። በዚህ ቪኒቨር ውስጥ ወደ ታሪክዎ ገጽ ለመቀጠል እና ለመረባት በሰለሞን እይታ ይጠቀሙ። በኢትዮጵያ ቦሪያ ውስጥ በአማርኛ መጽሐፍና ጽሑፍ በተፈረመ ሰዎች በእምነት መጽሐፍና አፍ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

19 Feb, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

አማኝ ታዳሽ ኅይል አለው። ይህም ኅይል አምላኩን ተስፋ ከማድረጉና ከርሱ ጋር ከመሆኑ—ከመጣበቁ—የተነሣ የሚመጣ ነው። የእግዚአብሔር ሕዝብ በደከመበት፣ ተስፋ በጣለበትና ባመነታበት ጊዜ መልእክት መጣለት፤ "እግዚአብሔርን ተስፋ የሚያደርጉ ግን፣ ኀይላቸውን ያድሳሉ፤ እንደ ንስር በክንፍ ይወጣሉ፤ ይሮጣሉ፤ አይታክቱም፤ ይሄዳሉ፤ አይደክሙም" (ኢሳ 40፥31)። ሕይወት ብዙ ትግልና ውጣ ውረድ ስላለው ኅይል ጨራሽ ነው፤ ሰዎችም ይደክማሉ፤ ይታክታሉም። አቅም የሆነውን አምላክ የሚጠጋጉ ግን ደክመው አይቀሩም፤ ይታደሳሉ፤ ጕዟቸውም እንደ ንስር ወደ ላይ ይሆናል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

19 Feb, 04:04


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔርን ተስፋ የሚያደርጉ ግን፣ ኀይላቸውን ያድሳሉ፤ እንደ ንስር በክንፍ ይወጣሉ፤ ይሮጣሉ፤ አይታክቱም፤ ይሄዳሉ፤ አይደክሙም።"

(ኢሳ 40፥31 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Feb, 11:04


የዕለቱ ሐሳብ

አቅምና ብርታት ለሁሉ የሚያስፈልግ፣ ሁሉም የሚሻው ነው። ዘማሪው እንዲህ አለ፤ "እግዚአብሔር ለሕዝቡ ብርታታቸው ነው፤ ለቀባውም የመዳን ዐምባ ነው። ሕዝብህን አድን፤ ርስትህንም ባርክ፤ እረኛ ሁናቸው፤ ለዘላለሙም ዐቅፈህ ያዛቸው" (መዝ 28፥8-9)። የእግዚአብሔር ሕዝብም ከሌላው የሚለየው አምላኩ ብርታቱ ስለሆነ ነው። ብርታቱ ግን የምንካፈለው እንጂ ወስደን የራሳችን የምናደርገው አይደለም፤ ከርሱ የራቁ ከብርታቱም ይርቃሉና።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Feb, 04:01


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔር ለሕዝቡ ብርታታቸው ነው፤ ለቀባውም የመዳን ዐምባ ነው። ሕዝብህን አድን፤ ርስትህንም ባርክ፤ እረኛ ሁናቸው፤ ለዘላለሙም ዐቅፈህ ያዛቸው።"

(መዝ 28፥8-9 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Feb, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

"የእግዚአብሔር ሰው ሙሴ ከመሞቱ" በፊት እስራኤላውያንን ባረከ፤ እርሱ ወደ ተስፋዪቱ ምድር እንዳይገባ የሕዝቡ ዐመፅ ሰበብ ሆኖበት ተከልክሏል። ወደ ፊት የሚጓዘውን እስራኤልን ግን በነገድ በነገድ ስም ባረከ፤ "ስለ አሴርም እንዲህ አለ፦ 'አሴር ከሌሎች ልጆች ይልቅ የተባረከ ነው፤ በወንድሞቹ ዘንድ ተወዳጅ ይሁን፤ እግሩንም በዘይት ውስጥ ያጥልቅ። የደጃፍህ መቀርቀሪያ ብረትና ናስ ይሆናል፤ ኀይልህም በዘመንህ ሁሉ ይኖራል'" (ዘዳ 33፥24-25)። ለአሴር የተባለለት በረከት የልቀት ብቻ ሳይሆን፣ የቅርበትም ነው—ከፍ ከፍ እያለ የሚወደድና የሚቀረብ ማኀበር። ከእግዚአብሔር የተነሣ እግሮቹ ተራማጅና ብርቱ፣ ኅይሉም በዘመን መካከል የማይነጥፍ ሆኖለታል። እግዚአብሔር ሕዝቡን የሚባርክበት ባርኮት ፈቃዱንና አብሮነቱን የሚያሳውቅበትና የሚያጸናበት ነው። በረከቱ የተጠራበት ሕዝብም በረከቱን ይካፈላል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Feb, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ስለ አሴርም እንዲህ አለ፦ 'አሴር ከሌሎች ልጆች ይልቅ የተባረከ ነው፤ በወንድሞቹ ዘንድ ተወዳጅ ይሁን፤ እግሩንም በዘይት ውስጥ ያጥልቅ። የደጃፍህ መቀርቀሪያ ብረትና ናስ ይሆናል፤ ኀይልህም በዘመንህ ሁሉ ይኖራል።'"

(ዘዳ 33፥24-25 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

16 Feb, 07:04


መልእክተ ሰንበት

ጳውሎስ የኤፌሶን መልእክቱን ሲያጠቃልል በጌታ ስለ መበርታትና ለመንፈሳዊ ውጊያ ስለ መሰናዳት ተናግር እንዲህ አለ፤ "በሁሉ ዐይነት ጸሎትና ልመና፣ በማንኛውም ሁኔታ በመንፈስ ጸልዩ፤ ይህንም በማሰብ ንቁ፤ ስለ ቅዱሳንም ሁሉ በትጋት ልመና አቅርቡ" (6፥18)። ለጸሎት ንቃት፣ በመንፈስ እየታገዙ መጸለይ፣ እንዲሁም ስለ ሌሎች ልመና ማቅረብ አስፈላጊ ስለሆኑ በትእዛዝ ተሰጡ። ሌሎችን በጸሎት ማሰብ ሲመቸን አንዳንዴ ብቻ የምናደርገው ሳይሆን፣ "በትጋት" ሁልጊዜ የምንፈጽመው ነው። ግሩም ጸሎት ጉዳይ የበዛበት ሳይሆን፣ ሌሎች የተጨመሩበት ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Feb, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ስለ ሰዎች ለሰዎች እንደምንጸልይ ሁሉ ለራሳችንም ብለን ለሌሎች እንማልዳለን፤ "እንግዲህ ከሁሉ አስቀድሞ ልመናና ጸሎት፣ ምልጃና ምስጋና ለሰዎች ሁሉ፣ ለነገሥታትና ለባለሥልጣናት ሁሉ እንዲደረግ አሳስባለሁ፤ ይህም በእውነተኛ መንፈሳዊ ሕይወትና በቅድስና ሁሉ፣ በሰላምና በጸጥታ እንድንኖር ነው" (2ጢሞ 2፥1-2)። የሚበዙቱ ለበጎነት በበጎነት የተከበቡ አይደሉም፤ በዐመፀ ተጽዕኖ ሥር ሆነው ዐመፃን የሚያበዙ እንጂ። ስለ ሁሉም ዐይነት ሰዎች ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት መታየት፣ ምልጃና ጸሎትም ማድረግ ለዕረፍታችንና ቅድስናችን፣ ሰላማችንና ጸጥታችን ሁነኛ ምላሽ ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Feb, 04:01


የዕለቱ ቃል

"እንግዲህ ከሁሉ አስቀድሞ ልመናና ጸሎት፣ ምልጃና ምስጋና ለሰዎች ሁሉ፣ ለነገሥታትና ለባለሥልጣናት ሁሉ እንዲደረግ አሳስባለሁ፤ ይህም በእውነተኛ መንፈሳዊ ሕይወትና በቅድስና ሁሉ፣ በሰላምና በጸጥታ እንድንኖር ነው።"

(1ጢሞ 2፥1-2 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

13 Feb, 11:03


የዕለቱ ሐሳብ

ጌታ የመጨረሻውን ቅድመ-ሞት የምልጃ ጸሎት በመስቀል ላይ እንዲህ ጸለየው፤ "ኢየሱስም፣ 'አባት ሆይ፤ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው' አለ። እነርሱም ልብሱን በዕጣ ተከፋፈሉት" (ሉቃ 23፥34)። በስቃዩ መካከል ብቻ ሳይሆን ጡዘቱ ላይ እንኳን ሆኖ ማለደ። ለጠላቶቹ ተከላከል፤ በዐመፃቸውና በሰውነታቸው መካከል ገባ። ጸሎቱ እነርሱን ከክፋታቸው ለየ። እየገደሉት ማራቸው፤ እየሞተ ማለደላቸው፤ በሞቱም የምሕረት ጸሎቱ መልስ ሆነላቸው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

13 Feb, 04:02


የዕለቱ ቃል

"ኢየሱስም፣ 'አባት ሆይ፤ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው' አለ። እነርሱም ልብሱን በዕጣ ተከፋፈሉት።"

(ሉቃ 23፥34 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

12 Feb, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ጌታ በተራራው ስብከት መካከል ብሉዩን ከዐዲስ ጋር እያነጻጸረ ሕጉን ከፍ አደረገ፤ እንዲህም አለ፤ “‘ወዳጅህን ውደድ፤ ጠላትህን ጥላ’ እንደ ተባለ ሰምታችኋል። እኔ ግን ጠላቶቻችሁን ውደዱ፤ ለሚያሳድዷችሁም ጸልዩ እላችኋለሁ" (ማቴ 5፥43-44)። ጥያቄው እንግዲህ፣ 'ለምን ለሚያሳድዱን እንጸልያለን?' አይደለም፤ 'እንዴት እንጸልይ?' እንጂ! ሰዎች እውነትንና ጽድቅን ከልባቸው እየተከተሉ ሌሎች ቢቃወሟቸው፣ ችግሩ ከተሳዳጁ ሳይሆን ከአሳዳጁ ነው የሚሆነው። ጫናውም ሆነ ክስተቱ ስሜት ቢነካ፣ ምቾት ቢያጎድል ወይም መከራ ቢያመጣም፣ የሰዎቹ ስህተትና ዐመፅ በበጎነት በመከበብ እየቀነሰ ወይም እየከሰመ ይመጣል። ጸሎቱ እንግዲህ፣ የአስባቸው እንጂ የአስወግዳቸው አይደለም። እግዚአብሔር የሚጸለይላቸውን ሰዎች እንዴት እንደሚገናኝ ወይም እንደሚከብብ ያውቅበታል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

12 Feb, 04:00


የዕለቱ ቃል

“‘ወዳጅህን ውደድ፤ ጠላትህን ጥላ’ እንደ ተባለ ሰምታችኋል። እኔ ግን ጠላቶቻችሁን ውደዱ፤ ለሚያሳድዷችሁም ጸልዩ እላችኋለሁ።"

(ማቴ 5፥43-44 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

11 Feb, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

መቆምና መጽናት ችለው ሌሎችን የሚያጸኑ የተባረኩ ናቸው። እነርሱም የእግዚአብሔርን ፈቃድ ብቻ ሳይሆን፣ ምሕረቱንና ከለላውን በሕዝቡ ላይ ያሰፍናሉ። እነዚህ ማላጆች ሲጠፉ ግን ኪሳራው ትልቅ ይሆናል። ምሕረቱን ከቍጣው የሚያስቀድመው አምላክ በሕዝቅኤል በኩል እንዲህ አለ፤ “ምድሪቱን እንዳላጠፋት ቅጥሩን የሚጠግን፣ በፈረሰውም በኩል በፊቴ የሚቆምላት ሰው ከመካከላቸው ፈለግሁ፤ ነገር ግን አንድም አላገኘሁም" (22፥30)። ከሃይማኖት ተቋም እስከ ፍትሕ አደባባይ፣ ከጓዳ እስከ ደጅ የነበረው ዐመፅ ከመብዛቱና ጉዳቱ ከመንሰራፋቱ የተነሣ ለእግዚአብሔርና ለእውነት በድፍረት ዘብ የሚቆሙ ጠፍተው ነበር። ይህም እግዚአብሔርን አማራጭ 'አሳጣው'።ባለንበት በመጨረሻው ዘመን ዐመፃ እንደሚበዛ መጽሐፍ ቢናገርም፣ ተጽዕኖውን የሚቋቋሙና ለምስኪኖች የሚቆሙ ማላጆች ሊበዙ ይገባል። ይህም የጌታን የከበረውን የሊቀ ክህነት ሥራ የሚያከብር የሚያሰፋም ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

11 Feb, 04:02


የዕለቱ ቃል

“ምድሪቱን እንዳላጠፋት ቅጥሩን የሚጠግን፣ በፈረሰውም በኩል በፊቴ የሚቆምላት ሰው ከመካከላቸው ፈለግሁ፤ ነገር ግን አንድም አላገኘሁም።"

(ሕዝ 22፥30 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

10 Feb, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

የኢዮብ መከራ ድንገተኛ፣ ብዙና ጥልቅ ነበር፤ በእግዚአብሔር ይሁንታ ሰይጣን ያፈራረቀበት ሳያንስ ሊያጽናኑት የመጡት ሦስቱ ባልንጀሮቹ ከርኅራኄ ይልቅ 'መጠበብን'፣ ከሐዘኔታም ይልቅ ትንተናዊ ፍርድን አፈራረቁበት። አራተኛ ሆኖ ትረካው ላይ ዘግይቶ የተዋወቀው ወጣቱ ኤሊሁ ከነርሱ የተሻለ ሲናገር፣ ኢዮብንም ለእግዚአብሔር ንግግር አዘጋጀው። አምላኩ ከተገለጠለትና አደራረጉን ብቻ ሳይሆን ክብሩን አሣየው፤ "ኢዮብ ለወዳጆቹ ከጸለየ በኋላ፣ እግዚአብሔር እንደ ገና አበለጸገው፤ ቀድሞ በነበረው ፈንታ ዕጥፍ አድርጎ ሰጠው" (42፥10)። የእግዚአብሔርን እጥፍ ካሳ ከቍስሉ በላይ የሚጠዘጥዙ ቃላት ላወረዱበት ባልንጀሮቹ ከጸለየ በኋላ ተቀበለ። የምሕረት ጸሎት በዳዮቹን ያነጻል፤ የሚጸልዩትን ደግሞ ወደ እግዚአብሔር በረከት ያቀርባል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

10 Feb, 04:04


የዕለቱ ቃል

"ኢዮብ ለወዳጆቹ ከጸለየ በኋላ፣ እግዚአብሔር እንደ ገና አበለጸገው፤ ቀድሞ በነበረው ፈንታ ዕጥፍ አድርጎ ሰጠው።"

(ኢዮ 42፥10 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

09 Feb, 07:03


መልእክተ ሰንበት

"ታላቅ ነገር" የሚያደርግ ጸሎት ለመጸለይ ልዩ ሰው መሆን አያስፈልገውም፤ "ኤልያስ እንደ እኛ ሰው ነበረ፤ ዝናብ እንዳይዘንብ አጥብቆ ጸለየ፤ በምድርም ላይ ሦስት ዓመት ተኩል ዝናብ አልዘነበም። እንደ ገናም ጸለየ፤ ዝናብም ከሰማይ ዘነበ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች" (ያዕ 5፥17-18)። ከእግዚአብሔር ጋራ የሚስማሙና እንደ ፈቃዱ የሚራመዱ፣ እንደ ኤልያስ ሁሉ ራሳቸውን ሳይሆን አምላካቸውን ይገልጣሉ፤ የርሱ ሥራም እያስገረመ ይቀጥላል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

06 Feb, 04:04


የዕለቱ ቃል

"የእግዚአብሔር መልአክ ግን ቴስብያዊውን ኤልያስን እንዲህ አለው፤ 'ተነሥተህ የሰማርያን ንጉሥ መልእክተኞች ለመገናኘት ውጣና፣ "የአቃሮንን አምላክ ብዔልዜቡልን ለመጠየቅ የምትሄዱ በእስራኤል አምላክ ስለሌለ ነውን?" ብለህ ጠይቃቸው።'"

(2ነገ 1፥3 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

05 Feb, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ያሳደዱት ሊያሳድድ ይችላል፤ ኤልያስ በአምላኩ ተወራርዶ ከበኣል ነቢያት ጋራ ፊት ለፊት ከተጋጠመ በኋላ የእግዚአብሔርን ስም ከፍ ከፍ አደረገ። ምድሪቱንም ከጣዖቱ ተጽዕኖ ብቻ ሳይሆን ከነቢያቱም ካጠራ በኋላ የኤልዛቤል ዛቻ እንዲሰደድ አደረገው። "በቅቶኛል...ነፍሴን ውሰዳት" ባለበት በዚህ የተስፋ ማጣት ጉዞ—ሽሽት—ላይ ግን እግዚአብሔር መራው፤ ወደ ኮሬብ ተራራ በደረሰ ጊዜም ተገናኘው፤ "ኤልያስም ይህን ሲሰማ፣ ፊቱን በመጎናጸፊያው ሸፍኖ ወጣና በዋሻው ደጃፍ ቆመ። ከዚያም፣ 'ኤልያስ ሆይ፤ እዚህ ምን ታደርጋለህ?' የሚል ድምፅ ሰማ" (1ነገ 19፥13)። ኅይለኛ ነፋስ፣ የምድር መናወጥና እሳት ሆነ፤ እግዚአብሔር ግን "ለስለስ" ባለ ድምፅ ተናገረው። ስለ ፈራ አርቆ አናገረው። ድምፁን የሰማበት ቦታ ግን የአምላኩን ሥራ የሚሠራበት አልነበረም—"እዚህ ምን ታደርጋለህ?" እንደ ተባለ። አቅም አግኝቶና ታጥቆ እንዲመለስ ተደረገ። ከቃሉ የተነሣም ከፍርሀቱ ወጥቶ የአምላኩን ሥራ ጨረሰ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

05 Feb, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ኤልያስም ይህን ሲሰማ፣ ፊቱን በመጎናጸፊያው ሸፍኖ ወጣና በዋሻው ደጃፍ ቆመ። ከዚያም፣ 'ኤልያስ ሆይ፤ እዚህ ምን ታደርጋለህ?' የሚል ድምፅ ሰማ።"

(1ነገ 19፥13 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

04 Feb, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

በእስራኤል የተከለከለው ዝናብ የሚለቀቅበት ጊዜ ሲደርስ ድርቁ በረታ፤ ንጉሡ ራሱም ለምለም ሳር ፍለጋ ወጣ። ያን ጊዜም ኤልያስ ለአክዓብ እንዲገለጥ እግዚአብሔር ስላሳሰበው ተገኘላቸው። ለምለም ሳር ፍለጋ ለወጣው የቤተ መንግሥቱ አዛዥና መልካም ሰው አብድዩ ተገኘለት፤ እንዲህም አለው፤ "በፊቱ የቆምሁት ሁሉን የሚገዛ ጌታ እግዚአብሔርን፣ ዛሬ በአክዓብ ፊት በርግጥ እገለጣለሁ" (1ነገ 18፥15)። ንጉሡ ከሚስቱ ኤልዛቤል ጋራ ሆነው በኤልያስ ላይ ቢያሤሩም፣ እርሱ ግን የላከውን እግዚአብሔርን ታምኖ ቀረባቸው። ቍጣቸውንም ሳይፈራ የአምላኩን ስምና ዝና በፊታቸውም ሆነ በምድሪቱ ላይ ገናና ሊያደርግ ተነሣ። በእግዚአብሔር ፊት ቆሞ ስለ ነበርም፣ በነርሱ ፊት ለመቆም አልተሸበረም—"በፊቱ የቆምሁት" እንዳለ። ኤልያስ ጌታ ሲሸሽገው ተሸሽጓልል፤ ሲገልጠውም ተገልጧል፤ አካሄዱ የድፍረት ሳይሆን የምሪት ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

04 Feb, 04:03


የዕለቱ ቃል

"ኤልያስም፣ 'በፊቱ የቆምሁት ሁሉን የሚገዛ ጌታ እግዚአብሔርን፣ ዛሬ በአክዓብ ፊት በርግጥ እገለጣለሁ' አለ።"

