የትንቢት ድምፅ @voiceofprophecy Channel on Telegram

የትንቢት ድምፅ

@voiceofprophecy


እግዚአብሔር ምን አለ? እርሱ የሚናገረው እውነት ነው። ቃሉን በዚህ ገጽ ይከታተሉ። የኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል ሐዋርያት እንደሰበኩት እናቀርብላችኋለን።

የትንቢት ድምፅ (Amharic)

የትንቢት ድምፅ በተከታተሉት ድምፅዎች እና የክፉ መረጃዎች እንዲያመለክቱ የትንቢት አውታኝ ቅኔን እንዲለውጥ እና ተከታታይ መረጃዎችን በአሁኑ የትንቢት ላይ ይዘትልናል። 'የትንቢት ድምፅ' በኢትዮጵያ በመነሻ የሚገኝ የውጭ ስርጭቶችን እንዲሰራ፣ መረጃዎችን እና መዝገብዎን እንድፈልጉ እንዲሰራ እንደምንሆን አስተያየቁ። እግዚአብሔር ብቻ ወደ ብዙ ምላሽና ቅኔ መምከር ያለባቸው መረጃዎችን የሚገኝ እና እንዲህ የሚቃረኝን መረጃዎችን እንዴት እንደሚጠቀሙ እና እንደሚታይ እንነጋገራለን። ኢትዮጵያዊን ሐዋርያን እንዲሰራቸው እንጸልይ፣ በትንቢት ድምፅ።

የትንቢት ድምፅ

18 Jan, 19:42


የእግዚአብሔርን ጽድቅ ለመፈጸም ነው!

አንድ የክርስትና ተቺ፣ “‘እግዚአብሔር ፍቅር ነው፤ ሰውን ይወድዳል’ ትላላችሁ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ‘ክርስቶስ እግዚአብሔርን ኃጢአታችንን ይቅር እንዲለን ለማሳመን ሞተ’ ትላላችሁ፤ ይህ እርስ በርሱ ይጋጫል” አለ።

ወንጌልን እየጠሉ የሚሰሙት አያስተውሉትም። የቱ ጋር ነው ወንጌል፣ “ክርስቶስ እግዚአብሔርን ኃጢአታችንን ይቅር እንዲለን ለማሳመን ሞተ” የሚለው? እግዚአብሔር መሐሪ ነው፤ ይቅር ማለት ይወድዳል። እርሱን ይቅር እንዲለን ማሳመን አያስፈልግም። እንዲህ ይላል፦

“‘በውኑ ኃጢአተኛ ይሞት ዘንድ እፈቅዳለሁን?’ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ‘ከመንገዱስ ይመለስና በሕይወት ይኖር ዘንድ አይደለምን? ... ‘ስለ ምን ትሞታላችሁ? የምዋቹን ሞት አልፈቅድምና’ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ‘ስለዚህ ተመለሱና በሕይወት ኑሩ።’” (ሕዝ.18፥23፣32)

በሌላም ስፍራ፣ “አንተ ቸርና መሐሪ አምላክ ነህና በምሕረትህ ብዛት ፈጽመህ አላጠፋሃቸውም፥ አልተውሃቸውምም” ይላል (ነህ.9፥31)።

ያዳነን እግዚአብሔር ራሱ ነው፤ የድነታችን መሐንዲስ፤ ድነትን ያዘጋጀልን፥ ያሰበ፥ ያቀደና የሠራልን። መዳናችን ከእግዚአብሔር መሐሪነትና እኛን ከመውደዱ የተነሣ ነው። “... እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለ ጠጋ ስለ ሆነ፥ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን፥ በጸጋ ድናችኋልና” ይላል (ኤፌ.2፡4-5)። ዓለም በእርሱ እንዲድን አንድያ ልጁን ቤዛ አድርጎ ሰጥቷል።

ይህ ከሆነ ታዲያ፥ ይቅርታን የማይወድ ይመስል፥ እግዚአብሔርን ሰውን ይቅር እንዲል ማሳመን እንደሚያስፈልገው አድርገን ማሰብ የለብንም። ይቅር ባይነት ባሕሪው ነው።

ይልቁን ክርስቶስ እንዲሠዋ ያስፈለገው የእግዚአብሔርን ጽድቅ ለመፈጸም ነው።

እግዚአብሔር ለሰው ምሕረት ሲያደርግ በሰው ኃጢአት ላይ በሕጉ መሠረት እንዲፈርድ ግድ ነው። ያለዚያ ግን ብይኑ ሕገ-ወጥ ይሆናል፤ ከእግዚአብሔርም ጻድቅነት ጋር ይቃረናል። ዳሩ ግን ሕጉ ሊጣስ አይቻልም፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ጻድቅ ነው። ጌታ ኢየሱስም ሕግን ሊፈጽም እንጂ ሊሽር አልመጣም። “እኔ ሕግንና ነቢያትን ለመሻር የመጣሁ አይምሰላችሁ፤ ልፈጽም እንጂ ለመሻር አልመጣሁም። እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይና ምድር እስኪያልፍ ድረስ፥ ከሕግ አንዲት የውጣ ወይም አንዲት ነጥብ ከቶ አታልፍም፥ ሁሉ እስኪፈጸም ድረስ” ይላል (ማቴ.5፥17-18)።

በመሆኑም እግዚአብሔር ሕጉ በሚጠይቀው መሠረት በክርስቶስ ሥጋ በሰው ኃጢአት ላይ ፈረደ።

“... እግዚአብሔር የገዛ ልጁን በኃጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ በኃጢአትም ምክንያት ልኮ አድርጎአልና፤ እንደ መንፈስ ፈቃድ እንጂ እንደ ሥጋ ፈቃድ በማንመላለስ በእኛ የሕግ ትእዛዝ ይፈጸም ዘንድ ኃጢአትን በሥጋ ኰነነ።” (ሮሜ.8፥3-4)

“የሕግ ትእዛዝ ይፈጸም ዘንድ” የሚለው ሕጉ የሚጠይቀውን የጽድቅ ፍርድ ማለት ነው። እሱን ክርስቶስ ለኃጢአተኛው ቤዛ ሆኖ (በሐዋርያው አገላለጽ “በኃጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ” ሆኖ) በመሞት ፈጽሞታል፤ “ኃጢአትን በሥጋ ኰነነ” የሚለው።

በዚህ ምክንያት፥ ሕጉ ሳይጣስ፥ እግዚአብሔር ጻድቅነቱን ጠብቆ በክርስቶስ የሚያምነውን ከኃጢአቱ ሊያጸድቀው ችሏል። “... በፊት የተደረገውን ኃጢአት በእግዚአብሔር ችሎታ ስለ መተው ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው፥ ራሱም (እግዚአብሔር) ጻድቅ እንዲሆን በኢየሱስም የሚያምነውን እንዲያጸድቅ አሁን በዚህ ዘመን ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው” ይላል (ሮሜ.3፥25-26)። የክርስቶስ ሞት አስፈላጊነት የማይታያቸው የእግዚአብሔርን ጻድቅነት የማያውቁና ያልተረዱ ናቸው።

የትንቢት ድምፅ

12 Jan, 22:11


ቅዱሳን ነቢያት በቃል፣ በጸሎት ወይም በሌላ መንገድ ኃጢአትን ማስወገድ ቢችሉ ኖሮ፥ ለዚህ ሙሴን ወይም ኤልያስን ወይም ሌላ ነቢይ መላክ በቂ ነበር፤ ክርስቶስም ስለ እኛ ሞትን እንዲቀምስ ባላስፈለገ ነበር። የሚሠዋበት ሰዓት ደረሰ ጊዜ እጅግ ተጨንቆ “አባቴ፥ ቢቻልስ፥ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ፤ ነገር ግን አንተ እንደምትወድ ይሁን እንጂ እኔ እንደምወድ አይሁን” አለ (ማቴ.26፥39)። ነገር ግን ሰዎች እንዲድኑ እርሱ መሠዋቱ በእግዚአብሔር ዘንድ ግድ ነበር። “ለገዛ ልጁ ያልራራለት ነገር ግን ስለ ሁላችን አሳልፎ የሰጠው” ይለዋል (ሮሜ.8፥32)። ደግሞም “እግዚአብሔር በደዌ ያደቅቀው ዘንድ ፈቀደ” ይላል (ኢሳ.53፥10)።

ይህን የእግዚአብሔር ፈቃድ ለመፈጸም ብቁ የሆነ ሌላ ማንም እንደሌለ ባለራእዩ ዮሐንስ እንዲህ እያለ በምሳሌ ይናገራል፦

“ብርቱ መልአክ፣ ‘መጽሐፉን ይዘረጋ ዘንድ ማኅተሞቹንም ይፈታ ዘንድ የሚገባው ማን ነው?’ ብሎ በታላቅ ድምፅ ሲያውጅ አየሁ። በሰማይም ቢሆን በምድርም ላይ ቢሆን ከምድርም በታች ቢሆን መጽሐፉን ሊዘረጋ ወይም ሊመለከተው ማንም አልተቻለውም። መጽሐፉን ሊዘረጋ ወይም ሊመለከተው የሚገባው ማንም ስላልተገኘ እጅግ አለቀስሁ።” (ራእ.5፥2-4)

መጽሐፉ እግዚአብሔር በዘመን መጨረሻ በዓለም ሊፈጽመው ያለው ፈቃዱ ነው። ለምሳሌ፣ “ስለ እኔ በመጽሐፍ እንደተጻፈ፣ አምላክ ሆይ፤ እነሆኝ፤ ፈቃድህን ለማድረግ መጥቻለሁ” ይላል (ዕብ.10፥7)።

ያልተፈለገበት ስፍራ የለም፤ በሰማይም ሆነ በምድር ከምድርም በታች መጽሐፉን ለመክፈት ወይም ገልጦ ለመመልከት የሚችል ማን አልነበረም። “በሰማይ” ሲል ከመላእክት መካከል አልተገኘም፥ “በምድር” ሲል ከሰዎች መካከል አልተገኘም፥ “ከምድር በታች” ሲል ከሙታን መካከል አልተገኘም ማለት ነው። እንግዲህ የቀረን ስፍራ የለም።

ከዚህ ሁሉ በኋላ አንድ ሰው ተገኘ፤ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ። “ከሽማግሌዎቹ አንዱ፣ ‘አታልቅስ፤ እነሆ፥ ከይሁዳ ነገድ የሆነው አንበሳ እርሱም የዳዊት ሥር መጽሐፉን ይዘረጋ ዘንድ ሰባቱንም ማኅተም ይፈታ ዘንድ ድል ነሥቶአል’ አለኝ። በዙፋኑና በአራቱ እንስሶች መካከልም በሽማግሌዎችም መካከል እንደ ታረደ በግ ቆሞ አየሁ ...” ይላል (ራእ.5፥5-6)።

ይህን ለማድረግ የተገባው ጌታ ኢየሱስ ብቻ መሆኑ ያለ ምክንያት አይደለም። ከእርሱ በቀር ሌላ የታረደ ስለሌለ ነው። በሰማይ ያሉት “መጽሐፉን ልትወስድ፣ ማኅተሞቹንም ልትፈታ ይገባሃል፤ ምክንያቱም ታርደሃል፤ በደምህም ከነገድ ሁሉ፣ ከቋንቋ ሁሉ፣ ከወገን ሁሉ፣ ከሕዝብ ሁሉ ሰዎችን ለእግዚአብሔር ዋጅተሃል” ይሉታል (ራእ.5፥9/አ.መ.ት.)።

በመሆኑም ክርስቶስ ብቻውን በሆነበት በዚህ ጉዳይ ሌሎችን በእርሱ ፈንታ ማድረግ ትልቅ ስሕተትም ሞኝነትም ነው።

ወንጌል “የጌታን ስም የሚጠራ ሁሉ ይድናል” ነው የሚለው። ከእርሱ ሌላ የማንንም ስም በመጥራት ድነት አይገኝም። ጠርተነው እንድንድንበት ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለም፤ ከኢየሱስ ስም ጋር ሌላ ስም ፈጽሞ አልተሰበከም (ሐዋ.4፥12)። ቅዱሳን ሐዋርያት ሁሉ በአንድ ቃል ሰዎች ሁሉ በክርስቶስ እንዲያምኑ ሰበኩ እንጂ፤ “ስሜን የጠራ፣ በጸበሌ የተጠመቀ፥ ይድናል” ብሎ ራሱን የሰበከ በመካከላቸው አይገኝም። በቆሮንቶስ ቤተክርስቲያን ውስጥ አንዱ፣ “እኔ የጳውሎስ ነኝ” ሲል፣ ሌላው፣ “እኔ የአጵሎስ ነኝ” እያለ፣ ደግሞም አንዱ “እኔ የጴጥሮስ ነኝ” እያለ፣ ተከፋፍለው የነበሩትን ምዕመናን ሲነቅፋቸው፥ ሐዋርያው ጳውሎስ ራሱ “ጳውሎስ ለእናንተ ተሰቅሏልን? ወይስ በጳውሎስ ስም ተጠምቃችኋልን?” ይላቸዋል (1ቆሮ.1፥13/አ.መ.ት.)።

በተቃራኒው፥ ገድላት የባለገድሉን ስም የጠራ እንደሚድን ይናገራሉ። “ገዳምህን የተሳለመ፣ ስምህን የጠራ፣ ዝክርህን የዘከረ፣ በጸበልህ የተጠመቀ፣ የታጠበ እስከ 24 ትውልድ አድነዋለሁ” በሚልና ይህን በመሳሰሉ ቃሎች የተሞሉ ናቸው።

ጳውሎስ አስቀድሞ የቤተክርስቲያን ዋነኛ አሳዳጅና በሰማዕቱ በእስጢፋኖስ ግድያ ተባባሪ ነበር (ሐዋ.7፥58-60፤8፥3)። “እኔ ከሐዋርያት ሁሉ የማንስ ነኝ፥ የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስላሳደድሁ ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ የማይገባኝ፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር ጸጋ የሆንሁ እኔ ነኝ ...” ይላል (1ቆሮ.15፥9-10)።

ጴጥሮስም ጌታ ኢየሱስን በመከራው ሰዓት “አላውቀውም!” ብሎ በሰው ፊት ክዶት ነበር (ሉቃ.22፥54-62)። ከዚህ ሁሉ በኋላ ከቅዱሳን ጋር መቆጠራቸውና የክርስቶስ ሐዋርያት መሆናቸው በጌታ ምሕረት ነው። “... ምሕረት እንደ ተሰጠን መጠን ይህ አገልግሎት ስላለን አንታክትም” ይላል (2ቆሮ.4፥1)።

ቅዱሳን ራሳቸው በክርስቶስ የዳኑ ናቸው እንጂ አዳኞች አይደሉም ማለት ነው። በፊት ኃጢአተኞች የነበሩ አሁን ግን በክርስቶስ ምሕረትን ያገኙ ናቸው። ሐዋርያው ጳውሎስ፣ “‘ክርስቶስ ኢየሱስ ኃጢአተኞችን ለማዳን ወደ ዓለም መጣ’ የሚለው ቃል እውነተኛና ሰው ሁሉ ሊቀበለው የሚገባ ነው፤ ከኃጢአተኞችም ዋና እኔ ነኝ። ነገር ግን ክርስቶስ ኢየሱስ በእርሱ ለሚያምኑና የዘላለምን ሕይወት ለሚቀበሉ ወሰን የሌለው ትዕግሥቱን ከኃጢአተኞች ዋና በሆንሁት በእኔ እንደ ምሳሌ አድርጎ ያሳይ ዘንድ ምሕረትን አገኘሁ” ይላል (1ጢሞ.1፥15-16/አ.መ.ት.)።

እነርሱ በክርስቶስ በማመን ያገኙትን ምሕረት አንተም እንድታገኝ ክርስቶስን ይሰብኩልሃል እንጂ ራሳቸውን አይሰብኩልህም። “ክርስቶስ ኢየሱስን ጌታ እንደ ሆነ እንጂ ራሳችንን አንሰብክም፥ ስለ ኢየሱስም ራሳችንን ለእናንተ ባሪያዎች እናደርጋለን” ይላል (2ቆሮ.4፥5)።

“የእከሌን ገዳም የተሳለመ፣ ስሙን የጠራ፣ ዝክሩን የዘከረ፣ በጸበሉ የተጠመቀ፣ የታጠበ ይድናል” የሚል፥ ክርስቶስን ሳይሆን ባለገድል ተብዬውን አዳኝ አድርጎ የሚያቀርብ ትምህርት ከክርስቶስ ወንጌል ጋር ፈጽሞ ይቃረናል፤ የእግዚአብሔርንም ጻድቅነት ያፈርሳል። እግዚአብሔር ለሰዎች ድነትን ያደረገበትን አሠራር ከመጽሐፍ ቅዱስ አንብቦ ያወቀ ማንኛውም ሰው እንደዚህ ዓይነቱን ተረት ሊቀበል አይችልም።

የትንቢት ድምፅ

12 Jan, 22:11


ድነት በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ! ለምን?

አንዳንዶች፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በነቢያትና በሐዋርያት እጅ ተአምራትና ፈውሶች ስለተደረጉ፥ በዚያ መንገድ እነርሱ “ጻድቃንና ቅዱሳን” ብለው የሚጠሯቸው ወገኖች ኃጢአታቸውን ሊያስወግዱላቸው እንደሚችሉ ያስባሉ፤ “ልብሳቸውን እንኳ የነካ ድውይ ይፈወሳል፤ አፅማቸው እንኳ ሬሳ ያስነሣል” እያሉ።

ዳሩ ግን ኃጢአትን ማስወገድ በሽታን እንደመፈወስ አይደለም። በሽታ በተአምር መፈወስ ይችላል፤ ኃጢአት ግን በተአምር አይወገድም፤ በደም (በሞት) ይሰረያል እንጂ።

ጌታ ኢየሱስ ራሱ በቃሉ አጋንንትን እያወጣ ሙታንንም እያስነሣ ድውዮችንም በእጁ እየዳሰሰ ሲፈውሳቸው ቆይቶ፥ የሰውን ኃጢአትን የሚያስወግድበት ሰዓት በደረሰ ጊዜ ግን ራሱን ነው የሠዋው።

እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፦

“የሥጋ ሕይወት በደሙ ውስጥ ነው፤ ደሙም ከሕይወቱ የተነሣ ያስተሰርያልና በመሠዊያው ላይ ለነፍሳችሁ ማስተስረያ ይሆን ዘንድ እኔ ለእናንተ ሰጠሁት።” (ሌዋ.17፥11)

ኃጢአትን ለማስተስርየት ሕይወትን መሠዋት ወይም “ደምን ማፍሰስ” ያስፈልጋል ማለት ነው። ለዚህ ነው ጌታ ኢየሱስ “ነፍሴን ስለ በጎች አኖራለሁ” (ሕይወቴን ስለ በጎቼ አሳልፌ እሰጣለሁ) ማለቱ (ዮሐ.10፥15)። አልፎ በተሰጠበት ሌሊት ደግሞ ጽዋን አንሥቶ “ስለ ብዙዎች ለኃጢአት ይቅርታ የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው” አለ (ማቴ.26፥28)።

ከዓለም መጀመሪያ አንሥቶ እግዚአብሔር በላካቸው ነቢያት እጅ ታላላቅ ተአምራትንና ፈውሶችን ቢያደርግም ኃጢአት ግን ገና አልተወገደም ነበር፤ ክርስቶስ እስኪሠዋ ድረስ። ክርስቶስ ግን “በዘመናት መጨረሻ ራሱን መሥዋዕት በማድረግ ኃጢአትን ለማስወገድ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ተገልጧል” (ዕብ.9፥26/አ.መ.ት.)።

የትንቢት ድምፅ

02 Jan, 17:48


ደም ሳይፈስ ስርየት የለም!

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ምልጃ እንደየአውዱ እንዲህ የተለያዩ ትርጉሞች እንዳሉት እንወቅ። ጥቅሶችንም ያለ ቦታቸው እየጠቀስን ራሳችን ስተን ሌሎችንም እንዳናስት እንጠንቀቅ።

የክርስቶስን መካከለኝነት ጥለው በእርሱ ፈንታ ሌሎችን አማላጆች የሚያደርጉ ወገኖች ስሕተት የሚሠሩት ቃሉን ከአውዱ ውጪ በመውሰድ ነው።

ስለ ምልጃ ስናነብ ምልጃው (ወይም ልመናው) ምንን አስመልክቶ እንደሆነ ማየት ያስፈልጋል። ለፈውስ ነው? ለቁሳቁስ አቅርቦት ነው? ወይስ ለኃጢአት ስርየት? ለኃጢአት ስርየት የሚደረግ ምልጃ ከሌሎቹ ይለያል። ለኃጢአት ስርየት ከሆነ “ደም ሳይፈስ ስርየት የለም” የሚል ሕግ አለ (ዕብ.9፥22)።

ለምሳሌ፣ የኢየሱስ እናት ማርያም በገሊላ ቃና ሰርግ ላይ የወይን ጠጅ እንዳለቀባቸው ለእርሱ መንገሯን አማላጅ ለመሆኗ ማስረጃ እንደሆነ አድርገው ያቀርባሉ። የምናወራው ስለ ነፍስ ድነት እንጂ ስለ ወይን ጠጅ እንዳይደለ ዘንግተዋል። ስለ ወይን ጠጅ መጠየቅ ሌላ ኃጢአትን ማስተስርየት ሌላ። ኃጢአትን ማስተስርየት ለፈውስና ለቁሳቁስ አቅርቦት ወዘተ እንደሚደረግ ልመና አይደለም፤ የበደል ማስተስሪያ መሥዋዕት ማቅረብን ይጠይቃል፤ ደም ሳይፈስ ስርየት የለማ። ጌታ ኢየሱስ ነፍሱን ስለ ኃጢአታችን በመሠዋቱ ነው ኃጢአታችንን የሚያስተሰርየው።

“... ነፍሱን ስለ ኃጢአት መሥዋዕት ካደረገ በኋላ ዘሩን ያያል ... ጻድቅ ባሪያዬም በእውቀቱ ብዙ ሰዎችን ያጸድቃል፥ ኃጢአታቸውን ይሸከማል። ... ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ሰጥቶአልና፥ ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና፤ እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ።” (ኢሳ.53፥10-12)

አማላጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው ስንል ድነት የሚገኝበትን በደሙ ላይ የተመሠረተውን ምልጃ ማለታችን ነው። ሰው ድነትን የሚያገኘው፥ ከኃጢአቱ የሚጸድቀው፥ ከእግዚአብሔር ጋር የሚታረቀው፥ ጠላት የነበረው የእግዚአብሔር ልጅ የሚሆነው፥ በክርስቶስ መካከለኝነት (አማላጅነት) ብቻ ነው። ያ ማለት ለመጽደቅ ግለሰቡ ራሱ “በክርስቶስ መሆን” ይኖርበታል። “እኛ በእርሱ ሆነን የእግዚአብሔር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ኃጢአት ያላወቀውን እርሱን ስለ እኛ ኃጢአት አደረገው” ነው የሚለው (2ቆሮ.5፥21)፤ “በእርሱ መሆን”ን ይጠይቃል ማለት ነው።

ሰዎች (ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ መጋቢዎች ወዘተ) እንዲፈውስህና የሚያስፈልጉህን ቁሳዊና መንፈሳዊ ነገሮች እንዲሰጥህ እግዚአብሔርን ሊለምኑልህ ይችላሉ። የኃጢአትን ስርየት ግን የምታገኘው በኢየሱስ ደም ብቻ ነው። ያ ደግሞ የአንተን እምነት ይጠይቃል። በእምነት እንደሚገኝ በግልጥ ተጽፏል። “እርሱን እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ አቆመው” ይላል (ሮሜ.3፥25)። በእግዚአብሔር ፊት መጽደቅህና መኮነንህ የሚወሰነው በክርስቶስ በማመንህና ባለማመንህ ነው። “ያመነ የተጠመቀም ይድናል፥ ያላመነ ግን ይፈረድበታል” (ማር.16፥16)።

እንግዲህ በእግዚአብሔር ፊት መጽደቅህና መኮነንህ በእጅህ ነው። ያማልዱኛል ብለህ ከምታስባቸው ከሌሎች አካላት ፈጽሞ አይመጣም። በክርስቶስ ካመንክ ትጸድቃለህ፤ ካላመንክ ደግሞ ይፈረድብሃል።

“በሰዎች የሚደረግ ምልጃ የለም፤ አይሠራም፤ ምንም ዋጋ የለውም” አላልንም። ሰው ኃጢአቱ እንዲሰረይለትና የዘላለምን ሕይወት እንዲያገኝ የክርስቶስ አገልጋዮች ወይም ደቀ መዛሙርት ሊጸልዩለት ይችላሉ። ለምሳሌ፣ አዲስ ክርስቲያን ጌታን ሲቀበል በቤተክርስቲያን አገልጋዮች ይጸልዩለታል። ነገር ግን ይህ ምልጃ ውጤት የሚኖረው ሰውየውም የሚጸድቀውና የሚድነው በክርስቶስ በማመኑ ነው። እልከኛ ሆኖ በክርስቶስ የማያምነውን ሰው በምልጃው ሊያጸድቀው የሚችል ማንም የለም። በክርስቶስ የማያምን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይሆናል እንጂ ምሕረትን አያገኝም። “በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም” ተብሏል (ዮሐ.3፥36)።

ስለዚህ የሰዎች ምልጃ በድነት ረገድ ሊያደርግ የሚችለው በጣም የተገደበ ነው። ወሳኙ ግለሰቡ ራሱ በክርስቶስ ማመኑ ነው። ካመንክ ድነትን ሊነሣህ የሚችል ማንም የለም፤ የማታምን ከሆንክ ደግሞ ሊሰጥህ የሚችል የለም። ስለዚህ እንድትድን አንተ ራስህ በክርስቶስ እመን።

ከኃጢአታችን እንዲያጸድቀን የኃጢአታችን ማስተስሪያ አድርጎ እግዚአብሔር ያቆመልን ኢየሱስ ክርስቶስን ብቻ ነው። “እርሱን እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ አቆመው” (ሮሜ.3፥25)፤ “እርሱ የኃጢአታችን ማስተስሪያ ነው” ይላል (1ዮሐ.2፥2)። ከእርሱም በቀር ሌላ የለም። “መዳን በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና።” (ሐዋ.4፥12) የክርስቶስን መካከለኝነት ክደው በእርሱ ፈንታ ሌሎችን አማላጆች እንደሆኑ የሚሰብኩ ግን ሰዎች እምነታቸውን በክርስቶስ ላይ እንዳያደርጉ እንቅፋት ሆነዋል።

የትንቢት ድምፅ

28 Dec, 23:38


የመንፈስ ቅዱስና የኢየሱስ መማለድ

አንድ ሰው፥ “ሮሜ ምዕራፍ 8 ቁጥር 26 ‘መንፈስ ቅዱስ ይማልድልናል’ ይላል፤ ቁጥር 34 ደግሞ ‘ኢየሱስ ክርስቶስ ይማልድልናል’ ይላል፤ ልዩነት አላቸው ወይ?” ብሎ ጠይቋል።

የ“መማለድ” ወይም የ“ማማለድ” ትርጉሞች ቀጥሎ ቀርበዋል። ትርጉሞቹ እርስ በርሳቸው በጣም ተያያዥና ተቀራራቢ ናቸው። እርስ በርሳቸው የሚጣረሱ አይደሉም፤ ስለዚህ ሊጣመሩ ይችላሉ። ካሉት አማራጮች መካከል ትክክለኛውን ትርጉም ለማወቅ ቃሉ የተጠቀሰበትን አውድ መመልከት ያስፈልጋል። “መማለድ” ወይም “ማማለድ” ማለት፤

(1) ስለ ሌላው ሆኖ፥ የሌላውን ጉዳይ ይዞ መፍትሔና ብያኔ ለማግኘት መቆም፤ በደለኛ ምሕረትን እንዲያገኝ የበደለኛውን ጉዳይ ይዞ ወደ ተበዳይ መግባት ወይም በፈራጁ ፊት መቆም፤

(2) ማስታረቅ፤ (ቃሉ የሊቀ ካህናትን አገልግሎት ለመግለፅ ሲውል፦) መሥዋዕትን በማቅረብ በደልን ማስተስርየትና የእግዚአብሔርን ቁጣ ከሰው ማራቅ፣ ሰውን ከእግዚአብሔር ጋር ማስታረቅ፣ ወይም በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ግንኙነትን ለመፍጠር መካከለኛ መሆን፤

(3) ለሌላ ሰው መለመን ወይም መጸለይ፤

ወደ ጥያቄው ስንመለስ፣ በሮሜ ምዕራፍ 8 ቁጥር 34 የሚለው እንደዚህ ነው፦

“እግዚአብሔር የመረጣቸውን የሚከስስ ማን ነው? የሚያጸድቅ እግዚአብሔር ነው፤ ታዲያ የሚኰንን ማን ነው? የሞተው፣ እንዲሁም ከሞት የተነሣው፣ በእግዚአብሔር ቀኝ የተቀመጠው ክርስቶስ ኢየሱስ፣ ስለ እኛ ይማልዳል።” (ሮሜ.8፥33-34/አ.መ.ት.)

እዚህ ላይ “ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ይማልዳል” ሲል ትርጉሙ በተራ ቁጥር (1) እና (2) የተቀመጡትን ፍቺዎች ይይዛል። “እግዚአብሔር የመረጣቸው ቢከሰሱ ስለ እነርሱ በእግዚአብሔር ፊት የቆመ ኢየሱስ ክርስቶስ አለ” ማለት ነው። ይህም እርሱ የኃጢአታችን ማስተስሪያ (ሮሜ.3፥25)፣ በሰማያት በእግዚአብሔር ቀኝ “ሊቀ ካህናት” (ዕብ.7፥24-25) እና “ጠበቃችን” (1ዮሐ.2፥1-2) መሆኑ ነው።

በሮሜ ምዕራፍ 8 ቁጥር 26 ደግሞ “ይማልዳል” የሚለው “ይጸልይናል” ማለት ነው።

“... መንፈስ በድካማችን ያግዘናል፤ እንዴት መጸለይ እንደሚገባን አናውቅም፤ መንፈስ ግን በቃላት ሊገለጥ በማይችል መቃተት ለእኛ ይማልድልናል። ልባችንንም የሚመረምረው እርሱ የመንፈስን ሐሳብ ያውቃል፤ ምክንያቱም መንፈስ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለቅዱሳን ይማልዳልና።” (ሮሜ.8፥26-27/አ.መ.ት.)

በአጭር ቃል፣ ቁጥር 34 ላይ “ይማልዳል” ሲል “ኢየሱስ ክርስቶስ በደላችንን ለማስተስርየትና እኛን ለማጽደቅ በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ ይቆማል” ማለት (ትርጉም 1 እና 2) ሲሆን፤ ቁጥር 26 ላይ “ይማልዳል” ሲል ደግሞ “እንዴት መጸለይ እንዳለብን ስለማናውቅ መንፈስ ቅዱስ ይጸልይልናል” ማለት (ትርጉም 3) ነው።

ልዩነታቸው ግልጽ ነው፤ አንደኛው መሥዋዕትን በማቅረብ የሚፈጸም ሲሆን ሁለተኛው ጸሎት ነው።

የትንቢት ድምፅ

28 Dec, 23:37


ሳይንስ “ሞትን” ማስቀረት ይችላል?

ሳይንቲስቶች፥ የሰውን ዕድሜ በከፍተኛ ሁኔታ ማራዘም፥ እርጅናን ማዘግየትና፥ በሽታን በመከላከልና በመቋቋም ሰውን ረጅም ዕድሜ በጤና ማቆየት የሚያስችሉ ዘዴዎችን ለማግኘት፥ ምርምር እያደረጉ ናቸው። የፀረ-እርጅና መድኃኒቶች፣ ያረጁ ሕዋሳትን ማስወገድ ወይም ማደስ፣ የሰውን አካል በቤተ ሙከራ ውስጥ ማሳደግና የደከሙና ያረጁ የሰው አካላትን መተካት፣ ጄኔቲክስና አርቴፊሺያል ኢንተሊጀንስ የሚጠቀሟቸው ዘዴዎች ናቸው። ቢሊየነሮችም የምርምሩ ውጤት ቀዳሚ ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተስፋ በማድረግ ምርምሩን በገንዘባቸው እየደገፉት ይገኛሉ።

ምርምሩ የዕድሜ ማራዘሚያ ለማግኘት የታለመ ቢሆንም አንዳንዶች ሞትን በማስቀረት ዘላለም ለመኖር የሚያስችል ውጤት ያስገኛል እያሉ ያጋንኑታል። አንድ ፕሮፌሰር ስለ ምርምሩ ሲናገር፥ ክርስቲያኖችን ለማስቆጣት ይመስላል፥ “ሞትን ለማሸነፍ የክርስቶስን ዳግም ምጽአት መጠበቅ አያስፈልገንም። ጥቂት ሳይንቲስቶች በቤተ ሙከራ ውስጥ ሊያደርጉት ይችላሉ” ብሏል። በምርምሩ የሚፈልጉትን ውጤት ካገኙ ወንጌላችንን ዋጋ እንዳይኖረው የሚያደርግ መስሏቸዋል፤ ወንጌል “የዘላለምን ሕይወት የሚሰጥ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው” ስለሚል።

ዳሩ ግን በምርምሩ የሚፈልጉትን ውጤት ቢያገኙ እንኳ እነርሱ እንደመሰላቸው የዘላለምን ሕይወት የሚሰጥ ወይም የሚተካ አይደለም። ሲጀመር ከዘላለም ሕይወት ጋር ለንፅፅርና ለውድድር የሚቀርብ አይደለም። ከዘላለም ሕይወት ጋር እኩል ያደረጉት የዘላለምን ሕይወት ስለማያውቁት ነው።

በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኘው የዘላለም ሕይወት፥ የኃጢአትን ስርየት በማግኘት ከዘላለም ፍርድ መዳንና ከእግዚአብሔር መወለድ ነው እንጂ እንዲያው በምድር ላይ ረጅም ዕድሜ ማስቆጠር አይደለም። ኑሮ ከተባለማ ወደ ዘላለም ሕይወት የሚገቡ እንዳሉ ሁሉ ወደ ዘላለም ጕስቍልና የሚገቡም አሉ። “በምድር አፈር ውስጥ ካንቀላፉት ብዙዎች ይነቃሉ፤ አንዳንዶቹ ለዘላለም ሕይወት፣ ሌሎቹም ለውርደትና ለዘላለም ጕስቍልና ይነሣሉ” ይላል (ዳን.12፥2)።

በሕክምና እየታገዙ ሥጋዊ ሞትን ለጊዜው ማዘግየት ቢቻል እንኳ ያ ከመጨረሻው ፍርድ አያድንም። በፍርድ ቀን ሰማይና ምድር ራሳቸው ይጠፋሉ።

“አሁን ያሉ ሰማያትና ምድር ግን እግዚአብሔርን የማያመልኩት ሰዎች እስከሚጠፉበት እስከ ፍርድ ቀን ድረስ ተጠብቀው በዚያ ቃል ለእሳት ቀርተዋል። ... በዚያም ቀን ሰማያት በታላቅ ድምፅ ያልፋሉ፥ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኵሳት ይቀልጣል፥ ምድርም በእርስዋም ላይ የተደረገው ሁሉ ይቃጠላል።” (2ጴጥ.3፥7-10)

ሰማይና ምድር እንኳ የሚጠፉ ከሆኑ ታዲያ ማን ሊያመልጥ ይችላል? የትኛው ሕክምና፥ የትኛው ቴክኖሎጂ ያድነዋል? ወደየት ይሰወራል?

ሰው በሕክምና አልያም በሌላ ቴክኖሎጂ እየታገዘ ምናልባት ምናልባት ዕድሜውን ለጊዜው ማራዘም ቢችል እንኳ በሕይወት የሚቆየው ግፋ ቢል እስከ ፍርድ ቀን ድረስ ብቻ ነው፤ እንጂ ከፍርድ ሊያመልጥ አይችልም። የፍርድ ቀን የሰው ዕድሜ የመጨረሻ ጣሪያ ነች። በዚያን ቀን ደግሞ ዓመፀኞች የሚቀጡት እንደዛሬው በሥጋዊ ሞት ሳይሆን በእሳት ባሕር ውስጥ በመጣል ነው፤ “ሁለተኛው ሞት” ይባላል። “... የእሳት ባሕር ሁለተኛው ሞት ነው። በሕይወትም መጽሐፍ ተጽፎ ያልተገኘው ማንኛውም በእሳት ባሕር ውስጥ ተጣለ” ይላል (ራእ.20፥14-15)። ከዚህ የዘላለም ፍርድ መዳን ነው የዘላለም ሕይወት። ያ የሚሆነው ደግሞ በክርስቶስ በማመን ኃጢአታችን ሲሰረይልን ነው። “እውነት እላችኋለሁ፤ ቃሌን የሚሰማ በላከኝም የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ ከሞት ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይመጣም” ይላል (ዮሐ.5፥24)። ሳይንስ ግን ይህን ሞት አያውቀውም፤ ለሱ መድኃኒትም የለውም።

አንዳንድ ወንጀለኞች ከፍርድ ለማምለጥ አንዳንድ ወታደሮች ደግሞ ጠላት እንዳይዛቸው ራሳቸውን ያጠፋሉ። የዘላለም ፍርድ ግን ሞተው እንኳ የማያመልጡት ፍርድ ነው፤ የሞቱትንም አሥነስቶ ለፍርድ ስለሚያቀርባቸው። “ባሕር በውስጡ የነበሩትን ሙታን ሰጠ፤ ሞትና ሲኦልም በውስጣቸው የነበሩትን ሙታን ሰጡ፤ እያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን ተፈረደበት” ይላል (ራእ.20፥13)። ስለዚህ ጌታ ኢየሱስ እንዲህ አለ፤ “ሥጋን የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ፤ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ።” (ማቴ.10፥28)

ክርስቶስን እንድንመስል እንጂ የተበላሸውን ባሕርይ (ወይም ተፈጥሮ) ይዘን ዘላለም እንድንኖር የእግዚአብሔር ፈቃድ አይደለም፤ “አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአል” እንደሚል (ሮሜ.8፥29)። በመሆኑም የዘላለም ሕይወት የሚሞተውና የሚጠፋው ሰውነታችንን ወደማይሞትና ወደማይጠፋ የክርስቶስ ዓይነት ሰውነት መለወጥ ይጨምራል። ይህም ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ “ሁሉን ለራሱ በሚያስገዛበት ኃይል (ወይም አሠራር)” የሚያደርገው ነው (ፊልጲ.3፥20-21)። በሳይንስ፣ በቴክኖሎጂ፣ በሕክምና አልያም በሌላ ጥበብ አይመጣም። ሳይንቲስቶቹ እየጣሩ ያሉት ቢቻላቸው አሮጌውን ተፈጥሮአችንን ለማቆየት ነው። ጌታ ግን “እነሆ፥ ሁሉን አዲስ አደርጋለሁ” ይላል (ራእ.21፥5)።

የትንቢት ድምፅ

18 Dec, 17:39


ዋናው መልእክት ግን፦ በሙሴ በኩል የተሰጠው የሌዊ ክህነት ለሚያመልኩት የሚፈለገውን ፍጹምነት አስገኝቶ ቢሆን ኖሮ ትንቢቱ የተነገረለት እንደ መልከጼዴቅ ያለ ሌላ ካህን እንዲመጣ ባላስፈለገ ነበር። ያ ሥርዓት የሚያመልኩትን ሰዎች በሕሊና ፍጹም ሊያደርግ ስላልቻለ አሁን ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት የተሻለ ተስፋ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቷል ነው የሚለው።

“ፍጹምነት የተገኘውና ሕጉ ለሕዝቡ የተሰጠው በሌዊ ክህነት መሠረት ቢሆን ኖሮ፣ እንደ አሮን ሳይሆን እንደ መልከጼዴቅ ሹመት ያለው ሌላ ካህን መምጣቱ ለምን አስፈለገ? የክህነት ለውጥ ካለ ሕጉም ሊለወጥ ግድ ነውና። ይህ ሁሉ የተነገረለት እርሱ ከሌላ ነገድ ነው፤ ከዚያም ነገድ በመሠዊያ ያገለገለ ማንም የለም። ጌታችን ከይሁዳ ነገድ እንደ መጣ ግልጽ ነውና፤ ሙሴ ስለ ካህናት ሲናገር ይህን ነገድ አስመልክቶ የተናገረው ምንም ነገር የለም። እንደ መልከጼዴቅ ያለ ሌላ ካህን ቢነሣ ግን እኛ የተናገርነው ይበልጥ ግልጽ ይሆናል፤ እርሱ ካህን የሆነው በማይጠፋ የሕይወት ኀይል መሠረት እንጂ፣ እንደ ትውልዱ የሕግ ሥርዓት አይደለም፤ እንዲህ ተብሎ ተመስክሮለታል፤ “እንደ መልከጼዴቅ ሹመት፣ አንተ ለዘላለም ካህን ነህ።” የቀድሞው ትእዛዝ ደካማና የማይጠቅም በመሆኑ ተሽሯል፤ ሕጉ ማንንም ፍጹም ሊያደርግ ስለማይችል፣ ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት የተሻለ ተስፋ መጥቷል። ይህ ያለ መሐላ አልሆነም፤ ሌሎች ካህናት የሆኑት ያለ መሐላ ነው፤ እርሱ ግን ካህን የሆነው በመሐላ ነው፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ተናግሮለታል፤ “ጌታ ማለ፤ አሳቡንም አይለውጥም፤ ‘አንተ ለዘላለም ካህን ነህ።’” ከዚህ መሐላ የተነሣ፣ ኢየሱስ ለተሻለ ኪዳን ዋስ ሆኗል።” (ዕብ.7፥11-22)

“እርሱ (ማለትም ጌታ ኢየሱስ) ካህን የሆነው በማይጠፋ የሕይወት ኀይል መሠረት እንጂ፣ እንደ ትውልዱ የሕግ ሥርዓት አይደለም” የሚለውን (ቁ.16) እናስተውል። “እንደ ትውልዱ የሕግ ሥርዓት” ማለት ሌዋውያኑ ካህናት አንዱ ሲሞት በሌላው እየተተካ የሚቀጥል ከእነዚያ ካህናት ዘር በመወለድ ላይ የተመሠረተ ክህነት ነው። ጌታ ኢየሱስ ከይሁዳ ነገድ እንጂ ከካህናት ዘር ስላልተወለደ ክህነቱን ያገኘው በዚያ አግባብ አይደለም፤ “ጌታችን ከይሁዳ ነገድ እንደ መጣ ግልጽ ነውና፤ ሙሴ ስለ ካህናት ሲናገር ይህን ነገድ አስመልክቶ የተናገረው ምንም ነገር የለም” የሚለው (ቁ.14)።

ክህነቱም በሌዋውያኑ አገልግሎት ሊገኝ ያልቻለውን ፍጹምነት አስገኝቷል። “በአንዱ መሥዋዕት የሚቀደሱትን ለዘላለም ፍጹማን አድርጎአቸዋል” ይላል (ዕብ.10፥14)። “ሕጉ ማንንም ፍጹም ሊያደርግ ስለማይችል፣ ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት የተሻለ ተስፋ መጥቷል” የሚለው ለዚህ ነው (ቁ.19)።

ጌታ ኢየሱስ ካህን የሆነው “በማይጠፋ የሕይወት ኀይል” መሠረት ነው (ቁ.16)። እርሱ ዘላለም ስለሚኖር እንደ ሌዋውያኑ ካህናት የሚሻርና በሌላ የሚተካ አይደለም ማለት ነው። “በአንድ በኩል አሥራት የሚቀበሉት ሟች ሰዎች ናቸው፤ በሌላ በኩል ግን ሕያው ሆኖ እንደሚኖር የተመሰከረለት ይቀበላል” እያለ ከእነርሱ ጋር ያነፃፅረዋል (ቁ.8)።

“በአገልግሎታቸው እንዳይቀጥሉ ሞት ስለ ከለከላቸው፣ የቀድሞዎቹ ካህናት ቍጥራቸው ብዙ ነበር፤ ኢየሱስ ግን ለዘላለም የሚኖር በመሆኑ፣ ክህነቱ የማይሻር ነው። ስለዚህ ስለ እነርሱ እየማለደ ሁልጊዜ በሕይወት ስለሚኖር፣ በእርሱ በኩል ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል።” (ዕብ.7፥23-25)

የክርስቶስን ክህነት ትታችሁ በሌሎች ሰዎች አማላጅነት ወደ እግዚአብሔር ለመድረስ የምትጥሩ አስተውሉ እንግዲህ። ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት የተሻለ ተስፋ እርሱም ኢየሱስ መጥቷል የሚለውን እየሰማችሁ (ቁ.19) በእግዚአብሔር ፊት ፍጹምነትን ሊያጎናጽፋችሁ ወደማይችል ራሳቸው ደካማ በሆኑ ሰዎች ላይ ወደተመሠረተ ሥርዓት እንደገና ለምን ትመለሳላችሁ? ፍጹም የሆነው የእግዚአብሔር ልጅ አይሻላችሁም? ለእኛ የሚያስፈልገን እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ነው።

“እንግዲህ ለእኛ የሚያስፈልገን፣ ቅዱስ፣ ነቀፋ የሌለበት፣ ንጹሕ፣ ከኀጢአተኞች የተለየና ከሰማያት በላይ የከበረ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ነው። እርሱም እንደ ሌሎቹ ሊቃነ ካህናት መጀመሪያ ስለ ራሱ ኀጢአት፣ ከዚያም ስለ ሕዝቡ ኀጢአት በየቀኑ መሥዋዕት ማቅረብ አያስፈልገውም፤ ራሱን በሰጠ ጊዜ፣ ስለ ኀጢአታቸው ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መሥዋዕት አቅርቧልና። ሕጉ ደካማ የሆኑትን ሰዎች ሊቃነ ካህናት አድርጎ ይሾማልና፤ ከሕግ በኋላ የመጣው መሐላ ግን ለዘላለም ፍጹም የሆነውን ልጅ ሾሟል።” (ዕብ.7፥26-28)

ክርስቶስ በመልከጼዴቅ መመሰሉ እርሱ ፈራጅ እንጂ ካህን (አማላጅ) አይደለም ለሚሉ፥ ፈራጅ መሆኑ ካህን ከመሆን የሚያግደው ለሚመስላቸው በቂ መልስ ነው። መልከጼዴቅ ካህን ብቻ አልነበረም፤ “የስሙ ትርጓሜ በመጀመሪያ ‘የጽድቅ ንጉሥ’ ነው፥ ኋላም ደግሞ ‘የሳሌም ንጉሥ’ ማለት ‘የሰላም ንጉሥ’ ነው።” (ዕብ.7፥2) መልከጼዴቅ ንጉሥና የልዑል እግዚአብሔር ካህን እንደነበረ ክርስቶስም እንደዚሁ ነው። ሰው ሳይሆን እግዚአብሔር ራሱ “እንደ መልከጼዴቅ ሥርዓት አንተ ለዘላለም ካህን ነህ” ብሎታልና ክርስቶስ ካህን መሆኑ ሊካድ የማይቻል ነው። የጽድቅ ንጉሥ ስለመሆኑ ደግሞ “አምላክ ሆይ፥ ዙፋንህ ለዘላለም ነው፤ የመንግሥትህ በትር የቅንነት (የጽድቅ) በትር ነው። ጽድቅን ወደድህ ዓመፃንም ጠላህ፤ ...” ይላል (መዝ.45፥6-7፣ዕብ.1፥8-9)። የሰላም ንጉሥ ስለመሆኑ ደግሞ “... የሰላም አለቃ (ልዑል) ተብሎ ይጠራል ... ለሰላሙም ፍፃሜ የለውም” ይላል (ኢሳ.9፥6-7)። ስለዚህ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ንጉሥ ነው፥ በጽድቅ ይፈርዳል፤ ካህን ነው፥ በደላችንን ያስተሰርያል።