(1ነገ 18፥15 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

03 Feb, 11:02


የዕለቱ ሐሳብ

ኤልያስ "እንደ እኛ ሰው ነበር" ተብሎለታል። ከብሉይ እስከ አዲስ ስሙ የተጠቀሰው፣ ብዙ የሠራውና ከርሱ በኋላ ለተነሡ በምሳሌ የተጠቀሰው ነቢይ፣ ተልዕኮውን በጽናት ተወጥቷል፤ ገዢዎች ፊት ቀርቧል፤ ለመበለትም ተገልጧል። 'ብርቱ' ሰዎች ፊት ብቻ ሳይሆን ደካሞችም መካከል ተገኝቷል። ከጌታው ከተቀበለው መልእክት የተነሣ ድርቅ ባስከተለበት ወራት በታምራት ኖሯል። ወደ መበለቲቱ በተላከ ጊዜ እንዲህ አላት፦ "አይዞሽ አትፍሪ፤ ወደ ቤት ገብተሽ እንዳልሽው አድርጊ፤ በመጀመሪያ ግን ከዚያችው ካለችሽ ትንሽ ዕንጎቻ ጋግረሽ አምጪልኝ፤ ከዚያም ለራስሽና ለልጅሽ ጋግሪ፤'" (1ነገ 17፥13)። የመጨረሻ መብሏ ላይ እግዚአብሔር ደረሰ። ነቢዩን ብቻ ሳይሆን መበለቲቷንም አከረመ። በመጀመሪያ ባዶው ማድጋና ማሰሮ በቃሉ ተሞላ፤ ከዚያም ዱቄቱና ዘይቱ ተከተለ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

03 Feb, 04:02


የዕለቱ ቃል

"ኤልያስም መልሶ እንዲህ አላት፤ 'አይዞሽ አትፍሪ፤ ወደ ቤት ገብተሽ እንዳልሽው አድርጊ፤ በመጀመሪያ ግን ከዚያችው ካለችሽ ትንሽ ዕንጎቻ ጋግረሽ አምጪልኝ፤ ከዚያም ለራስሽና ለልጅሽ ጋግሪ፤'"

(1ነገ 17፥13 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

02 Feb, 07:01


መልእክተ ሰንበት

ጌታ በጎቹን ያውቃል፤ እነርሱም በርሱ የታወቁ ስለሆኑ፣ ድምፁን የተለማመዱ፣ ለይተውም የሚሰሙ ናቸው። የጌታ ስለሆኑም ዋስትናቸው በሰማይ እንጂ በምድር አይደለም። ጌታም እንዲህ አለ፤ "እኔ የዘላለም ሕይወት እሰጣቸዋለሁ፤ ከቶ አይጠፉም፤ ከእጄም ሊነጥቃቸው የሚችል ማንም የለም" (ዮሐ 10፥28)። ጽኑ ዋስትና፣ ፍጹም ዕረፍት፣ ድንቅ መተማመኛም ይሆናል። በግ በእጅ ካልተያዘ እንዴት ይጸናል። እኛም በእጆቹ የዳንን፣ በእጆቹ የበላን፣ በእጆቹም የተያዝንና የተመራን፣ እንዲሁም የተከለልን ነን። ሊነጥቀን የሚሻ ሁሉም መጀመጀሪያ ከእጆቹ ጋር ነው የሚገናኘው። አይ መጨረሻ!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

31 Jan, 11:02


የዕለቱ ሐሳብ

እግዚአብሔር በወጀብ መካከል የሚመራ አምላክ ነው። ወጀቡን (አስፈሪውን ሁኔታ) ሳያስቆም ትቶት፣ ሕዝቡን ያሻግራል። ይሁዳ ለምርኮ አልፋ ልትሰጥ ባለችበት ጊዜ፣ ኤርምያስ ርስት (ቦታ) እንዲገዛ እግዚአብሔር ተናገረው፤ እርሱም የተባለውን ፈጸመ፤ በምትወረር ምድር ኑሮን ቀጠለ። በኋላም እንዲህ ብሎ ጸለየ፤ "አቤት፣ ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተ ሰማያትንና ምድርን በታላቅ ኀይልህና በተዘረጋች ክንድህ ፈጥረሃል፤ የሚሳንህም አንዳች ነገር የለም" (32፥17)። የኪዳኑ ሕዝብ ወደ ምርኮ እየወረደና ነጻነቱ እየተገደበ፣ ባለ ኪዳኑ አምላክ ሥራውን አያቋርጥም፤ እጁ ከመሥራት አትቦዝንም። ሕዝብ ይጋዛል፤ እግዚአብሔር ግን መግዛቱን ይቀጥላል፤ የሰው ክንድ ይዝላል፤ የእግዚአብሔር ክንድ ግን እንደ ተዘረጋች (እንደ ሠራች) ትቀጥላለች። ሰማይና ምድርን የፈጠረባት ክንዱ የምድሩን እንዴት ማቅናት ይሳናታል!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

31 Jan, 04:03


የዕለቱ ቃል

“አቤት፣ ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተ ሰማያትንና ምድርን በታላቅ ኀይልህና በተዘረጋች ክንድህ ፈጥረሃል፤ የሚሳንህም አንዳች ነገር የለም።"

(ኤር 32፥17 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

30 Jan, 11:03


የዕለቱ ሐሳብ

ሰዎች፣ 'ክንዴን አልንተራስም' ይላሉ፤ ምላሽ እሰጣለሁ፤ የምችለውን ሁሉ አደርጋለሁ እንጂ እንዲሁ አልቀመጥም ማለታቸው ነው። የተንተራሱት ክንድ የማይንቀሳቀስና በሥራ ያልተጠመደ እንደሆነ ልብ ይሏል። ነቢዩ ኢሳይያሰ የእግዚአብሔር ክንድ እንዲነሣ ይጠይቃል፤ "የእግዚአብሔር ክንድ ሆይ፤ ተነሥ፤ ተነሥ! ኀይልን ልበስ፤ እንዳለፉት ዘመናት፣ በጥንት ትውልዶችም እንደ ሆነው ሁሉ ተነሥ" (51፥9)። የጌታ ክንድ ሥራ ባይፈታም፣ በመካከላችን እንዲታይና እንዲገለጥ ግን እንጸልያለን። ከገነኑና ካስቸገሩ ነገሮች በላይም ክንዱ ከፍ ከፍ እንዲል እንናፍቃለን። ያኔ የነቢዩን ጥሪ እናስተጋባለን። እግዚአብሔር ሲመለከተንም፣ ክንዱ ዕይታውን ይከተላል፤ እጁ ዐይኑ ወዳየበት ይዘረጋል፤ ያኔም "ተድላና ደስታ" ይሆናል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

30 Jan, 04:02


የዕለቱ ቃል

"የእግዚአብሔር ክንድ ሆይ፤ ተነሥ፤ ተነሥ! ኀይልን ልበስ፤ እንዳለፉት ዘመናት፣ በጥንት ትውልዶችም እንደ ሆነው ሁሉ ተነሥ። ረዓብን የቈራረጥህ፣ ታላቁን ዘንዶ የወጋህ አንተ አይደለህምን?"

(ኢሳ 51፥9 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

29 Jan, 11:04


የዕለቱ ሐሳብ

ለመዝሙር 139 ዘማሪ፣ እግዚአብሔር ሁሉ በሁሉ ነው። ሁሉን አዋቂ ነው (ቍ. 4)፤ በሁሉ ስፍራ የሚገኝ ነው (ቍ. 7)፤ ሁሉን ቻይ ነው (ቍ. 12)። ከፊቱ የሚሰወር፣ ከዕይታውም የሚደበቅ አካልም ሆነ ሐሳብ የለም። ወደ ሰማይ ቢወጣ ግዛቱ ነው፣ ወደ ጥልቁም ቢወረድ የእጁ ሥራ ነው። ዘማሪው፣ "ከመንፈስህ ወዴት እሄዳለሁ?" ካለ በኋላ፣ "እጅህ ትመራኛለች፤ ቀኝ እጅህም አጥብቃ ትይዘኛለች" አለ (ቁ. 10)። የእግዚአብሔር እጅ ለመሥራትም ሆነ ለመያዝ፣ ለማዳንም ሆነ ለመምራት የማትዘረጋበት ሰፍራ የለም። ሐሳቡ ባለበት እጁ አለች፤ ፈቃዱንም ሙሉ ለሙል ትፈጽማለች።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

29 Jan, 04:04


የዕለቱ ቃል

"በዚያም ቢሆን እጅህ ትመራኛለች፤ ቀኝ እጅህም አጥብቃ ትይዘኛለች።"

(መዝ 139፥10 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

28 Jan, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ዘማሪው እግዚአብሔር "መከራንና ሐዘንን" እንደሚያይ ይናገራል። ይህንም የሚለው ክፉዎች እንደ ፈለጉ እንደሚሆኑ ምስኪኖችንም እንደሚበድሉ ከተናገረ በኋላ ነው። ባለቅኔው ምሬቱንና ግራ መጋባቱን ወደ ጸሎት ቀየረ፣ "እግዚአብሔር ሆይ ተነሥ፤ አምላክ ሆይ፤ ክንድህን አንሣ፤ ረዳት የሌላቸውንም አትርሳ" በማለት (መዝ 10፥12)። አምላኩን ደጋግሞ ተጣራ፤ ክንዱ—እጁ—እንደማይዝል ስለሚያውቅም ለፍትሕና ለትድግና እንዲነሣ አነሣሣ። አምላክ ሰው ስላይደለ አይረሳም፤ ሰዎች የተረሱ ሲመስላቸው ግን፣ እንደ ዘማሪው "አትርሳ" እንጂ ይሉታል። እርሱም የጸሎት ቋንቋን (አገላለጽን) ሳያርም፣ ክንዱን ከሚራራው ልቡ ጋር ያዘነብላል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

28 Jan, 04:00


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔር ሆይ ተነሥ፤ አምላክ ሆይ፤ ክንድህን አንሣ፤ ረዳት የሌላቸውንም አትርሳ።"

(መዝ 10፥12 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

27 Jan, 11:04


የዕለቱ ሐሳብ

ዳዊት ለቤተ መቅደሱ ሥራ የሚሆነውን ሁሉ ከሰበሰበና ካሰበሰበ በኋላ ጸሎትን ወደ እግዚአብሔር አቀረበ—ሰጥቶ መጸለይ! ስጦታው ሁሉ "በገዛ ፈቃድና በፍጹም ልብ የቀረበ" ስለ ነበረ ዳዊትም ሆነ ሕዝቡ ደስ ተሰኝተዋል (1ዜና 29)። በጸሎቱ መካከልም እንዲህ አለ፤ “ሁሉ የተገኘው ከአንተ ነው፤ ለአንተም የሰጠንህ ከእጅህ የተቀበልነውን ብቻ ነው። ታዲያ እንዲህ ያለ ቸርነት እናደርግ ዘንድ እኔ ማነኝ? ሕዝቤስ ማነው?" (ቍ. 14)። (የተሰበሰበው ወርቅ ብቻውን፣ በዛሬ የገንዘብ ዋጋ ተመን ብዙ ቢልዮን ዶላር ይሆናል፤) ያ ሁሉ ተሰጥቶ የታየው ግን የእግዚአብሔር እጅ ነው—"ከእጅህ የተቀበልነውን ብቻ ነው።" የእግዚአብሔር እጅ አይደክምም፤ የእግዚአብሔር እጅ አይነጥፍም፤ የእግዚአብሔር እጅም አይታጠፍም። ማንም ምንም ቢሰጥ፣ ከሚቀበለው በላይ በሰጪው እጅ ላይ ሊያስቀምጥ የሚችል የለም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

27 Jan, 04:00


የዕለቱ ቃል

“ሁሉ የተገኘው ከአንተ ነው፤ ለአንተም የሰጠንህ ከእጅህ የተቀበልነውን ብቻ ነው። ታዲያ እንዲህ ያለ ቸርነት እናደርግ ዘንድ እኔ ማነኝ? ሕዝቤስ ማነው?"

(1ዜና 29፥14 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

26 Jan, 07:03


መልእክተ ሰንበት

የእግዚአብሔር ሰዎች እያለቀሱ ሊቆዩ ይችላሉ፤ እንዳለቀሱ ግን አይኖሩም። አምላካቸው እንባቸውን ያቋርጣል፤ በመጨረሻ ደግሞ ያቆመዋል፤ "እንባን ሁሉ ከዐይናቸው ያብሳል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ሞት ወይም ሐዘን ወይም ልቅሶ ወይም ሥቃይ አይኖርም፤ የቀድሞው ሥርዐት ዐልፏልና” (ራእ 21፥4)። እንባ መነሻ አለው፤ ሰበብ አለው። የወደቀችው ዓለም አስጨናቂ ነገሮች የሞሉባት፣ ክፋት የበዛባትና መከራ የሚፈራረቅባት ነች። እነዚህ ሁሉም፣ አነሰም በዛም ነዋሪዎቿን ሁሉ ያካልላሉ። አምላካቸውን የሚደገፉ ግን መጽናኛና መታመኛ አላቸው። በመጨረሻም፣ ሥርዓቱ ሁሉ በሚቀየርበት መንግሥት ይከበራሉ፤ ያለ መከራ ሥጋት ይኖራሉ፤ ፊታቸውም ያለ እምባ ያበራል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

24 Jan, 11:05


የዕለቱ ሐሳብ

ጌታ ለአልዓዛር አልቅሷል—የሐዘኔታ ለቅሶ። ለኢየሩሳሌምም እንዲሁ አልቅሷል—የቅሬታ ለቅሶ፣ "በተረዳሽ ኖሮ" እያለ። በአባቱ ፊት ሲቀርብ፣ እያነባ እንደ ጸለየ የዕብራውያን ጸሐፊ ይነግረናል፤ "ኢየሱስ በዚህ ምድር በኖረበት ዘመን ከሞት ሊያድነው ወደሚችለው ጸሎትንና ልመናን ከታላቅ ጩኸትና ከእንባ ጋር አቀረበ፤ ፍጹም ትሑት ሆኖ በመታዘዙም ጸሎቱ ተሰማለት" (ዕብ 5፥7)። ጌታ በምድር ሳለ ኅይሉንና ችሎታውን ከአባቱ ፈቃድ በስተ ኋላ ስላስቀመጠ፣ ጠያቂ (ጸላይ) ነበር። ልጅና አምላክ ሆኖ ሳለም ልመናውን "ከእንባ ጋር" ካቀረበ፣ ሰዎች የሆንነው ልጆቹ እንዴት ባለ ጥልቅ ስሜትና ከበሬታ ወደ አብ መቅረብ ይገባን ይሆን! ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ከመብት በላይ ችሮታ—ስጦታ—ነው፤ ልመናንም ማቅረብ ሥልጣን ሳይሆን መገዛት ነው። በእንባ የራሰ ጸሎት ጥልቅ ስሜትን ስለሚወክል፣ እንባን በሰውነት ውስጥ ያስቀመጠን አምላክ ይነካል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

24 Jan, 03:59


የዕለቱ ቃል

"ኢየሱስ በዚህ ምድር በኖረበት ዘመን ከሞት ሊያድነው ወደሚችለው ጸሎትንና ልመናን ከታላቅ ጩኸትና ከእንባ ጋር አቀረበ፤ ፍጹም ትሑት ሆኖ በመታዘዙም ጸሎቱ ተሰማለት።"

(ዕብ 5፥7 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

23 Jan, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

በአገራችን 'እዬዬም ሲደላ ነው' ይባላል። ለቅሶ ወይም በአግባቡ እያነቡ ማዘን ዕድል ነው የሚል ትርጕም ይይዛል። የሐዋርያት ሥራው እስጢፋኖስ በድፍረትና በዕውቀት ብሉይ ኪዳንን መሠረት አድርጎ ወንጌልን የሚናገር፣ "ጸጋንና ኀይልን ተሞልቶ በሕዝቡ መካከል ድንቅ ነገሮችንና ታምራዊ ምልክቶችን" (6፥8) ያደርግ የነበረ አገልጋይ ነበር፤ እውነቱን የሰሙ ግን በተነገራቸው እውነት ላይ ያመጹ አይሁድ ግን በድንጋይ ወግረው ገደሉት፤ ከዚያም "በመንፈሳዊ ነገር የተጉ ሰዎችም እስጢፋኖስን ቀበሩት፤ ደግሞም እጅግ አለቀሱለት" (8፥2)። ከመወገሩ በፊት በአብ ቀኝ ቆሞ ያየው ጌታ ከወገራው አልከለለውም፤ በክብር በመንግሥቱ ተቀበለው እንጂ። የእስጢፋኖስ ነፍስ በሰማይ ስትከብር፣ በድኑ በልቅሶ ተሸኘ። ይህንን ወግ ያገኙትም "በመንፈሳዊ ነገር" የተጉቱ ነበሩ። በወጉ ማልቀስም ብድራት—ሽልማት—ይሆናል ለካ!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

23 Jan, 03:59


የዕለቱ ቃል

"በመንፈሳዊ ነገር የተጉ ሰዎችም እስጢፋኖስን ቀበሩት፤ ደግሞም እጅግ አለቀሱለት።"

(ሐሥ 8፥2 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

22 Jan, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

እንባ ለፍጡር የተሰጠ ስሜት ገላጭ ፈሳሽ ነው። ሥጋ የለበሱ ያነባሉ፤ ጌታም ሥጋ ስለሆነ፣ ከሰውነቱ ጋር እንባን አብሮ ተቀብሏል። በአንድ ወቅት፣ የሚወደው "አልዓዛር ታሟል" መባሉን ሰማ። የጌታ ቀጠሮም ከአልዓዛር የታመመ ሰውነት ጋር ሳይሆን፣ ከበድኑ—ከሞተው ሰውነት—ጋር ስለ ነበር ዘገየ፤ እርሱም ሞተ። መጥቶ እህቶቹን ካናገረ፣ ሐዘንተኞችንም ከተመለከተ በኋላ ግን ልቡ ተነካ፤ "ኢየሱስም እንባውን አፈሰሰ" (ዮሐ 11፥35)። ስሜቱ ፈቃዱን አለፈ፤ ሊያስነሣው እንዳለ እያወቀና እየቻለም ሐዘናቸውን ተካፈለ። አጃቢ እንባ ሳይሆን አዛኝ እንባ አፈሰሰ። በርግጥም፣ በሁሉ ነገር እኛን መምሰል ስለ ተገባው ስሜታችንንም ሆኗል፤ ተጋርቷልም። ዛሬም እየቻለ ያዝናል፣ እያዘነልንም ያስችለናል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

22 Jan, 03:59


የዕለቱ ቃል

"ኢየሱስም እንባውን አፈሰሰ።"

(ዮሐ 11፥35 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

21 Jan, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

ኢሳይያስ በትንቢቱ ስለ ዘመን ፍጻሜ ተስፋ ይናገራል፤ በሞቱ፣ በሞት ላይ ድል ከተጎናጸፈው በኋላ ሕዝቡን ታድጎ በሕይወትና በተስፋ የሞላው ክርስቶስ ጌታ ስለሚመጣበትና ስለሚነግሥበት ዘመን የሚናገረው ይሄው ትንቢት እንዲህ ይላል (25፥8)፤ "ሞትንም ለዘላለም ይውጣል። ጌታ እግዚአብሔር ከፊት ሁሉ እንባን ያብሳል፤ የሕዝቡንም ውርደት ከምድር ሁሉ ያስወግዳል፤ እግዚአብሔር ተናግሯልና።" የእንባ ምክንያት ብዙ ነው፤ ከሐዘንና ከስብራት የሚወጣውም ትልቁን ድርሻ ይይዛል። ጌታም ሰዎችን የሚያስለቅሰውን ነገር ሁሉ ከመሠረቱ ያነሣዋል። እርሱ እንባን ሲያብስ ፊትን አይደለም የሚያደርቀው፤ የእንባን ምክንያት ሁሉ እንጂ! ሞት ሲዋጥ፣ እንባም አብሮ ይጠፋል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

21 Jan, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ሞትንም ለዘላለም ይውጣል። ጌታ እግዚአብሔር ከፊት ሁሉ እንባን ያብሳል፤ የሕዝቡንም ውርደት ከምድር ሁሉ ያስወግዳል፤ እግዚአብሔር ተናግሯልና።"

(ኢሳ 25፥8 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

20 Jan, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

በምርኮ—በመከራ—ላሉ 'የዘር' ጊዜ ረጅም ይሆናል፤ የመከራ ወቅት፣ እንደ መኸር ጊዜ፣ ጥቂት ወራት ላይሆን ይችላልና። መከራ ሲጨምቅ የሚያወጡት እንባ ከምድር ይልቅ ሰማይ ላይ ሲያርፍ—ሲዘራ—ግን በጊዜው ያሳቅፋል፤ ዘማሪው እንዲህ እንዳለ፣ "በእንባ የሚዘሩ፣ በእልልታ ያጭዳሉ" (126፥5)። ሰማይ እምባ አያባክንም፤ የሚንጠባጠበው ርኁሩኅ በሆነው አምላክ ላይ ነውና። በእንባ የተለወሰ ጸሎትም፣ በእልልታ የታቀፈ ምላሽ ያስገኛል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

20 Jan, 04:03


የዕለቱ ቃል

"በእንባ የሚዘሩ፣ በእልልታ ያጭዳሉ።"

(መዝ 126፥5 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

19 Jan, 06:59


መልእክተ ሰንበት

እግዚአብሔርን ታምነው በርሱ የሚጸኑ ድል አድራጊዎች እንጂ ድል ናፋቂዎች አይደሉም። ጳውሎስ በሌላኛው የቆሮንቶስ መልእክቱ እንዳለ፣ መጠቃት እንጂ ሽንፈት አያገኛቸውም፤ ማመንታት እንጂ ተስፋ መቍረጥ ውስጥ አይገቡም፤ ይንገዳደገዱ እንደ ሆነ እንጂ አይወድቁም። በ1ቆሮንቶሱ የትንሣኤ ምዕራፍ ላይም ይህንኑ እውነት ያውጃል፤ "ነገር ግን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ድልን ለሚሰጠን ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን" (15፥57)። ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን በሞቱና ትንሣኤው ድል እንዳደረገ፣ የሚያምኑበትን እንዲሁ ድል አድራጊ ያደርጋቸዋል። እርሱን ከለላ ላደረጉ፣ የኅጢአት ፍርሀት፣ የሞት ፍርሀት፣ የዲያብሎስም ፍርሀት ዕውቀት እንጂ ልምምድ አይሆኑም፤ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አቅማቸውን ሁሉ አምክኖታልና።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Jan, 11:03


የዕለቱ ሐሳብ

'እግዚአብሔር ሕዝቡን እንዴት ያጸናል?' ተብሎ ቢጠየቅ፣ ምላሹ 'በቃሉ!' ነው፤ "በዘላለማዊ አምላክ ትእዛዝ...በአስተማርሁት ወንጌልና በኢየሱስ ክርስቶስ መሰበክ ሊያጸናችሁ ለሚችለው፣ እርሱ ብቻ ጥበበኛ ለሆነ አምላክ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን" (ሮሜ 16፥25-27)። ቃሉ ሁልጊዜ "ሕያውና የሚሠራ" ስለሆነ የሚቀድስ፣ የሚያስተምርና የሚያጸና ነው። ቃሉ ፈቃዱንና ኀይሉን ይይዛልና ያጸናል። በተነበበና በተገለጠ ቁጥርም እየደገፈ ይረዳል፤ እያገዘም ያለመልማል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Jan, 04:03


የዕለቱ ቃል

"በዘላለማዊ አምላክ ትእዛዝ...በአስተማርሁት ወንጌልና በኢየሱስ ክርስቶስ መሰበክ ሊያጸናችሁ ለሚችለው፣ እርሱ ብቻ ጥበበኛ ለሆነ አምላክ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን።"

(ሮሜ 16፥25-27 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

16 Jan, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ለሚለዩት ወዳጅ የተስፋን ቃል የሚያክል የለም። ጌታ ለሦስት ዓመታት አብረውት የነበሩትን ደቀ መዛሙርት ሊለያቸው ሲል አብሮነቱ እንደሚቀጥል አስረዳቸው፤ "...እኔም እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ” (ማቴ 28፥20)። "እስከ ዓለም ፍጻሜ...ሁልጊዜ"--ግሩም ተስፋ፣ ድንቅ አብሮነት፣ ብርቱ ደጋፍ! የጌታ ረድኤትነት ለአሥራ አንዱ ብቻ ሳይሆን፣ ቃሉን ሰምተው ለሚያምኑ ሁሉ ነው። እርሱ አይቋረጥም፤ ስለዚህ መገኘቱን አያቋርጥም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

16 Jan, 04:04


የዕለቱ ቃል

"...እኔም እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ።”

(ማቴ 28፥20 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

15 Jan, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

የእግዚአብሔር ሕዝብ መጽናኛና ማበረታቺያ የሚፈልጉባቸው ጊዜአት ብዙ ናቸው። የልብ አውቃ የሆነውና እውነተኛው አምላክም ሕዝቡን በቃሉ ይደግፋል፤ "እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ፤ አምላክህ ነኝና አትደንግጥ። አበረታሃለሁ፤ እረዳሃለሁ፤ በጽድቄም ቀኝ እጄ ደግፌ እይዝሃለሁ" (ኢሳ 41፥10)። ቃሉ ፈቃዱን ብቻ ሳይሆን አቅሙን ይወክላል። እርሱ የሆነውን ይናገራል፤ የተናገረውንም ያደርጋል። ስለዚህ፣ ያበረታል፤ ይረዳል፤ ደግፎም ይይዛል። በእግዚአብሔር እጅ የተያዙም በርሱ ፍጥነት እንዲጓዙ፣ በርሱ ይታገዛሉ። እርሱም ከሚያስፈሩና ከሚያስደነግጡ ነገሮች በላይ፣ እንዲሁም ቅርብ ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

15 Jan, 04:01


የዕለቱ ቃል

"እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ፤ አምላክህ ነኝና አትደንግጥ። አበረታሃለሁ፤ እረዳሃለሁ፤ በጽድቄም ቀኝ እጄ ደግፌ እይዝሃለሁ።"

(ኢሳ 41፥10 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Jan, 11:03


የዕለቱ ቃል

ተራሮች የሠራቸውን አይመስሉም፤ የሠራቸው ትልቅ ነውና። የሠራቸውን ግን ያሳያሉ፤ ዘማሪው፣ "ዐይኖቼን ወደ ተራሮች አነሣሁ፤ ረድኤቴ ከወዴት ይመጣል? ረድኤቴ ሰማይንና ምድርን ከፈጠረ፣ ከእግዚአብሔር ዘንድ ይመጣል" (መዝ 121፥1-2) ብሎ ተቀኘ። ተራራው ይበልጥ ቀና እንዲል ሳያደርገው አልቀረም፤ ከተራራው በላይ እጅግ ከፍ ያለውን መመልከት ቻለ። ብዙ ገናናዎች ከፊት ለፊታችን ሊቀመጡ ይችላሉ። ከነርሱ በላይ በክብር የተቀመጠውን ለረድኤታችን እንድንመለከት ካደረጉን፣ ጠቀሙን እንጂ አልጎዱንም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Jan, 04:04


የዕለቱ ቃል

"ዐይኖቼን ወደ ተራሮች አነሣሁ፤ ረድኤቴ ከወዴት ይመጣል? ረድኤቴ ሰማይንና ምድርን ከፈጠረ፣ ከእግዚአብሔር ዘንድ ይመጣል።"

(መዝ 121፥1-2 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

13 Jan, 11:04


የዕለቱ ሐሳብ

መዝሙር 46 የቆሬ ልጆች መዝሙር ነው፤ እነዚህ ሙሴን የተቃወመውንና የጠፋውን የአባታቸውን—የቆሬን—መንገድ ሳይሆን፣ የእግዚአብሔርን መንገድ የተከተሉ ነበሩ። በዳዊት ዘመን የቤተ መቅደሱን ዝማሬ የመሩትም ልጆች እንዲህ ብለው ዘምረዋል፤ "አምላካችን መጠጊያችንና ኀይላችን፣ በሚደርስብን መከራ ሁሉ የቅርብ ረዳታችን ነው" (መዝ 46፥1)። እግዚአብሔር በርግጥም መጠጊያ (ዐምባ) ነው፤ አቅም ነው፤ የቅርብ ረዳትም ነው። እርሱ በነውጥ መካከል ዕረፍት፣ ሥጋት ሲያጠላ መጠለያ፣ አቅም ሲከዳም የቅርብ ረዳት ነው። የታመኑበትም የሚያርፉበት ብቻ ሳይሆን አፋቸውን ሞልተው የሚናገሩለት፣ ከመከራቸውም በላይ የሚያዩትና ከፍ የሚያደርጉት አምላክ ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

13 Jan, 04:15


የዕለቱ ቃል

"አምላካችን መጠጊያችንና ኀይላችን፣ በሚደርስብን መከራ ሁሉ የቅርብ ረዳታችን ነው።"

(መዝ 46፥1 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

12 Jan, 07:01


መልእክተ ሰንበት

የጌታ ሰውነት በመለኮቱ አልተገደበም፤ (መለኮቱ ስለ ተልዕኮው በሰውነቱ ቢወሰንም፤) ስለዚህ ሕፃንነቱና ልጅነቱ የሰውን መንገድ የተከተለ፣ ዕድገቱም በሁሉ ፊት ግልጽ ነበር፤ "ኢየሱስም በጥበብና በቁመት በሞገስም በእግዚአብሔርና በሰው ፊት አደገ" (ሉቃ 2፥52 አመት)። እግዚአብሔር፣ በእግዚአብሔር ፊት ያደገው ሰው ሆኖ ስለ ተወለደ ነው። አንዳንዶች በልጅነቱ እንዲህና እንዲያ አድርጓል ቢሉም፣ ግለ ታሪኩ--አዲስ ኪዳን--ያንን አይነግረንም። ታምራት ማድረግ የጀመረውም የምድር ቆይታው አንድ አሥረኛ ብቻ ሲቀር ነበር። እስከዚያው እያደገ ወላጆቹን እየታዘዘ ኖሯል። ማደግ መፍጠን አይደለም፤ ሂደት መጨረስ እንጂ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

10 Jan, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ከሰማይ የመጣን ምድርን ሁሉ አካለው ቢፈልጉት አይገርምም። ብርሃን የሆነው ጌታ ከብርሃን ቀድሞ በምድር ቢወለድም ሰው በመሆን (ሂደት) እጅግ ብዙ ተጉዟል። ይህንን ፍለጋ የፈለጉም ጥቂቶች ናቸው። ከነርሱም መካከል የምሥራቆቹ ጠቢባን ይገኛሉ፤ "ወደ ቤትም በገቡ ጊዜ ሕፃኑን ከእናቱ ከማርያም ጋር አዩ፤ ተንበርክከውም ሰገዱለት። ሣጥኖቻቸውን ከፍተው ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤም አቀረቡለት" (ማቴ 2፥11)። የጉዟቸው አድራሻ ቦታ ሳይሆን ጌታ፣ ግባቸው ሰዎች ሳይሆኑ "የተወለደው ንጉሥ" ነበር። "ሕፃኑን" ኢየሱስ ባዩትም ጊዜ ከዐላማቸው ወደ ኋላ አላሉም። ለመለኮት ክብሩ ሰገዱለት። ለሰጪነቱም ስጦታቸውን አቀረቡለት። ጌታን ፍለጋ፣ መለኮታዊ ምሪት፣ ለጌታ ስግደትና ስጦታ የጉዟቸው ጅማሬና ፍጻሜ ሆነ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

10 Jan, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ወደ ቤትም በገቡ ጊዜ ሕፃኑን ከእናቱ ከማርያም ጋር አዩ፤ ተንበርክከውም ሰገዱለት። ሣጥኖቻቸውን ከፍተው ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤም አቀረቡለት።"

(ማቴ 2፥11 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

09 Jan, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ጌታን ለማየት ምን ያህል ጊዜ መጠበቅ ያስፈልጋል? ጠብቀው ሲያገኙትስ እንዴት ይገለጥላቸው ይሆን? ስምዖን በመጠበቅ የኖረ፣ ጌታንም በ8ኛ ቀኑ አግኝቶ የታቀፈ ነው። "ጻድቅና ትጉ" ሆኖ "መንፈስ ቅዱስ በላዩ ያደረ" ይህ ሰው፣ ጌታን ዐይቶ፣ ተቀብሎ ካቀፈው በኋላ እንዲህ አለ፤ “ጌታ ሆይ፤ ቃል በገባኸው መሠረት፣ አሁን ባሪያህን በሰላም አሰናብተው፤ ዐይኖቼ በሰዎች ሁሉ ፊት ያዘጋጀኸውን ማዳንህን አይተዋልና። ይህም ለአሕዛብ መገለጥን የሚሰጥ ብርሃን፣ ለሕዝብህ ለእስራኤልም ክብር ነው” (ሉቃ 2፥29-32)። ትልቁ የሕይወቱ ግብ እግዚአብሔር ለሰዎች ልጆች ያዘጋጀውን አዳኝና ብርሃን መመልከት ነበር። ሕፃኑን ጌታ አምኖ ታቀፈው፤ ስለ እውነትም መሰከረ፤ የምድር ጕዞውንም በክብር ለመጨረሰ ጠየቀ። በትንሹ (በሕፃኑ) ኢየሱስ ይህን ያህል ከረካ፣ በትልቁና በከበረው ኢየሱስ ምን ያህል መርካት ይኖርብን ይሆን!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

09 Jan, 04:01


የዕለቱ ቃል

“ጌታ ሆይ፤ ቃል በገባኸው መሠረት፣ አሁን ባሪያህን በሰላም አሰናብተው፤ ዐይኖቼ በሰዎች ሁሉ ፊት ያዘጋጀኸውን ማዳንህን አይተዋልና።"

(ሉቃ 2፥29-31 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

08 Jan, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ለሰዎች ልጆች፣ ክብር ከሰላም አይበልጥም። ተከባሪ ወይም አክባሪ ሰላም ከሌላቸው፣ ጌጥ ያለ ልብስ እንደ ማለት ነው፤ በደንብ ሳይለብሱ አይጌጡምና። በጌታ ልደት የሰማይ ሰራዊት እንዲህ ብለው ዘመሩ፤ “ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም፣ ሰላምም እርሱ ለሚወድዳቸው ሰዎች በምድር ይሁን!” (ሉቃ 2፥14)። በርግጥም፣ የክርስቶስ መወለድ ክብርን ለሚገባውና ብቸኛ ለሆነው አምላክ አምጥቷል፤ ይኸው ውልደትም በምድር ላሉ ሰላምን አጎናጽፏል። ስጦታውን የሚቀበሉ፣ የስጦታውን ጥቅም ይካፈላሉ። ዝማሬው እግዚአብሔርን በሰማይ እያከበረ፣ ለሰዎች በምድር በጎውን ይመኛል፤ እግዚአብሔር የከበረበት ነገር ሁሉ ሰዎችን የሚጠቅም ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

08 Jan, 04:04


የዕለቱ ቃል

“ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም፣ ሰላምም እርሱ ለሚወድዳቸው ሰዎች በምድር ይሁን!”

(ሉቃ 2፥14 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

06 Jan, 11:04


የዕለቱ ሐሳብ

ዮሴፍ ፈቃዱ፣ ማንነቱና ምንነቱ የሌለበትን ልጅ ማርያም እንደምትወልድ ተነገረው፤ "ወንድ ልጅ ትወልዳለች፤ ስሙንም ኢየሱስ ብለህ ትጠራዋለህ፤ ሕዝቡን ከኀጢአታቸው ያድናቸዋልና" (ማቴ 1፥21)። እግዚአብሔር ያንን ቤተሰብ ሳያስፈቅድ፣ ሐሳቡንና የከበረውን ዕቅዱን አስቀመጠባቸው። በጊዜው የታመኑና የተዘጋጁ ስለ ነበሩ የርሱ ዕቃ ሆኑ። ሕፃኑ ኢየሱስ በዚያ ቤት ቢወለድም፣ ልጅ ሳይሆን ወላጅ ነው የሚሆናቸው። መወለዱም የሰው ልጆችን ሁሉ ከኀጢአት ለማንፃት ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

06 Jan, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ወንድ ልጅ ትወልዳለች፤ ስሙንም ኢየሱስ ብለህ ትጠራዋለህ፤ ሕዝቡን ከኀጢአታቸው ያድናቸዋልና።"

(ማቴ 1፥21 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

05 Jan, 07:00


መልእክተ ሰንበት

ሰላም ፈላጊዋን አትሸሽም። ፈላጊዎቿም ሲበዙ፣ እንዲሁ ትበዛለች። የዕብራውያን ጸሐፊ እንዲህ አለ፤ "ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር የሚቻላችሁን ሁሉ አድርጉ፤ ለመቀደስም ፈልጉ፤ ያለ ቅድስና ማንም ጌታን ማየት አይችልም" (ዕብ12፥14)። ሰላም ለሰዎች፣ ቅድስና ለእግዚአብሔር፤ እነዚህ ሁለቱ እሴቶች አብረው የሚሄዱና የሚሞላሉ ናቸው። እግዚአብሔር ፍጹም ስለሆነ፣ ከርሱ ጋራ ኀብረት ማድረግ (መወዳጀት) አያስቸግርም። ሰዎች ግን ብዙ የሚጎድለን ነገር ስላለ፣ ሰላምን ስንከተል ለመቀበል ከመዘጋጀት ይልቅ ለማካፈል (ለማስፈን) እየወሰንን መሆን ይኖርበታል። እርሱም ከርሱና ከሌሎች ጋራ አብሮ ለመራመድ የሚቆርጡትን በብዙ ያግዛቸዋል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

03 Jan, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ሰላም ጌታ አላት—ሠሪና ገዢ። እውነተኛዪቱን ሰላም ፈላጊዋ ብዙ (አብላጫ) አይደለም፤ የምትገኘው ከጌታ ዘንድ ነውና። ጳውሎስ የ2ኛ ተሰሎንቄን መልእክት ሲያጠቃልል ይህቺኑ ሰላም በቡራኬ በመመኘት ነው፤ "የሰላም ጌታ ራሱ በሁሉም ነገር ዘወትር ሰላም ይስጣችሁ" (2ተሰ 3፥16)። እርሱ የሰላም ጌታ ስለሆነ፣ መገኘቱ፣ ህልውናውም ሆነ ፈቃዱ ሰላምን የያዙ፣ ያማከሉም ናቸው። ሰላሙንም የርሱ ለሆኑ ሁሉ ባለማቋረጥ ይሰጣል፤ ያበዛልም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

03 Jan, 05:30


የዕለቱ ቃል

"የሰላም ጌታ ራሱ በሁሉም ነገር ዘወትር ሰላም ይስጣችሁ።"

(2ተሰ 3፥16 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

02 Jan, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

የክርስቶስ ሰላም የተሰጠ ሰላም፣ የተቸረ ሰላም ነው። የእርሱ ሰላም በአምላካዊ ኅልውናው ላይ የተመሠረተ፣ ከዚያም የሚመነጭ ስለሆነ እርሱ በሙላት ወይም በአካል ካልተገኘ አይመጣም የሚባል አይደለም፤ በአምላካዊ ህልውናው ይመሠረታልና፤ "ሰላምን እተውላችኋለሁ፤ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጣችሁ አይደለም። ልባችሁ አይጨነቅ፤ አይፍራም" (ዮሐ 14፥27)። የጌታ ተስፋ በጌታ አቅም የሚፈጸም፣ ባሕርይውን የሚከተል ስለሆነ ያለ ጥርጥር ይፈጸማል። የሰጠውና የሚሰጠው ሰላም በዘመን መካከል ያልቀነሰና ያልተሸራረፈ ሰላም ነው። እርሱን ያመኑና በርሱ የኖሩ ሁልጊዜ የሰላሙ ተካፋይ ናቸው። ሰላሙን ሊጠጉ የሚሞክሩ ብዙ ነገሮች ሊኖሩ ይችላሉ፤ ሰላሙ ግን አይነኬ ነው። ለዚህም ነው ጭንቀትንና ፍርሀትን የሚያስጥለው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

02 Jan, 04:04


የዕለቱ ሐሳብ

"ሰላምን እተውላችኋለሁ፤ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጣችሁ አይደለም። ልባችሁ አይጨነቅ፤ አይፍራም።"