የትንቢት ድምፅ

18 Dec, 17:38


(8) በሰማያት ለዘላለም ሊቀ ካህናት ነው።

ክርስቶስ ለዘላለም ካህን መሆኑ በእግዚአብሔር ቀኝ ከመቀመጡ ጋር ተያይዞ በትንቢት ተነግሯል። እንዲህ ይላል፦

“እግዚአብሔር ጌታዬን ‘ጠላቶችህን ለእግርህ መቀመጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ’ አለው። ... ‘እንደ መልከ ጼዴቅ ሥርዓት አንተ ለዘላለም ካህን ነህ’ ብሎ፥ እግዚአብሔር ማለ አይጸጸትም።” (መዝ.110፥1-4)

ይህ የተነገረው ስለ ጌታ ኢየሱስ ነው። ሐዋርያው ይህን የትንቢት ቃል ጠቅሶ የእርሱን ክህነት እንዲህ እያለ ያስረዳል፦

“ሊቀ ካህናት ሁሉ ስለ ኃጢአት መባንና መስዋዕትን ሊያቀርብ ከሰው ተመርጦ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ ስለ ሰው ይሾማል፤ ... እንደ አሮንም በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር ማንም ክብሩን ለራሱ የሚወስድ የለም። እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ ሊቀ ካህናት ሊሆን ራሱን አላከበረም፤ ነገር ግን፣ ‘አንተ ልጄ ነህ፤ እኔ ዛሬ ወልጄሃለሁ’ ያለው እርሱ ነው፤ እንደዚህም በሌላ ስፍራ ደግሞ፣ ‘አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ካህን ነህ’ ይላል። እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፥ እግዚአብሔርንም ስለ መፍራቱ ተሰማለት፤ ምንም ልጅ ቢሆን፥ ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ፤ ከተፈጸመም በኋላ በእግዚአብሔር እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ሊቀ ካህናት ተብሎ ስለ ተጠራ፥ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆነላቸው።” (ዕብ.5፥1-10)

በክህነቱ በክርስቶስ ስለተመሰለው ስለ መልከጼዴቅ የሚለው እንደዚህ ነው፦

“የሳሌም ንጉሥና የልዑል እግዚአብሔር ካህን የሆነ ይህ መልከ ጼዴቅ አብርሃም ነገሥታትን ገድሎ ሲመለስ ከእርሱ ጋር ተገናኝቶ ባረከው፤ ለእርሱም ደግሞ አብርሃም ከሁሉ አስራትን አካፈለው። የስሙም ትርጓሜ በመጀመሪያ ‘የጽድቅ ንጉሥ’ ነው፥ ኋላም ደግሞ ‘የሳሌም ንጉሥ’ ማለት ‘የሰላም ንጉሥ’ ነው። አባትና እናት የትውልድም ቍጥር የሉትም፥ ለዘመኑም ጥንት ለህይወቱም ፍጻሜ የለውም፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ልጅ ተመስሎ ለዘላለም ካህን ሆኖ ይኖራል።” (ዕብ.7፥1-3)

እዚህ ላይ፣ “አባትና እናት የትውልድም ቍጥር የሉትም፥ ለዘመኑም ጥንት ለህይወቱም ፍጻሜ የለውም፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ልጅ ተመስሎ ለዘላለም ካህን ሆኖ ይኖራል” የሚለው የብዙዎችን ትኩረት ስቧል፤ ጥያቄ የፈጥራል፤ አነጋግሯል።

አንዳንዶች ይህ ቃል መልከጼዴቅ ከአባትና ከእናት እንዳልተወለደ ለሕይወቱም ጅማሬ እንደሌለውና እንዳልሞተ ይናገራል ብለው ያምናሉ። ሞትን እንዳያይ እግዚአብሔር ከወሰደው ከሄኖክና በአውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ካወጣው ከነቢዩ ኤልያስ ጋር ይመድቡታል።

አንዳንዶች በትውፊት የአይሁድና የክርስትና መጻሕፍት አድርገው የሚቀበሏቸው ነገር ግን ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጪ የሆኑ አንዳንድ ጥንታዊ ጽሑፎችም መልኬጼዴቅን መልአክ ወይም አምላክ አድርገው ያቀርቡታል። ዳሩ ግን የመጽሐፍ ቅዱሱ መልከጼዴቅ ሰው እንደሆነ ግልጥ ነው።

በእግዚአብሔር አሠራር ኪዳን፣ ንግሥናና ክህነት በዘር ስለሚተላለፍ የሰዎች የትውልድ ሐረግ በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶት እናያለን። ዋነኞቹ ቅዱሳን ሰዎች፣ ነቢያትና ነገሥታት የትውልድ ሐረጋቸው ከአዳም ጀምሮ ተዘርዝሯል። ይህ ያስፈለገው ክህነት ያለው የክህነቱን፥ ንግሥና ያለው የንግሥናውን፥ ኪዳን ያለው የኪዳኑን ሕጋዊ ወራሽነቱንና አግባብነቱን ለማስረገጥ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ስለ ሕይወታቸው ፍጻሜ ስለ ሞታቸውና ስለ ቀብራቸው ተጽፏል።

መልከጼዴቅ ግን በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ አባቱንና እናቱን ወይም የትውልድ ሐረጉን አናገኝም። ታሪኩም ጅማሬና ፍጻሜ የለውም። የልዑል እግዚአብሔር ካህን እንደሆነና አብርሃምን ነገሥታትን ድል አድርጎ መልስ አግኝቶት እንደባረከው ብቻ ነው የተነገረን። “አባትና እናት የትውልድም ቍጥር የሉትም፥ ለዘመኑም ጥንት ለህይወቱም ፍጻሜ የለውም” የሚለው ይህን ለመግለጽ ይሆናል ብሎ መውሰድ ስሕተት አይሆንም።

የትንቢት ድምፅ

08 Dec, 17:42


እግዚአብሔር ለዳዊት የመንግሥቱን ዙፋን ለዘላለም ሊያጸናለት ቃል ገብቶለታል። እንዲህ ሲል፦

+ “ዕድሜህ በተፈጸመ ጊዜ ከአባቶችህም ጋር ባንቀላፋህ ጊዜ፥ ከወገብህ የሚወጣውን ዘርህን ከአንተ በኋላ አስነሣለሁ፥ መንግሥቱንም አጸናለሁ። ... ቤትህና መንግሥትህም በፊቴ ለዘላለም ይጠነክራል፥ ዙፋንህም ለዘላለም ይጸናል።” (2ሳሙ.7፥12-16)

+ “ከመረጥሁት ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ፥ ለባሪያዬም ለዳዊት ማልሁ፤ ‘ዘርህን ለዘላለም አዘጋጃለሁ፥ ዙፋንህንም ለልጅ ልጅ እመሠርታለሁ።’” (መዝ.89፥3-4)

የዚህ ተስፋና ትንቢት ፍጻሜ ጌታ ኢየሱስ መሆኑን መልአኩ ገብርኤል እርሱን እንደምትወልድ ማርያምን ሲያበስራት ከተናገረው ቃል እንረዳለን። እንዲህ ነበር ያላት፦

“እነሆም፥ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፥ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ። እርሱ ታላቅ ይሆናል የልዑል ልጅም ይባላል፥ ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፤ በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘለላም ይነግሣል፥ ለመንግሥቱም መጨረሻ የለውም።” (ሉቃ.1፥31-33)

የነቢዩ ኢሳይያስ ትንቢትም በዚህ ተፈጸመ፤ እንዲህ የሚለው፦

“ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል። ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም ድረስ በፍርድና በጽድቅ ያጸናውና ይደግፈው ዘንድ በዳዊት ዙፋንና በመንግሥቱ ላይ አለቅነቱ ይበዛል፥ ለሰላሙም ፍፃሜ የለውም። የእግዚአብሔር ቅንዓት ይህን ያደርጋል።” (ኢሳ.9፥6-7)

ካህኑ ዘካርያስም መንፈስ ቅዱስ ሞልቶበት የጌታን መወለድ አስመልክቶ እንዲህ ሲል ተናገረ፦

“የእስራኤል ጌታ አምላክ ይባረክ፥ ጐብኝቶ ለሕዝቡ ቤዛ አድርጎአልና፤ ከጥንት ጀምሮ በነበሩት በቅዱሳን ነቢያት አፍ እንደ ተናገረ፥ በብላቴናው በዳዊት ቤት የመዳን ቀንድን አስነስቶልናል፤ ማዳኑም ከወደረኞቻችንና ከሚጠሉን ሁሉ እጅ ነው፤ እንደዚህ ለአባቶቻችን ምሕረት አደረገ፤ ለአባታችን ለአብርሃምም የማለውን መሐላውን ቅዱሱን ኪዳን አሰበ፤ በእርሱም ከጠላቶቻችን እጅ ድነን በዘመናችን ሁሉ ያለ ፍርሃት በቅድስናና በጽድቅ በፊቱ እንድናገለግለው ሰጠን። ... ይህም ከላይ የመጣ ብርሃን በጐበኘበት በአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ምክንያት ነው፤ ብርሃኑም በጨለማና በሞት ጥላ ተቀምጠው ላሉት ያበራል እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናል።” (ሉቃ.1፥68-79)

ዳሩ ግን፣ በመጀመሪያው መምጣቱ ብዙሃኑ እስራኤል በእርሱ ስላላመኑበት የተነገረላቸውን ያን መንግሥት አላገኙም። “‘እነሆ። በጽዮን የእንቅፋት ድንጋይና የማሰናከያ ዓለት አኖራለሁ፤ በእርሱም የሚያምን አያፍርም’ ተብሎ እንደ ተጻፈ በእንቅፋት ድንጋይ ተሰናከሉ።” (ሮሜ.9፥32-33)

በዚህም ምክንያት፥ ጌታ፥ ከእነርሱ አለመታዘዝ የተነሣ የድነት ደጅ ለአሕዛብ እንደሚከፈትላቸው ሲያመለክት፥ “ስለዚህ እላችኋለሁ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተ ትወሰዳለች ፍሬዋንም ለሚያደርግ ሕዝብ ትሰጣለች” አላቸው (ማቴ.21፥43)። ደግሞም “የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም። ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው” ይላል (ዮሐ.1፥11-12)።

እንዲያም ሆኖ ግን እግዚአብሔር ሕዝቡን ፈጽሞ አልጣላቸውም (ሮሜ.11፥2)። “እግዚአብሔር በጸጋው ስጦታና በመጥራቱ አይጸጸትምና።” (ሮሜ.11፥29) “... በአለማመናቸው ጸንተው ባይኖሩ በዛፉ ውስጥ ይገባሉ፤ እግዚአብሔር መልሶ ሊያገባቸው ይችላልና” ይላል (ሮሜ.11፥23)። ወደ እርሱ ቢመለሱ እርሱም ወደ እነርሱ ተመልሶ ይመጣል። ሐዋርያው እንዲህ ይላቸዋል፦

“... ከጌታ ፊት የመጽናናት ዘመን እንድትመጣላችሁ አስቀድሞም ለእናንተ የመረጠውን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዲልክላችሁ፥ ኃጢአታችሁ ይደመሰስ ዘንድ ንስሐ ግቡ ተመለሱም።” (ሐዋ.3፥19-20)

እምቢታቸው “የአሕዛብ ሙላት እስኪገባ” ድረስ ነው (ሮሜ.11፥25)። በመጨረሻው ዘመን የገፉትን መሲሕ ይሹታል። ነቢዩ ሆሴዕ “ከዚያም በኋላ የእስራኤል ልጆች ተመልሰው አምላካቸውን እግዚአብሔርንና ንጉሣቸውን ዳዊትን ይፈልጋሉ፤ በኋለኛውም ዘመን ፈርተው ወደ እግዚአብሔርና ወደ በረከቱ ይመጣሉ” ይላል (ሆሴ.3፥5)።

ያን ጊዜ ጌታ ኢየሱስ በእስራኤልና በምድር ሁሉ ላይ ይነግሣል። ፍትሕን፣ ጽድቅንና ሰላምን በዓለም ሁሉ ያሰፍናል፤ ከመከራቸውም ሁሉ ያሳርፋቸዋል። ይህ የሚሆነው በዳግም ምጽአቱ ነው።

“እነሆ፥ ለዳዊት ጻድቅ ቍጥቋጥ የማስነሣበት ዘመን ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር፥ እርሱም እንደ ንጉሥ ይነግሣል፥ ይከናወንለታልም፥ በምድርም ፍርድንና ጽድቅን ያደርጋል። በዘመኑም ይሁዳ ይድናል እስራኤልም ተዘልሎ ይቀመጣል፥ የሚጠራበትም ስም፣ ‘እግዚአብሔር ጽድቃችን’ ተብሎ ነው።” (ኤር.23፥5-6)

ይቀጥላል ...

የትንቢት ድምፅ

08 Dec, 17:41


(7) ከዳዊት ዘር ይወለዳል።

ክርስቶስ ከዳዊት ዘር እንደሚመጣ እግዚአብሔር በነቢያቱ አፍ አንድ ጊዜ ብቻ ሳይሆን ደጋግሞ ተናግሯል።

በትንቢቱም መሠረት ጌታ ኢየሱስ በሥጋ ከዳዊት ዘር ተወለደ።

ምናልባት “ዳዊት ለእኛ ምናችን ነው? ኢየሱስም ከእርሱ ዘር መወለዱ ለእኛ ምን ዋጋ አለው?” የሚል ይኖራል።

ጉዳዩ ከዳዊት ከሰውየው ከራሱ ሳይሆን እግዚአብሔር ለዳዊት ከማለለት የማይለወጥ መሐላ የተነሣ ነው። “ለዘላለም ምሕረቴን ለእርሱ እጠብቃለሁ፥ ኪዳኔም በእርሱ ዘንድ የታመነ ነው። ዘሩንም ለዓለምና ለዘላለም፥ ዙፋኑንም እንደ ሰማይ ዘመን አደርጋለሁ። ... ዳዊትን እንዳልዋሸው አንድ ጊዜ በቅዱስነቴ ማልሁ። ዘሩ ለዘላለም፥ ዙፋኑም በፊቴ እንደ ፀሐይ ይኖራል። ለዘላለም እንደ ጨረቃ ይጸናል፤ ምስክርነቱ በሰማይ የታመነ ነው” ይላል (መዝ.89፥28-37)።

ጌታ ራሱ “ድነት ከአይሁድ ነው” ብሏል (ዮሐ.4፥22)፤ ደግሞም “እኔ የዳዊት ሥርና ዘር ነኝ” ይላል (ራእ.22፥16)።

የእግዚአብሔር ቃል ሊሻር ስለማይቻል፥ እግዚአብሔር ክርስቶስ ከዳዊት ዘር እንደሚመጣ ከተናገረ፥ አንድ ክርስቶስ እንጂ ሌላ ስለሌለ፥ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደሆነ ስንመሰክር፥ ከዳዊት ዘር መወለዱን ማረጋገጥ ለተቃዋሚዎችም ፈንታ አለመስጠት ያስፈልጋል።

ስለዚህ በወንጌላትና በሐዋርያት ስብከትና በመልእክቶቻቸው ውስጥ ኢየሱስ ከዳዊት ዘር መወለዱ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶት እናገኛለን።

ለምሳሌ፣ ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ይላል፦

“ሐዋርያ ሊሆን የተጠራ የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ ጳውሎስ በነቢያቱ አፍ በቅዱሳን መጻሕፍት አስቀድሞ ተስፋ ለሰጠው ለእግዚአብሔር ወንጌል ተለየ። ይህም ወንጌል በሥጋ ከዳዊት ዘር ስለ ተወለደ እንደ ቅድስና መንፈስ ግን ከሙታን መነሣት የተነሣ በኃይል የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ ስለ ተገለጠ ስለ ልጁ ነው፤ እርሱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።” (ሮሜ.1፥1-4)

ጢሞቴዎስን ደግሞ “በወንጌል እንደምሰብከው፥ ከሙታን የተነሣውን፥ ከዳዊት ዘርም የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን አስብ” ይለዋል (2ጢሞ.2፥8)።

እግዚአብሔር አብርሃምን “የምድር አሕዛብ ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ” ብሎ (ዘፍ.22፥18) የዓለም መድኃኒት ክርስቶስ ከእርሱ ዘር እንደሚመጣ ካመለከተ በኋላ ለዚሁ ዓላማ ከአብርሃም ልጆች ይስሐቅን መረጠ፤ ከይስሐቅም ልጆች ያዕቆብን መረጠ፤ ከአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገዶች ደግሞ ይሁዳን መረጠ።

ያዕቆብ ልጆቹን ሲባርካቸው ክርስቶስ ከይሁዳ ነገድ እንደሚመጣ እንዲህ ሲል ትንቢት ተናገረ፦

“በትረ መንግሥት ከይሁዳ አይጠፋም፥ የገዥም ዘንግ ከእግሮቹ መካከል፥ ገዥ የሆነው እስኪመጣ ድረስ፤ የአሕዛብ መታዘዝም ለእርሱ ይሆናል።” (ዘፍ.49፥10)

ከይሁዳ ነገድ እግዚአብሔር የእሴይን ልጅ የዳዊትን ቤት መረጠ። ሐዋርያው ለአይሁድ ሲመሰክር “‘እንደ ልቤ የሆነ ሰው ፈቃዴንም ሁሉ የሚያደርግ የእሴይን ልጅ ዳዊትን አገኘሁ’ አለ። ከዚህም ሰው ዘር እግዚአብሔር እንደ ተስፋው ቃል ለእስራኤል መድኃኒትን እርሱም ኢየሱስን አመጣ” ይላል (ሐዋ.13፡22-23)።

አንዳንዶች ግን ኢየሱስ ከዳዊት ዘር እንደመጣ አላወቁም ነበር።

“... ከሕዝቡ አያሌ ሰዎች ይህን ቃል (የኢየሱስን ቃል) ሲሰሙ፣ ‘ይህ በእውነት ነቢዩ ነው’ አሉ፤ ሌሎች፣ ‘ይህ ክርስቶስ ነው’ አሉ፤ ሌሎች ግን፣ ‘ክርስቶስ በእውኑ ከገሊላ ይመጣልን? ክርስቶስ ከዳዊት ዘር ዳዊትም ከነበረባት መንደር ከቤተ ልሔም እንዲመጣ መጽሐፍ አላለምን?’ አሉ። እንግዲህ ከእርሱ የተነሣ በሕዝቡ መካከል መለያየት ሆነ።” (ዮሐ.7፡40-43)

ዳሩ ግን ኢየሱስ በገሊላ ናዝሬት አደገ እንጂ አልተወለደም። አውግስጦስ ቄሣር በግዛቱ የሚኖሩ ሰዎች ሁሉ እንዲመዘገቡ ባዘዘው ትእዛዝ መሠረት እናቱ ማርያምና ዮሴፍ ሊመዘገቡ የዳዊት ከተማ ወደ ሆነችው የትውልድ ስፍራቸው ወደ ቤተ ልሔም ሄደው ሳሉ የመውለጃዋ ጊዜ ደርሶ በዚያ ነበር የተወለደው (ሉቃ.2፡1-7)።

ይህም “አንቺ ቤተ ልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል” በሚለው በነቢዩ ሚክያስ ትንቢት መሠረት ሆነ (ሚክ.5፡2)።

የጌታም መልአክ በዚያች ሌሊት ለእረኞች ተገልጦ “ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋል” ብሎ መወለዱን አበሰራቸው (ሉቃ.2፡8-20)።

ያደገው ግን በገሊላ ናዝሬት ነበር። ሠላሳ ዓመት ያህል በሆነው ጊዜ መንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ ማስተማር የጀመረውም እዚያ ነበር። “ኢየሱስ በምኩራቦቻቸው እያስተማረ የመንግሥትንም ወንጌል እየሰበከ በሕዝብም ያለውን ደዌና ሕማም ሁሉ እየፈወሰ በገሊላ ሁሉ ይዞር ነበር።” (ማቴ.4፡23) ይህንም ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ትንቢት ተናግሮ ነበር፦

“... ተጨንቃ ለነበረች ጨለማ አይሆንም። በመጀመሪያው ዘመን የዛብሎንንና የንፍታሌምን ምድር አቃለለ፤ በኋለኛው ዘመን ግን በዮርዳኖስ ማዶ በባሕር መንገድ ያለውን የአሕዛብን ገሊላ ያከብራል። በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን አየ፤ በሞት ጥላ አገርም ለኖሩ ብርሃን ወጣላቸው።” (ኢሳ.9፥1-2)

የትንቢት ድምፅ

27 Nov, 18:41


ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ መክበሩ በአዳም በደል ምክንያት ከሰይጣን አገዛዝ ሥር መውደቃችን የተቀለበሰበት ለሰው ልጆች ሁሉ ታላቅ የምሥራች የሆነ ወሳኝ ኩነት ነው። ሞቱና ትንሣኤው ስለ እኛ እንደሆነ ሁሉ በእግዚአብሔር ቀኝ መቀመጡም ስለ እኛ ነው። እግዚአብሔር ከሙታን አሥነስቶ በቀኙ ሲያከብረው በአዳም መተላለፍ ጠንቅ ሁላችን ኃጢአተኞች ሆነን የእግዚአብሔር ክብር ጎድሎን የነበርነውን (ሮሜ.3፥23) በእርሱ በኩል ሊያከብረን ነው። “በአንዱ በደል ሞት በአንዱ በኩል ከነገሠ፥ ይልቁን የጸጋን ብዛትና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሣሉ” ይላል (ሮሜ.5፥17)።

“የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር ለማግኘት በወንጌላችን ጠራችሁ” ሲል (2ተሰ.2፥14) ክርስቶስ ከሙታን ተነሥቶ በእግዚአብሔር ቀኝ የተቀመጠበት የዚህ ታላቅ ክብር ተካፋዮች እንድትሆኑ ማለቱ ነው። ይህንም “... ከእርሱ ጋር አስነሣን በክርስቶስ ኢየሱስም በሰማያዊ ስፍራ ከእርሱ ጋር አስቀመጠን” በማለት ያረጋግጣል (ኤፌ.2፥6-7)።

የክርስትና ጉልበት ይህን በማወቅና አጥብቆ በመያዝ ነው። “እንግዲህ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ፥ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን እሹ። በላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም” ተብሏል (ቆላ.3፥1-2)።

እርሱን በማመን እስከ መጨረሻ ለሚጸኑት እስከ ሞት ድረስ ታማኝ ለሚሆኑት ጌታ ኢየሱስ የሰጣቸው ተስፋ የዚህ ክብሩ ተካፋዮች ሊያደርጋቸው ነው። “እኔ ደግሞ ድል እንደ ነሣሁ ከአባቴም ጋር በዙፋኑ ላይ እንደተቀመጥሁ፥ ድል ለነሣው ከእኔ ጋር በዙፋኔ ላይ ይቀመጥ ዘንድ እሰጠዋለሁ” ይላል (ራእ.3፥21)። በሌላም ስፍራ “ብንጸና፥ ከእርሱ ጋር ደግሞ እንነግሣለን” ይላል (2ጢሞ.2፥12)።

ለሰይጣን ያስገዛንን ኃጢአታችንን ክርስቶስ በመስቀል ላይ ከደመሰስ ወዲያ የሰይጣንን ሥልጣን ከዓለም ላይ ገፎታል። አሁን በዓለም ያለው የሰይጣን ሥልጣን ክርስቶስን ስላልተቀበሉ በሚጠፉት ልብ ላይ ነው። “ለእነርሱ የእግዚአብሔር ምሳሌ የሆነ የክርስቶስ የክብሩ ወንጌል ብርሃን እንዳያበራላቸው፥ የዚህ ዓለም አምላክ የማያምኑትን አሳብ አሳወረ።” (2ቆሮ.4፥4)

ኃጢአት ዕዳ ነው። ባለ ዕዳ ዕዳውን እስካልከፈለ ድረስ አበዳሪው በእርሱና የእርሱ በሆነው ነገር ላይ ሕጋዊ መብት አለው። መብቱንም ለማስከበር ለዳኛ ይከሰዋል። ሰይጣንም እንደዚሁ በኃጢአተኛ ላይ ሥልጣን አለው።

ክርስቶስ የሰውን የኃጢአት ዋጋ በሞቱ ከከፈለ ወዲያ ግን ሰይጣን በሰው ላይ ምንም መብት የለውም። ዳኛውም ለተከሳሽ ይፈርድለታል፤ ከሳሹንም ወደ ውጪ ያስወጣዋል። ስለዚህ ጌታ ኢየሱስ ሊሠዋ ወደ መስቀል ሲሄድ “አሁን የዚህ ዓለም ፍርድ ደርሶአል፤ አሁን የዚህ ዓለም ገዥ ወደ ውጭ ይጣላል” አለ (ዮሐ.12፥31)። የዮሐንስ ራእይ ደግሞ “... አሁን የአምላካችን ማዳንና ኃይል መንግሥትም የክርስቶስም ሥልጣን ሆነ፥ ቀንና ሌሊትም በአምላካችን ፊት የሚከሳቸው የወንድሞቻችን ከሳሽ ተጥሎአልና። እነርሱም ከበጉ ደም የተነሣ ከምስክራቸውም ቃል የተነሣ ድል ነሡት፥ ...” ይላል (ራእይ.12፥10-11)።

ይቀጥላል ...

የትንቢት ድምፅ

27 Nov, 18:40


(6) በእግዚአብሔር ቀኝ ይቀመጣል።

ከጌታ ኢየሱስ ጋር አብረው የኖሩ፥ የሞቱና የትንሣኤውም የዓይን እማኞች የሆኑ፥ ያዩትንም በወንጌላት ጽፈው ያስተላለፉልን ሐዋርያቱ ስለ እርሱ አጽንዖት ሰጥተው ከጻፏቸው ጉዳዮች አንዱ ከትንሣኤው በኋላ ወደ ሰማይ ዐርጎ “በእግዚአብሔር ቀኝ” መቀመጡ ነው። “ጌታ ኢየሱስ ከእነርሱ ጋር ከተናገረ በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ በእግዚአብሔርም ቀኝ ተቀመጠ” ይላል (ማር.16፥19)።

ሐዋርያቱ ራሳቸው ይህ ቃል የእነርሱና የመንፈስ ቅዱስ የምስክርነታቸው ማዕከል መሆኑን ይገልፃሉ፤ እንዲህ በማለት፦

“እናንተ በእንጨት ላይ ሰቅላችሁ የገደላችሁትን ኢየሱስን የአባቶቻችን አምላክ አስነሣው፤ ይህን እግዚአብሔር፥ ለእስራኤል ንስሐን የኃጢአትንም ስርየት ይሰጥ ዘንድ፥ ራስም መድኃኒትም አድርጎ በቀኙ ከፍ ከፍ አደረገው። እኛም ለዚህ ነገር ምስክሮች ነን፥ ደግሞም እግዚአብሔር ለሚታዘዙት የሰጠው መንፈስ ቅዱስ ምስክር ነው።” (ሐዋ.5፥30-32)

በተጨማሪም ጌታ ኢየሱስ በእግዚአብሔር ቀኝ ስለመቀመጡ የሚናገሩትን የሚከተሉትን ቃሎች እናገኛለን።

+ “የሞተው፥ ይልቁንም ከሙታን የተነሣው፥ በእግዚአብሔር ቀኝ ያለው፥ ደግሞ ስለ እኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው።” (ሮሜ.8፥34)

+ “እርሱ የክብሩ መንጸባረቅና የባሕርዩ ምሳሌ ሆኖ፥ ሁሉን በስልጣኑ ቃል እየደገፈ፥ ኃጢአታችንን በራሱ ካነጻ በኋላ በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀመጠ።” (ዕብ.1፥3)

+ “ከተናገርነውም ዋና ነገሩ ይህ ነው፤ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን።” (ዕብ.8፥1)

+ “እርሱ ስለ ኃጢአት አንድን መሥዋዕት ለዘላለም አቅርቦ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ፥ ጠላቶቹም የእግሩ መረገጫ እስኪደረጉ ድረስ ወደ ፊት ይጠብቃል።” (ዕብ.10፥12-13)

+ “... እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአል።” (ዕብ.12፥2)


ሁሉንም እዚህ አንዘረዝራቸውም። ነገር ግን ቀጥለን ስናወራ እንጠቅሳቸዋለን። ወንጌል ጌታ ኢየሱስ በእግዚአብሔር ቀኝ ስለመቀመጡ በእርግጥ እጅግ አብዝቶ እንደሚያወራ ታያላችሁ። እስከ ዛሬ አላስተዋላችሁም እንደሆን አሁን ታስተውላላችሁ። ደግሞም “ጉዳዩ የዚህን ያህል ትኩረት የተሰጠው ለምንድነው?” ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው።

ያለ ምክንያት አይደለም ሐዋርያት ለጉዳዩ አጽንዖት ሰጥተው እንዲህ እየደጋገሙ መናገራቸው። ሊያረጋግጡልን የፈለጉት ነገር አለ። የጉዳዩን ክብደት በእርሱ የማያምኑ አይሁድ እንኳ ያውቁታል።

የሕዝብ ሽማግሌዎች፣ የካህናት አለቆችና ጸሐፍት በሸንጓቸው “አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ?” ብለው ሲጠይቁት ጌታ ኢየሱስ “ከአሁን ጀምሮ የሰው ልጅ በእግዚአብሔር ኃይል ቀኝ ይቀመጣል” ብሎ ነበር የመለሰላቸው። እነርሱም “በእግዚአብሔር ላይ የስድብ ቃል ተናግሯል፤ ሞት ይገባዋል!” አሉ። (ማቴ.26፥63-68፣ ማር.14፥61-64፣ ሉቃ.22፥66-71)

እስጢፋኖስንም በድንጋይ የወገሩት ወደ ሰማይ ትኵር ብሎ ሲመለከት የእግዚአብሔርን ክብር እንዲሁም ኢየሱስ በእግዚአብሔር ቀኝ ቆሞ አይቶ “እነሆ፥ ሰማያት ተከፍተው የሰው ልጅም በእግዚአብሔር ቀኝ ቆሞ አያለሁ” ባለ ጊዜ ነበር (ሐዋ.7፥55-58)።

ስለ መሲሑ (ክርስቶስ) ከተነገሩት ትንቢቶች አንዱና ዋነኛው በእግዚአብሔር ቀኝ የሚቀመጥ መሆኑ ነው። ሐዋርያቱም ጌታ ኢየሱስ በእግዚአብሔር ቀኝ መቀመጡን በአጽንዖት የሰበኩትና የጻፉት እርሱ ክርስቶስ እንደሆነ ለማስረገጥ ነው፤ በተለይም ለአይሁድ።

ትንቢቱ ዳዊት በመዝሙሩ የተናገረው ነው። “እግዚአብሔር ጌታዬን ‘ጠላቶችህን ለእግርህ መቀመጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ’ አለው” ይላል (መዝ.110፥1)።

መንፈስ ቅዱስ በወረደ ጊዜ ሐዋርያው ጴጥሮስ ይህን ቃል ጠቅሶ ትንቢቱን ለኢየሩሳሌም ሰዎች እንዲህ ብሎ ተረጎመላቸው፦

“... በእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ ብሎና የመንፈስ ቅዱስን የተስፋ ቃል ከአብ ተቀብሎ ይህን እናንተ አሁን የምታዩትንና የምትሰሙትን አፈሰሰው። ዳዊት ወደ ሰማያት አልወጣምና፥ ነገር ግን እርሱ ‘ጌታ ጌታዬን፣ ጠላቶችህን የእግርህ መረገጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ አለው’ አለ። እንግዲህ ይህን እናንተ የሰቀላችሁትን ኢየሱስን እግዚአብሔር ጌታም ክርስቶስም እንዳደረገው የእስራኤል ወገን ሁሉ በእርግጥ ይወቅ።” (ሐዋ.2፥33-36)

በትንቢቱ መሠረት ክርስቶስ “ጠላቶቹን ሁሉ ከእግሩ በታች እስኪያደርግ ድረስ ሊነግሥ ይገባዋል። የኋለኛው ጠላት የሚሻረው ሞት ነው።” (1ቆሮ.15፥25-26) ይህም እርሱ ሲገለጥ በሚሆነው የሙታን ትንሣኤ ነው። ያን ጊዜ “‘ሞት በድል ተዋጠ’ ተብሎ የተጻፈው ቃል ይፈጸማል” ይላል (1ቆሮ.15፥54)።

“በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ” ማለት በአጭር ቃል ከእግዚአብሔር ጋር በዙፋኑ ላይ ተቀመጠ ማለት ነው፤ “እኔ ደግሞ ድል እንደ ነሣሁ ከአባቴም ጋር በዙፋኑ ላይ እንደተቀመጥሁ ...” ስለሚል (ራእ.3፥21)። ይህም በእግዚአብሔር ግዛት ሁሉ ላይ እርሱ ገዥ መሆኑን ያሳያል። ለዚህ ነው ከሙታን ሲነሣ “ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ” ማለቱ (ማቴ.28፥18)። ደግሞም “ሁሉን ወራሽ አደረገው” ይላል [ዕብ.1፥2]። “የፈቃዱን ምሥጢር አስታውቆናል” ይልና ይህ ምሥጢር ምን እንደሆነ ሲገልጽ “በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡ በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው” ይላል (ኤፌ.1፥10)። በአሁኑና በሚመጣው ዓለም ዙፋናት፣ ኃይላት፣ አለቆችና ሥልጣናት ሁሉ ከክርስቶስ ሥልጣን ሥር ተገዝተዋል።

“ክርስቶስን ከሙታን ሲያስነሣው ከአለቅነትና ከሥልጣንም ከኃይልም ከጌትነትም ሁሉ በላይና በዚህ ዓለም ብቻ ሳይሆን ነገር ግን ሊመጣ ባለው ዓለም ደግሞ ከሚጠራው ስም ሁሉ በላይ በሰማያዊ ስፍራ በቀኙ ሲያስቀምጠው በክርስቶስ ባደረገው ሥራ የብርታቱ ጉልበት ይታያል፤ ሁሉንም ከእግሩ በታች አስገዛለት ከሁሉ በላይም ራስ እንዲሆን ለቤተ ክርስቲያን ሰጠው።” (ኤፌ.1፥20-22)

በሌላም ስፍራ፣ “... እግዚአብሔር ያለ ልክ ከፍ ከፍ አደረገው፥ ከስምም ሁሉ በላይ ያለውን ስም ሰጠው፤ ይህም በሰማይና በምድር ከምድርም በታች ያሉት ሁሉ በኢየሱስ ስም ይንበረከኩ ዘንድ፥ መላስም ሁሉ ለእግዚአብሔር አብ ክብር ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታ እንደ ሆነ ይመሰክር ዘንድ ነው” ይላል (ፊልጲ.2፥9-11)።

ዙፋናት፣ ኃይላት፣ አለቆች፣ ሥልጣናትና ጌትነት የሚባሉት ዓለምን የሚቆጣጠሩ የመላእክት መዋቅርና ተዋረድ ናቸው። “እርሱ መላእክትና ሥልጣናት ኃይላትም ከተገዙለት በኋላ ወደ ሰማይ ሄዶ በእግዚአብሔር ቀኝ አለ” (1ጴጥ.3፥22)፤ ደግሞም “ከመላእክት ይልቅ እጅግ የሚበልጥ ስምን በወረሰ መጠን እንዲሁ ከእነርሱ አብዝቶ ይበልጣል” ይላል (ዕብ.1፥4)።

የትንቢት ድምፅ

25 Nov, 22:50


የተከበራችሁ የትንቢት ድምፅ ተከታታዮች መልእክቶቻችንን ጠቃሚ ሆነው ስላገኛችኋቸውና ቻናላችንን ስለተቀላቀላችሁ እናመሰግናለን። ሰብስክራይብ ያደረጋችሁን መልእክቶቻችንን ጠቃሚ ሆነው አግኝታችኋቸው ከሆነ ታዲያ መልእክቶቻችን ሲዘገዩና ቻናላችን ጭር ያለ ሲመስላችሁ በፍጹም ከቻናላችን ወጥታችሁ አንዳትሄዱ እንጠይቃችኋለን። ምን ጨነቃችሁ? አይቆጥርባችሁ። እኛ የእግዚአብሔርን ቃል ወደ እናንተ ለማድረስ መትጋትን ፈጽሞ አልተውንም፤ ወደፊትም አንተውም፤ ይልቁን እንጨምራለን እንጂ። ነገር ግን ከማያመቹ አንዳንድ ሁኔታዎች የተነሣ ነው መልእክቶችን ስናዘጋጅ ብዙ ጊዜ የምንዘገየው። ቢዘገይም ሲለጠፍ በሰዓቱ እንዲደርሳችሁ እስከ መጨረሻው አብራችሁን ቆዩ።

የትንቢት ድምፅ

07 Nov, 15:06


(5) ከሞት ሊነሣ ይገባዋል።

ዳዊት ትንሣኤውን አስቀድሞ አይቶ እንዲህ ሲል ስለ እርሱ ትንቢት ተናገረ፦

“ነፍሴን በሲኦል አትተዋትም፥ ቅዱስህንም መበስበስን ያይ ዘንድ አትሰጠውም።” (ሐዋ.2፥27)

እዚህ ላይ ዳዊት ስለ ራሱ አይደለም የሚናገረው። ዳዊትማ እንደ አባቶቹ ሁሉ ሞቶ፥ ተቀብሮ መበስበስን አይቷል።

“ዳዊት በራሱ ዘመን የእግዚአብሔርን አሳብ ካገለገለ በኋላ አንቀላፋ፥ ከአባቶቹም ጋር ተጨምሮ መበስበስን አየ፤ ይህ እግዚአብሔር ያስነሣው (ኢየሱስ) ግን መበስበስን አላየም።” (ሐዋ.13፥36-37)

ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ የዳዊት ዘር ነው፥ ዳዊት በትንቢት መንፈስ በዘሩ የሚሆነውን ነገር ተረድቶ፥ በዘሩ የሚሆነውን በራሱ እንደሚሆን አድርጎ፥ ስለ እርሱ የተናገረው። ሐዋርያው ጴጥሮስ እንዲህ ይላል፦

“ወንድሞች ሆይ፥ ስለ አባቶች አለቃ ስለ ዳዊት እንደ ሞተም እንደ ተቀበረም ለእናንተ በግልጥ እናገር ዘንድ ፍቀዱልኝ፤ መቃብሩም እስከ ዛሬ በእኛ ዘንድ ነው። ነቢይ ስለ ሆነ፥ ከወገቡም ፍሬ በዙፋኑ ያስቀምጥ ዘንድ እግዚአብሔር መሐላ እንደ ማለለት ስለ አወቀ፥ ስለ ክርስቶስ ትንሣኤ አስቀድሞ አይቶ፥ ነፍሱ በሲኦል እንዳልቀረች ሥጋውም መበስበስን እንዳላየ ተናገረ። ይህን ኢየሱስን እግዚአብሔር አስነሣው ለዚህም ነገር እኛ ሁላችን ምስክሮች ነን።” (ሐዋ.2፥29-32)

ቀድሞ ክርስቲያኖችን ያሳድድ የነበረው ሐዋርያው ጳውሎስም ክርስቶስ ተገልጦለት ካመነ በኋላ ወደ አይሁድ ምኵራብ እየገባ፥ “... ከእነርሱ ጋር ከመጻሕፍት እየጠቀሰ ይነጋገር ነበር፤ ሲተረጉምም ክርስቶስ መከራ እንዲቀበልና ከሙታን እንዲነሣ ይገባው ዘንድ እያስረዳ ‘ይህ እኔ የምሰብክላችሁ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ ነው’ ይል ነበር።” (ሐዋ.17፥1-3)

“እውነትን አምናችሁ እንድትድኑ መርጧችኋል” ሲል (2ተሰ.2፥13)፥ ይህን እውነት በማመን ማለቱ ነው። አንዳንዶች ሞቱ ኃጢአታችንን ለማስተስርየት የግድ እንደሚያስፈልግ ስላልተረዱ ክርስቶስ የእውነት መሞቱን አያምኑም። ሌሎች ደግሞ ሙታን እንደሚነሡ ስለማያምኑ ክርስቶስም ከሞት መነሣቱን አያምኑም። ወንጌሉ ግን እንዲህ ይላል፦

“... በልብህ ‘ማን ወደ ሰማይ ይወጣል’ አትበል፤ ይህ ክርስቶስን ለማውረድ ነው፤ ወይም በልብህ ‘ወደ ጥልቁ ማን ይወርዳል’ አትበል፤ ይህ ክርስቶስን ከሙታን ለማውጣት ነው። ነገር ግን ምን ይላል በአፍህ በልብህም ሆኖ ቃሉ ቀርቦልሃል፤ ይህም የምንሰብከው የእምነት ቃል ነው። ኢየሱስ ጌታ እንደ ሆነ በአፍህ ብትመሰክር እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳስነሣው በልብህ ብታምን ትድናለህና፤ ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይድናልና።” (ሮሜ.10፥6-10)

ይቀጥላል ...

የትንቢት ድምፅ

07 Nov, 15:04


(3) ሰውን ከዲያብሎስ አገዛዝ ነጻ እንዲያወጣ በእግዚአብሔር የተቀባ አዳኝ ነው።

በዕብራይስጥ “መሲሕ” በግሪክ ደግሞ “ክርስቶስ” ትርጉሙ “የተቀባው” ማለት ነው። በኃጢአቱ ጠንቅ ለሰይጣን አልፎ የተሰጠውን ሰው ከሰይጣን አገዛዝ ነጻ እንዲያወጣ ነው የተቀባው። “እግዚአብሔር የናዝሬቱን ኢየሱስን በመንፈስ ቅዱስ በኃይልም ቀባው፥ እርሱም መልካም እያደረገ ለዲያብሎስም የተገዙትን ሁሉ እየፈወሰ ዞረ፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነበረና” ይላል (ሐዋ.10፥38)።

ጌታ ኢየሱስም ከነቢዩ ኢሳይያስ መጽሐፍ ጠቅሶ እንዲህ አለ፦

“የጌታ መንፈስ በእኔ ላይ ነው፥ ለድሆች ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ቀብቶኛልና፤ ለታሰሩትም መፈታትን ለዕውሮችም ማየትን እሰብክ ዘንድ፥ የተጠቁትንም ነጻ አወጣ ዘንድ የተወደደችውንም የጌታን ዓመት እሰብክ ዘንድ ልኮኛል።”

ከዚያም “ዛሬ ይህ መጽሐፍ በጆሮአችሁ ተፈጸመ!” በማለት ትንቢቱ የተነገረለት እግዚአብሔር የቀባው ነጻ አውጪ እርሱ ራሱ መሆኑን በምኵራብ ለተሰበሰቡት ገለጠላቸው (ሉቃ.4፥16-21)።

በተወለደ ጊዜ፦

“እነሆም፥ በኢየሩሳሌም ስምዖን የሚባል ሰው ነበረ፥ ይህም ሰው የእስራኤልን መጽናናት ይጠባበቅ ነበር፤ ጻድቅና ትጉህም ነበረ፥ መንፈስ ቅዱስም በእርሱ ላይ ነበረ። በጌታም የተቀባውን ሳያይ ሞትን እንዳያይ በመንፈስ ቅዱስ ተረድቶ ነበር። በመንፈስም ወደ መቅደስ ወጣ፤ ወላጆቹም እንደ ሕጉ ልማድ ያደርጉለት ዘንድ ሕፃኑን ኢየሱስን በአስገቡት ጊዜ፥ እርሱ ደግሞ ተቀብሎ አቀፈው እግዚአብሔርንም እየባረከ እንዲህ አለ፥ ‘ጌታ ሆይ፥ አሁን እንደ ቃልህ ባሪያህን በሰላም ታሰናብተዋለህ፤ ዓይኖቼ በሰዎች ሁሉ ፊት ያዘጋጀኸውን ማዳንህን አይተዋልና፤ ይህም ለአሕዛብ ሁሉን የሚገልጥ ብርሃን ለሕዝብህም ለእስራኤል ክብር ነው።’” (ሉቃ.2፥25-32)

በሥጋና በደም የመካፈሉ (ሰው የመሆኑ) ዓላማም ይኸው ነው፤ ሰውን ነጻ ማውጣት።

“... ልጆቹ በሥጋና በደም ስለሚካፈሉ፥ እርሱ ደግሞ በሞት ላይ ሥልጣን ያለውን በሞት እንዲሽር፥ ይኸውም ዲያብሎስ ነው፥ በሕይወታቸውም ሁሉ ስለ ሞት ፍርሃት በባርነት ይታሰሩ የነበሩትን ሁሉ ነጻ እንዲያወጣ፥ በሥጋና በደም እንዲሁ ተካፈለ።” (ዕብ.2፥14-15)

(4) ከመክበሩ በፊት የሞትን መከራ መቀበል ይገባዋል።

ጌታ ኢየሱስ፥ “ሙሴ በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ እንዲሁ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ የሰው ልጅ (መሲሕ) ይሰቀል ይገባዋል” አለ (ዮሐ.3፥14-15)።

የመሲሑን መምጣት ሲጠባበቁ የነበሩ አንዳንድ አይሁድ ግን ይህን አያውቁም ነበር። “እኛስ ክርስቶስ ለዘላለም እንዲኖር ከሕጉ ሰምተናል፤ አንተስ የሰው ልጅ ከፍ ከፍ ይል ዘንድ (ሊሰቀል) እንዲያስፈልገው እንዴት ትላላህ? ይህ የሰው ልጅ ማን ነው?” አሉት (ዮሐ.12፥34)።

ደቀ መዛሙርቱም ይህን ባለማወቃቸው ነበር አልፎ በተሰጠ ጊዜ የተሰናከሉበት። ኢየሱስ መሲሑ መሆኑን ምንም ቢያምኑም መሲሑ ከመንገሡ በፊት ስለ ሰው ኃጢአት ሊሞት እንደሚገባው ስላላወቁ ተሰቅሎ ሲሞት ሲያዩ ተስፋ ቆረጡ። “እኛ ግን እስራኤልን ይቤዣል ብለን ተስፋ ያደረግነው እርሱን ነበር” አሉ። ስለዚህ፣ ጌታ ኢየሱስ ከሞት ሲነሣ እንዲህ አላቸው፦ “እናንተ የማታስተውሉ፥ ነቢያትም የተናገሩትን ሁሉ ልባችሁ ከማመን የዘገየ፤ ክርስቶስ ይህን መከራ ይቀበል ዘንድና ወደ ክብሩ ይገባ ዘንድ ይገባው የለምን?” (ሉቃ.24፥13-27)።

ደግሞም፣ እንዲህ አላቸው፦

“... ከእናንተ ጋር ሳለሁ በሙሴ ሕግና በነቢያት በመዝሙራትም ስለ እኔ የተጻፈው ሁሉ ይፈጸም ዘንድ ይገባል ብዬ የነገርኋችሁ ቃሌ ይህ ነው ... ‘ክርስቶስ መከራ ይቀበላል በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ይነሣል፥ በስሙም ንስሐና የኃጢአት ስርየት ከኢየሩሳሌም ጀምሮ በአሕዛብ ሁሉ ይሰበካል’ ተብሎ እንዲሁ ተጽፎአል። እናንተም ለዚህ ምስክሮች ናችሁ።” (ሉቃ.24፥44-47)

ስለ መከራው ከተነገሩ ቃሎች መካከል ሁላችን የምናውቀው የሚከተለው የነቢዩ ኢሳይያስ ትንቢት ዋነኛው ነው።

“በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ ሕመማችንንም ተሸክሞአል፤ ... ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ፤ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን። እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፤ እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ። ... እግዚአብሔር በደዌ ያደቅቀው ዘንድ ፈቀደ፤ ነፍሱን ስለ ኃጢአት መሥዋዕት ካደረገ በኋላ ዘሩን ያያል፥ ዕድሜውም ይረዝማል፥ የእግዚአብሔርም ፈቃድ በእጁ ይከናወናል። ከነፍሱ ድካም ብርሃን ያያል ደስም ይለዋል፤ ጻድቅ ባሪያዬም በእውቀቱ ብዙ ሰዎችን ያጸድቃል፥ ኃጢአታቸውን ይሸከማል። ስለዚህም እርሱ ብዙዎችን ይወርሳል፥ ከኃያላንም ጋር ምርኮን ይከፋፈላል፤ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ሰጥቶአልና፥ ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና፤ እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ።” (ኢሳ.53፥4-6)

ከመከራው ወዲያ ግን፥ “በእግዚአብሔር ጸጋ ስለ ሰው ሁሉ ሞትን ይቀምስ ዘንድ፥ ከመላእክት ይልቅ በጥቂት አንሶ የነበረውን ኢየሱስን ከሞት መከራ የተነሣ የክብርና የምስጋናን ዘውድ ተጭኖ እናየዋለን” ይላል (ዕብ.2፥9)።

የትንቢት ድምፅ

29 Oct, 18:59


ክርስቶስ (መሲሕ) ማን ነው?