(ዮሐ 14፥27 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

01 Jan, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

እግዚአብሔር የሚታመኑበትን በሰላሙ ይጠብቃቸዋል—በርሱ ሰላም። የርሱ ሰላምም ከትግል ወይም ከድል በኋላ የምትሰፍን አይደለችም፤ ማንነቱና አቅሙ ላይ ያረፈች ናት። እርሱም የሚታመኑበትን በሰላሙ ይጠብቃቸዋል፤ "በአንተ ላይ ታምናለችና፣ በአንተ የምትደገፈውን ነፍስ ፈጽመህ በሰላም ትጠብቃታለህ" (ኢሳ 26፥3)። እግዚአብሔር ጋሻና ዕረፍት ነው፤ በርሱ የሚከለሉም ጥበቃን ከሰላም ጋራ ያገኛሉ፤ ይረጋጋሉ። በዙሪያ ሥጋት እንኳን ቢኖር፣ ሰላሙ አረጋግቶ ያስቀምጣቸዋል፤ እንዲወጡና እንዲገቡ፣ እንዲያፈሩም አቅም ይሆናቸዋል። መታመናቸውን ላልጣሉ፣ ሰላሙ ይትረፈረፍላቸዋል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

01 Jan, 04:03


የዕለቱ ቃል

"በአንተ ላይ ታምናለችና፣ በአንተ የምትደገፈውን ነፍስ ፈጽመህ በሰላም ትጠብቃታለህ።"

(ኢሳ 26፥3 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

31 Dec, 11:01


ሰላም ግዛቷ ሰፊ ነው፤ አቃፊም አግላይም ነች። የሰላምን ሰዎች ስትይዝ፣ ሌሎቹ ከወሰኗ ውጪ ይሆናሉ። ሰላማውያን ሲበዙም ድንበሯ እየሰፋ ይሄዳል። ሰላምን ከሚያሰፋ መንገዶች መካከል አንዱ የሰዎች አካሄድ ነው። በአካሄዳቸው ጽድቅንና በጎነት የሚያስቀድሙ ሰላምን ያሰፋሉ፤ "የሰው መንገድ እግዚአብሔርን ደስ ሲያሰኘው፣ ጠላቶቹ እንኳ አብረውት በሰላም እንዲኖሩ ያደርጋል" (ምሳ 16፥7) ይላልና። የሰላም ባለቤት የሆነው አምላክ ሰላምን እንደ ዘር እየዘራ ያበዛታል። እርሱ፣ 'እንዴት አደረገ?' አይባልም። ሥራው ለተሠራላቸው ግልጽ ነው፤ ሰላሙም ለቀረቡት ይበዛላቸዋል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

31 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"የሰው መንገድ እግዚአብሔርን ደስ ሲያሰኘው፣ ጠላቶቹ እንኳ አብረውት በሰላም እንዲኖሩ ያደርጋል።"

(ምሳ 16፥7 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

30 Dec, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

ሰላም ለሁልጊዜ የሚሆን ስንቅ፣ ሰዎች ሁሉ የሚሹት፣ መንገዱን ግን አጥልቀው ያልተረዱት የከበረ እሴት—ሐብት—ነው። በጸጥታና ስክነት መካከል ተገኘ ሲባል በውስጥ ጩኸት ይረበሻል፤ ውስጥን ማረጋጋት ሲችሉ ደግሞ የሌሎች ጭንቀትና ስቃይ ሰላምን ያደፈርሳል። ሰላም ዘላቂ ሰጪና የሁልጊዜ ጠባቂ ከሌላት አስቸጋሪ ይሆናል። እርሱም እግዚአብሔር ነው፤ "እግዚአብሔር ለሕዝቡ ብርታትን ይሰጣል፤ እግዚአብሔር ሕዝቡን በሰላም ይባርካል" (መዝ 29፥11)። እርሱም ብርታትን ከሰላም ጋራ የሚሰጥ፣ የሰጠውን ሰላምም በማንነቱና በህልውናው የሚጠብቅ ነው። እግዚአብሔር የባረከው ሰላም እግዚአብሔር ላይ ብቻ ነው ሊያልቅ የሚችለው፤ እርሱም አያልቅበትም!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

30 Dec, 04:00


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔር ለሕዝቡ ብርታትን ይሰጣል፤ እግዚአብሔር ሕዝቡን በሰላም ይባርካል።"

(መዝ 29፥11 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

29 Dec, 07:02


መልእክተ ሰንበት

መልካም ሥራ ሁሉን ይቀድማል፤ ሁሉንም ያልፋል። ማኀበራዊ ቀውስና ብዙ ችግሮች ባሉበት ይሁንታዊ ምላሽና ሁኔታ አለፍ ተግባር ሊከብድ ቢችልም፣ መልካም ማድረግ የተጠየቀ፣ የተፈቀደና የታገዘ ተግባር ነው፤ ጴጥሮስ እንዲህ እንዳለ፤ "መልካም በማድረግ የአላዋቂዎችን ከንቱ ንግግር ዝም እንድታሰኙ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው" (1ጴጥ 2፥15)። በግራም ሆነ ቀኝ ብዙ ንግግር፣ ስንፍናና ክፋት ቢኖርም የእግዚአብሔር ፈቃድ ለመልካምነት፣ በመልካምነትና ስለ መልካምነት ነው። ከንቱ ንግግርን ብርቱ ሥራ ያሸንፈዋል። መልካምነትን መሸፈን የሚችል ስንፍናና ዐመፅም የለም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

27 Dec, 11:02


የዕለቱ ሐሳብ

የእግዚአብሔር ፈቃድ እንዲፈጸም የሚጸለየውን ያህል እንዲታወቅም መጸለይ ያስፈልጋል። 'በዚህ ጉዳይ ላይ የጌታ ፈቃድ ምንድነው?' ተብሎ ይጠየቃል። የፈቃዱን ዕውቀት ለማወቅ ደግሞም ይጸለያል። ይህም ሰማያዊ ጥበብና ግልጽ መረዳትን የሚፈልግ ነው፤ ጳውሎስ እንዲህ ብሎ እንደ ጻፈ፤ "እግዚአብሔር የፈቃዱን ዕውቀት በመንፈሳዊ ጥበብና መረዳት ሁሉ ይሞላችሁ ዘንድ ስለ እናንተ መጸለይና መለመን አላቋረጥንም" (ቈላ 1፥9)። ፈቃዱን ለማወቅና ለመረዳት፣ ሌሎችም እንዲሁ የፈቃዱን ዕውቀት እንዲያስተውሉ መጸለይ፣ ፈቃዱን ለመለየትና ለመፈጸም ዐይነተኛ መፍትሄ ነው። ብርሃን ያላገኘ ዐይን ማየት እንደማይችል ሁሉ፣ "መንፈሳዊ ጥበብና መረዳት" ያላገኘ ልብና አእምሮ ፈቃዱን መለየት ይቸገራል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

27 Dec, 03:59


የዕለቱ ቃል

"...እግዚአብሔር የፈቃዱን ዕውቀት በመንፈሳዊ ጥበብና መረዳት ሁሉ ይሞላችሁ ዘንድ ስለ እናንተ መጸለይና መለመን አላቋረጥንም፤"

(ቈላ 1፥9 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

26 Dec, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

የእግዚአብሔር ፈቃድ የሚታወቅ፣ የምንረዳው ነው። ለመረዳት ግን የታደሰ አእምሮ ይጠይቃል፤ ፈቃዱ ከመረጃ ያለፈ ነውና። መንፈሳዊ ስለሆነም ልብ ብቻ የሚሳተፍበት አይደለም፤ የተለወጠና የጠራ አእምሮ ይፈልጋል ፤ "መልካም፣ ደስ የሚያሰኝና ፍጹም የሆነውን የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደ ሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በአእምሯችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ" (ሮሜ 12፥2)። ፈቃዱ ከመልካምነት ፈጽሞ የማይጎድል፣ የውስጥ ደስታ—ርካታ—ያለበት፣ እንዲሁም ፍጹም (እንከን አልባ) ነው። ይህን ለመረዳት ነው እንግዲህ የተለወጠ፣ በቃሉም ሁልጊዜ የሚታደስ አእምሮ የሚያስፈልገው። ፈቃዱን በዓለም ካለው አሠራር ጋራ እያነጻጸርን ወይም እየተነተንን የምንረዳው አይደለም፤ አእምሮን የሠራው ራሱ አዳሽ ስለሆነ፣ በርሱ እየታገዝን የምንረዳውና በተረዳንበት አቅም የምንፈጽመው እንጂ!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

26 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"መልካም፣ ደስ የሚያሰኝና ፍጹም የሆነውን የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደ ሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በአእምሯችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ።"

(ሮሜ 12፥2 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

25 Dec, 11:02


የዕለቱ ሐሳብ

ጸሎት ፈቃድ ማስገዢያ ነው፤ ደግሞም የስሜት ቋንቋ ነው። ጌታ ኢየሱስ ሥጋ የሆነውና የተወለደው፣ የኖረውና ያስተማረው፣ መጨረሻ ላይ ለመሞት ነው። የገዛ ተማሪው (ጴጥሮስ) 'ሞት ይቅርብህ' ባለው ጊዜ እንኳን ጥንድ ተግሣጽን ተቀብሏል። የልደቱ ማኀተም የሆነውን የሞት ጽዋ ሊጠጣ ባለ ጊዜ ግን ከጭንቀቱ የተጨመቀ ጸሎት ጸለየ፤ "እንዲህም አለ፤ 'አባት ሆይ፤ ፈቃድህ ከሆነ፣ ይህችን ጽዋ ከእኔ ውሰድ፤ ነገር ግን የእኔ ፈቃድ ሳይሆን የአንተ ፈቃድ ይፈጸም'” (ሉቃ 22፥42)። ይህ ጸሎት ብርሃን (ዕውቀት) ፈላጊ አይደለም፤ ጌታ ተልዕኮውን ሊያጣው አይችልምና። ጸሎቱ ግን ተገዢነትን፣ እገዛ ፍለጋን ያመለክታል። 'መልአክም...አበረታታው" የተባለው ለዚህ ነው። እንግዲህ፣ በተገለጠ ፈቃድ ለአቅምና ብርታት ይጸለያል ማለት ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

25 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"እንዲህም አለ፤ 'አባት ሆይ፤ ፈቃድህ ከሆነ፣ ይህችን ጽዋ ከእኔ ውሰድ፤ ነገር ግን የእኔ ፈቃድ ሳይሆን የአንተ ፈቃድ ይፈጸም።'”

(ሉቃ 22፥42 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

24 Dec, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

እግዚአብሔር ለሁሉ የተመረጠና የተዘጋጀ ፈቃድ አለው። ፈቃዱም ከርሱ ጋራ በሰማይ አለ። ፈቃዱ አንዴ ተገልጦና ታውቆ እኛ ሲያስፈልገን ወይም ሲመቸን ተግባራዊ የምናደርገው አይደለም፤ ሁልጊዜ የምንጠይቀው፣ ሁልጊዜም የምንታመንበት እንጂ። እንዲህ እንደ ተባለ፤ "ፈቃድህ በሰማይ እንደ ሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን" (ማቴ 6፥10)። ፈቃዱ በሰማይ ታቅዳለች፤ በሰማይ ተሠርታለች፤ በሰማይም ትገኛለች፤ ከሰማይም ትወርዳለች። እርሱም ፈቃዱን በጥቅል ለሰዎች ልጆችና በልዩ ሁኔታም በርሱ ለሚያምኑ እንደ ገለጠ ሁሉ፣ ለእያንዳንዳችንም የተዘጋጀች ፈቃድ አለችው። አምነው የሚጠይቁና የሚፈልጉት፣ የተዘጋጁ ስለሆኑ ከፈቃዱ ጋራ ይገናኛሉ። ፈቃዱም አቅሙን ይዛ ስለምትወርድ ለሚፈጽሟት ብርታት እንጂ ሸክም አትሆንም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

24 Dec, 04:00


የዕለቱ ቃል

"...ፈቃድህ በሰማይ እንደ ሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን።"

(ማቴ 6፥20 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

23 Dec, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

የእግዚአብሔር ማንነት የታወቀውን ያህል ፈቃዱም እንዲሁ የተገለጠ ነው፤ "ሰው ሆይ፤ መልካም የሆነውን አሳይቶሃል፤ እግዚአብሔር ከአንተ የሚፈልገው ምንድን ነው? ፍትሕን ታደርግ ዘንድ፣ ምሕረትንም ትወድድ ዘንድ፣ በአምላክህም ፊት በትሕትና ትራመድ ዘንድ አይደለምን?" (ሚክ 6፥8)። የታወቀውን ፈቃዱን ስናደርግ ያልደረስንበት ላይ በቀላሉ እንደርሳለን፤ ፈቃዱ በሂደት እየታወቀ ይሄዳልና። "መልካም የሆነውን" ማድረግ፣ "ፍትሕን" መወዳጀት፣ "ምሕረትንም" መውደድ የተጠየቁ፣ የተፈቀዱና እገዛ ያለባቸው ናቸው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

23 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ሰው ሆይ፤ መልካም የሆነውን አሳይቶሃል፤ እግዚአብሔር ከአንተ የሚፈልገው ምንድን ነው? ፍትሕን ታደርግ ዘንድ፣ ምሕረትንም ትወድድ ዘንድ፣ በአምላክህም ፊት በትሕትና ትራመድ ዘንድ አይደለምን?"

(ሚክ 6፥8 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

22 Dec, 07:00


መልእክተ ሰንበት

ሽማግሌው ዮሐንስ "ለእውነት ታማኝ" ለሆነው ወዳጁ ጋይዮስ ደብዳቤ ጽፎለታል—3ኛ ዮሐንስን። የጸሎት ምኞቱንም ይገልጽለታል፤ "ወዳጅ ሆይ፤ ነፍስህ በመልካም ሁኔታ ላይ እንዳለች ሁሉ መልካም ጤንነት እንዲኖርህና በነገር ሁሉ እንዲሳካልህ እጸልያለሁ" (3ዮሐ 1፥2)። ይህ ጸሎት ታማኝ፣ የፍቅር ሰውና ሠራተኛ ከሆነው ዮሐንስ፣ ታማኝ፣ የፍቅር ሰውና በሥራው የተመሰከረለት ለሆነው ጋይዮስ የቀረበ ነው። ስኬት በታማኝነት፣ በሥራና በጸሎት ይመጣል። የነፍስ ጤንነት ያላቸው የአካል ጤንነት ሲያገኙ አልሚ እንጂ አጥፊ አይሆኑም። እንዲህ ዐይነቶችም ጤንነታቸውንና ስኬታቸውን ለሌሎች ለመትጋትና ለመትረፍ ያውሉታል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

20 Dec, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

የዘራ ያጭዳል፤ የሠራም ይበላል። ስኬትና መከናወን ትጋትንና ጽናትን ይከተላሉ። በማስተዋል የሚሠራ ሥራም ብድራቱ ትልቅ። በእምነትም ሆነ በሥራ እጅግ የተመሰከረለት ጳውሎስ ለመንፈሰደ ልጁ ጢሞቴዎስ እንዲህ አለው፤ "ትጉህ ገበሬም ከሰብሉ ለመጠቀም የመጀመሪያው ሊሆን ይገባዋል። እኔ የምለውን ልብ በል፤ ጌታ በሁሉም ነገር ማስተዋልን ይሰጥሃልና" (2ጢሞ 2፥6-7)። ሰምተው የሚያስተውሉ፣ አስተውለውም የሚሠሩ ያለ ፍሬ አይቀሩመረ። ፍሬያቸውም ወደ ታች ሳይሆን ወደ ላይ 'የሚንዠረገግ' ነው--ሰማይ የሚለቅመው ፍሬ!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

20 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ትጉህ ገበሬም ከሰብሉ ለመጠቀም የመጀመሪያው ሊሆን ይገባዋል። እኔ የምለውን ልብ በል፤ ጌታ በሁሉም ነገር ማስተዋልን ይሰጥሃልና።"

(2ጢሞ 2፥6-7 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

19 Dec, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ለጳውሎስ መቻል ከሚያስችለው የሚመጣ ነው። ሐዋርያው ብዙ ሠርቷል፤ ብዙ ደክሟል፤ መከራ አይቷል፤ ጠግቧልም። መንፈሳዊ ስኬትን እንደ እርሱ ያየ ማገኘት አይቻልም። 13 መጻሕፍትን ጽፏል፤ የክርስትናን መሠረት ከጌታው ባገኘው መገለጥ አደላድሏል፤ ቤተ ክርስቲያናትን መሥርቷል፤ ሐዋርያነትን ለአሁኗና ለመጪዋ ቤተ ክርስቲያን ጭምር አጽንቷል። ይህን ሁሉም በክርስቶስ እንዳደረገው ደንግጓል፤ "ኀይልን በሚሰጠኝ በእርሱ ሁሉን ማድረግ እችላለሁ" (ፊል 3፥13)። የጌታ አስቻይነት ከሚቀመጡ ይልቅ ለሚሠሩ ይታወቃል። የሚወጡ አመራሩንና ጥበቃውን ያውቃሉ፤ የሚደክሙ እገዛውን ይረዳሉ፤ የሚጸኑም ግሩም አደራረጉንና ታላቅ ስኬቱን ይለማመዱታል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

19 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ኀይልን በሚሰጠኝ በእርሱ ሁሉን ማድረግ እችላለሁ።"

(ፊል 3፥13 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Dec, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ታማኝነት፣ ጽናትና ትጋት ፈተና አልባ ባይሆንም ታላቅ ብድራት—ዋጋ—አለው። ዳንኤል ጽድቁን እየጨመረ፣ ታማኝነቱን እያጠለቀ ከ60 ዓመታት በላይ ከፍ ባሉ (የአሕዛብ) መንግሥታት ኅላፊነት ቆየ። ነቀፌታ ወይም ሰበብ ሲታጣበት በአምላኩ ሕግ መጡበት፤ መንፈሳዊ ስደት ገጠመው፤ ሕይወቱ አደጋ ላይ ወደቀ። እርሱ ግን ከሰው ፊት በላይ በአምላኩ ፊት ታማኝ ስለ ነበር፣ ልቡ ጸና፤ ጸሎቱን ከምስጋና ጋራ ሳያቋርጥ ቀጠለ። በዚህ ምክንያት አንበሳ ጕድጓድ ውስጥ ቢጣልም፣ የወደቀው ግን አምላኩ እጅ ላይ ነበር። እግዚአብሔርም በክብር እንዲወጣ አደረገው፣ አከበረውም፤ "ስለዚህ ዳንኤል በዳርዮስ ዘመነ መንግሥትና በፋርሳዊው በቂሮስ ዘመነ መንግሥት ሁሉ ኑሮው ተሳካለት" (ዳን 6፥28)። ስኬትና መቃናት በመከራ ተፈትኖ ሲያልፍ፣ ማንም ዝቅ ሊያደርገው ወይም ሊያወርደው አይችልም፤ እግዚአብሔር የበጎ ነገር ሁሉ መጨረሻ ወይም ጫፍ ነውና።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Dec, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ስለዚህ ዳንኤል በዳርዮስ ዘመነ መንግሥትና በፋርሳዊው በቂሮስ ዘመነ መንግሥት ሁሉ ኑሮው ተሳካለት።"

(ዳን 6፥28 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Dec, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ሰዎች ከማይገቡ ነገሮች ሲርቁ ወይም ከማይሆን ኅብረት ሲታቀቡ "ብፁዕ"—የተባረኩ—ይባላሉ። መዝሙር 1 ይህንን ያሳውቀናል—"የማይሄድ"፣ "የማይቆም"፣ "የማይቀመጥ" እያለ። እየተከላከሉና እየራቁ ብቻ ግን ብዙ ርቀት መሄድ አይቻልም። ሌላ ርምጃ፣ ሌላ አቋም፣ ሌላ መቀመጥም ያስፈልጋል፤ "ነገር ግን ደስ የሚሰኘው በእግዚአብሔር ሕግ ነው፤ ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያሰላስለዋል። እርሱም በወራጅ ውሃ ዳር እንደ ተተከለች፣ ፍሬዋን በየወቅቱ እንደምትሰጥ፣ ቅጠሏም እንደማይጠወልግ ዛፍ ነው፤ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል።" (ቍ. 2-3)። የጌታን ቃል የሚያነቡ፣ የሚያሰላስሉትና የሚኖሩበት ወቅት-አለፍ (የሁልጊዜ) ልምላሜ ያላቸው፣ በእጃቸው ያለው ሥራም የሚከናወንላቸው ናቸው። በውሃ ዳር የተተከለ ተክል የወቅት መለዋወጥም ይሁን የዘመን መዘበራረቅ እንደማያሰጋው ሁሉ፣ እነርሱም በየትኛውም ጊዜና ሁኔታ መካከል ፍሬ የሚያፈሩ ናቸው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"...ደስ የሚሰኘው በእግዚአብሔር ሕግ ነው፤ ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያሰላስለዋል። እርሱም በወራጅ ውሃ ዳር እንደ ተተከለች፣ ፍሬዋን በየወቅቱ እንደምትሰጥ፣ ቅጠሏም እንደማይጠወልግ ዛፍ ነው፤ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል።"