ኢየሱስ፥ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑ፥ አዳኝነቱ፥ ስለ ኃጢአታችን መሞቱና መነሣቱ፥ ክህነቱ፥ የዘላለም አምላክነቱ (ገዥነቱ) እና ፈራጅነቱ፥ በዚህ አንድ ቃል “እርሱ ክርስቶስ ነው” በሚለው ተጠቃለዋል።

ምክንያቱም፣ ክርስቶስ (ትንቢቱ በተነገረበት በዕብራይስጥ ቋንቋ “መሲሕ”) እነዚህን ሁሉ እንደሆነ (ወይም እንደሚሆን) በቅዱሳን መጻሕፍት በሕግና በነቢያት ተጽፏል።

ጌታ ኢየሱስ፣ አይሁድን “እናንተ በመጻሕፍት የዘላለም ሕይወት እንዳላችሁ ይመስላችኋልና እነርሱን ትመረምራላችሁ፤ እነርሱም ስለ እኔ የሚመሰክሩ ናቸው” አላቸው (ዮሐ.5፥39)።

የወንጌልም ዓላማ በቅዱሳን መጻሕፍት ስለ ክርስቶስ የተነገረው ሁሉ ፍጻሜ ጌታ ኢየሱስ መሆኑን ለሰዎች መግለጥ ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ ወንጌሉን የጻፈበትን ምክንያት ሲናገር “... ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ ታምኑ ዘንድ፥ አምናችሁም በስሙ ሕይወት ይሆንላችሁ ዘንድ ይህ ተጽፎአል” ይላል (ዮሐ.20፥31)።

ዕጣ ፈንታችንን፥ መዳን አለመዳናችንን የሚበይን ይህ እምነት ነው። “ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ በሚታመን ሁሉ እግዚአብሔር በእርሱ ይኖራል እርሱም በእግዚአብሔር ይኖራል” (1ዮሐ.4፥15)፥ ደግሞም “ክርስቶስ ነው ብሎ በኢየሱስ የሚያምን ሁሉ ከእግዚአብሔር ተወልዶአል” ይላል (1ዮሐ.5፥1)።

በአንጻሩ ደግሞ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ መሆኑን አለማመን ኃጢአት ነው፤ ያውም ሞትን የሚያመጣ ኃጢአት። የማያምኑትን “እኔ እንደሆንሁ ባታምኑ በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁ” ይላቸዋል (ዮሐ.8፥24)።

በቅዱሳን መጻሕፍት ስለ ክርስቶስ የሚከተሉት ተጽፈዋል።

(1) የእግዚአብሔር ልጅ ነው።

“... እግዚአብሔር አለኝ፥ ‘አንተ ልጄ ነህ፥ እኔ ዛሬ ወለድሁህ።’” (መዝ.2፥7) በመዝሙረ ዳዊት የሚገኘው ይህ ቃል ስለ መሲሑ የተነገረ መሆኑን ሐዋርያው እንዲህ እያለ ይገልጣል፦

“... ለአባቶች የተሰጠውን ተስፋ የምስራቹን ለእናንተ እንሰብካለን፤ ይህን ተስፋ እግዚአብሔር በሁለተኛው መዝሙር ደግሞ፥ ‘አንተ ልጄ ነህ፥ እኔ ዛሬ ወለድሁህ’ ተብሎ እንደ ተጻፈ፥ ኢየሱስን አስነሥቶ ለእኛ ለልጆቻቸው ፈጽሞአልና። እንደገናም ወደ መበስበስ እንዳይመለስ ከሙታን እንደ አስነሣው፥ እንዲህ፥ ‘የታመነውን የዳዊትን ቅዱስ ተስፋ እሰጣችኋለሁ’ ብሎአል።” (ሐዋ.13፥32-34)

(2) እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠው ተስፋ ፍጻሜ ነው።

እግዚአብሔር አብርሃምን “የምድር አሕዛብ ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ፥ ቃሌን ሰምተሃልና” አለው (ዘፍ.22፥18)። “ዘርህ” የሚለው ክርስቶስን ነው። የምድር ሕዝቦች ሁሉ የሚድኑበት መሲሕ በሥጋ ከአብርሃም ዘር እንደሚወለድ ይገልጣል። “ለአብርሃምና ለዘሩ የተስፋው ቃል ተነገረ። ስለ ብዙዎች እንደሚነገር፥ ‘ለዘሮቹም’ አይልም፤ ስለ አንድ እንደሚነገር ግን፥ ‘ለዘርህም’ ይላል፥ እርሱም ክርስቶስ።” (ገላ.3፥16)

ለአሕዛብ የመጣላቸው ይህ በረከት “ወተትና ማር የምታፈስስ ምድር” ሳይሆን በክርስቶስ በማመን የሚገኘው ጽድቅና የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ነው።

“መጽሐፍ እግዚአብሔር አሕዛብን በእምነት እንዲያጸድቅ አስቀድሞ አይቶ። ‘በአንተ አሕዛብ ሁሉ ይባረካሉ’ ብሎ ወንጌልን ለአብርሃም አስቀድሞ ሰበከ። እንደዚህ ከእምነት የሆኑት ካመነው ከአብርሃም ጋር ይባረካሉ። ... የመንፈስን ተስፋ በእምነት እንድንቀበል፥ የአብርሃም በረከት ወደ አሕዛብ በኢየሱስ ክርስቶስ ይደርስላቸው ዘንድ። ... እናንተም የክርስቶስ ከሆናችሁ እንኪያስ የአብርሃም ዘር እንደ ተስፋውም ቃል ወራሾች ናችሁ።” (ገላ.3፥8-29)

ብሉይ ኪዳን እስራኤልን ለእግዚአብሔር ቅዱስ ሕዝብ አድርጎ የቀሩትን የምድር ሕዝቦች ያገለለ ነበረ። “እኔ እግዚአብሔር ቅዱስ ነኝና፥ ለእኔም ትሆኑ ዘንድ ከአሕዛብ ለይቻችኋለሁና ቅዱሳን ትሆኑልኛላችሁ” ነበር ያላቸው (ዘሌ.20፥26)።

ክርስቶስ ግን ይህን ልዩነት አስቀርቶ አሕዛብን ከእስራኤል ጋር የተስፋውን ቃል ወራሾች አድርጓቸዋል። “... ታርደሃልና፥ በደምህም ለእግዚአብሔር ከነገድ ሁሉ ከቋንቋም ሁሉ ከወገንም ሁሉ ከሕዝብም ሁሉ ሰዎችን ዋጅተህ ለአምላካችን መንግሥትና ካህናት ይሆኑ ዘንድ አደረግሃቸው ...” ይሉታል (ራእ.5፥9-10)።

ሐዋርያውም የኤፌሶንን ቅዱሳን እንዲህ ይላቸዋል፦

“... እናንተ አስቀድሞ በሥጋ አሕዛብ የነበራችሁ፥ በሥጋ በእጅ የተገረዙ በተባሉት ያልተገረዙ የተባላችሁ፥ ይህን አስቡ፤ በዚያ ዘመን ከእስራኤል መንግሥት ርቃችሁ ለተስፋውም ቃል ኪዳን እንግዶች ሆናችሁ በዚህም ዓለም ተስፋን አጥታችሁ ከእግዚአብሔርም ተለይታችሁ ያለ ክርስቶስ ነበራችሁ። አሁን ግን እናንተ በፊት ርቃችሁ የነበራችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆናችሁ በክርስቶስ ደም ቀርባችኋል። እርሱ ሰላማችን ነውና፤ ሁለቱን ያዋሐደ በአዋጅ የተነገሩትንም የትእዛዛትን ሕግ ሽሮ በመካከል ያለውን የጥል ግድግዳን በሥጋው ያፈረሰ፤ ይህም ከሁለታቸው አንድን አዲስን ሰው በራሱ ይፈጥር ዘንድ ሰላምንም ያደርግ ዘንድ፥ ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን በአንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋር ያስታርቅ ዘንድ ነው። መጥቶም ርቃችሁ ለነበራችሁ ለእናንተ ሰላምን፥ ቀርበው ለነበሩትም ሰላምን የምስራች ብሎ ሰበከ፤ በእርሱ ሥራ ሁላችን በአንድ መንፈስ ወደ አብ መግባት አለንና። እንግዲያስ ከእንግዲህ ወዲህ ከቅዱሳን ጋር ባላገሮችና የእግዚአብሔር ቤተ ሰዎች ናችሁ እንጂ እንግዶችና መጻተኞች አይደላችሁም።” (ኤፌ.2፥11-19)

የትንቢት ድምፅ

24 Oct, 17:53


ለ: nigus

በዕብራይስጥ “መሲሕ” በግሪክ ደግሞ “ክርስቶስ” ትርጉሙ “የተቀባው” ማለት ነው።

ነገር ግን ጥያቄህ “‘የተቀባ ብቻ ነው’ ለማለት ነው?” የሚል ነው?

አይደለም! “የተቀባ ብቻ ነው” አይልም። ከየት አመጣኸው?

“ኢየሱስ የተቀባ ብቻ ነው” የሚሉ “እርሱ ሰው ብቻ ነው፤ መለኮት አይደለም” ማለታቸው ነው። ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ መለኮት እና እውነተኛ ሰው እንጂ ሰው ብቻ ወይም መለኮት ብቻ አይደለም። ለዚህ “በሥጋ የተገለጠ መለኮት” እንዲሁም “ሰው የሆነ ክርስቶስ” የሚሉትን መልእክቶች አንብብ።

የኢየሱስ ክርስቶስን መለኮትነት ሐዋርያው በሚከተለው ቃል ያረጋግጣል።

“እርሱም የማይታይ አምላክ ምሳሌ ነው። የሚታዩትና የማይታዩትም፥ ዙፋናት ቢሆኑ ወይም ጌትነት ወይም አለቅነት ወይም ሥልጣናት፥ በሰማይና በምድር ያሉት ሁሉ በእርሱ ተፈጥረዋልና ከፍጥረት ሁሉ በፊት በኵር ነው። ሁሉ በእርሱና ለእርሱ ተፈጥሮአል። እርሱም ከሁሉ በፊት ነው ሁሉም በእርሱ ተጋጥሞአል።” (ቆላ.1፥15-17)

ቀቢ እግዚአብሔር ተቀቢ ደግሞ ሰው ነው። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም የተቀባው በሰውነቱ ነው። እርሱ መለኮትም ሰውም መሆኑን ካወቅን “የተቀባ” መሆኑ ጥያቄ አይፈጥርብንም። እግዚአብሔርን (አብን) ለማገልገል ዝቅ ብሎ ራሱን ባዶ አድርጎ ሰው ሆኖ የመጣ እንደመሆኑ (ፊልጲ.2፥6-8) የእግዚአብሔርን ሥራ ለመሥራት በእግዚአብሔር መንፈስ መቀባት ነበረበት።

ለአንዳንዶች ግን የተቀባው መለኮት ባይሆን ይመስላቸዋል። ዳሩ ግን መቀባቱ ሰው የመሆኑን እውነታ ያረጋግጣል እንጂ መለኮት አለመሆንን አያሳይም።

“ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ ነው!” ማለት በአጭሩ እግዚአብሔር ሊልክልን ተስፋ ሰጥቶን የነበረው ነቢያትም ትንቢት የተናገሩለት ወደ ዓለም የሚመጣው መድኃኒት (ክርስቶስ) እርሱ እንደሆነ የሚያረጋግጥ ቃል ነው። ለአብነት ያህል፦ ደቀ መዛሙርቱ “መሲሕን አግኝተናል ... ፤ ትርጓሜውም ክርስቶስ ማለት ነው። ሙሴ በሕግ ነቢያትም ስለ እርሱ የጻፉትን የናዝሬቱን ኢየሱስን አግኝተነዋል” አሉ (ዮሐ.1፥35-52)። እንዲሁም ማርታ “... ጌታ ሆይ፤ አንተ ወደ ዓለም የሚመጣው ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆንህ እኔ አምናለሁ” አለችው (ዮሐ.11፥27)።

የማያምኑ አይሁድ የሚቃወሙት ይህንኑ ነው። “‘እርሱ ክርስቶስ ነው’ ብሎ የሚመሰክር ቢኖር ከምኵራብ እንዲያወጡት አይሁድ ከዚህ በፊት ተስማምተው ነበር” ይላል (ዮሐ.9፥22)።

ጳውሎስ ግን ክርስቶስ ከተገለጠለት በኋላ፦

“ወዲያውም ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ በምኵራቦቹ ሰበከ። ... በደማስቆም ለተቀመጡት አይሁድ ይህ ክርስቶስ እንደ ሆነ አስረድቶ መልስ ያሳጣቸው ነበር።” (ሐዋ.9፥20-22)

“በአንፊጶልና በአጶሎንያም ካለፉ በኋላ ወደ ተሰሎንቄ መጡ፥ በዚያም የአይሁድ ምኵራብ ነበረ። ጳውሎስም እንደ ልማዱ ወደ እነርሱ ገባ፥ ሦስት ሰንበትም ያህል ከእነርሱ ጋር ከመጻሕፍት እየጠቀሰ ይነጋገር ነበር፤ ሲተረጉምም ክርስቶስ መከራ እንዲቀበልና ከሙታን እንዲነሣ ይገባው ዘንድ እያስረዳ ‘ይህ እኔ የምሰብክላችሁ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ ነው’ ይል ነበር።” (ሐዋ.17፥1-3)

የትንቢት ድምፅ

21 Oct, 19:04


ራሳችንን ብንመረምር ባልተፈረደብን ነበር

ክርስቲያን ንስሐ መግባት አያስፈልገውም ወይም ንስሐ አይገባም የሚል የተሳሳተ ትምህርት አለ።

ሰው አንዴ በክርስቶስ በማመን ከጸደቀ ወዲህ እንደገና ንስሐ ይገባል ማለት ጸድቆ የነበረውን መልሶ ኃጢአተኛ ማድረግ (እንደ ኃጢአተኛ መቁጠር) ነው የሚል ነው ምክንያታቸው።

ነገር ግን፣ ሁለት የንስሐ ዓይነቶች አሉ።

የመጀመሪያው ንስሐ፣ ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት የታረቅንበት (ሮሜ.5፥10)፥ ከሰይጣን አገዛዝ ወደ እግዚአብሔር የዞርንበት፥ ከእግዚአብሔርም ጋር በክርስቶስ ደም አማካኝነት ኪዳን ያደረግንበት ነው።

ጌታ ኢየሱስ ጳውሎስን ሐዋርያ አድርጎ ወደ አሕዛብ የሚልክበትን ምክንያት ሲገልፅለት “የኃጢአትን ስርየት በእኔም በማመን በተቀደሱት መካከል ርስትን ያገኙ ዘንድ፥ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሰይጣንም ሥልጣን ወደ እግዚአብሔር ዘወር እንዲሉ” አለው (ሐዋ.26፥17-18)።

ይህ የንስሐ ጥሪ ለሰዎች ሁሉ የቀረበ ነው።

“... እግዚአብሔር ያለማወቅን ወራት አሳልፎ አሁን በየቦታቸው ንስሐ ይገቡ ዘንድ ሰውን ሁሉ ያዛል፤ ቀን ቀጥሮአልና፥ በዚያም ቀን ባዘጋጀው ሰው እጅ በዓለሙ ላይ በጽድቅ ሊፈርድ አለው፤ ስለዚህም እርሱን ከሙታን በማስነሣቱ ሁሉን አረጋግጦአል።” (ሐዋ.17፥30-31)

ይኼኛው ንስሐ አንዴ ነው። ሰው አንዴ በክርስቶስ ከሆነ በኋላ በፈረቃ አንዴ በክርስቶስ አንዴ በዓለም መሆን አይችልም።

ነገር ግን፣ ሰው በክርስቶስ ሳለ ኃጢአትን ቢያደርግ ወይም ለክርስቲያን የማይገባ ኑሮ የሚኖር ከሆነ መታረም አለበት። ሁለተኛው የንስሐ ዓይነት እሱ ነው። ይኼኛው ንስሐ የሚደረገው አንድ ጊዜ ብቻ አይደለም። ስላደረግነው ነገር የእግዚአብሔር ቃልና መንፈስ ቅዱስ በሚገስጹን ሕሊናችንም በሚወቅሰን ነገር ሁሉ በማንኛውም ጊዜ ንስሐ መግባት ይኖርብናል።

እዚህ ላይ መረሳት የሌለበት፣ ንስሐ ጸሎት አይደለም። ንስሐ ከተሳሳተ አካሄድ መመለስ ስሕተትን ማረም ነው። “... ንስሐ ግቡ ኃጢአትም ዕንቅፋት እንዳይሆንባችሁ ከኃጢአታችሁ ሁሉ ተመለሱ” ነው የሚለው (ሕዝ.18፥30)።

ንስሐ፣ ሰው በሕሊናው ተወቅሶ ስሕተቱን አምኖ ክፉ ሥራውን ለመተው ሲወስን ነው እንጂ እንዲሁ “እኔ ኃጢአተኛ ነኝ፤ ማረኝ” እያሉ መጸለይን ልማድ ማድረግ አይደለም።

በእርግጥ የንስሐ ጸሎት አለ፤ ሰው ኃጢአቱን ለእግዚአብሔር የሚናዘዝበትና ምሕረትን የሚለምንበት። ነገር ግን፣ ከክፉ ሥራው መመለሱ እንጂ ጸሎቱ አይደለም ንስሐ።

ስለዚህ ንስሐ በግልፅ የሚታይ ተጨባጭ ፍሬ ያለው ነው፤ ምናባዊ አይደለም። ስለ ነነዌ ሰዎች ንስሐ ሲናገር “እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸው እንደተመለሱ ሥራቸውን አየ” ይላል (ዮና.3፥10)።

አንድ ክርስቲያን ንስሐ ያስፈልገዋል ማለት ክርስትናው ተሽሯል በክርስቶስ ያለውን ማንነት አጥቷል ማለት አይደለም። ነገር ግን፣ ዓላማውን ስቷል፥ ስለዚህ አካሄዱን ማስተካከል አለበት ማለት ነው።

እግዚአብሔር ያለ ሥራ በጸጋው አድኖናል ማለት ኃጢአት እንድንሠራ ተፈቅዶልናል ማለት አይደለም። ጸጋው ከኵነኔ ነው ነጻ ያወጣን፤ ጽድቅን ከማድረግ ግዴታ ነጻ አላደረገንም። ይልቁን ጽድቅን ማድረግ የተፈጠርንበት ዓላማ እና በምድር እንድንፈጽመው የተሰጠን ተልእኮአችን ነው። “እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን” ነው የሚለው (ኤፌ.2፥10)።

ደግሞም “ሰዎችን ሁሉ የሚያድን የእግዚአብሔር ጸጋ ተገልጦአል፤ ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል” ይላል (ቲቶ.2፥11-14)።

ክርስቲያን ከዚህ ዓላማ አንፃር ነው አካሄዱን መመርመርና መንገዱን ስቶ ሲገኝ መታረም ያለበት። ክርስቲያን ንስሐ አያስፈልገውም ከተባለ ግን ቢሳሳትም አይታረምም ማለት ነው። ይህ ትክክል እንዳልሆነ ግልጥ ነው።

በአዲስ ኪዳን በብዙ ስፍራ ለቤተክርስቲያንና ለምዕመናን ንስሐ እንዲገቡ የእግዚአብሔር ቃል ይናገራል። ይህም ንስሐ ላልዳኑ ሰዎች ብቻ እንዳልሆነ ነው የሚያሳየው።

ለምሳሌ፣ ሲሞን በፊት ጠንቋይ የነበረ ኋላ ግን በሐዋርያው ፊልጶስ ስብከት በጌታ አምኖ የተጠመቀ አዲስ ክርስቲያን ነበረ። ነገር ግን የእግዚአብሔርን ጸጋ ከሐዋርያት በገንዘብ ለመግዛት በፈለገ ጊዜ ሐዋርያው ጴጥሮስ “የእግዚአብሔርን ስጦታ በገንዘብ እንድታገኝ አስበሃልና ብርህ ከአንተ ጋር ይጥፋ። ልብህ በእግዚአብሔር ፊት የቀና አይደለምና ከዚህ ነገር ዕድል ወይም ፈንታ የለህም” አለውና ንስሐ እንዲገባ መከረው። “እንግዲህ ስለዚህ ክፋትህ ንስሐ ግባ፥ ምናልባትም የልብህን አሳብ ይቅር ይልህ እንደ ሆነ ወደ እግዚአብሔር ለምን፤ በመራራ መርዝና በዓመፅ እስራት እንዳለህ አይሃለሁና” አለው (ሐዋ.8፥20-23)። ይህ ለክርስቲያን የተነገረ ቃል መሆኑን እናስተውል።

በዮሐንስ ራእይ ደግሞ ከሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት አምስቱን ጌታ ንስሐ እንዲገቡ ሲያስጠነቅቃቸው እናያለን (ራእ.2-3)።

በመሆኑም ክርስቲያን ንስሐ መግባት አያስፈልገውም የሚለው ትምህርት ምዕመኑን ይጎዳዋል። ምክንያቱም፣ እግዚአብሔር ሥራችንን ሁሉ ወደ ፍርድ ማምጣቱ አይቀርም።

“አትሳቱ፤ እግዚአብሔር አይዘበትበትም። ሰው የሚዘራውን ሁሉ ያንኑ ደግሞ ያጭዳልና፤ በገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና፥ በመንፈስ ግን የሚዘራው ከመንፈስ የዘላለምን ሕይወት ያጭዳል።” (ገላ.6፥7-8)

ራስን መመርመርና ማረም ይጠቅማል፤ “እንደ ቆመ የሚመስለው እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ” (1ቆሮ.10፥12)፣ ደግሞም “ራሳችንን ብንመረምር ግን ባልተፈረደብን ነበር” ይላል (1ቆሮ.11፥31)።

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

10 Oct, 21:08


[10] ኢየሱስ ክርስቶስ በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ በይፋ ዳግመኛ ይመጣል።

የዘላለም ፍርድ ከክርስትና መሠረታዊ እምነቶች አንዱ ነው (ዕብ.6፥2)። ይህም እግዚአብሔር በሕይወት ዘመናችን የሠራነውን ሁሉ ወደ ፍርድ የሚያመጣው መሆኑና እያንዳንዳችን ላደረግነው ነገር ሁሉ ተጠያቂ መሆናችን ነው። “... እያንዳንዳችን ስለ ራሳችን ለእግዚአብሔር መልስ እንሰጣለን።” (ሮሜ.14፥12) ስለተናገርነው ነገር ጭምር እንጂ ስላደረግነው ነገር ብቻ አይደለም። ጌታ ኢየሱስ “... ሰዎች ስለሚናገሩት ስለ ከንቱ ነገር ሁሉ በፍርድ ቀን መልስ ይሰጡበታል” ይላል (ማቴ.12፥36)። ይህን ያወቀ አፉ እንዳመጣለት አይናገርም።

የሚፈርደው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ዳግመኛ ሲመጣ ሙታን ተነሥተው በሕይወት ካሉት ጋር ከእርሱ ፍርድን ይቀበላሉ። “የሰው ልጅ በአባቱ ክብር ከመላእክት ጋር ይመጣል፤ ለእያንዳንዱም ሰው እንደ ሥራው ዋጋውን ይከፍለዋል።” (ማቴ.16፥27/አ.መ.ት.)

ክርስቶስ ዳግመኛ የሚመጣው በይፋ መሆኑ ይሰመርበት። ዳግመኛ መምጣቱ እንደ ልደቱ አይሆንም። ክርስቶስ መወለዱ ለጥቂቶች ማለትም ከምሥራቅ ለመጡት ጠቢባን፣ ለእረኞችና ለተመረጡ ቅዱሳን ብቻ ነበር የተገለጠላቸው። ለሕዝብ ሲገለጥም እርሱ ክርስቶስ መሆኑን ያወቁና ያመኑ ውሱን ነበሩ።

ዳግመኛ ሲመጣ ግን ፀሐይ በሰማይ ላይ ስታበራ ለዓለም ሁሉ እንደምትታይ ሰዎች ሁሉ ያዩታል። በመላእክት አጀብ በብዙ ክብር ስለሚመጣ ጌትነቱን የማያይ አይኖርም፤ ተቃዋሚዎቹ ሳይቀሩ። “እነሆ፥ ከደመና ጋር ይመጣል፤ ዓይንም ሁሉ የወጉትም ያዩታል፥ የምድርም ወገኖች ሁሉ ስለ እርሱ ዋይ ዋይ ይላሉ ...” ይላል (ራእ.1፥7)። በዚህም ምክንያት ዳግም ምጽአቱ “የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ክብር መገለጥ” ተብሏል (ቲቶ.2፥13)።

ክርስቶስ በማይታይ ሁኔታ ከዚህ በፊት ዳግመኛ መጥቷል የሚሉ ሐሰተኛ ትምህርቶችና ሃይማኖቶች ስላሉ ዳግመኛ መምጣቱ በይፋ እንደሚሆን ማወቅ ምዕመኑን ከስሕተት ይጠብቀዋል።

[11] ሰው ሁሉ ኃጢአተኛና ራሱን ማዳን የማይችል ነው።

ሰው አስቀድሞ ኃጢአተኛና ከእግዚአብሔር ፍርድ በታች የሚገኝ፥ ከዚያም ፍርድ በክርስቶስ ቤዛነት አማካኝነት ነጻ መውጣት የሚያስፈልገው ነው። “ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል።” (ሮሜ.3፥23)

ሰው ኃጢአተኛና ራሱን ማዳን የማይችል በመሆኑ ነው ክርስቶስ እንዲቤዠው ግድ የሆነው። ሰው ኃጢአት ባይኖርበት ወይም ደግሞ በነፍሱ ምትክ ሊከፍለው የሚችለው ዋጋ ቢኖረው ኖሮ ክርስቶስ መሠዋቱ ባላስፈለገ ነበር።

ሰው ኃጢአተኛ መሆኑን የማይቀበል ትምህርት ሁሉ የክርስቶስን መሠዋት ርካሽና አላስፈላጊ እንደሆነ አድርጎ ይቆጥራል። “... ጽድቅ በሕግ በኩል ከሆነ እንኪያስ ክርስቶስ በከንቱ ሞተ” ይላል (ገላ.2፥21)።

[12] ድነት የእግዚአብሔር ጸጋ ነው።

“ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል” ካለ በኋላ መፍትሔውን ሲያስቀምጥ “በኢየሱስ ክርስቶስም በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ” ይላል (ሮሜ.3፥23-24)።

ለሰው ያልተቻለውን ጽድቅ እግዚአብሔር በክርስቶስ አማካኝነት ፈጽሞታል። “ከሥጋ የተነሣ ስለ ደከመ ለሕግ ያልተቻለውን፥ እግዚአብሔር የገዛ ልጁን በኃጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ በኃጢአትም ምክንያት ልኮ አድርጎአል” (ሮሜ.8፥3)።

“ጸጋ” ማለት ስጦታ ነው። ድነትን በሥራችን እንዳላገኘነው ያመለክታል። “ጸጋው በእምነት አድኖአችኋል፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም” ይላል (ኤፌ.2፥8-9)።

[13] መዳን በእምነት ነው።

ሰው ይህን ድነት ወይም የእግዚአብሔርን የዘላለም ሕይወት ስጦታ የሚቀበለው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ነው።

“እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።” (ዮሐ.6፥47)

ቃሉን ሰምቶ በክርስቶስ የማያምን ግን ይፈረድበታል።

“በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል።” (ዮሐ.3፥18)

“ያመነ የተጠመቀም ይድናል፥ ያላመነ ግን ይፈረድበታል።” (ማር.16፥16)

[14] የኃጢአት ስርየት የሚገኘው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ነው።

“በእርሱ የሚያምን ሁሉ በስሙ የኃጢአቱን ስርየት እንዲቀበል ነቢያት ሁሉ ይመሰክሩለታል።” (ሐዋ.10፥43)

[15] አማኞች ዓለማዊነትን ክደው በጽድቅ በቅድናና እግዚአብሔርን በመፍራት ሊኖሩ ይገባል።

[16] ጋብቻ ወንድ ከሴት ጋር ብቻ ነው። የተመሣሣይ ጾታ የሥጋ ግንኙነት ዝሙት ነው።

[17] መጽሐፍ ቅዱስ፣ በእግዚአብሔር መንፈስ የተጻፈ፥ የእግዚአብሔር ቃል፥ የአስተምህሮና የልምምድ ሁሉ የበላይ ባለ ሥልጣንና መመዘኛ ነው።

በቀጣይ፣ ጌታ ቢፈቅድ፥ እዚህ ያልተብራሩትን ነጥቦች በዝርዝር እናያለን።

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

10 Oct, 21:06


የክርስትና መሠረታዊ እምነቶች

[1] እግዚአብሔር አንድ ነው። እውነተኛ አምላክ እግዚአብሔር ብቻ ነው።

ጌታ ኢየሱስ፦ “እኔና አብ አንድ ነን።” (ዮሐ.10፥30)

እንዲሁም፦ “እስራኤል ሆይ፥ ስማ፤ አምላካችን እግዚአብሔር አንድ እግዚአብሔር ነው።” (ዘዳ.6፥4)

አምላካችን እግዚአብሔር ብቻ ነው ማለት ነው። ይህም “... እግዚአብሔር አምላክህ እኔ ነኝ። ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ” ከሚለው ጋር ይስማማል (ዘጸ.20፥2-3)።

“አማልክት” ተብለው የሚጠሩ ብዙዎች በዓለም ቢኖሩም እውነተኛ አምላክ እግዚአብሔር ብቻ ነው።

“ብቻህን እውነተኛ አምላክ የሆንህ አንተን የላክኸውንም ኢየሱስ ክርስቶስን ያውቁ ዘንድ ይህች የዘላለም ሕይወት ናት።” (ዮሐ.17፥3)

[2] እግዚአብሔር በሦስት አካላት፥ ይኸውም በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ፥ ይኖራል።

[3] ኢየሱስ፥ ክርስቶስ እና የእግዚአብሔር ልጅ ነው፤ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ነው የተፀነሰው፤ በጾታዊ ግንኙነት አይደለም።

እግዚአብሔር ለአብርሃም “የምድር ሕዝቦች ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ” ብሎ የሰጠው ተስፋ (ዘፍ.22፥18) እና በቅዱሳን ነቢያቱ በኩል ለእስራኤልና ለዓለም የቀባውን መድኃኒት ሊልክላቸው የሰጠው ተስፋ ኢየሱስ ነው። “ክርስቶስ” የግሪክ ቃል ሲሆን ትርጉሙ “የተቀባው” ማለት ነው።

የወንጌል ዓላማ ይህን ለሰዎች መግለጥ ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ ወንጌሉን የጻፈበትን ዓላማ ሲገልጽ “... ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ ታምኑ ዘንድ፥ አምናችሁም በስሙ ሕይወት ይሆንላችሁ ዘንድ ይህ ተጽፎአል” ይላል (ዮሐ.20፥31)።

እርሱም በጾታዊ ግንኙነት ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የተፀነሰ ነው።

መልአኩ ገብርኤል እናቱን ማርያምን ኢየሱስን እንደምትወልድ እንዲህ ሲል ነበር ያበሰራት፦ “መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፥ የልዑልም ኃይል ይጸልልሻል ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል።” (ሉቃ.1፥35)

[4] ኢየሱስ ክርስቶስ መለኮት (እግዚአብሔር) እና እውነተኛ ሰው ነው።

ክርስቶስ፥ ሕልውናው በእናቱ ማህፀን ሲፀነስ አልጀመረም። መፀነሱ፥ “ቃል ሥጋ ሆነ” እንደሚል ሰው የመሆኑ ጅማሬ ነው እንጂ የመኖሩ ጅማሬ አይደለም።

አይሁድ “ገና አምሳ ዓመት ያልሆነህ አብርሃምን አይተሃልን?” ባሉት ጊዜ ጌታ ኢየሱስ “አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ” አላቸው (ዮሐ.8፥57-58)፤ ምክንያቱም፥ ሰው ሆኖ ሳይወለድ በፊት፥ ዓለምም ሳይፈጠር፥ እርሱ ከእግዚአብሔር (ከአብ) ጋር መለኮት ነው። “በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር (በአብ) ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር (መለኮት) ነበረ።” (ዮሐ.1፥1)

ሲቀጥል “ሁሉ በእርሱ ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም” ይላል (ዮሐ.1፥3)። ከእግዚአብሔር (ከአብ) ጋር አብሮ ፈጣሪ መሆኑን ያሳያል። ስለ ኃጢአታችን ለመሞት በሥጋ የተገለጠው ይኸው ነው። “ቃልም ሥጋ (ሰው) ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን” ይላል (ዮሐ.1፥14)።

በሌላም ስፍራ እንዲህ ይላል፦

“እርሱ በባሕርዩ አምላክ ሆኖ ሳለ፣ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን ሊለቅቀው እንደማይገባ አድርጎ አልቈጠረውም፤ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ፣ በሰውም አምሳል ተገኝቶ፣ ራሱን ባዶ አደረገ፤ ሰው ሆኖ ተገልጦም፣ ራሱን ዝቅ አደረገ፤ እስከ ሞት፣ ያውም በመስቀል ላይ እስከ መሞት ድረስ ታዛዥ ሆነ።” (ፊልጲ.2፥6-8/አ.መ.ት.)

[5] ኢየሱስ ክርስቶስ ኃጢአት የለበትም።

“እርሱ ኃጢአትን ሊያስወግድ እንደ ተገለጠ ታውቃላችሁ፥ በእርሱም ኃጢአት የለም።” (1ዮሐ.3፥5)

[6] ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን ሞቷል፤ ከሞትም ተነሥቷል።

“... መጽሐፍ እንደሚል ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን ሞተ፥ ተቀበረም፥ መጽሐፍም እንደሚል በሦስተኛው ቀን ተነሣ።” (1ቆሮ.15፥3-4)

ይህ የክርስትና መሠረት ነው። ሐዋርያው እንዲህ ይላል፦

“ክርስቶስም ካልተነሣ እንግዲያስ ስብከታችን ከንቱ ነው እምነታችሁም ደግሞ ከንቱ ናት፤ ... ክርስቶስም ካልተነሣ እምነታችሁ ከንቱ ናት፤ እስከ አሁን ድረስ በኃጢአታችሁ አላችሁ።” (1ቆሮ.15፥14-17)

[7] በክርስቶስ ሞት የምትክነት አስተስርዮ (Substitutionary Atonement) ተደርጎልናል።

“ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን ሞተ” ማለት ምንም ግልጥ ቢሆን ትርጉሙን የሚያድበሰብሱ ትምህርቶች ስላሉ እውነቱን በአጽንዖት መናገር ያስፈልጋል።

አንዳንዶች እንደሚሉት ክርስቶስ የጽድቅን መንገድ ሊያሳየን በአርአያነት ብቻ አይደለም የሞተው።

ክርስቶስ ጻድቅ ሆኖ ሳለ በእግዚአብሔር ፈቃድ መከራን ሲቀበል በመታገሡ እኛም ያለ ጥፋታችን ስንገፋና መከራን ስንቀበል እንድንታገሥ ምሳሌ ትቶልን ማለፉ እውነት ቢሆንም የሞተው ምሳሌ ሊሆነን ብቻ ነው ማለት አይደለም።

ቃሉ በግልጥ እንደሚናገር ክርስቶስ ኃጢአታችንን ተሸክሞ በእኛ ፈንታ ሆኖ ነው የሞተው። ይህም “ደዌያችንን ተቀበለ”፣ “እግዚአብሔር የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ”፣ “ኃጢአታችንን ተሸከመ” ወዘተ. በሚሉ የማያሻሙ ቃሎች ተገልጾአል።

“በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ ሕመማችንንም ተሸክሞአል፤ ... ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ፤ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን። እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፤ እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ።” (ኢሳ.53፥4-6)

“ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ። በመገረፉ ቁስል ተፈወሳችሁ። ...” (1ጴጥ.2፥24-25)

እኛ ጽድቅ እንዲቆጠርልን፥ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኝ የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው (ሮሜ.3፥22)፥ ክርስቶስ በእኛ ምትክ እንደ ዓመፀኛ ተቆጥሯል ማለት ነው።

“... ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ሰጥቶአል፥ ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአል፤ እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ።” (ኢሳ.53፥12)

“እኛ በእርሱ ሆነን የእግዚአብሔር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ኃጢአት ያላወቀውን እርሱን ስለ እኛ ኃጢአት አደረገው።” (2ቆሮ.5፥21)

[8] ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሰማይ ዐርጓል።

[9] ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማያት ሊቀ ካህናት፣ የአዲስ ኪዳን መካከለኛ፣ አማላጅ፣ አስታራቂና ጠበቃችን ነው።

የትንቢት ድምፅ

26 Sep, 18:19


እግዚአብሔርን ያለመስማት አደጋ

መስማት የሚያስፈልገንን ሳይሆን መስማት የምንፈልገውን ብቻ እየመረጥን የምንሰማ ከሆንን፥ ስንስት እግዚአብሔር ሲገሥጸን አንሰማም፤ ከጥፋትም ራሳችንን አናድንም። ከእግዚአብሔር ቃል የሚጣል አንዳች የለም። “የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል።” (2ጢሞ.3፥16-17)

የእግዚአብሔር ቃል ሁልጊዜ የምሥራች ብቻ ይዞልን አይመጣም፤ ለደከመው እንዲበረታ ተስፋን፥ ላዘነው መጽናናትን፥ ለሳተው እንዲመለስ ተግሣጽን ይናገራል እንጂ።

በራእይ መጽሐፍ ውስጥ ጌታ ኢየሱስ ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያን ከሚናገረው ቃል ይህን እናያለን። የኤፌሶንን ቤተክርስቲያን “ከወዴት እንደ ወደቅህ አስብ ንስሐም ግባ የቀደመውንም ሥራህን አድርግ” ሲል (ራእ.2፥5) የፊልድልፍያን ቤተክርስቲያን ግን “እነሆ፥ በአንተ ፊት የተከፈተ በር ሰጥቼአለሁ ማንምም ሊዘጋው አይችልም፤ ኃይልህ ምንም ትንሽ ቢሆን ቃሌን ጠብቀሃልና፥ ስሜንም አልካድህምና” ይላል (ራእ.3፥8)።

እያንዳንዱን እንደ ሥራው የሚገባውን ይናገረዋል እንጂ ሁሉንም አያመሰግናቸውም ወይም ሁሉንም አይነቅፋቸውም። መነቀፍ ያለበትን ይነቅፈዋል፤ ምስጋና የሚገባውን ያመሰግነዋል። ለፊልድልፍያ ቤተክርስቲያን መጣላትን ቃል ብንወድም የሚያስፈልገን ለኤፌሶን ቤተክርስቲያን የተነገረው ቃል ሊሆን ይችላል፤ እንደ ሁኔታችን፤ እልል የሚያስብል ባይሆንም። ለፊልድልፍያ ቤተክርስቲያን መጣላት ቃል ያለ ምክንያት አልነበረም፤ “ኃይልህ ምንም ትንሽ ቢሆን ቃሌን ጠብቀሃልና፥ ስሜንም አልካድህምና” በሚል ምክንያት ነው።

እግዚአብሔር ሲገሥጸን እየተጣላን አይደለም። የሚወዳቸውን ነው ከጥፋት እንዲጠበቁ የሚገሥጻቸው። “እኔ የምወዳቸውን ሁሉ እገሥጻቸዋለሁ እቀጣቸውማለሁ፤ እንግዲህ ቅና ንስሐም ግባ” ነው የሚለው (ራእ.3፥19)። ንስሐንም የሚሰጥ እግዚአብሔር ራሱ ነው። “... እግዚአብሔር እውነትን ያውቁ ዘንድ ንስሐን ይሰጣቸዋልና ፈቃዱን ለማድረግ በዲያብሎስ ሕያዋን ሆነው ከተያዙበት ወጥመድ ወጥተው፥ ወደ አእምሮ ይመለሳሉ ...” ይላል (2ጢሞ.2፥25-26)።

ዓመፀኞች ግን ለስሕተት አልፈው ይሰጣሉ። “... በእውነት ያላመኑ ነገር ግን በዓመፅ ደስ ይላቸው የነበሩ ሁሉ ፍርድን እንዲቀበሉ፥ ሐሰትን ያምኑ ዘንድ እግዚአብሔር የስሕተትን አሠራር ይልክባቸዋል።” (2ተሰ.2፥11-12) ደግሞም “እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው” ይላል (ሮሜ.1፥28)። እግዚአብሔርን ያለመስማት አደጋ እሱ ነው።

የእስራኤል ንጉሥ አክዓብ እንዲህ ያደርግ ነበር። በእግዚአብሔር ፊት ክፉ እያደረገ መልካም የሚናገሩለትን ነቢያት ለራሱ ሰብስቦ ነበር። ይገሥጸውና የእግዚአብሔርን ቃል በግልጥ ይናገር ስለነበር ነቢዩን ሚክያስን ግን ይጠላው ነበር። “ክፉ እንጂ መልካም ትንቢት አይናገርልኝምና እጠላዋለሁ” አለ። ንጉሡ ሶርያውያንን ሊዋጋ ሲሄድ ነቢያቱ “እግዚአብሔር ድል ይሰጥሃል፤ ሂድ!” አሉት። ንጉሡ ግን በጦር ሜዳ ተወግቶ ሞተ። እውነትን ለመስማት ስላልፈለገ በሐሰተኛ ትንቢት ለሞት አልፎ እንዲሰጥ ተወስኖበት ነበር (1ነገ.22፥1-40)።

ጥበብ እንዲህ ትላለች፦ “እውቀትን ጠልተዋልና፥ እግዚአብሔርንም መፍራት አልመረጡምና፤ ምክሬን አልፈቀዱምና፥ ዘለፋዬንም ሁሉ ንቀዋልና፤ ስለዚህ የመንገዳቸውን ፍሬ ይበላሉ፥ ከራሳቸው ምክር ይጠግባሉ። አላዋቂዎችን ከጥበብ መራቅ ይገድላቸዋልና፥ ሰነፎችንም ቸልተኛ መሆን ያጠፋቸዋልና። የሚሰማኝ ግን በእርጋታ ይቀመጣል፥ ከመከራም ሥጋት ያርፋል።” (ምሳ.1፥29-33)

ደግሞም “ተግሣጽን ቸል የሚል የራሱን ነፍስ ይንቃል፤ ዘለፋን የሚሰማ ግን አእምሮ ያገኛል” ይላል (ምሳ.15፥32)።

እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ይናገራል እንጂ ሰውን ደስ ለማሰኘት አይደለም (ዮሐ.3፥34)። መምከርና መገሠጽም ሥራው ነው። “በእግዚአብሔር ፊት በሕያዋንና በሙታንም ሊፈርድ ባለው በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ፊት፥ በመገለጡና በመንግሥቱም እመክርሃለሁ፤ ቃሉን ስበክ፥ በጊዜውም አለጊዜውም ጽና፥ ፈጽመህ እየታገሥህና እያስተማርህ፥ ዝለፍና ገሥጽ ምከርም” ይላል (2ጢሞ.4፥1-2)።

ከዚያ ሲቀጥል ተግሣጽን ስለሚጠላ ትውልድ ነው የሚናገረው፦ “ሕይወት የሚገኝበትን ትምህርት የማይታገሡበት ዘመን ይመጣልና፤ ነገር ግን ጆሮቻቸውን የሚያሳክክ ስለ ሆነ፥ እንደ ገዛ ምኞታቸው ለራሳቸው አስተማሪዎችን ያከማቻሉ። እውነትንም ከመስማት ጆሮቻቸውን ይመልሳሉ፥ ወደ ተረትም ፈቀቅ ይላሉ።” (2ጢሞ.4፥3-4) ይህ አይሁንብን።

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

07 Sep, 20:04


... እንግዲህ ንቁ!