(መዝ 1፥2-3 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

16 Dec, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ስኬት ወይም መከናወን በመከራ ይፈተን እንደሆን እንጂ አይቋረጥም። ዮሴፍ 'ሕልመኛ' ብቻ አልነበረም፤ ታዛዥና ታታሪም ነበር። የአባቱን መልእክት ይዞ ወደ ወንድሞቹ ቢሄድ ልብሱ ተገፍፎ ተሸጠ። በግብፅ ለባርነት ቢወርድም፣ አምላኩ ከርሱ ጋራ ነበር፤ "እግዚአብሔር ከዮሴፍ ጋር ነበረ፤ ኑሮው ተቃናለት፤ እርሱም በግብፃዊው አሳዳሪው ቤት ኖረ" (ዘፍ 39፥2)። ከአባቱ በተንኮልና ጭካኔ ቢለይም፣ የሰማዩ አባቱ ግን አልተለየውም ነበር። እርሱም 'በወረደበት' እየቀደመ ሞገስና መከናወን ሆነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

16 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔር ከዮሴፍ ጋር ነበረ፤ ኑሮው ተቃናለት፤ እርሱም በግብፃዊው አሳዳሪው ቤት ኖረ።"

(ዘፍ 39፥2 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

15 Dec, 07:00


መልእክተ ሰንበት

የጳውሎስ የክርስትና ጉዞ አጭር ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን የተዋጣለትና ውጤታማ ነበር። የተሰጠውን ሠርቶ እንደ ጨረሰ ለጢሞቴዎስ ከእስር ቤት ሆኖ በላከው የመጨረሻ መልእክቱ ገልጧል፤ "መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፤ ሩጫውን ጨርሻለሁ፤ ሃይማኖትንም ጠብቄአለሁ" (2ጢሞ 4፥7)። በደማስቆው ዐላማ የሳተ ጉዞው ላይ ጌታው ያገኘው ሐዋርያ፣ የጌታን ድምፅ ታዝዞ ብዙ ተጓዘ፤ (ከ14 ሺ ኪሎ ሜትር በላይ እንደ ሸፈነ ይታመናል፤) ብዙ ደከመ፤ አሥራ ሦስት መልእክቶችን ጻፈ። የተሰመረለትን ጉዞ ፍጥነቱን ሳይቀንስ ጨረሰ። እየተጓዘ ሠራ (እስር ላይም ሆኖ)፤ እየሠራም ተጓዘ። ጉዞውንም በሰማያዊው ቤት ዕረፍትና ሽልማት ጨረሰው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

13 Dec, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ዮሐንስ እንደ ተወለደ የዘካርያስ አንደበት ተከፈተ። በመጠራጠሩ የተዘጋው ይሄው አፍ በተከፈተ ጊዜ ትንቢት ተናገረ፤ "ከአምላካችንም በጎ ምሕረት የተነሣ፣ የንጋት ፀሓይ ከሰማይ ወጣችልን፤ ይኸውም በጨለማ ለሚኖሩት፣ በሞት ጥላ ውስጥም ላሉት እንዲያበራና፣ እግሮቻችንንም ወደ ሰላም መንገድ እንዲመራ ነው" (ሉቃ 1፥78-79)። ስለ ልጁ ተናግሮ፣ ስለ እግዚአብሔር ልጅ መናገር ቀጠለ። እርሱም ብርሃን እየሆነ የሚያራምድ፣ ሰላም እየሰጠም ጉዟችንን የሚያስቀጥል ነው። ከሰማይ ወደ ምድር ከተጓዘ፣ በምድር ያሉትን በርሱ መንገድ ወደ ሰማይ ያስጉዛል። ብርሃኑም ሁልጊዜ ከመንገዱ አይጠፋም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

08 Dec, 07:00


መልእክተ ሰንበት

ጌታ "ከነገድና ከቋንቋ ሁሉ" ያዳናቸውን ሰዎች በክብር ከፍ ከፍ ያደርጋል፤ ከመከራቸው ያሳርፋል፤ በንግሥናው ሥርም ያነግሣቸዋል፤ "ለአምላካችንም መንግሥትና ካህናት አድርገሃቸዋል፤ እነርሱም በምድር ላይ ይነግሣሉ” (ራእ 5፥10)። ጌታ ሕዝቡን በርቀት የሚገዛ አይደለም፤ ሞቶ እንደ ዋጃቸው፣ በእግዚአብሔር ኅይል ተነሥቶ አክብሯቸዋል። ሕዝቡም በክህነታቸው ላይ ንግሥናን—ማዕረግንና ከፍታን—ይጨምራሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

06 Dec, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

ጴጥሮስና ዮሐንስ ወደ ቤተ መቅደስ ሲሄዱ ላገኙት ተመጽዋች ያላቸውን ሰጡት—የናዝሬቱን የኢየሱስ ክርስቶስን ስም። ይህ ስጦታም እስከዚያች ቅጽበት ድረስ ከተቀበለው ሁሉ እጅግ የራቀ ነበር፤ ከስሙ የተነሣ ተነሣ፤ ሽባ የነበረውም እግሩ ተስተካክሎ ጸና። ወደ መቅደሱም አስከተሉት። ነገሩ ምስጋና ለእግዚአብሔር ያመጣውን ያህል ተቃውሞ አስነሣ። የአይሁድ አለቆችም ተቆጡ! "ከጠሯቸውም በኋላ፣ በኢየሱስ ስም ፈጽሞ እንዳይናገሩና እንዳያስተምሩ አዘዟቸው። ጴጥሮስና ዮሐንስ ግን መልሰው እንዲህ አሏቸው፤ 'ከእግዚአብሔር ይልቅ ለእናንተ መታዘዝ በእግዚአብሔር ፊት ይገባ እንደ ሆነ እስቲ እናንተው ፍረዱ!'" (ሐሥ 4፥18-19)። የሥልጣን ምንጭ እግዚአብሔር ነው፤ በተዋረድ ያለውን የትእዛዝ ሥርዓትም ደንግጓል። በዚያ ላይና በሁሉም ላይ ግን ሁልጊዜ የበላይና ገዢ ነው። የወደደውንም በግልጽ ሲያደርግ ሰዎችን ያሳትፋል፤ እነርሱም ፍጹም የበላይ ለሆነው ለእርሱ በብቸኝነት (ያለ ማቅማማትና ይሉኝታ) ይገዛሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

06 Dec, 03:59


የዕለቱ ቃል

"ከጠሯቸውም በኋላ፣ በኢየሱስ ስም ፈጽሞ እንዳይናገሩና እንዳያስተምሩ አዘዟቸው። ጴጥሮስና ዮሐንስ ግን መልሰው እንዲህ አሏቸው፤ 'ከእግዚአብሔር ይልቅ ለእናንተ መታዘዝ በእግዚአብሔር ፊት ይገባ እንደ ሆነ እስቲ እናንተው ፍረዱ!'"

(ሐሥ 4፥18-19 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

05 Dec, 11:02


የዕለቱ ሐሳብ

እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎችን ሊፈሩ አይችሉም፤ የእርሱ ፍርሃት ጽድቅና አቅም ያላብሳልና። ዳንኤል በምርኮ ባገለገለባቸው መንግሥታት ዘንድ ፍጹም ታማኝ ነበር፤ ታማኝነቱም ብርቱና ባለ ሞገስ አድርጎታል። ይህንንም ያገኘው ከአምላኩ ነበር። የንጉሥ ዳርዮስ ትእዛዝ—ወደ እርሱ ካልሆነ በቀር ወደማንም ለወር እንዳይጸለይ የሚለው—ወሰን ሲያልፍም ባለመናወጥ ጸና፤ "ዳንኤልም ዐዋጁ እንደ ወጣ ባወቀ ጊዜ ወደ ቤቱ ሄደ፤ መስኮቶቹ በኢየሩሳሌም አንጻር ተከፍተው ባሉበት በሰገነቱ ቀድሞ ያደርግ እንደ ነበረው በቀን ሦስት ጊዜ ተንበርክኮ ጸለየ፤ አምላኩንም አመሰገነ" (ዳን 6፥10)። ዐዋጁ ብርቱ ነበር፤ ዳንኤልን ግን አልነቀነቀውም። የወትሮ ምስጋናውንና ጸሎቱን ቀጠለ። ይህን ተከትሎ አንበሳ ጉድጓድ ቢገባም፣ ጸሎቱ ቀድሞት ገብቶ ስለ ነበር አምላኩ ታደገው። በታላቁ ፍርሀት ሥር ትናንሾቹ ፍርሀቶች ይከስማሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

05 Dec, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ዳንኤልም ዐዋጁ እንደ ወጣ ባወቀ ጊዜ ወደ ቤቱ ሄደ፤ መስኮቶቹ በኢየሩሳሌም አንጻር ተከፍተው ባሉበት በሰገነቱ ቀድሞ ያደርግ እንደ ነበረው በቀን ሦስት ጊዜ ተንበርክኮ ጸለየ፤ አምላኩንም አመሰገነ።"

(ዳን 6፥10 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

04 Dec, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

ሰው ገደብ አለው፤ ንጉሥ ገደብ አለው፤ ኅያላንም ገደብ አላቸው፤ ላይገባቸው ግን ይችላል። ናቡከደነፆር ትልቅ ምስል በወርቅ አሠርቶ ስግደትን ከሚያስተዳድረው ሕዝብ ሁሉ ጠየቀ። ሁሉም ስግደቱን እየቀየረም ይሁን በስግደቱ ላይ ሌላ እየጨመረ ተደፋ፤ ለምስሉ ተጎነበሰ። በልዩነት ግን ሦስቱ አይሁድ ወጣቶች ቆመው ታዩ። ይህም ኅያሉን ንጉሥ አስቆጣ፣ እሳቱንም እንዲጨምር አስደረገው። እርሱም በአቋሙ፣ እነርሱም በአቋማቸው ጸኑ፤ በአምላካቸውም ተወራረዱ፤ "ንጉሥ ሆይ፤ በሚንበለበለው የእቶን እሳት ውስጥ ብንጣል፣ የምናመልከው አምላክ ሊያድነን ይችላል፤ ከእጅህም ያድነናል። ነገር ግን ንጉሥ ሆይ፤ ባያድነንም እንኳ፣ አማልክትህን እንደማናገለግል፣ ላቆምኸውም የወርቅ ምስል እንደማንሰግድ ዕወቅ" (ዳን 3፥17-18)። ወጣቶቹ ገደቡን አሳዩት። ታማኝነታቸው ለአምላካቸውና ለንጉሡ ሙሉ ነበር፤ ጕልበታቸውንም ለተሰጣቸው የመንግሥት ኅላፊነት አልሰሰቱም፤ ለጣዖትና ቅዠት ለወለደው ምስል ግን የሚንበረከክ አልነበረም። አቅማቸውን ቀና ብለው ተመለከቱ፤ ፍጹም ተገዢነታቸውንም ለሰማዩ አምላካቸው አደረጉ፤ እርሱም ከአርያም ታዳጊ ልኮ አከበራቸው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

04 Dec, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ንጉሥ ሆይ፤ በሚንበለበለው የእቶን እሳት ውስጥ ብንጣል፣ የምናመልከው አምላክ ሊያድነን ይችላል፤ ከእጅህም ያድነናል። ነገር ግን ንጉሥ ሆይ፤ ባያድነንም እንኳ፣ አማልክትህን እንደማናገለግል፣ ላቆምኸውም የወርቅ ምስል እንደማንሰግድ ዕወቅ።"

(ዳን 3፥17-18 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

03 Dec, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

እስራኤል መልካም ያደረጉ መሪዎች እንደ ነበሯት፣ ክፉ ያደረጉና እግዚአብሔርን ያስቆጡ መሪዎችም ነበሯት። ከእነዚያ መካከል አንዱ አክዓብ ነበር። ይህ ንጉሥ ባገባት ሚስቱ (ኤልዛቤል) ምክንያት በምድሪቱ ላይ ባዕድ አምልኮ እንዲስፋፋ በማድረግ ቀናተኛውን አምላክ አስቆጣ፣ አገሪቱንም በድርቅ (ረሃብ) አስቀጣ። ማንነቱንና ዐላማውን የሚያሳውቅ አምላክ ግን በነቢዩ በኩል ተገለጠ። ኤልያስ ለቃሉ እንጂ ለክብሩ ያላደረ፣ ከፍርሃቱም ባሻገር እግዚአብሔርን ያከበረ ስለ ነበረ፣ አክዓብንና መንግሥቱን ለዕብደቱ አልተወም፤ የተሰጠውን መልእክት 'እንደ ወረደ' ያስተላልፍ ነበር፤ "ኤልያስም፣ 'በፊቱ የቆምሁት ሁሉን የሚገዛ ጌታ እግዚአብሔርን፣ ዛሬ በአክዓብ ፊት በርግጥ እገለጣለሁ' አለ" (1ነገ 18፥15)። ኤልያስ ከገዢዎች በላይ ገዢ—"ሁሉን የሚገዛ"—ለሆነው አምላክ የተገዛ ስለ ነበር፣ ሙሉውን የጌታ ቃል በሙሉ ልቡ ይናገር ነበር። ለእግዚአብሔር የተገዙ ለርሱ ብቻ ያድራሉ!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

03 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ኤልያስም፣ 'በፊቱ የቆምሁት ሁሉን የሚገዛ ጌታ እግዚአብሔርን፣ ዛሬ በአክዓብ ፊት በርግጥ እገለጣለሁ' አለ።"

(1ነገ 18፥15 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

02 Dec, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

የእግዚአብሔር ሐሳብ በእግዚአብሔር ጊዜ እየከበደ ይሄዳል። ሐሳቡ ያለባቸውም እንዲሁ እየከበዱ ይመጣሉ። ሙሴ በተወለደበት ዘመን የዕብራውያን ሕፃናት ወንዶች እንዲገደሉ ትእዛዝ ወጣ። (የግብፅ ንጉሥ ፈርዖንና ሹማምንቱ አንዳች ነገር ሳይታያቸው አልቀረም።) የእግዚአብሔር እጅ በርትታ ስለ ነበር ግን አዋላጆቹ ከድንጋጌው በላይ ለሕሊናቸው ታማኝ ሆኑ፤ "አዋላጆቹ ግን እግዚአብሔርን ስለ ፈሩ የግብፅ ንጉሥ ያዘዛቸውን አልፈጸሙም፤ ወንዶቹንም ልጆች በሕይወት እንዲኖሩ ተዉአቸው" (ዘፀ 1፥17)። ነገሩ ፈርዖንን ቢያስከፋም፣ እግዚአብሔርን ግን ደስ አሰኘ፤ እርሱም "ለአዋላጆቹ መልካም ሆነላቸው።" በክፉው የተተበተቡና ከሕሊና በላይ የሆኑ ሕጎች ለእግዚአብሔርና ለእውነት በመገዛት ጥበብ ባለው ብልኀት መምከን ይችላሉ። ሙሴ ተወልዶ ተሸሸገ፤ ታምረኛ የሆነው አምላክም ድንጋጌው በወጣበት በፈርዖን ቤት በክብካቤ እንዲያድግ አደረገው። በዚህ ሁሉ፣ እናቱን ጨምሮ፣ የሴቶቹ ጥበብ ድንቅ ነበር።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

02 Dec, 04:01


የዕለቱ ቃል

"አዋላጆቹ ግን እግዚአብሔርን ስለ ፈሩ የግብፅ ንጉሥ ያዘዛቸውን አልፈጸሙም፤ ወንዶቹንም ልጆች በሕይወት እንዲኖሩ ተዉአቸው።"

(ዘፀ 1፥17 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

01 Dec, 07:00


መልእክተ ሰንበት

እግዚአብሔር ጥላ አያውቅም፤ የብርሃናት አባት፣ የብርሃንም መንጭ ነውና። ከርሱም በጎ፣ ፍጹምና ንጹሕ የሆነው ሁሉ ይወጣል፤ "በጎ ስጦታና ፍጹም በረከት ሁሉ ከላይ፣ ከሰማይ ብርሃናት አባት ይወርዳሉ፤ በእርሱ ዘንድ መለዋወጥ፣ ከመዞር የተነሣ የሚያርፍ ጥላም የለም" (ያዕ 1፥17)። ስጦታው ሁሉ ከባሕርይው ይመነጫል። ፍጹም ስለሆነ ባርኮቱና ስጦታውም እንዲሁ ፍጹም ነው። እርሱ ለፍቶ ወይም 'ከየትም ብሎ' አይደለም የሚሰጠው፣ ከሆነው እንጂ፤ የመልካም ነገር ሁሉ መገኛ ነውና። በረከቱም የማይቀነስ፣ የማይታረምም ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

29 Nov, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ትናንሽ ትላልቆች—ያልተረዱ አዋቂዎች—ትላልቅ ትናንሾችን—የሚያድጉ ሕፃናትን—መከልከል የለባቸውም። ሰዎች ሕፃናት በጌታ እንዲዳሰሱ ወደ ጌታ ኢየሱስ ሲያቀርቧቸው 'ትልልቆቹ' ደቀ መዛሙርት ተከላከሉ። ጌታ ግን ገሣጮቹን "ተቆጥቶ" እንዲህ አለ፤ "እውነት እላችኋለሁ፤ የእግዚአብሔርን መንግሥት እንደ ሕፃን የማይቀበል ሁሉ ከቶ አይገባባትም። ሕፃናቱንም ዐቀፋቸው፤ እጁንም ጭኖ ባረካቸው" (ማር 10፥15-16)። ሕፃናቱን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የመግቢያ ምሳሌ አድርጎ ተጠቀመባቸው። እንደ ሕፃን ቀና፣ የዋህና ሙሉ መተማመን የማይፈልግ ለመንግሥቱ ብቁ አይሆንም፤ እንዲህ ዐይነቶቹ ደግሞ ሕፃናቱ እንደ ተባረኩ ይባረካሉ። ሕፃናቱን ዐቅፎ እንደ ባረከ በፊቱ እንደ ሕፃን ሆነው የሚቀርቡትን ጌታ እያስጠጋ ይዳስሳል፤ ይባርካልም!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

29 Nov, 04:00


የዕለቱ ቃል

"እውነት እላችኋለሁ፤ የእግዚአብሔርን መንግሥት እንደ ሕፃን የማይቀበል ሁሉ ከቶ አይገባባትም። ሕፃናቱንም ዐቀፋቸው፤ እጁንም ጭኖ ባረካቸው።"

(ማር 10፥15-16 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

28 Nov, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

የሰርክ መዝሙሮች የሚሰኙ አሉ፤ መዝሙር 134 ከነዚህ መዝሙሮች መካከልም—120-134—የመጨረሻው ነው። እነዚህ መዝሙሮችም የእግዚአብሔር ሕዝዝ ወደ ጽዮን ወይም ወደ መቅደስ እየወጣ የሚዘምራቸው መዝሙሮች ነበሩ። እግዚአብሔርን በመቅደሱ የሚባርኩ (በአክብሮት የሚያመሰግኑ)፣ እነርሱም የበረከቱ ተካፋዮች ይሆናሉ። እግዚአብሔር ሲባርክም "ሰማይንና ምድርን" በሠራበት ደግነቱና በጎነቱ፣ ኅይሉና አቅሙ ነው የሚባርከው። ባርኮቱም ወደ ባራኪው ያቀርባል። የእግዚአብሔር ባርኮትም የአንድ ጊዜ ዝርግፍ ስጦታ ሳይሆን፣ ሁሉጊዜ እርሱን በመጠጋጋት የምናገኘው ነው። እርሱ ካለበት የሚወርደው ባርኮቱም ያለንበትን (ስፍራና ሁኔታ) የሚያልፍ ነው!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

28 Nov, 05:49


የዕለቱ ቃል

"ሰማይንና ምድርን የሠራ እግዚአብሔር፣ ከጽዮን ይባርክህ።"

(መዝ 34፥3 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

27 Nov, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

እግዚአብሔር በሚባርካቸው ላይ ፊቱን እንደሚያበራ ሁሉ፣ ፊቱንም ይመልሳል፤ "እግዚአብሔር ፊቱን ይመልስልህ፤ ሰላሙንም ይስጥህ" (ዘኁ 6፥26) ተብሎ በክህነት ባርኮት እንደ ታዘዘ። ሰው ፊቱን እንደሚያዞር እግዚአብሔርም ያዞራል፤ የሰው ፊት በሌላ ሰው ፊት ይተካል፤ የእግዚአብሔር ፊት ቢዞር ግን በምን ይተካል? የሚባረክ ሕዝብ ግን ፊቱ የተመለሰለት ነው። እግዚአብሔር ፊቱን የሚመልስላቸውም የሚምራቸው፣ የሚራራላቸው፣ ጸጋውንና በጎነቱን የሚሰጣቸው ናቸው። በርግጥም ልጁን ሲሰጠን ፊቱን በአስደናቂ ምሕረቱ መልሶልናል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

27 Nov, 04:00


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔር ፊቱን ይመልስልህ፤ ሰላሙንም ይስጥህ፤"

(ዘኁ 6፥26 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

26 Nov, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

የአሮን ባርኮት ካህናት ሕዝቡን እንዲባርኩ የተሰጣቸው ትእዛዝ ነው፤ ትእዛዙም "ስሙን በእስራኤል ላይ ስለሚያደርግ" የእግዘብሔርን ባርኮት በሕዝቡ ላይ ያመጣል። ሁለተኛውም አንጓ እንዲህ ይላል፤ "እግዚአብሔር ፊቱን ያብራልህ፤ ይራራልህም፤" (ዘኁ 6፥25)። የፊቱ ብርሃን በርሱ መታወቃችንን የምናውቅበት ብቻ ሳይሆን፣ ተቀባይነት ማግኘታችንን የምናረጋግጥበትም ነው። የፊቱ ብርሃን የበራላቸውም ፊታቸውን ከርሱ ሊያዞሩ አይገባም። ርኅራኄውም ወሰን አያውቅም፤ ወገንም አያውቅም። ስሙ በተጠራባቸው ሁሉ ላይ ያርፋል፤ በእውነት ይራራልና።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

26 Nov, 04:01


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔር ፊቱን ያብራልህ፤ ይራራልህም፤"

(ዘኁ 6፥25 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

25 Nov, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

በረከት የጸጋ፣ የሞገስ፣ የበጎነት ችሮታ ነው። እግዚአብሔር ሕዝቡን ባርኳል፤ እንዲባረኩም ደንግጓል። የአሮን ባርኮት አንዱ ባርኮት ነው፤ ካህናት ሕዝቡን እንዲባርኩ የተሰጣቸው የባርኮት ትእዛዝ። ትእዛዙም "ስሙን በእስራኤል ላይ ስለሚያደርግ" የእግዘብሔርን ባርኮት በሕዝቡ ላይ ያመጣል። የመጀመሪያው አንጓም እንዲህ ይላል፤ "እግዚአብሔር ይባርክህ፤ ይጠብቅህም" (ዘኁ 6፥24)። እግዚአብሔር ባራኪ ነው፤ ጠባቂም ነው። የርሱ ባርኮት ያገኛቸው ምሕረቱ የደረሳቸው፣ ሞገሱን የተላበሱ፣ በጎነቱ የከበባቸውና ሰላሙ ያገኛቸው ናቸው። እርሱ የሚባርካቸውንም ይጠብቃል፤ ፍጹም በጎነት ከጥበቃ ጋራ ከእግዚአብሔር ብቻ ነው የሚገኘው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

25 Nov, 04:00


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔር ይባርክህ፤ ይጠብቅህም፤"

(ዘኁ 6፥24 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

24 Nov, 07:00


መልእክተ ሰንበት

የእግዚአብሔር ሞገስ በጌታ ላይ ነበር፤ በተልዕኮው መጀመሪያ፣ መካከልና መጨረሻ ላይ። መላእክት በውልደቱ እንደ ዘመሩ በክብሩም ዘመሩ፤ "በታላቅ ድምፅም እንዲህ ብለው ዘመሩ፤ 'የታረደው በግ ኀይልና ባለጠግነት፣ ጥበብና ብርታት፣ ክብርና ሞገስ፣ ምስጋናም ሊቀበል ይገባዋል'" (ራእ 5፥12)። በሥጋው ወራት ለእግዚአብሔር ክብርን አመጣ፤ አባቱን የተሰጠውን ሥራ በመጨረስ አከበረ። በመጨረሻም ብዙ ውዳሴ፣ ገናና ክብር፣ እልፍ ምስገሰና፣ ታላቅ ሞገስ ተቀበለ፤ ስለ ተገባውም ተዘመረለት፤ ብዙዎችንም እያዳነ ስለ ቀጠለ ዛሬም ይዘመርለታል። ሞገሱን አይተው የቀረቡት ክብሩን ያስተውላሉ፤ ወድደውም ያመልኩታል። እነርሱም ከሕይወቱ ጋራ ሞገሱን ይካፈላሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

22 Nov, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ጌታ ኢየሱስ በነገር ሁሉ የመታዘዝ ምሳሌ፣ የትሕትና ማሳያ፣ የተልዕኮ ተምሳሌት ሆኖልናል። የአባቱን ፈቃድ በሙሉ መታዘዝ ፈጸመ። በተራራ ላይ ከሦስት ደቀ መዛሙርቱ ጋራ በተገኘበት ጊዜ ከሰማይ ሞገስን ተቀበለ፤ ጴጥሮስ በቦታው ተገኝቶ የሰማውንና ያን ጊዜ ብዙ ያልተረዳውን በመልእክቱ (2ጴጥ 1፥17-18) አጸናው፤ "...ከግርማዊው ክብር 'በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወድደው ልጄ ይህ ነው' የሚል ድምፅ በመጣለት ጊዜ ከእግዚአብሔር አብ ክብርና ሞገስ ተቀብሏል፤ እኛም ከእርሱ ጋር በቅዱሱ ተራራ ላይ በነበርንበት ጊዜ ይህ ድምፅ ከሰማይ ሲመጣ ሰምተናል።" የሰማዩ ድምፅ እርሱን በዚያ ከነበሩት ሁሉ ለየው፤ የተገለጠው ሞገስና ክብር ታላቅነቱን የተለየ ብቻ ሳይሆን የከበረ መሆኑን አረጋገጠ። ከአባቱ የተቀበለው "ክብርና ሞገስ" እኛን ወደ አባቱ ያቀረበ፣ የርሱንም ሞገስ ያላበሰ ነው። እግዚአብሔር ደስ ስለ ተሰኘበትም፣ በርሱ አምነው፣ በርሱ በኩል የሚታዩት ሁሉ አብ አምላክ ደስ የሚሰኝባቸው ይሆናሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

22 Nov, 03:59


የዕለቱ ቃል

"...ከግርማዊው ክብር 'በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወድደው ልጄ ይህ ነው' የሚል ድምፅ በመጣለት ጊዜ ከእግዚአብሔር አብ ክብርና ሞገስ ተቀብሏል፤"

(2ጴጥ 1፥17 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

21 Nov, 11:02


የዕለቱ ሐሳብ

ድርጊት በውጤት ይደመደማል። ክፉ ሥራም ውጤት—መዘዝ—አለው፤ በጎ ሥራም እንዲሁ። ክፋትን ለሚያደርጉ ያለ ልዩነት (አይሁድም ይሁኑ አሕዛብ) "መከራና ጭንቀት ይሆናል፤" "ነገር ግን በጎ ለሚሠራ ለማንኛውም፣ አስቀድሞ ለአይሁድ ከዚያም ለአሕዛብ ክብር፣ ሞገስና ሰላም ይሆንለታል" (ሮሜ 2፥10)። ይህ "ለማንም አያደላምና" ከተባለለት አምላክ የሚሆን ነው። ሞገስ እንደ ክብርና ሰላም ሁሉ በበጎነት ይመጣል፤ ፍሬ ነውና። ይህ፣ ሞገስ መልካም ሥራን ለመጠየቁ ማሳያ ነው። በአምላካቸው ጸጋ ታምነው በጎ የሚያደርጉም የሞገስን ፍሬ ይበላሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

21 Nov, 03:59


የዕለቱ ቃል

"ነገር ግን በጎ ለሚሠራ ለማንኛውም፣ አስቀድሞ ለአይሁድ ከዚያም ለአሕዛብ ክብር፣ ሞገስና ሰላም ይሆንለታል፤"

(ሮሜ 2፥10 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

20 Nov, 11:02


የዕለቱ ሐሳብ

እረኞች ሲጎድሉ ወይም ሲጠፉ እግዚአብሔር ራሱ እረኛ ያዘጋጃል፤ ለሕዝቡ ይራራል፤ ያሰማራል፤ ይመግባል፤ ይጠብቃልም። ነቢዩ ዘካርያስ አፍ እንዲህ አለ፤ "ሁለት በትሮች ወስጄም፣ አንዱን 'ሞገስ' ሌላውንም 'አንድነት' ብዬ ጠራኋቸው፤ መንጋውንም አሰማራሁ" (11፥7)። እረኛ በትር እንደሚይዝ፣ ጌታም በትር ይይዛል (መዝ 23፥4)፤ በትሩንም ለሚመሩ ያቀብላል። የበትሩ አንዱ ስም ደግሞ 'ሞገስ' ተብሎ ተሰይሟል፤ እየመራ ሞገስ የሚሰጥ በትር፤ እያቀና ሞገስ የሚሰጥ በትር፤ እየተከላከለ ሞገስ የሚሰጥ በትር! በታላቁ እረኛ ሥር የሚመሩ የሚጠበቁ ብቻ ሳይሆን ሞገስን እየተቀበሉ አንድ የሚሆኑም ናቸው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

20 Nov, 03:59


የዕለቱ ቃል

"ሁለት በትሮች ወስጄም፣ አንዱን 'ሞገስ' ሌላውንም 'አንድነት' ብዬ ጠራኋቸው፤ መንጋውንም አሰማራሁ።"

(ዘካ 11፥7 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

19 Nov, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

መዝሙር 90 የሙሴ ጸሎት ነው። "ከዘላለም እስከ ዘላለም" የሚኖረውን አምላክ እያሰበ የሰውን በዘመን ውስንነትና አላፊነት ይጸልየዋል፤ ይዘምረዋልም። የጸሎቱ ማሳረጊያም፣ "የጌታ የአምላካችን ሞገስ በላያችን ይሁን፤ የእጆቻችንን ሥራ ፍሬያማ አድርግልን፤ አዎን፣ ፍሬያማ አድርግልን" የሚል ነበር (ቁ.7)። የሰው ልጆች ጥቂት ፍሬያማ ዘመን--70 ወይም 80--ቢኖሩም፣ ዘመናቸው እንዲሁ ያለ ፍሬና ውጤት መጠቅለል የለበትም። የሞገስና ፍሬያማነት ልመናውም ለዚህ ነበር። ከእግዚአብሔር ሳይቀበሉ ተቀባይነት ለማግኘት የሚጥሩም ድካማቸው በሰው ፊት ለጊዜው 'ያደምቃቸው' እንደ ሆነ እንጂ አያከብዳቸውም። ከጌታ የሚመጣ ሞገስ ግን ሰማያዊ ይዘት ስላለው የማይተካ ነው፤ ይህን ሞገስ የለበሱም በሌላ በምንም መድመቅ አይፈልጉም፤ ሞገሱ ዋና (የክት) ልብሳቸው ነውና።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

19 Nov, 04:00


የዕለቱ ቃል

"የጌታ የአምላካችን ሞገስ በላያችን ይሁን፤ የእጆቻችንን ሥራ ፍሬያማ አድርግልን፤ አዎን፣ ፍሬያማ አድርግልን።"

(መዝ 90፥17 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Nov, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ሙሴ የሕዝብ መሪ ነበር፤ የብዙና አስቻጋሪ ሕዝብ መሪ። በርሱ ሥር በጌታ ክንድ የወጣው ሕዝብ መዋጋት የሚችለው ብቻ 600000፣ አጠቃላዩም በጥቂት ሚልዮኖች ይገመታል። "እነዚህን ሕዝብ ምራ" የተባለው ሙሴም እግዚአብሔርን ተማጸነ፤ "በእኔ ደስ ተሰኝተህ ከሆነ፣ አንተን ዐውቅህና ያለ ማቋረጥ በፊትህ ሞገስ አገኝ ዘንድ መንገድህን አስተምረኝ" (ዘፀ 33፥13)። ሞገስ ተቀባይነት፣ ተደማጭነት፣ ተፈላጊነትም ነው። ሙሴም ከአምላኩ ሞገስን ለመነ። መሪነት ያለ ሞገስ፣ ሕዝብን ያለ ተጽዕኖ እንደ መምራት ነው። ሞገስ ይለመናል፤ የሚጠይቁም ከእግዚአብሔር እየተማሩና በሞገስ እየጨመሩ ይሄዳሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Nov, 03:59


የዕለቱ ቃል

"በእኔ ደስ ተሰኝተህ ከሆነ፣ አንተን ዐውቅህና ያለ ማቋረጥ በፊትህ ሞገስ አገኝ ዘንድ መንገድህን አስተምረኝ፤"

(ዘፀ 33፥13 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Nov, 07:00


መልእክተ ሰንበት

ዮሐንስ "ስለ እግዚአብሔር ቃልና ስለ ክርስቶስ ምስክርነት" በፍጥሞ ደሴት በግዞት (እስር) በነበረበት መንፈሱ እንደ አካሉ አልታሰረም፤ ነጻ ነበር። ስለዚህም የጌታውን ድምፅ በቀላሉ ለመስማት ቻለ። ለሰማው ድምፅ ምላሽ ሲሰጥም "የሰው ልጅ የሚመስለውን" አየ፤ "እግሮቹ በእቶን እሳት የጋለ ናስ ይመስሉ ነበር፤ ድምፁም እንደ ብዙ ወራጅ ውሃ ድምፅ ነበረ" (ራእ 1፥15)። ዮሐንስ ጌታን እንደ አዲስ ያህል ተዋወቀ። በምድር በቅርበት ያውቀው የነበረው ጌታ በመለኮት ክብሩ ሲገለጥ ሁለመናው ክብርንና ግርማን ተላብሶ ነበር። የድምፁም መጠን ኀይሉን ገለጠ። ይህ ድምፅ ከብዙ ውሃ በላይ ሕይወት ይሰጣል፣ ያረካል፣ የሚወስደውንም ይወስዳል። በርሱ የጸኑም በድምፁ ይታነጻሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

15 Nov, 11:02


የዕለቱ ሐሳብ

የጳውሎስ የደማስቆ ጉዞ ሁለት ዐላማ ነበረው፤ አንዱ የርሱ፣ ሌላው ደግሞ የጌታ። እርሱ ያመኑትን ለመከራ ሊያሳድድ ሲሄድ፣ ጌታ ደግሞ እርሱን ለሕይወት አሳደደው፤ በብርሃኑና በድምፁ ያዘው፤ "ከእኔ ጋር የነበሩትም ብርሃኑን አዩ፤ ነገር ግን የሚናገረኝን የእርሱን ድምፅ በትክክል አልሰሙም። እኔም፣ ‘ጌታ ሆይ፤ ምን ላድርግ?’ አልሁት" (ሐሥ 22፥9-10)። ድምፁ ለሁሉ ቢሰማም፣ ተለይቶ (መልእክት ሆኖ) የተሰማው ግን ለጳውሎስ ነው። እርሱም ለዚያ ድምፅ ምላሽ ሰጠ። ከዚያ ቅፅበት ጀምሮም ድምፁን ያለማቋረጥ ሰማ፤ ከሰማው ድምፅ የተነሣም 13 መልእክቶችን ጻፈ። እኛም የጌታን ድምፅ በመልእክቶቹ ሁልጊዜ እንሰማለን።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

15 Nov, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ከእኔ ጋር የነበሩትም ብርሃኑን አዩ፤ ነገር ግን የሚናገረኝን የእርሱን ድምፅ በትክክል አልሰሙም። እኔም፣ ‘ጌታ ሆይ፤ ምን ላድርግ?’ አልሁት።"

(ሐሥ 22፥9-10 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Nov, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ጌታ ወደ ድምፁ ይመራናል። ድምፁም በተሰማበት ስፍራ ወይም ሁኔታ ሁሉ እርሱ አለ፤ ድምፁን ሰምተው የሚከተሉትም ወደ ኀልውናው ይቀርባሉ፣ ከርሱም ጋራ ይሆናሉ፤ "በጎቼ ድምፄን ይሰማሉ፤ እኔ ዐውቃቸዋለሁ፤ እነርሱም ይከተሉኛል" (ዮሐ 10፥27)። የጌታ ድም ፅ የሚሰማ ብቻም ሳይሆን ተለይቶ የሚታወቅ ነው። በበጎቹ መካከልም ያለ ልዩነት የልም፣ ሁሉም በጎች ናቸውና፤ ጥቂት ቀጥታ ሰሚዎች፣ ብዙዎች ደግሞ ከሰሙት ሰሚዎች አይደሉም። ሁሉም ይሰማሉ። በኀብረት መካከል እርስ በርስ መደማመጥና መቀባበል ቢኖርም፣ ቀጥታ የማይሰማ በግ—ተከታይ—የለም። ለጌታ ድምፅ ጆሮ የሚሰጡ ሁሉ መንገዱ ይለያይ እንጂ ድምፁን ይሰማሉ፤ አጥርተው እንዲሰሙም ይታገዛሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Nov, 04:30


የዕለቱ ቃል

"በጎቼ ድምፄን ይሰማሉ፤ እኔ ዐውቃቸዋለሁ፤ እነርሱም ይከተሉኛል፤"

(ዮሐ 10፥27 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

13 Nov, 11:29


የዕለቱ ሐሳብ

ድምፅ ርግብግቢት ወይም ንዝረት ብቻ ሳይሆን ቃልም አለው። የእግዚአብሔር ድምፅ እንዲህ ባለው ሁኔታ ተሰምቷል፤ "ድምፅም፣ 'ጩኽ' አለኝ፤ እኔም፣ 'ምን ብዬ ልጩኽ?' አልሁ። 'ሰው ሁሉ እንደ ሣር ነው፤ ክብሩም ሁሉ እንደ ሜዳ አበባ ነው'" (ኢሳ 40፥6)። ይህ ድምፅ ከብዙ የተሻሉ ከሚመስሉ ድምፆች በላይ መሰማት አለበት። ሰው የሁልጊዜ እንደ ሆነ (እንዳለ የሚኖር)፣ ክብሩም ባለበት እንደሚቀጥል ካሰበ፣ ይህን ድምፅ አልሰማም ወይም አላገናዘበም። የአፍታ እንደ ሆነ፣ የያዘውን ለቅቆ እንደሚሄድ ከተረዳ ግን፣ የዘላለሙን ያስባል፣ ያከብራልም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

13 Nov, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ድምፅም፣ 'ጩኽ' አለኝ፤ እኔም፣ 'ምን ብዬ ልጩኽ?' አልሁ። 'ሰው ሁሉ እንደ ሣር ነው፤ ክብሩም ሁሉ እንደ ሜዳ አበባ ነው።'"