“የአሥሩ ቆነጃጅት ምሳሌ በታላቁ መከራ ውስጥ የሚያልፉትን እንጂ እኛን አይመለከትም፤ እኛ ከአስተዋዮቹም ከዝንጉዎቹም ውስጥ የለንበትም” የሚለው ትምህርት ትክክል አይደለም።

ምሳሌው፤ ጌታ የሚመጣበትን ጊዜ ስለማያውቁ ሁልጊዜ ተዘጋጅተው ሊኖሩ እንደሚገባ ሲያስተምራቸው ለደቀ መዛሙርቱ ከነገራቸው ሦስት ምሳሌዎች አንዱ ነው። የሦስቱም ምሳሌዎች መልእክት አንድ ሲሆን “ጌታችሁ በምን ሰዓት እንዲመጣ አታውቁምና እንግዲህ ንቁ። ያን ግን እወቁ፤ ባለቤት ከሌሊቱ በየትኛው ክፍል ሌባ እንዲመጣ ቢያውቅ ኖሮ፥ በነቃ ቤቱም ሊቈፈር ባልተወም ነበር። ስለዚህ እናንተ ደግሞ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፥ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና” የሚል ነው (ማቴ.24፥42-44)።

ከሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ጋር በማስተያየት ይህ ምክር በታላቁ መከራ ውስጥ ለሚያልፉ ለእስራኤልና ለአሕዛብ ብቻ የተሰጠ እንዳልሆነ መረዳት ይቻላል።

ድንገት የሚሆን ነገር ያልተዘጋጁበትና ያልጠበቁት ነገር ነው። እንዲሁም የጌታ መምጣት ድንገት የሚሆንባቸው ያልተዘጋጁት ናቸው፤ አማኞችም ቢሆኑ፤ ካልተዘጋጁ። ለምሳሌ፣ ጌታ ለሰርዴስ ቤተክርስቲያን እንደ ሌባ በድንገት እንደሚመጣ ሲናገር በራእይ መጽሐፍ ውስጥ እናያለን። በአጭሩ “... የነቃህ ሁን ... ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ” ነው የሚለው። እንዲህ ይላል፦

“ሥራህን በአምላኬ ፊት ፍጹም ሆኖ አላገኘሁትምና የነቃህ ሁን፥ ሊሞቱም ያላቸውን የቀሩትን ነገሮች አጽና። እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ። እንግዲያስ ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ በማናቸውም ሰዓት እንድመጣብህ ከቶ አታውቅም።” (ራእ.3፥2-3)

ታዲያ “ይህ እኛን አይመለከትም” እንዴት ይባላል? ቃሉ ጌታ ራሱ በቀጥታ ለቤተክርስቲያን የተናገረው እንደሆነ እያወቅን? ጸጋውን ብቻ ወደን ኃላፊነት ጠል እንዳንሆን። ጌታ እንድንሠራ ሥራ ሰጥቶን ከሆነ የሰጠንን ሥራ እንድንፈጽም ከእኛ ይጠብቃል።

“ቤቱን ትቶ ወደ ሌላ አገር እንደ ሄደ ሰው ነው፥ ለባሮቹም ሥልጣን ለእያንዳንዱም ሥራውን ሰጥቶ በረኛውን እንዲተጋ አዘዘ። እንግዲህ በማታ ቢሆን ወይም በእኩለ ሌሊት ወይም ዶሮ ሲጮኽ ወይም በማለዳ ቢሆን ባለቤቱ መቼ እንዲመጣ አታውቁምና ድንገት መጥቶ ተኝታችሁ እንዳያገኛችሁ ስለዚህ ትጉ። ለእናንተም የምነግራችሁ ለሁሉ እላለሁ፤ ትጉ።” (ማር.13፥34-37)

የእግዚአብሔርንና የእኛን ድርሻ ማወቅ ይኖርብናል። በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ የእኛን ትጋት የሚጠይቁ ኃላፊነት የምንወስድባቸውና በፍርድ ቀን ተጠያቂ የምንሆንባቸው ሥራዎች እንዳሉን መዘንጋት የለብንም። ጸጋን የሚሰጥ እግዚአብሔር ነው። በተሰጠን ጸጋ ማገልገል ደግሞ የእኛ ኃላፊነት ነው። “ከእግዚአብሔር ጋር አብረን የምንሠራ እንደ መሆናችን መጠን፣ የተቀበላችሁትን የእግዚአብሔርን ጸጋ ከንቱ እንዳታደርጉት አደራ እንላችኋለን” ይላል (2ቆሮ.6፥1)። ጌታ ሲመጣ ቆጥሮ የሰጠንን ሥራ ለመፈጸም ስንተጋ ሊያገኘን ይፈልጋል። እንዲህ ይላል፦

“እንኪያስ ምግባቸውን በጊዜው ይሰጣቸው ዘንድ ጌታው በቤተ ሰዎች ላይ የሾመው ታማኝና ልባም ባሪያ ማን ነው ጌታው መጥቶ እንዲህ ሲያደርግ የሚያገኘው ያ ባሪያ ብፁዕ ነው፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ባለው ሁሉ ላይ ይሾመዋል። ያ ክፉ ባሪያ ግን። ጌታዬ እስኪመጣ ይዘገያል ብሎ በልቡ ቢያስብ፥ ባልንጀሮቹን ባሮች ሊመታ ቢጀምር ከሰካሮችም ጋር ቢበላና ቢጠጣ፥ የዚያ ባሪያ ጌታ ባልጠበቃት ቀን ባላወቃትም ሰዓት ይመጣል፥ ከሁለትም ይሰነጥቀዋል፥ እድሉንም ከግብዞች ጋር ያደርግበታል፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል።” (ማቴ.24፥45-51)

ምሳሌው አይመለከተንም የሚለው ሐሳብ ስለ ዝንጉዎቹ ዕጣ ፈንታ የተነገረውን ቃል በመፍራት የመነጨ ይመስላል፤ “የማይጠቅመውን ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል” የሚለውን (ማቴ.25፥30) እና ወደ ሰርግ እንዳይገቡ በሩን ዘግቶ ሰነፎቹን ቆነጃጅት “እውነት እላችኋለሁ፥ አላውቃችሁም” የሚለውን (ማቴ.25፥12)።

ነገር ግን የሚያስፈራ ነገር የለም። ምሳሌዎቹ ዝንጉዎች እንዳንሆን ለማሳሰብና ዝንጉ መሆን የሚያስከትለውን ጉዳት በአጽንዖት ለመግለጽ የተነገሩ ናቸው። ጉዳቱ ምን ድረስ እንደሚሆን በጅምላ እንዲህ ተብሎ ሊገለጽ አይችልም። እግዚአብሔር በእያንዳንዱ ላይ እንደ ሥራው ስለሚፈርድ (1ጴጥ.1፥17) ውጤቱ ከሰው ሰው ይለያያል። እንዲህ ነው የሚለው፦

“ከተመሠረተው በቀር ማንም ሌላ መሠረት ሊመሠርት አይችልም፥ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ማንም ግን በዚህ መሠረት ላይ በወርቅ ቢሆን በብርም በከበረ ድንጋይም በእንጨትም በሣርም ወይም በአገዳ ቢያንጽ፥ የእያንዳንዱ ሥራ ይገለጣል፤ በእሳት ስለሚገለጥ ያ ቀን ያሳያልና፥ የእያንዳንዱም ሥራ እንዴት መሆኑን እሳቱ ይፈትነዋል። ማንም በእርሱ ላይ ያነጸው ሥራ ቢጸናለት ደመወዙን ይቀበላል፤ የማንም ሥራ የተቃጠለበት ቢሆን ይጎዳበታል ...” (1ቆሮ.3፥11-15)

ስለዚህ፣ መልእክቱ ለሁሉም ነው፤ ጌታ ሲመጣ አማኙ በእምነቱ አገልጋዩም በአገልግሎቱ ሲተጋ እንዲገኝ የሚያሳስብ። “እንግዲህ በገደብ የለሽ ሕይወት፣ በመጠጥ ብዛትና ስለ ኑሮ በመጨነቅ ልባችሁ እንዳይዝልና ያ ቀን እንደ ወጥመድ ድንገት እንዳይደርስባችሁ ተጠንቀቁ፤ ይህ በመላው ምድር በሚኖሩት ሁሉ ላይ ይደርሳልና። ስለዚህ ከሚመጣው ሁሉ እንድታመልጡና በሰው ልጅ ፊት መቆም እንድትችሉ ሁልጊዜ ተግታችሁ ጸልዩ።” (ሉቃ.21፥34-36)

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

22 Aug, 21:45


እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን ...

“የእግዚአብሔርን መንግሥት መውረስ” ሲባል አንዳንዶቻችን ምድርን ለቅቆ በሰማይ መኖር ይሆናል የሚታየን። እሱ ስሕተት ባይሆንም ትልቁን ምስል አያሳየንም። የበለጠ ትክክለኛና ሙሉ የሆነ ትርጉም አለ።

የእግዚአብሔር መንግሥት እንደስሟ መንግሥት (አገዛዝ) ናት እንጂ ስፍራ (ሰማይም ሆነ ምድር) አይደለችም። ነገር ግን ሰማይንና ምድርን ትገዛለች። “እግዚአብሔር ዙፋኑን በሰማይ አዘጋጀ፥ መንግሥቱም ሁሉን ትገዛለች” ይላል (መዝ.103፥19)።

በኃጢአት ምክንያት የአሁኑ ዓለም ከእግዚአብሔር ቁጣ ወይም ፍርድ በታች ነው የሚገኘው። ይኸውም በሰይጣን እጅ ነው። ስለዚህም ሰይጣን “የዚህ ዓለም ገዥ” ተብሏል (ዮሐ.14፥30)። ደግሞም “ዓለም በሞላው በክፉው እንደ ተያዘ እናውቃለን” ይላል (1ዮሐ.5፥19)። ሰይጣን በዓመፀኞች ላይ የሚሠራው መንፈስ አለቃ ነው። እንዲህ ይላል፦

“በበደላችሁና በኃጢአታችሁ ሙታን ነበራችሁ፤ በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው።” (ኤፌ.2፥1-2)

የእግዚአብሔር መንግሥት እንድትመጣ የሚያስፈልገው ለዚህ ነው። የእግዚአብሔር መንግሥት ስትመጣለት ሰው ከዚያ ፍርድ ምሕረትን ያገኛል፤ ከሰይጣን ሥልጣን ነጻ ይወጣል። ጌታ ኢየሱስ አጋንንትን እያወጣ አይሁድን “በእግዚአብሔር መንፈስ አጋንንትን የማወጣ ከሆንሁ፥ እንግዲህ የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ ደርሳለች” አላቸው (ማቴ.12፥28)። ደግሞም “እርሱ መልካም እያደረገ ለዲያብሎስም የተገዙትን ሁሉ እየፈወሰ ዞረ” ይላል (ሐዋ.10፥38)።

ነገር ግን የሥጋን ፈውስ መቀበል ብቻውን በቂ አይደለም። ሰው ከሰይጣን አገዛዝ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የሚሻገረው በክርስቶስ በማመን የኃጢአትን ስርየት ሲያገኝ ነው። ለሰይጣን እንዲገዛ ያደረገው ኃጢአት እንደመሆኑ፥ ኃጢአቱ ሲወገድለት ሰው ከሰይጣን አገዛዝ አርነት ይወጣል። “እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን” ነው የሚለው (ቆላ.1፥13-14)። ወደ መንግሥቱ መፍለስ ከቁጣው ወደ ምሕረቱ መሻገር ነው። “በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቁጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።” (ዮሐ.3፥36)

ሰው ብቻ አይደለም ፍጥረት ሁሉ ምድርም ራሷ ፈውስን ይሻሉ። እግዚአብሔር አዳምን “ምድር ከአንተ የተነሣ የተረገመች ትሁን” ብሎ ስለፈረደ አሁን በምድር ላይ ልዩ ልዩ መከራ ሥቃይና ሐዘን አለ (ዘፍ.3፥17)። ፍጥረት ሁሉ ከዚህ መርገም ነጻ መውጣትን ይጠብቃል።

“የአሁኑ ዘመን ሥቃያችን ወደ ፊት ሊገለጥ ካለው፣ ለእኛ ከተጠበቀልን ክብር ጋር ሲነጻጸር ምንም እንዳይደለ እቈጥራለሁ። ፍጥረት ሁሉ የእግዚአብሔርን ልጆች መገለጥ በናፍቆት ይጠባበቃል። ፍጥረት ሁሉ ለከንቱነት ተዳርጓል፤ ይኸውም በራሱ ምርጫ ሳይሆን፣ ለተስፋ እንዲገዛ ካደረገው ከፈቃዱ የተነሣ ነው። ይህም ፍጥረት ራሱ ከመበስበስ ባርነት ነጻ ወጥቶ ለእግዚአብሔር ልጆች ወደ ሆነው ወደ ከበረው ነጻነት እንዲደርስ ነው። እስከ አሁን ድረስ ፍጥረት ሁሉ በምጥ ጊዜ እንዳለው ሥቃይ በመቃተት ላይ እንደሚገኝ እናውቃለን።” (ሮሜ.8፥18-22)

ይህ ፍጥረት በናፍቆት የሚጠባበቀው “የእግዚአብሔር ልጆች መገለጥ” የእግዚአብሔር መንግሥት ስትገለጥ የሚፈጸም ነው፤ “ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ፥ በዚያን ጊዜ እናንተ ደግሞ ከእርሱ ጋር በክብር ትገለጣላችሁ” እንደሚል (ቆላ.3፥4)።

በመሆኑም ምድር ለዓመፀኞች እንደተተወች አድርገን ልናስብ አይገባም። በሰማይ በእግዚአብሔር ዘንድ ያለው ጽድቅና ሰላም በምድርም ይሆናል፤ ጌታ እንዳስተማረን “መንግሥትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደ ሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን” ብለን እንደምንጸልይ (ማቴ.6፥10)። የእግዚአብሔር ፈቃድም እንዲህ ነው፦ “በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው።” (ኤፌ.1፥10)

ክርስቶስ ሲገለጥ የሰይጣን የዚህ ዓለም ገዥነቱ ያበቃል። “የዓለም መንግሥት ለጌታችንና ለእርሱ ለክርስቶስ ሆነች፥ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ይነግሣል” ይላል (ራእ.11፥15)።

በእርግጥ ጌታ ኢየሱስ ከሙታን በተነሣ ጊዜ “ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ” እንዳለው (ማቴ.28፥18) የሰይጣንን ሥልጣን አስቀድሞ ገፎታል። ነገር ግን መንግሥቱ በምድር ላይ ወዲያው አልተገለጠችም። ይህም የሆነው መንግሥቱ ስትገለጥ ዓመፀኞችን ከሰይጣንና ከመላእክቱ ጋር ስለሚቀጣቸው ሰዎች ከሚመጣው ፍርድ በንስሐ እንዲያመልጡ ዕድል ለመስጠት ነው። “ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፥ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል” ይላል (2ጴጥ.3፥9)።

እንዲያም ሆኖ ግን የአሁኑ ሰማይና ምድር ይጠፋሉ። “ጽድቅ የሚኖርባትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደ ተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን” (2ጴጥ.3፥13)። ሰማይና ምድር ቢለወጡም የክርስቶስ መንግሥት ግን ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል።

በመጀመሪያ፣ በራእይ መጽሐፍ በግልፅ እንተጻፈ ክርስቶስ ሲገለጥ ምድርን ለሺህ ዓመት ነው የሚገዛው (ራእ.20፥4)። ሺሁ ዓመት ሲፈጸም ታላቁና የመጨረሻው ፍርድ ይሆናል። ዓለም ከተፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ ያሉ ሙታን ተነሥተው በሕይወት ካሉት ጋር ፍርድን ይቀበሉና ፍጻሜ ይሆናል (ራእ.20፥11-15)። ከዚያም እግዚአብሔር አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርን ይፈጥራል። በአሁኑ ዓለም ያለው መርገም በዚያ ፈጽሞ አይሆንም። ባለራእዩ ዮሐንስ እንዲህ ይላል፦

“አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፥ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፥ ባሕርም ወደ ፊት የለም። ... ታላቅም ድምፅ ከሰማይ፤ ‘እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ነው፤ ከእነርሱም ጋር ያድራል፥ እነርሱም ሕዝቡ ይሆናሉ፤ እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል፤ እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና’ ብሎ ሲናገር ሰማሁ።” (ራእ.21፥1-4)

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

09 Aug, 14:03


ከሞት ወደ ሕይወት ተሻግሯል

በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፥ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻግሯል (ዮሐ.5፥24)።

ከጌታ ኢየሱስ ጋር የበሉና የጠጡ የሞቱና የትንሣኤውም የዓይን እማኞች የሆኑ ሐዋርያቱ ይህን ቃል ከአፉ ተቀብለው ለዓለም ሁሉ ሰበኩ።

“በክርስቶስ የሚያምን የዘላለም ሕይወት ካለው ታዲያ ሐዋርያቱ ራሳቸው ለምን ሞቱ? አሁንም ድረስ፥ በእርሱ ያመኑ ሁሉ እንደማንኛውም ሰው ይሞታሉ፤ ለምንድነው?” ያልተማረ ሰው ሊጠይቅ የሚችለው ጥያቄ ነው።

ጌታ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ይህን ምሳሌ ነገራቸው፦

“በአረጀ ልብስ አዲስ እራፊ የሚጥፍ የለም፤ ቢደረግ ግን፥ አዲሱ መጣፊያ አሮጌውን ይቦጭቀዋል፥ መቀደዱም የባሰ ይሆናል። በአረጀ አቁማዳም አዲስ የወይን ጠጅ የሚያኖር የለም፤ ቢደረግ ግን፥ የወይን ጠጁ አቁማዳውን ያፈነዳል የወይኑም ጠጅ ይፈሳል አቁማዳውም ይጠፋል፥ አዲሱን የወይን ጠጅ ግን በአዲስ አቁማዳ ያኖራሉ።” (ማር.2፥21-22)

የዘላለምን ሕይወትም እንደዚሁ በአሮጌው ፍጥረታዊው ሰውነታችን መኖር አይቻልም። ፍጥረታዊ ሰውነት የዘላለምን ሕይወት ማስተናገድ አይችልም። “ሥጋና ደም የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊወርሱ አይችሉም፥ የሚበሰብሰውም የማይበሰብሰውን አይወርስም። ... ይህ የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሊለብስ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ሊለብስ ይገባዋል።” (1ቆሮ.15፥50፤53)

“በሚሞት ሥጋችሁ ኃጢአት አይንገሥ” ሲል (ሮሜ.6፥12) አሁን በክርስቶስ አምነንም ለጊዜው በሚሞት አካላችን እንደምንኖር ያሳያል፤ የማይሞተውን እስንክንለብስ ድረስ። በክርስቶስ የሚያምን የዘላለም ሕይወት ካለው አሁን ለምን ይሞታል ለሚለው ጥያቄ መልሱ እሱ ነው።

“በዚህ ቋሚ ከተማ የለንም፤ ነገር ግን ወደ ፊት የምትመጣዋን ከተማ እንጠብቃለን” ነው የሚለው (ዕብ.13፥14)። ተጓዥ በመንገዱ ሳለ ድንኳን ይተክላል እንጂ ቋሚ ነዋሪ ባልሆነበት ስፍራ ሕንጻ አይገነባም። ከመድረሻው ሲደርስ ግን ቋሚ መኖሪያ ቤቱን ሊያንጽ ይችላል። አላፊ የሆነውን ምድራዊውን አካላችንን እንደዚሁ “ድንኳን” ብሎ ይጠራዋል። የማይሞተውንና ጸንቶ የሚኖረውን አካላችንን ደግሞ በሕንጻ ይመስለዋል። እንዲህ እያለ፦

“ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ፥ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘላለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንጻ እንዳለን እናውቃለን። በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፥ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና ለብሰን ራቁታችንን አንገኝም። በእውነትም የሚሞተው በሕይወት ይዋጥ ዘንድ ልንለብስ እንጂ ልንገፈፍ የማንወድ ስለ ሆነ፥ በድንኳኑ ያለን እኛ ከብዶን እንቃትታለን።” (2ቆሮ.5፥1-4)

በመሆኑም አሁን “የዘላለም ሕይወት አለን” ስንል የአሁኑ ሰውነታችን ሲጠፋ የማይሞተውን እንደምንለብስ እግዚአብሔር የሰጠን የድነት ተስፋ አለን ማለት ነው። “ልጅን (ክርስቶስን) አይቶ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወትን እንዲያገኝ የአባቴ ፈቃድ ይህ ነው፥ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ” ይላል (ዮሐ.6፥40)።

ድነት አሁን “ተስፋ” እንደሆነ ስንሰማ (ሮሜ.8፥24) አንዳንዶቻችን ሰው እንደሚሰጠው ተስፋ መስሎን አይቅለልብን። ሰው ተስፋ ሲሰጥ ለማድረግ ፈቃደኝነቱን፣ ተነሳሽነቱንና እቅዱን ብቻ ነው የሚያሳየው። ነገሩ ለመፈጸሙ ዋስትና የለም። ሰው ሙሉ ዋስትና መስጠትም አይችልም። ሰው አቅም ስላለውና ለማድረግ ፈቃደኛ ስለሆነ ብቻ አንድን ነገር ማድረግ አይችልም፤ ከቁጥጥሩ ውጪ የሆኑ ነገሮች ሊከሰቱ ስለሚችሉ። ስለዚህም መዝሙረኛው “ንጉሥ በሠራዊቱ ብዛት አይድንም ኃያልም በኃይሉ ብዛት አያመልጥም” ሲል (መዝ.33፥16)፥ ጥበበኛው ደግሞ “ፈረስ ለጦርነት ቀን ይዘጋጃል፤ ድል ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው” ይላል (ምሳ.21፥31)።

የእግዚአብሔር ሐሳብ ግን እንዳይፈጸም የሚከለክል የለም። ስለዚህ ተስፋው እርግጥ ነው። “የተስፋን ቃል የሰጠን ታማኝ ስለሆነ አምነን የምንናገርለትን ተስፋ አጥብቀን እንያዝ” ይላል (ዕብ.10፥23)። የዘላለም ሕይወት ተስፋችን እርግጠኛነት በእግዚአብሔር ማንነትና ባሕርይ ላይ የተመሠረተ እንደሆነ እናያለን።

ይህ ብቻም አይደለም። እግዚአብሔር ፈቃዱ እንደማይለወጥ ሊያሳየን የተስፋ ቃሉን በመሓላ አትሞታል። ይኸውም በክርስቶስ ደም ባደረገልን የድነት ኪዳን አማካኝነት ነው። እንዲህ ይላል፦

“ሰዎች ከእነርሱ በሚበልጠው ይምላሉና፥ ለማስረዳትም የሆነው መሐላ የሙግት ሁሉ ፍጻሜ ይሆናል፤ ስለዚህም እግዚአብሔር፥ የተስፋውን ቃል ለሚወርሱ ፈቃዱ እንደ ማይለወጥ አብልጦ ሊያሳያቸው ስለ ፈቀደ፥ እግዚአብሔር ሊዋሽ በማይቻል በሁለት በማይለወጥ ነገር፥ በፊታችን ያለውን ተስፋ ለመያዝ ለሸሸን ለእኛ ብርቱ መጽናናት ይሆንልን ዘንድ፥ በመሓላ በመካከል ገባ፤ ይህም ተስፋ እንደ ነፍስ መልሕቅ አለን እርሱም እርግጥና ጽኑ የሆነ ወደ መጋረጃውም ውስጥ የገባ ነው፤ በዚያም ኢየሱስ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ሊቀ ካህናት የሆነው፥ ስለ እኛ ቀዳሚ ሆኖ ገባ።” (ዕብ.6፥16-20)

የዘላለም ሕይወት ተስፋ በእግዚአብሔር በኩል እርግጥ ሲሆን ተስፋውን ለማግኘት ከእኛ የሚጠበቀው እምነትና ትዕግሥት ነው፤ እንደ አብርሃም። “በእምነትና በትዕግሥትም የተስፋውን ቃል የሚወርሱትን እንድትመስሉ እንጂ ዳተኞች እንዳትሆኑ፥ ተስፋ እስኪሞላ ድረስ እያንዳንዳችሁ ያን ትጋት እስከ መጨረሻ እንድታሳዩ እንመኛለን። እግዚአብሔርም ለአብርሃም ተስፋ በሰጠው ጊዜ። ‘በእውነት እየባረክሁ እባርክሃለሁ፤ እያበዛሁም አበዛሃለሁ’ ብሎ፥ ከእርሱ በሚበልጥ በማንም ሊምል ስላልቻለ፥ በራሱ ማለ፤ እንዲሁም እርሱ ከታገሰ በኋላ ተስፋውን አገኘ።” (ዕብ.6፥11-15)

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

01 Aug, 14:22


ካመለጡ በኋላ ዳግመኛ ተጠላልፈው ...