(ኢሳ 40፥6 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

12 Nov, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

የእግዚአብሔር ድምፅ መልእክት አለው፤ ሐሳብ አለው፤ በዚህ ብቻ የሚወሰንም አይደለም። በድምፁ ውስጥ አቅም አለ፤ ኅይል አለ። ዘማሪው እንዲህ ያለው በዚህ ምክንያት ነው፤ "የእግዚአብሔር ድምፅ የእሳት ነበልባል ይረጫል" (29፥7)። ዓለማትን የፈጠረበት ቃሉ፣ "ይሁን" ሲል ድምፅ ሆኖ ተሰምቷል። የድምፁ ኅይልም እጅግ ብርቱ ነው፤ የሌለውን ወደ መኖር ያመጣል፤ ያለውንም እንዳልነበረ ያደርጋል። የድምፁ እሳትም የእርሱ ለሆኑት 'ዕቃዎች' መሠሪያና መጠቀሚያ ሲሆን፣ የእርሱ ጠላት ለሆኑ ደግሞ—መናፍስትም ሆኑ ሰዎች—መጥፊያ ነው። የድምፁ እሳት እያቃጠለ የሚያስወግድ፣ እያጠራም የሚሠራ ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

12 Nov, 04:00


የዕለቱ ቃል

"የእግዚአብሔር ድምፅ የእሳት ነበልባል ይረጫል።"

(መዝ 29፥7 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

11 Nov, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ድምፅ መግባቢያ ነው፤ ተግባቦት ነው፤ መልእክት ለመቀበልና ለማስተላለፍ እንጠቀምበታለን። ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ እንስሳትም ድምፅ እየተለዋወጡ ይግባባሉ። የእግዚአብሔር ድምፅ የእግዚአብሔርን ተግባቦታዊ ማንነት—ዝምድናዊ ባሕርይ—ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔርን ማንነት ይወክላል። እርሱም አውራ ፍጥረቱ ለሆኑት ሰዎች ድምፁን ያሰማል፤ በመዝሙር 29 ስለ እግዚአብሔር ድምፅ ተዘርዝሯል፤ ቍ. 4ም እንዲህ ይላል፦ "የእግዚአብሔር ድምፅ ኀያል ነው፤ የእግዚአብሔር ድምፅ ግርማዊ ነው።" ድምፁ ሐሳብ ያለበት፣ እውነት ያለበት፣ የሚሰሙትም እንዲረዱት ሆኖ የሚቀርብ ነው። የሚናገረው ኅያል እንደ ሆነ፣ ድምፁ ኅያል ነው፤ የሚናገረው ባለ ግርማ እንደ ሆነም፣ ድምፁ ባለ ግርማ ነው። ድምፁን የሚሰሙና የሚናፍቁም በኅይሉ እየታገዙ፣ በግርማው ደግሞ እየተደነቁ ይኖራሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

11 Nov, 04:01


የዕለቱ ቃል

"የእግዚአብሔር ድምፅ ኀያል ነው፤ የእግዚአብሔር ድምፅ ግርማዊ ነው።"

(መዝ 29፥4 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

10 Nov, 07:02


መልእክተ ሰንበት

ጸጋው ድነት ለሚያስፈልጋቸው ሁሉ የተገለጠ፣ የተሰጠም ነው። ይህ ጸጋ ነጻ ስጦታ ነው፤ የሚያድን ነው፤ አቅም ነው፤ አስቻይ ነው፤ ስንቅ ነው፤ ድጋፍ ነው፤ ዕድገት ነው፤ ጥበብ ነው፤ ልምላሜም ነው፤ ጳውሎስ የቲቶ መልእክት ላይ እንዲህ ብሎለታል፤ "ድነት የሚገኝበት የእግዚአብሔር ጸጋ ለሰዎች ሁሉ ተገልጧልና፤ ይህም ጸጋ በኀጢአት መኖርንና ዓለማዊ ምኞትን ክደን፣ በአሁኑ ዘመን ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ፣ በእውነተኛ መንፈሳዊ ሕይወት እንድንኖር ያስተምረናል" (2፥11-12)። ጸጋው የማይጠቅመውንና በመጨረሻም ገዳይ የሆነውን እያስካደ ለእውነተኛ መንፈሳዊ ሕይወት የሚያበቃ ነው። ጸጋውን እየተቀበሉ በጸጋው የተማሩም ለዓለም የከበዱ፣ ለእግዚአብሔር ግን የቀለሉ—የተመቹ—ናቸው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

08 Nov, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ስለትም ሆነ ቃታ ካቆሰለው በላይ ቃል ያቆሰለው ይበልጣል። ንግግር—የሐሳብና ስሜት ልውውጥ—የኀልውና መገለጫ፣ አብሮ የመኖር ምክንያትና ማስቀጠያ ነው፤ ነገር ግን በጥበብና በጥንቃቄ ካልተያዘ አብሮነትንም ሆነ ኀብረትን ይጎዳል፤ የተገነባን ግንኙነት ሊያፈርስም ይችላል። ለዚህ ነው ጳውሎስ ያሳሰበው፤ "ለእያንዳንዱ ሰው እንዴት መልስ መስጠት እንደሚገባችሁ ታውቁ ዘንድ ንግግራችሁ በጨው እንደ ተቀመመ ሁልጊዜ በጸጋ የተሞላ ይሁን" (ቈላ 4፥6)። ጸጋ ለቃልም ያስፈልጋል ማለት ነው፤ ጸጋ ያለበት ቃልም ጠጋኝ እንጂ ጎጂ አይደለም። ለእውነተኛ ሕይወትን ጸጋን የምንፈልገውን ያህል ለቃላችንም ልንፈልገው ይገባል። ንግግራቸው ልስልስ የሆኑ ሰዎች እንኳን፣ ቃላቸውን በጸጋ ሲያደርጉት ቃላቻው የማይረብሽ ብቻ ሳይሆን የሚያንጽም ይሆናል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

08 Nov, 03:59


የዕለቱ ቃል

"ለእያንዳንዱ ሰው እንዴት መልስ መስጠት እንደሚገባችሁ ታውቁ ዘንድ ንግግራችሁ በጨው እንደ ተቀመመ ሁልጊዜ በጸጋ የተሞላ ይሁን።"

(ቆላ 4፥6 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

07 Nov, 10:59


የዕለቱ ሐሳብ

ጸጋው ምሕረት አስገኝቶልናል፣ ይቅርታ አሰጥቶናልም። ይህን ይቅርታ የተቀበልነውም "በደሙ በተደረገ ቤዛነት" ነው። ጸጋው ይህንን አስችሏል። ይህ ጸጋም የሚበዛ ነው፤ "ጸጋውንም በጥበብና በማስተዋል ሁሉ አበዛልን" (ኤፌ 1፥8)። ጥበብም "ጥበባችን" ከሆነው ከጌታ ይቀዳል፤ የማስተዋል ምንጭም የእግዚአብሔር መንፈስ ነው። ጸጋውን ከጸጋ አምላክ ከእግዚአብሔር ጋራ ኅብረታችንን በማጽናት እናበዛለን። እንግዲህ፣ ጸጋው ነጻና የተትረፈረፈ ስለሆነ፣ ተቀብለን ብቻችንን የምንቀጥልበት አይደለም፤ ከጸጋው ምንጭ ጋራ በመሆን የምናበዛው እንጂ!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

07 Nov, 03:59


የዕለቱ ቃል

"ጸጋውንም በጥበብና በማስተዋል ሁሉ አበዛልን።"

(ኤፌ 1፥8 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

06 Nov, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ጸጋ በቂ ነው፤ የሚያግዝ እንጂ የሚታገዝም አይደለም። ከጸጋ ባሻገር ጌታን የምንጠይቃቸው ነገሮችም ጭማሪዎች እንጂ ተኪዎች አይደሉም፣ ጸጋ አይተካምና። ጳውሎስ የሰይጣን መውጊያ ከርሱ እንዲለይ "ጌታን ሦስት ጊዜ" ለመነ፤ "እርሱ ግን፣ 'ጸጋዬ ይበቃሃል፤ ኀይሌ ፍጹም የሚሆነው በድካም ጊዜ ነውና' አለኝ" (2ቆሮ 12፥9)። ጌታ በጸጋው ይተማመናል፣ የጳውሎስንም ሩጫ በደንብ እንደሚያስጨርሰው ያውቃል። ይህ ጸጋ ከየትኛውም ዐይነት ፈተናና መከራ በላይ የሚያራምድ፣ ለእግዚአብሔር ክብርም መኖር የሚያስችል ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

06 Nov, 04:01


የዕለቱ ቃል

"እርሱ ግን፣ 'ጸጋዬ ይበቃሃል፤ ኀይሌ ፍጹም የሚሆነው በድካም ጊዜ ነውና' አለኝ።"

(2ቆሮ 12፥9 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

05 Nov, 11:01


ጸጋን በክርስቶስ የሆኑ ሁሉ ይቀበላሉ፤ ያለ ልዩነት ይሰጣልና። ጳውሎስ የቆሮንቶስ አማኞችን የሚነቅፍባቸው ብዙ ነገር ቢኖርም፣ በጌታ ለሆኑትና ላገኙት ሁሉ ግን እውቅና ይሰጣል፤ "በክርስቶስ ኢየሱስ ስለ ተሰጣችሁ ጸጋ ዘወትር ስለ እናንተ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ" (1፥4)። ይህ ጸጋ ማንነት ላይ የሚመሠረት ስላልሆነ የሰዎችን መንፈሳዊነት አይለካም። ተቀባዮቹ ሲጠቀሙበት ግን ጸጋው መንፈሳዊ እንዲሆኑ ያስችላቸዋል። የጸጋ መብዛት ደግሞ ተቀባዮቹ እንዲታረሙ፣ እንዲያድጉና እንዲጸኑ ስለሚያደርግ እግዚአብሔርን ያስከብራል። ይህ ጸጋም በክርስቶስ የተሰጠ ብቻ ሳይሆን፣ በክርስቶስም የሚጠበቅ ነው። እግዚአብሔር ስለማይቋረጥ ስጦታው—ጸጋ—ሁልጊዜ ሊመሰገን ይገባል!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

05 Nov, 04:01


የዕለቱ ቃል

"በክርስቶስ ኢየሱስ ስለ ተሰጣችሁ ጸጋ ዘወትር ስለ እናንተ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ።"

(1ቆሮ 1፥4 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

04 Nov, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ጸጋ አቅም ነው፤ እውነት የሆነውንና የከበረውን ለመረዳት፣ ለመቀበልና ለመፈጸም ይረዳል። ሐዋርያው ጳውሎስ መልእክቱን ሁሉ—13ቱንም—በጸጋ ጀመሮ በጸጋ ይጠቀልላል። ጥልቅ ነገረ መለኮት የገለጸበትና የተነተነበትም የሮሜ መልእክት ይህንኑ የተከተለ ነው፤ "ከአባታችን ከእግዚአብሔር፣ ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን" (1፥7)። ነጻ ስጦታ፣ መንፈሳዊነትን አስረጂና የዕለት ተለት ኑሮን አስቻይ የሆነው ጸጋ እጅግ አስፈላጊ ስለሆነ ከአባትና ከልጅ በመንፈስ ቅዱስ የተሰጠ ነው። ጸጋው ትምህርቶችን በተጻፈባቸው መንፈስ ለመረዳትና ከራስ ጋራ ለማዋኅድ፣ እንዲሁም በሕይወት ለማሳየትና ለሌሎች ለማካፈል ዐይነተኛ ነው። "ጸጋና ሰላም"ን ከምንጫቸው፣ ያም ከመለኮት፣ የተቀበሉም የተባረኩና ባለ ብዙ ፍሬ ናቸው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

04 Nov, 04:00


የዕለቱ ቃል

"...ከአባታችን ከእግዚአብሔር፣ ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን።"

(ሮሜ 1፥7 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

03 Nov, 07:01


መልእክተ ሰንበት

ሰማያትና ምድር ተለዋጭ ናቸው። የእግዚአብሔር የክብሩ መገለጫዎች እንጂ የኅልውናው ተሸካሚዎች ስላሆኑ ይቀየራሉ። በመጨረሻውም ፍርድ ይህ እንደሚሆን በራእይ መጽሐፍ ተጽፋል፤ "ከዚህ በኋላ ታላቅ ነጭ ዙፋንና በእርሱም ላይ የተቀመጠውን አየሁ። ምድርና ሰማይ ከፊቱ ሸሹ፤ ስፍራም አልተገኘላቸውም" ( 20፥11)። ዘላለማዊው ጌታ በመታየት ሲቀጥል—"አየሁ"—የጊዜ ወሰን የተበጀላቸው ግን ስፍራ ይለቃሉ። በዙፋን ላይ የተቀመጠውም ሁሉን (ሰማያትን ጨምሮ) እያሳለፍ እርሱ ጸንቶ ይኖራል፤ ይገዛልም። እጅግ ግዙፍና ከአእምሮ በላይ የሆኑትን አካላት "ስፍራ" እንዳይኖራቸው አድርጎ ማስወገድ እንዴት ዐይነት ታላቅነት ነው!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

01 Nov, 11:02


የዕለቱ ሐሳብ

የእግዚአብሔር ዙፋን በሰማይ ነው። በምድር ላለነውም ሰማያትን የፈጠረበት ቃሉ ነግሮናል። ወደ አባቱ እንዴት መጸለይ እንዳለብን ያስተማረን ጌታ ኢየሱስ እንዲህ ብላችሁ ጸሎታችሁን ክፈቱ አለ፤ "በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፤ ስምህ ይቀደስ፤" (ማቴ 6፥9)። አባታችን በሰማያት ይኖራል፤ ይህ ምጥቀቱን፣ ክብሩንና አባትነቱንም በአንድ የገለጠ ነው። ይህ ጸሎት ከምንኖርበት—ጥያቄዎቻችን ካሉበት—አንጻር ሳይሆን የሚጸለየው አምላካችን ከሚገኝበት ነው። በመካከላችንና በአንደበታችን የሚጠራውን ስሙን ቀድሰን (አክብረን) የምንቀጥለውም ጸሎት ነው። የእግዚአብሔር ስም እግዚአብሔርን ኅልውና ሙሉ ለሙሉ ስለሚወክል፣ በምድር የምንጠራው ቢሆንም በሰማያዊ ክብሩ ሊታሰብና ሊሞገስ ይገባል። ስሙን የሚያከብሩም "በሰማይ ያለችውን" ፈቃዱን በምድር ለመቀበልና ለመፈጸም የተዘጋጁ ናቸው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

01 Nov, 04:00


የዕለቱ ቃል

"...በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፤ ስምህ ይቀደስ፤"

(ማቴ 6፥9 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

31 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ሰዎች ምንም ይህል ዐይናቸውን ወደ ሰማይ ቢያነሱ ከእግዚአብሔር ሥራ መመልከት የሚችሉት ትንሹን ብቻ ነው። (በቴክኖሎጂ—ቴሌስኮፕ—ቢታገዙም እንኳን የተሻለ፣ ሁሉንም ማየት አይታሰብም፤ ከዋክብት ብቻ ሴክስቲሊየን፣ 10*22፣ እንደሆኑ ይገመታልና።) የተገለጠልንን ያህል እንኳን በአስተውሎት ብንመለከት ግን የሠራቸውን—እግዚአብሔርን—ለማመን፣ ለመታመንም ይበቃናል፤ "ዐይናችሁን አንሡ፤ ወደ ሰማይ ተመልከቱ፤ እነዚህን ሁሉ የፈጠረ ማን ነው? የከዋክብትን ሰራዊት አንድ በአንድ የሚያወጣቸው፣ በየስማቸው የሚጠራቸው እርሱ ነው። ከኀይሉ ታላቅነትና ከችሎታው ብርታት የተነሣ፣ አንዳቸውም አይጠፉም" (ኢሳ 40፥26)። "በየስማቸው የሚጠራቸው?" አዎ፣ ያንን ሁሉ በስም ያውቀዋል። የእርሱ አቅም በሰማይ ብቻ የተወሰነም አይደለም፤ በምድር ያለውን ሁሉም እንዲሁ የቆጠረ ነው፤ ጠጕር ሳይቀር። በርግጥም፣ የእግዚአብሔር ኅይል እጅግ ታላቅ፣ ችሎታውም ማለቂያ የለውም!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

31 Oct, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ዐይናችሁን አንሡ፤ ወደ ሰማይ ተመልከቱ፤ እነዚህን ሁሉ የፈጠረ ማን ነው?የከዋክብትን ሰራዊት አንድ በአንድ የሚያወጣቸው፣በየስማቸው የሚጠራቸው እርሱ ነው። ከኀይሉ ታላቅነትና ከችሎታው ብርታት የተነሣ፣አንዳቸውም አይጠፉም።"

(ኢሳ 40፥26 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

30 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

'አምላክ የለም' የሚለው ባዶ ሙግት የመለኮትን ኀልውና የሚክዱ ሰዎችን ይገልጣል። የእግዚአብሔርን ኀልውና የሚያምኑ ደግሞ፣ 'የማይገኘው የት ይሆን?' ብለው ሊጠይቁ ይችላሉ። ዘማሪው እንዲህ አለ፤ "ወደ ሰማይ ብወጣ፣ አንተ በዚያ አለህ፤ መኝታዬንም በሲኦል ባደርግ በዚያ ትገኛለህ" (መዝ 139፥8)። እርሱ የሠራውን መሙላትና መቅደም እንደማይችለው ሰው አይደለም። (የሰዎች ልጆች በሠሩት ይበለጣሉ፣ የሠሩትንም ጥለው ይሄዳሉ፤) እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን የሞላ፣ ጊዜንና ቦታን ሁሉ የሚያልፍ፣ መላ ፍጥረቱንም ሁልጊዜ በሥሩ ያደረገ አምላክ ነው። በተገኘበት ሁሉም ለሚጠሩት፣ 'አለሁ!' ይላል፤ ለሚፈልጉትም የቅርብ ወዳጅና የዘወትር አጋር ይሆናል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

30 Oct, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ወደ ሰማይ ብወጣ፣ አንተ በዚያ አለህ፤ መኝታዬንም በሲኦል ባደርግ በዚያ ትገኛለህ።"

(መዝ 139፥8 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

29 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ሰው ለመኖር ወይም ኑሮን ለማቅለል ይሠራል፤ ይፈጥራል፤ በፈጠራ ውጤቱም ሕይወትን ያስተካክላል። እግዚአብሔር ግን ፍጥረትን ለኅልውናው አይጠቀምም፤ የፈጠረው ሁሉ ግን ለክብሩ ነው። ሰሎሞን ትልቁን ቤተ መቅደስ ሠርቶ ከጨረሰ በኋላ በጸለየው ጸሎት ለእግዚአብሔር ታላቅነትና ምጡቅነት ዕውቅና ሰጥቷል፤ "ነገር ግን ሰማይና ከሰማያት በላይ ያለው ሰማይ እንኳ እርሱን ይይዘው ዘንድ አይችልምና ቤተ መቅደስ ሊሠራለት የሚችል ማነው?" (2ዜና 4፥6)። ሰማያት በእግዚአብሔር ተሠርተዋል፤ ለትልቅነታቸውም ቃሉ ይመሰክራል፤ የሰው ልጆችም በጥበባቸውና ግኝታቸው ያንኑ ቀስ በቀስ እየመሰከሩ ነው። እርሱን እንኳን ምድርና ሰማይም ሊያስተናግደው አይችልም፤ በምድር የሚሠሩ ቤተ አምልኮዎችማ እንዴት! እግዚአብሔር ለመቍጠርና ለመድረስ ከሚቻለው ፍጥረቱ በላይና ቀዳሚ፣ ከፍ ያለና ታላቅ ነው። ሰማያት—አጽናፈ ዓለሙ—ካልተደረሰባቸው እርሱማ እንዴት እንዴት ይሆን!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

29 Oct, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ነገር ግን ሰማይና ከሰማያት በላይ ያለው ሰማይ እንኳ እርሱን ይይዘው ዘንድ አይችልምና ቤተ መቅደስ ሊሠራለት የሚችል ማነው?"

(2ዜና 4፥6 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

25 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

የቀደመው ኪዳን (ሕጉ) በመንፈስ የተሰጠ ቢሆንም፣ በመንፈስ አቅም ላይ የተመሠረተ አልነበረም። የኪዳኑ ሕግ ዐላማ እግዚአብሔር ከሕዝቡ የሚጠብቀውንና ሕዝቡ ማድረግ ያቃተውን ማሳየት፣ ይህንንም ተረድቶ ራሱን በጌታ ፊት እንዲያዋርድና አቅም እንዲጠይቅ ማስቻል ነው። በዚህም ወደ አዲሱ ኪዳን አሸጋገረ። ይህ ኪዳንም በጸጋ ላይ የተመሠረተና በክርስቶሰ ሙሉ መሥዋዕት የተመረቀ ነው፤ "እርሱም በፊደል ላይ ሳይሆን በመንፈስ ላይ የተመሠረተውን የአዲሱ ኪዳን አገልጋዮች እንድንሆን ብቁዎች አደረገን፤ ምክንያቱም ፊደል ይገድላል፤ መንፈስ ግን ሕይወትን ይሰጣል" (2ቆሮ 3፥6)። እርሱም በፊደል የተሰጠውን ሕግ ፈጽሞልን፣ በመንፈሱ በኩል ሕይወትን እንድንቀበል አደረገን። በሕጉ መሞት የነበረብንን በሞቱ ነጻ ስላወጣን፣ እንዲሁም የጸጋው ጉልበት ከሕግ በላይ ስላደረገን፣ ሕይወትን የምንካፈል ብቻ ሳይሆን እርሱንም የምናገለግል አደረገን።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

25 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"እርሱም በፊደል ላይ ሳይሆን በመንፈስ ላይ የተመሠረተውን የአዲሱ ኪዳን አገልጋዮች እንድንሆን ብቁዎች አደረገን፤ ምክንያቱም ፊደል ይገድላል፤ መንፈስ ግን ሕይወትን ይሰጣል።"

(2ቆሮ 3፥6 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

24 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

በደም የታሰረ ኪዳን ጽኑ ነው። ቀድሞ እነ አብርሃም በተጠየቅ መሥዋዕት በደም ከአምላካቸው ጋራ በኪዳን ጀምረው፣ በኪዳን ተጕዘዋል። የቀደመው ኪዳንም ለኋለኛውና ለፍጹሙ ቦታ ለቀቀ፤ ሁለተኛው ኪዳንም ከአብርሃም ዘር ሰው ሆኖ በተወለደው አምላክ ጸና፤ "ስለ ብዙዎች የኀጢአት ይቅርታ የሚፈስስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው" (ማቴ 26፥28)። ይህ ደም ከአካል የወጣ፣ ሞትን ያስከተለ፣ ንጹሕ፣ ለኅጢአት ፍጹም መሥዋዕት የሆነና ሁለመናን—ሕሊናን ጨምሮ—የሚያነጻ ደም ነው። የቀደመው ኪድን የእንስሳትን ደም፣ ዘወትር የሚታረዱ እንስሳትንም ይፈልግ ነበር። አዲሱ ኪዳን ግን አንድ ጊዜ ብቻ በፈሰሰ ደም ተመሠረተ። ይህ ደም ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው የሆነው የኢየሱስ ደም ስለሆነ ተበዳዩን ያረካ፣ በዳዩንም ንጹሕና ብቁ ያደረገ ደም ነው። ጌታም ስለ "ኅጢአት ይቅርታ" የሚፈሰውን ደም ካሳወቀ በኋላ በሥቃዩና በሞቱ አፈሰሰው። ያንኑ ደምም ይዞ በሰማይ ወዳለችው "ወደ ቅድስት" ገባ። ይህም ኪዳኑን የዘመን ሁሉ፣ የትውልድ ሁሉ፣ የሕዝቦችም ሁሉ አደረገው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

24 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ስለ ብዙዎች የኀጢአት ይቅርታ የሚፈስስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው።"

(ማቴ 26፥28 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

23 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋራ ኪዳን ይገባል፤ ሕዝቡን ይጣራል፣ ደግሞም ይሰበስባል፤ "በመሥዋዕት ከእኔ ጋር ኪዳን የገቡትን፣ ቅዱሳኔን ወደ እኔ ሰብስቧቸው" (መዝ 50፥5)። ይህ የአሳፍ መዝሙር እግዚአብሔር ስላቀረበው መሥዋዕት ሕዝቡን እንዳልነቀፈም ይናገራል (ቍ. 8)። የእግዚአብሔር ጥያቄ—ግዴታ—ደግሞ ጨርሶ ከባድ አይደለም፤ እየጠየቀ የሚረዳ፣ እየረዳም የማይተው አምላክ ነውና። ጌታ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ኪዳኑን እንዳጸና ሁሉ፣ ሕዝቡ "ሕያው መሥዋዕት" አድርጎ ራሱን እንዲያቀርብም ተጠይቋል (ሮሜ 12፥1)። ለቀደመው ኪዳን ታማኝነቱን ያላጓደለ አምላክ፣ ለአዲሱና ራሱን ላቀረበበት እንዴት ድንቅ ይሆን!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

23 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"በመሥዋዕት ከእኔ ጋር ኪዳን የገቡትን፣ ቅዱሳኔን ወደ እኔ ሰብስቧቸው።"

(መዝ 50፥5 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

22 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

እግዚአብሔር ሕዝቡን ከግብጽ ምድር ካወጣ በኋላ በምድረ በዳ ኪዳኑን በቃሉ አጸናላቸው—በዐሥርቱ ትእዛዛት። ይህን ተቀብሎ ለሕዝቡ ያደረሰው ሙሴ ነበር፤ "ሙሴ እህል ሳይበላ፣ ውሃም ሳይጠጣ ከእግዚአብሔር ጋር አርባ ቀንና አርባ ሌሊት በዚያ ነበር፤ በጽላቶቹ ላይ የቃል ኪዳኑን ቃሎች፣ ዐሥርቱ ትእዛዛትን ጻፈ" (ዘፀ 34፥28)። እግዚአብሔር ለአብርሃም እንደ ገባው ኪዳን ሕዝቡን በታላቅ ክንድ ካስወጣ በኋላ፣ ለኪዳኑ ፍጻሜ የሚጠበቅባቸውን በሕጉ በኩል ገለጠላቸው። ጌታ ኢየሱስ እንዳረጋገጠልንም፣ እነዚህ ትእዛዛት እግዚአብሔርንና ባልነጀራን በመውደድ የሚፈጸሙ ናቸው—ማቴ 22፥40። በ 40 ቀን ቆይታ ይዞ የወረደው ኪዳን፣ በቆይታ—በሕይወት ዘመን—የሚጸና ነው። እግዚአብሔር ፍጹምና የማይለወጥ ስለሆነ ኪዳኑን አያፈርስም፤ በኪዳኑ በመጽናት በርሱ የሚታገዙም እንዲሁ በፍቅር ኪዳኑ ውስጥ ይጸናሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

22 Oct, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ሙሴ እህል ሳይበላ፣ ውሃም ሳይጠጣ ከእግዚአብሔር ጋር አርባ ቀንና አርባ ሌሊት በዚያ ነበር፤ በጽላቶቹ ላይ የቃል ኪዳኑን ቃሎች፣ ዐሥርቱ ትእዛዛትን ጻፈ።"

(ዘፀ 34፥28 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

21 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ኪዳን የኀብረት ውል፣ የአንድነት ማኀተምም ነው። በመጽሐፍ የኪዳን ጀማሪ እግዚአብሔር እንደ ሆነ ተገልጧል። ውሃ ዓለምን ካጠፋ በኋላ እግዚአብሔር ታዞ በመርከብ ትውልድን ላስቀረው ኖህ እንዲህ አለው፤ "በእኔና በእናንተ መካከል፣ ከእናንተም ጋር ካሉ ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ጋር፣ ከሚመጣውም ትውልድ ሁሉ ጋር የማደርገው የኪዳኑ ምልክት ይህ ነው፤ ቀስተ ደመናዬን በደመና ላይ አደርጋለሁ፤ ይህም በእኔና በምድር መካከል ለገባሁት ኪዳን ምልክት ይሆናል" (ዘፍ 9፥12-13)። ይህ ምልክት አሁን በምድር እንደ ተጠለፈና ለሌላ ጥፋት እንደዋለ አይደለም፤ በደመና መካከል አሁንም ጻድቁንና መሓሪውን አምላክ ይገልጣል። ጌታ ለኪዳኑ ቁርጠኛ ስለሆነ ምልክቱን አልሻረም። ተለዋዋጭ ያልሆነ አምላክ ሁልጊዜ ታማኝ ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

21 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔርም እንዲህ አለ፤ 'በእኔና በእናንተ መካከል፣ ከእናንተም ጋር ካሉ ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ጋር፣ ከሚመጣውም ትውልድ ሁሉ ጋር የማደርገው የኪዳኑ ምልክት ይህ ነው፤ ቀስተ ደመናዬን በደመና ላይ አደርጋለሁ፤ ይህም በእኔና በምድር መካከል ለገባሁት ኪዳን ምልክት ይሆናል።'"

(ዘፍ 9፥12-13 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

20 Oct, 07:00


መልእክተ ሰንበት

የሰው ጸሎትና የእግዚአብሔር ፈቃድ ሲስማሙ ውጤቱ ትልቅ የሆናል፤ "በእግዚአብሔር ፊት ለመቅረብ ያለን ድፍረት ይህ ነው፤ ማንኛውንም ነገር እንደ ፈቃዱ ብንለምን እርሱ ይሰማናል። የምንለምነውን ሁሉ እንደሚሰማን ካወቅን፣ የለመንነውንም ነገር እንደ ተቀበልን እናውቃለን" (1ዮሐ 5፥14-15)። ፈቃዱን ለማወቅ እርሱን ማወቅ ያስፈልጋል፤ እርሱም በቃሉ ይታወቃል። ፈቃዱ ያረፈበት ቃሉም ለምንቀርብበትና ለምንጠይቅበት እምነት መሠረት ነው። የእግዚአብሔር ፈቃድና ማመን የጸሎት መሠረታውያን ከሆኑ፣ ጸሎት በቃሉ ይሠራል፤ ያድጋል፤ ቀላል መንፈሳዊ ተግባርም ይሆናል። በቃሉ ውስጥ የተጠቀሱት ከ600 በላይ ጸሎቶችም ብዙ ትምህርት ይሆናሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

"አትጨነቁ" የሚለው ቃል ለተናጋሪ የሚቀለውን ያህል ለሰሚ ቀላል አይደለም። ያለንበት ጊዜ፣ ሁኔታውና ዙሪያ ገባው ሁሉ አሳሳቢ ነው፤ አስጨናቂም ጭምር። ይሁንና ግን ከእግዚአብሔር ትከሻ የሚተልቅ፣ ከእጁም የሚርቅ ምንም ነገር የለም። ቃሉም እንዲህ ይለናል፤ "በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ፣ ከምስጋናም ጋር ልመናችሁን በእግዚአብሔር ፊት አቅርቡ እንጂ ስለ ማንኛውም ነገር አትጨነቁ" (ፊል 4፥6)። የእግዚአብሔር ፊት ጸሎት የተከፈተበት ቦታ ሁሉ ይገኛል። እርሱ ይሰማን ዘንድ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ቀርቦናል፤ ያጽናናንና ያበረታን ዘንድ፣ ይረዳንና ያጸናንም ዘንድ ትኩረቱ ሁልጊዜ በእኛ ላይ ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ፣ ከምስጋናም ጋር ልመናችሁን በእግዚአብሔር ፊት አቅርቡ እንጂ ስለ ማንኛውም ነገር አትጨነቁ።"

(ፊል 4፥6 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ወደ እግዚአብሔር ቤት ለሚመጡ ሁሉ እግዚአብሔርን ከመስማትና ሐሳብንና ሸክምን ለርሱ ከማሰማት የበለጠ ነገር የለም፣ ቤቱ የጸሎት ቤት ነውና። ጌታ ወደ መቅደሱ በክብር በገባ ጊዜ በድምቀቱና ሆታው፣ በዝማሬውና በስግደቱ የሚገባውና የጎደለው ነገር እንዲሸፈን አልፈቀደም። ይልቁንም ለዋጮችን ገሠጸ፤ ገባታንም ገለበጠ። በጊዜው የነበሩ ሰዎች 'ስሜታዊ ሆነ' ብለው አስበው ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ድርጊቱ የእግዚአብሔር ቃል ላይ የተመሠረተ፣ ስሜቱም "የቤትህ ቅናት ይበላኛል" እንደ ተባለ ቃሉ ላይ ያረፈ ነበር። እርሱም መቅደሱን እያጸዳ የጠቀሰው ቃሉን ነው፤ "‘ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል’ ተብሎ ተጽፏል፤ እናንተ ግን፣ የዘራፊዎች ዋሻ አደረጋችሁት አላቸው" (ማቴ 21፥13)። "የጸሎት ቤት!" ዛሬም ብዙ ስሙ የሚጠራባቸው 'ቤቶች' አሉ። ስንቶቹ ግን ትኩረታቸው ራሱ እግዚአብሔር፣ ፍለጋቸውም (በጸሎት) እርሱ ይሆን? ሕዝቡን መስማት የሚወድድ፣ ለሕዝቡም የሚጠነቀቅና የሚመልስ አምላክ ይህ እንዲስተጓጎል ወይም እንዲሸፈን አይፈልግም። እርሱን ከማነጋገር፣ እርሱንም ከመስማት በላይ ሰዎች እርስ በርሳቸው የሚነጋገሩበት የትኛውም ሃይማኖታዊ መሰብሰብ ዋነኛ ነገር አጉድሏል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Oct, 04:01


የዕለቱ ቃል

"‘ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል’ ተብሎ ተጽፏል፤ እናንተ ግን፣ የዘራፊዎች ዋሻ አደረጋችሁት አላቸው።"

(ማቴ 21፥13 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

16 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ዮናስ ለመታዘዝም ሆነ ወደ አምላኩ ለመጮኽ ወደ ምድር መጨረሻ መውረድ ነበረበት። በዓሣው ከተዋጠ በኋላ የአምላኩን ሉዓላዊነት፣ የፈቃዱንም ጉልበት ተረዳ። ቢርቅም እንኳን ልመናን አቀረበ፤ “ነፍሴ በዛለች ጊዜ፣ እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተን ዐሰብሁ፤ ጸሎቴም ወደ አንተ፣ ወደ ቅዱስ መቅደስህ ዐረገች" (2፥7)። ሰው እንጂ እግዚአብሔር አይርቅም፤ ከየትም ሆኖ ይሰማል። ነፍስ "በዛለች ጊዜ" ፍቱን መድኀኒቷም ጸሎት ነው። ደጋፊዋም ሩቅ አይደለም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

16 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

“ነፍሴ በዛለች ጊዜ፣ እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተን ዐሰብሁ፤ ጸሎቴም ወደ አንተ፣ ወደ ቅዱስ መቅደስህ ዐረገች።"

(ዮና 2፥7 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

15 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ጸሎት አይቋረጥም። ይህ ሲባል ግን ተግዳሮት አይገጥመውም ወይም አያታግልም ማለት አይደለም። አንድን ሰው ብቻ ለማጥቃት አንድ ትልቅ አገር ሕግ አወጣ፤ ጸሎት ለ30 ቀናት ይቋረጥ ተባለ። "ዳንኤልም ዐዋጁ እንደ ወጣ ባወቀ ጊዜ ወደ ቤቱ ሄደ፤ መስኮቶቹ በኢየሩሳሌም አንጻር ተከፍተው ባሉበት በሰገነቱ ቀድሞ ያደርግ እንደ ነበረው በቀን ሦስት ጊዜ ተንበርክኮ ጸለየ፤ አምላኩንም አመሰገነ" (ዳን 6፥10)። ለርሱ ጸሎት ብቻ ሳይሆን ምስጋናም አይቋረጥም። በገሃድ (በግልጽ) አምላኩን ማነጋገሩን ቀጠለ። እግዚአብሔር ከአዋጁ፣ ከዛቻውና ከአንበሳው በላይ እንደ ሆነ ለማመን አልተቸገረም። ስለዚህም የዘወትር መንፈሳዊ ተግባሩን ቀጠለ። የሚያምነውንና የሚወደውን አምላክ ሳያነጋግርስ እንዴተ ቀናት የቆጠራሉ!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

15 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ዳንኤልም ዐዋጁ እንደ ወጣ ባወቀ ጊዜ ወደ ቤቱ ሄደ፤ መስኮቶቹ በኢየሩሳሌም አንጻር ተከፍተው ባሉበት በሰገነቱ ቀድሞ ያደርግ እንደ ነበረው በቀን ሦስት ጊዜ ተንበርክኮ ጸለየ፤ አምላኩንም አመሰገነ።"

(ዳን 6፥10 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ሰሎሞን የመጀመሪያውንና ትልቁን ቤተ መቅደስ ሠርቶ በጨረሰ ጊዜ ጸሎት አቀረበ። ጸሎቱ ሥራ የጨረሰ ሰው ጸሎት ነው—ጸሎት ሥራ ለመጀመር ብቻ ሳይሆን ከጨረሱም በኋላ ለምረቃም ይደረጋል። የ1 ነገሥት 8ቱ ጸሎትም የምረቃ ጸሎት ነው። በቃሉ ተጽፎ ከቀረልን መካከል ረጅሙ የሆነው ይህ ጸሎት፣ አንድ ጊዜ ብቻ የሚሰማ ሳይሆን ዘወትር የሚሰማ ሆኖ የቀረበ ነበር፤ "...ይህች በእግዚአብሔር ፊት ያቀረብኋት የራሴ ልመና በቀንና በሌሊት ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር ፊት ትቅረብ" (ቍ. 59)። እግዚአብሔር በሰማይ የሚቀበላቸው እንዲህ ዐይነት ጸሎቶች ፈቃዱ ያረፈባቸው ስለሆኑ፣ በጽሞና ሲታሰቡ የሚሰሙ ናቸው። ኪዳን ያረፋባቸው ስለሆኑ ውጤታቸው ታላቅ ነው። በጸሎት መካከል ጽኑ ጸሎት ማቅረብ እግዚአብሔርን፣ ፈቃዱንና ለዘመኑ የሚሆነውን ዕቅዱንም መረዳት ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"...ይህች በእግዚአብሔር ፊት ያቀረብኋት የራሴ ልመና በቀንና በሌሊት ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር ፊት ትቅረብ።"

(1ነገ 8፥59 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

13 Oct, 07:01


መልእክተ ሰንበት

መጻሕፍት ሁሉ ስለ ጌታ ይናገራሉ። የመጨረሻው መጽሐፍ--ዮሐንስ ራእይ--ደግሞ በተለየ ትኩረት የመጨረሻውን ዘመን መጀመሪያና መጨረሻ ከሆነው ጌታ አንጻር ይተርከሰል። እርሱም በመጀመሪያው ምዕራፍ ላይም እንዲህ ተጽፏል፤ “ያለውና የነበረው፣ የሚመጣውም፣ ሁሉን ቻይ ጌታ አምላክ፣ 'አልፋና ዖሜጋ እኔ ነኝ' ይላል" (ራእ 1፥8)። ለሙሴ ራሱን ከገለጠበት ጊዜ ጀምሮ ያለና የሚኖር መሆኑ ተደጋግሞ ተገልጧል። ዘመን-አላፊ ብቻ ሳይሆንም ሁሉን ቻይ ነው። ይህ አምላካዊ ባሕርይው ትናንት፣ ዛሬ፣ ለዘላለምም አብሮት አለ። ጊዜና ለውጥ በርሱ ላይ አይነበቡም፤ እርሱ ግን ሁሉን ያነብባል፣ ይቆጣጠራልም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

11 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ጊዜና ሁኔታ የጌታ አገልጋዮች ናቸው፤ አንሰው ወይም በዝተው አስቸግረው አያውቁም። የእግዚአብሔር ጕብኝትም በነርሱ 'ሙላት' እና 'ጉድለት' አይወሰንም። መልአኩ ገብርኤል ወደ ማርያም መጥቶ፣ "የልዑል ኀይል ይጸልልሻል" ብሎ ከተናገራት በኋላ፣ ስለ ዘመዷ ኤልሳቤጥ "በስተርጅና" መጸነስ አሳሰባት። እግዚአብሔር ዮሐንስ በዕድሜ ባለጠጋዋ ኤልሳቤጥ፣ ክርስቶስ ጌታ ደግሞ በወጣቷ ማርያም እንዲጸነሱ አደረገ፤ የመጀመሪያው ታምራዊ፣ የሁለተኛው መለኮታዊ፣ "ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና" (ሉቃ 1፥37)። ይህም እውነት ዛሬም፣ ለዘላለምም ያው ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

11 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና።"

(ሉቃ 1፥37 አመት)