እስቲ ይህን ቃል ደግሞ እንመልከት፦

“በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እውቀት ከዓለም ርኵሰት ካመለጡ በኋላ ዳግመኛ በእርስዋ ተጠላልፈው የተሸነፉ ቢሆኑ፥ ከፊተኛው ኑሮአቸው ይልቅ የኋለኛው የባሰ ሆኖባቸዋል። አውቀዋት ከተሰጣቸው ከቅድስት ትእዛዝ ከሚመለሱ የጽድቅን መንገድ ባላወቋት በተሻላቸው ነበርና።” (2ጴጥ.2፥20-21)

ታዲያ እነዚህ በጌታ አምነው የነበሩና በኋላ የካዱ አይደሉም? ሰው አንዴ በክርስቶስ ካመነ በኋላ ፈጽሞ ሊክድ አይችልም የምትሉ እነዚህንም በፊትም በጌታ ያላመኑ ነበሩ ትላላችሁ?

ሰዎቹ “ከዓለም ርኵሰት አምልጠው የነበሩ” መሆናቸው በግልጥ ተጠቅሷል (ቁ.20)። ያ ደግሞ በክርስቶስ በማመን የሚገኝ ከኃጢአት መንጻት (ስርየት) ካልሆነ ምንድነው?

ደግሞም፣ “እነርሱ የዋጃቸውን ጌታ እንኳ ክደው የሚፈጥንን ጥፋት በራሳቸው ላይ እየሳቡ የሚያጠፋ ኑፋቄን አሹልከው ያገባሉ” ይላል (2ጴጥ.2፥1)። በፊትም ያላመኑ ከነበሩ “የዋጃቸውን ጌታ ካዱ” እንዴት ይላቸዋል? አምነው እንደነበሩና በኋላ ግን እንደካዱ ነው የሚያሳየው።

በተጨማሪም፣ “ዳግመኛ” በዓለም እንደተጠላለፉ ያወራል (ቁ.20)። “ዳግመኛ” ማለት “መመለስ”ን ነው የሚያመለክተው። ነገር ግን አስቀድመው ያልተለዩትን እንዴት ይመለሱበታል፤ ቢለዩት ነው እንጂ። ዓለምን ከተለዩአት በኋላ ነው የተመለሱባት። “‘ውሻ ወደ ትፋቱ ይመለሳል’ እንዲሁም ‘ዐሣማ ቢታጠብም ተመልሶ በጭቃ ላይ ይንከባለላል’ የሚለው ምሳሌ እውን ይሆንባቸዋል” ይላል (2ጴጥ.2፥22)።

በመሆኑም ሰዎች እንዲድኑ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን እስከ መጨረሻው መጽናት አለባቸው።

ይህን ስንል አማኞች መዳናቸውን እንዲጠራጠሩ እያደረግን እንደሆነ ተደርጎ ሊቆጠር አይገባም። ይልቁን መዳናቸውን ለማረጋገጥ ይህን ማወቅና መተግበር ስለሚያስፈልግ አማኞችን በየጊዜው በአጽንዖት ማሳሰብ ይገባል።

በቤተክርስቲያን ታሪክ ክርስቶስን የሚያስክዱ ልዩ ልዩ የሐሰት ትምህርቶች በየጊዜው እየተፈበረኩ ጥቂት የማይባሉ ምዕመናንን እንዳሳቱ አውቀን ይህን አብዝተን ማድረግ ይኖርብናል። ሐዋርያትም በመልእክቶቻቸው አማኞች እንዲጸኑ እምነታቸውን እንዲጠብቁና እንዲጠነቀቁ ያሳስባሉ።

ቃሉ፥ “ድናችኋል”፣ “ዳግመኛ ተወልዳችኋል”፣ “ከእግዚአብሔር ጋር ታርቃችኋል” ወ.ዘ.ተ. ሲል አሁን በክርስቶስ ማመናችንን ብቻ ሳይሆን በዚያ እምነት እስከ መጨረሻ እንደምንጸና ታሳቢ አድርጎ ነው።

ለአብነት ያህል፣ ከእግዚአብሔር ጋር ስለመታረቃችን ሲናገር፥ “ከክፉ ባሕርያችሁ የተነሣ ቀድሞ ከእግዚአብሔር የተለያችሁ በአሳባችሁም ጠላቶች ነበራችሁ። አሁን ግን ነውርና ነቀፋ የሌለባችሁ ቅዱሳን አድርጎ በእርሱ ፊት ሊያቀርባችሁ፣ በክርስቶስ ሥጋ በሞቱ በኩል አስታረቃችሁ” ይልና ይህ የሚሆንበትን ሁኔታ ሲገልፅ “ይህም የሚሆነው በእምነታችሁ ተመሥርታችሁና ተደላድላችሁ በመቆም ከሰማችሁት የወንጌል ተስፋ ሳትናወጡ ጸንታችሁ ብትኖሩ ነው” ይላል (ቆላ.1፥21-23/አ.መ.ት.)።

በሌላም ስፍራ እንዲህ ይላል፦

“... ወንድሞች ሆይ፤ የሰበክሁላችሁንና የተቀበላችሁትን፣ ደግሞም ጸንታችሁ የቆማችሁበትን ወንጌል ላሳስባችሁ እወድዳለሁ፤ የሰበክሁላችሁን ቃል አጥብቃችሁ ብትይዙ፣ በዚህ ወንጌል ትድናላችሁ፤ አለዚያ ያመናችሁት በከንቱ ነው።” (1ቆሮ.15፥1-2/አ.መ.ት.)

በክርስቶስ አምነን በሥጋ በምንኖረው በቀሪው ዘመናችን ሁሉ እምነታችንን እንዳያስጥለን ከሰይጣን ጋር መጋደል አለብን። ይህ ተጋድሎ “የዲያብሎስን ሽንገላ (ማታለል) ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ” የተባለው ነው (ኤፌ.6፥11)። ዋነኞቹ ማታለያዎቹ የክርስቶስን ማንነትና ሥራ የሚያስክዱ የስሕተት ትምህርቶች ናቸው። ሐዋርያው በዚህ ቃል ምክሩን ይቋጫል፦

“እንግዲህ እናንተ፥ ወዳጆች ሆይ፥ ይህን አስቀድማችሁ ስለምታውቁ፥ በዓመፀኞቹ ስሕተት ተስባችሁ ከራሳችሁ ጽናት እንዳትወድቁ ተጠንቀቁ፤ ነገር ግን በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና እውቀት እደጉ።” (2ጴጥ.3፥17-18)

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

25 Jul, 16:24


ቃሉ በግልፅ የሚናገረውን ትተን በዚህ መልኩ እንደፈለግን እየተርጎምነው የምንሄድ ከሆነ በዚህ አካሄድ በመጽሐፍ ቅዱስ መመራት አንችልም።

“ከመንፈስ ቅዱስ ተካፋዮች ሆነው የነበሩ” ማለት ከመንፈስ ቅዱስ ተካፋዮች ሆነው የነበሩ ማለት ነው። ጉባኤ የታደሙ፣ አብረው ያጨበጨቡ ወ.ዘ.ተ. ማለት አይደለም።

የተጠቀሰው ቃል ራሱ በዝርዝር የተገለጸና የተብራራ ነው። ተጨማሪ ማብራሪያ አያስፈልገውም። በትርጉም እያሳበብን ቃሉን ለቲዮሎጂያችን እንዲስማማ አድርገን ብንጠመዝዘው የምንጎዳው እኛው ነን። እውነትን ከማወቅ ራሳችንን እንከለክላለን።

ለመዳናችን ዋስትና በእርግጥ አለን። ጌታ ቢፈቅድ ይህን በዝርዝር እናያለን። ነገር ግን፣ ዋስትናው፥ የአማኙን እስከ መጨረሻው በእምነቱ የመጽናት ግዴታ አያስቀረውም።

የትንቢት ድምፅ

20 Jul, 19:23


መጽናት ያስፈልጋችኋል!

ሰው አንዴ በክርስቶስ ካመነ በኋላ ሊክድ አይችልም የምትሉ ይህን ቃል እንዴት ታዩታላችሁ?

“አንድ ጊዜ ብርሃን የበራላቸውን ሰማያዊውንም ስጦታ የቀመሱትን ከመንፈስ ቅዱስም ተካፋዮች ሆነው የነበሩትን መልካሙንም የእግዚአብሔርን ቃልና ሊመጣ ያለውን የዓለም ኃይል የቀመሱትን በኋላም የካዱትን እንደገና ለንስሐ እነርሱን ማደስ የማይቻል ነው፤ ለራሳቸው የእግዚአብሔርን ልጅ ይሰቅሉታልና ያዋርዱትማልና።” (ዕብ.6፥4-6)

ይህ ቃል የሚመለከተው አይሁድን ወይም ዕብራውያንን ብቻ እንደሆነ አድርጎ ለማቅረብ ብዙ አስተማሪዎች ሲጥሩ ይስተዋላል። ነገር ግን ለአይሁድ ብቻ የሚሠራ መርህ የለም፤ አማኝ፥ አማኝ ነው። አይሁድ ይሁኑ ወይም አሕዛብ አምነው ስለነበሩና በኋላ ግን ስለ ካዱ ሰዎች ነው የሚያወራው።

መጀመሪያም አላመኑም ነበር የሚለው ሐሳብ አያስኬድም። ምክንያቱም፣ እነዚህ ሰዎች፥

1ኛ- ብርሃን የበራላቸው
2ኛ- ከመንፈስ ቅዱስ ተካፋዮች ሆነው የነበሩ
3ኛ- የእግዚአብሔርን መንግሥት ኃይል የተለማመዱ

መሆናቸው በማያሻማ ቃል ተገልጾአል። እነዚህ ነገሮች ደግሞ ያለ እምነት ፈጽሞ የሚሆኑ አይደሉም። ለምሳሌ፣ ያለ እምነት መንፈስ ቅዱስን መቀበል (መካፈል) አይቻልም። ስለዚህ፣ አምነው የነበሩና በግልጥ እንደተጠቀሰው “በኋላ የካዱ” ናቸው (ቁ.6)።

በመሆኑም የሚከተሉትን ነጥቦች ማወቅ ይኖርብናል።

1ኛ- አሁን የዳንን በተስፋ ነው። በተስፋ ከሆነ ገና አልተገለጠም ማለት ነው፤ ተስፋ የሚደረግ ነገር የማይታይ ነገር ነው። “በተስፋ ድነናልና፤ ነገር ግን ተስፋ የሚደረግበቱ ነገር ቢታይ ተስፋ አይደለም፤ የሚያየውንማ ማን ተስፋ ያደርገዋል? የማናየውን ግን ተስፋ ብናደርገው በትዕግሥት እንጠባበቃለን” ይላል (ሮሜ.8፥24-25)።

ስለዚህ፣ አሁን ሳናየው ያመንነው የሰውነታችን መዳን (ቤዛነት) ገና ወደፊት እንዲፈጸም የምንጠብቀው ነው። “... የመንፈስ በኵራት ያለን ራሳችን ደግሞ የሰውነታችን ቤዛ የሆነውን ልጅነት እየተጠባበቅን ራሳችን በውስጣችን እንቃትታለን” ይላል (ሮሜ.8፥23)።

ይህም የቤዛ ቀን ተብሎ በሚጠራው በጌታችን መምጣት ነው የሚፈጸመው። “እኛ አገራችን በሰማይ ነው፥ ከዚያም ደግሞ የሚመጣ መድኃኒትን እርሱንም ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን እንጠባበቃለን፤ እርሱም ሁሉን እንኳ ለራሱ ሊያስገዛ እንደሚችልበት አሠራር፥ ክቡር ሥጋውን እንዲመስል የተዋረደውን ሥጋችንን ይለውጣል” የተባለው ነው (ፊልጲ.3፥20-21)።

2ኛ- ተስፋ ያደረግነውን ለማግኘት በእምነት መጽናት የግድ ያስፈልገናል፤ እስክናገኘው ድረስ።

“እንግዲህ ታላቅ ብድራት (ዋጋ) ያለውን ድፍረታችሁን (መታመናችሁን) አትጣሉ። የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና።” (ዕብ.10፥35-36)

ከእምነት ወደ ኋላ ማፈግፈግ ለጥፋት ነው። “ገና በጣም ጥቂት ጊዜ ነው፥ ሊመጣ ያለውም ይመጣል አይዘገይምም፤ ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል ወደ ኋላም ቢያፈገፍግ፥ ነፍሴ በእርሱ ደስ አይላትም። እኛ ግን ነፍሳቸውን ሊያድኑ ከሚያምኑቱ ነን እንጂ ወደ ጥፋት ከሚያፈገፍጉ አይደለንም” ይላል (ዕብ.10፥37-39)።

የመዳን ዋስትና ትምህርት በዚህ መሠረት መቃኘት ይኖርበታል። ምን ትላላችሁ? አስተያየት መስጫው ላይ እስቲ ተወያዩበት።

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

17 Jul, 22:56


አንዴ በክርስቶስ ያመነ ሰው በኋላ ቢክድ እንኳ ድነቱን አያጣም የሚሉ አሉ። ምክንያታቸው ደግሞ ድነት ስጦታ ስለሆነ አንዴ ከተሰጠ ወዲህ በምንም ሁኔታ አይወሰድም የሚል ነው።

ይህ እንዴት ይሆናል? “ልጁ ያለው ሕይወት አለው፤ የእግዚአብሔር ልጅ የሌለው ሕይወት የለውም” ነው ቃሉ የሚለው (1ዮሐ.1፥8-10)። ክርስቶስን ጥሎ ሕይወት የለም።

ደግሞም “የሙሴን ሕግ የናቀ ሰው ሁለት ወይም ሦስት ቢመሰክሩበት ያለ ርኅራኄ ይሞታል፤ የእግዚአብሔርን ልጅ የረገጠ ያንንም የተቀደሰበትን የኪዳኑን ደም እንደ ርኵስ ነገር የቆጠረ የጸጋውንም መንፈስ ያክፋፋ፥ እንዴት ይልቅ የሚብስ ቅጣት የሚገባው ይመስላችኋል?” ይላል (ዕብ.10፥28-29)። የሚያወራው ክርስቶስን ስለሚክድ ሰው መሆኑ ግልጥ ነው።

የዘላለም ሕይወት የእግዚአብሔር ስጦታ (በጸጋ) መሆኑን ቃሉ ሲናገር ከሰጪው እግዚአብሔር ተለይተን በራሳችን የሚኖረን ማለቱ ሳይሆን በሥራ እንዳላገኘነውና ደመወዛችን እንዳልሆነ ለመግለጽ ነው።

ክርስቲያን እንደ ዳነ ሰው የሆናቸውን ነገሮች ሁሉ የሆነው በክርስቶስ ውስጥ በመሆኑ ነው። የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችን የእግዚአብሔር ልጅ በሆነው በእርሱ ውስጥ በመሆናችን ነው። ከእርሱ ተነጥለን ልጆች አንሆንም።

የትንቢት ድምፅ

14 Jul, 06:42


የመስቀሉ ሥራ (የክርስቶስ ሞቱና ትንሣኤው) በአማኙ ላይ የሚተገበረው በጥምቀት አማካኝነት ነው!

“የሥጋንም ሰውነት በመገፈፍ፥ በክርስቶስ መገረዝ፥ በእጅ ባልተደረገ መገረዝ በእርሱ ሆናችሁ ደግሞ ተገረዛችሁ። በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀብራችሁ፥ በጥምቀት ደግሞ፥ ከሙታን ባስነሣው በእግዚአብሔር አሠራር በማመናችሁ፥ ከእርሱ ጋር ተነሣችሁ።” (ቆላ.2፥11-12)

ተቃራኒ ያልሆኑ ነገሮችን ተቃራኒ እንደሆኑ አድርገህ ነው የተናገርከው። እምነትና ጥምቀት የአንድ ሣንቲም ገጾች ናቸው።

“ከክርስቶስ ጋር ሞቻለሁ” “አዲስ ፍጥረት ሆኛለው” ወ.ዘ.ተ. ትላላችሁ። እነዚህ ኩነቶች የተከናወኑት በጥምቀት አማካኝነት መሆኑን በግልጽ የተጻፈውን ግን አትቀበሉም።

የትንቢት ድምፅ

14 Jul, 06:41


በውኃ ጥምቀት የኀጢአት ስርየት የሚገኝ ከሆነ የኢየሱስ የመስቀል ሥራ አያስፈልግም።

የትንቢት ድምፅ

09 Jul, 21:17


የወንጌል ፎረም አባል ይሁኑ! 🙂

ሰላም! የተከበራችሁ የትንቢት ድምፅ ቤተሰቦች። መልእክቶቻችንን ጠቃሚ ሆነው ስላገኛችኋቸውና ቻናላችንን ስለተቀላቀላችሁ ከልብ እናመሰግናለን።

የእግዚአብሔርን ቃልና የወንጌል አማኙን ማኅበረሰብ የሚመለከቱ ወቅታዊ ጉዳዮችን ለማጋራትና ለመከታተል የወንጌል ፎረም አባል ይሁኑ። ወንጌል ፎረም የመላው የኢትዮጵያ የወንጌል አማኞች የቴሌግራም ግሩፕ ነው። ቀጥሎ ባለው ሊንክ ያገኙታል፦

https://t.me/WengelForum

ከትንቢት ድምፅ ቻናል Forward የተደረጉ አንዳንድ መልእክቶችንም ግሩፑ ላይ ያገኟሉ። ግሩፑ ከቻናሉ በተለየ የሚሰጥዎት ጥቅም ከሌሎች መንጮች የተጋሩ መልእክቶችንም የሚያገኙበት መሆኑና የራስዎን መልእክትም እንዲያጋሩ የሚያስችል መሆኑ ነው።

ሮረሙን ከተቀላቀሉ በኋላ የሮረሙን አባላት ቁጥር ለማሳደግና ግሩፑ ላይ የሚለጠፉት የእግዚአብሔር ቃልና ሌሎች ጠቃሚ መልእክቶች እንዲደርሷቸው ወዳጆችዎንም ከስልክዎ ላይ ወደ ግሩፑ ይደምሯቸው።

የሚከተለውን መመሪያ ይከተሉ፦

1- ከላይ “ወንጌል ፎረም” የሚለውን የግሩፑን ስም ይጫኑ። የግሩፑ አባላት ዝርዝር ይከፈታል።
2- ከዚያም “Add Members” የሚለውን ይጫኑ።
3- ቀጥሎም ወደ ግሩፑ ለመጨመር የሚፈልጓቸውን ሰዎች ይምረጡና አስገብተው ይጨርሱ።

ጊዜዎትን ለመቆጠብ ብዙ ሰዎችን በአንድ ላይ ይደምሩ። በአንድ ቀን መደመር የሚችሉት እስከ 50 ሰዎችን ብቻ ነው።

የትንቢት ድምፅ

01 Jul, 01:42


ክርስቶስ ሥጋን መልበሱ መከራን ለመቀበሉና ለሞቱ ቅድመ ሁኔታ ነው። ነገር ግን፥ የሞተው፥ ሥጋን በመልበሱ ምክንያት አይደለም፤ ኃጢአታችንን በሥጋው በመሸከሙ እንጂ። ሞት የኃጢአት ውጤት ነው። “እግዚአብሔር የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ” ይላል (ኢሳ.53፥6)።

ይህም እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር ያስረዳል (ሮሜ.5፥8)። “አንድያ ልጁን እስከ መስጠት ድረስ ዓለምን እንዲሁ ወድዷል” ተብሎ እኛን የወደደበት የፍቅሩ መጠን የተለካው በዚህ ነው (ዮሐ.3፥16)። እግዚአብሔር ጨክኖ አንድያ ልጁን ስለ ኃጢአታችን እንዲሞት አሳልፎ ለመስጠት መገደዱ የምንድንበት ሌላ አማራጭ መንገድ እንደሌለ ያሳያል።

ክርስቶስ ከሞት ከተነሣ ወዲያ ዳግመኛ አይሞትም እንጂ ሰው መሆኑ አልቀረም። እርሱ አሁንም ወደፊትም ሰው ሆኖ የሚኖር መለኮት ነው። ነገር ግን ያ የመከራው ምዕራፍ እንዳበቃና እንዳለፈ ወደፊትም እንደማይደገም መገንዘብ ያስፈልጋል። ዛሬም ሰው ነው ሲባል ያኔ በዓመፀኞች እጅ መከራን እንደተቀበለ አሁንም ሊሠቃይና ሊሞት የሚችል ነው ማለት አይደለም።

ያኔ ክርስቶስ ወደ ክብሩ ከመግባቱ በፊት መከራን መቀበሉ ግድ ነበረ። ከሙታን በተነሣ ጊዜ፥ በመከራው ምክንያት ተሰናክለውበት የነበሩትን ደቀ መዛሙርቱን፣ “ክርስቶስ ይህን መከራ ይቀበል ዘንድና ወደ ክብሩ ይገባ ዘንድ ይገባው የለምን?” አላቸው (ሉቃ.24፥26)። አሁን ግን ከሞት ተነሥቶ መላእክት ሥልጣናትና ኃይላት ከተገዙለት በኋላ ወደ ሰማይ ሄዶ በእግዚአብሔር ቀኝ ነው ያለው (1ጴጥ.3፥22)። ወደ ክብሩ ገብቷል። ከሞት ከተነሣ ወዲህ የማይሞት ነው። “ክርስቶስ ከሙታን ተነሥቷልና፣ ዳግመኛ እንደማይሞት እናውቃለን፤ ሞት ከእንግዲህ በእርሱ ላይ ጉልበት አይኖረውም” ይላል (ሮሜ.6፥9/አ.መ.ት.)። ይልቁን ግን፣ ሰይጣንንና ዓመፀኞችን ሊቀጣ ይገለጣል።

ደግሞም፣ “ኢየሱስ ጌታ ከሆነ ታዲያ ለምን ሞተ? ራሱን ከገዳዮቹ እጅ ማዳን እንዴት ተሣነው? ጌታ ባይሆን ነው” ይላሉ። ይህን ሲሉ ጠንካራ መከራከሪያ ያቀረቡ ይመስላቸዋል።

ዳሩ ግን፣ አሁንም ይህ ጥያቄ ወንጌሉን ካለመረዳት የመነጨ ነው። ኃጢአተኞችን ሊያድን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም እንደመጣ አላወቁም። ኃጢአተኛ የሚድንበትን የእግዚአብሔርን አሠራርም ፈጽሞ አልተረዱም።

ኃጢአተኛን ማዳን እኮ የፍርድ ሂደት ነው እንጂ በጉልበት የሚረግ ነገር አይደለም። ምክንያቱም በኃጢአተኛው ላይ የፈረደበት እግዚአብሔር ነው። የእግዚአብሔር ፍርዱ ደግሞ ጻድቅ (ትክክል) ነው። የኃጢአተኛው ተተኪ (ቤዛ) ሆኖ ፍርዱን (ሞትን) በመቀበል ነው ኃጢአተኛውን ከፍርድ ነጻ በማውጣት ማዳን የሚቻለው።

ስለዚህ፥ ሞቱ፥ ክርስቶስ ሊፈጽመው ወደ ዓለም የመጣበት ዋነኛው ዓላማው ነው። ነፍሱን ለኃጢአተኞች ቤዛ ለመስጠት ነው የመጣው። እርሱ ራሱ፣ “... የሰው ልጅ ሊያገለግልና ነፍሱን ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ እንጂ እንዲያገለግሉት አልመጣም” ይላል (ማር.10፥45)።

እግዚአብሔርም ስለ ኃጢአታችን ማስተስሪያ እንዲሆን (እንዲሞት) ነው ክርስቶስን ወደ ዓለም የላከው (1ዮሐ.4፥10)። ሰቅለው የገደሉት አይሁድ እግዚአብሔር አስቀድሞ የወሰነውን ሐሳቡን ነው የፈጸሙት። “እርሱን በእግዚአብሔር በተወሰነው አሳቡና በቀደመው እውቀቱ ተሰጥቶ በዓመፀኞች እጅ ሰቅላችሁ ገደላችሁት” ይላቸዋል (ሐዋ.2፥23)።

* * * መጨረሻ * * *