አንድ የክርስትና ተቺ፣ “‘እግዚአብሔር ፍቅር ነው፤ ሰውን ይወድዳል’ ትላላችሁ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ‘ክርስቶስ እግዚአብሔርን ኃጢአታችንን ይቅር እንዲለን ለማሳመን ሞተ’ ትላላችሁ፤ ይህ እርስ በርሱ ይጋጫል” አለ።
ወንጌልን እየጠሉ የሚሰሙት አያስተውሉትም። የቱ ጋር ነው ወንጌል፣ “ክርስቶስ እግዚአብሔርን ኃጢአታችንን ይቅር እንዲለን ለማሳመን ሞተ” የሚለው? እግዚአብሔር መሐሪ ነው፤ ይቅር ማለት ይወድዳል። እርሱን ይቅር እንዲለን ማሳመን አያስፈልግም። እንዲህ ይላል፦
“‘በውኑ ኃጢአተኛ ይሞት ዘንድ እፈቅዳለሁን?’ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ‘ከመንገዱስ ይመለስና በሕይወት ይኖር ዘንድ አይደለምን? ... ‘ስለ ምን ትሞታላችሁ? የምዋቹን ሞት አልፈቅድምና’ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ‘ስለዚህ ተመለሱና በሕይወት ኑሩ።’” (ሕዝ.18፥23፣32)
በሌላም ስፍራ፣ “አንተ ቸርና መሐሪ አምላክ ነህና በምሕረትህ ብዛት ፈጽመህ አላጠፋሃቸውም፥ አልተውሃቸውምም” ይላል (ነህ.9፥31)።
ያዳነን እግዚአብሔር ራሱ ነው፤ የድነታችን መሐንዲስ፤ ድነትን ያዘጋጀልን፥ ያሰበ፥ ያቀደና የሠራልን። መዳናችን ከእግዚአብሔር መሐሪነትና እኛን ከመውደዱ የተነሣ ነው። “... እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለ ጠጋ ስለ ሆነ፥ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን፥ በጸጋ ድናችኋልና” ይላል (ኤፌ.2፡4-5)። ዓለም በእርሱ እንዲድን አንድያ ልጁን ቤዛ አድርጎ ሰጥቷል።
ይህ ከሆነ ታዲያ፥ ይቅርታን የማይወድ ይመስል፥ እግዚአብሔርን ሰውን ይቅር እንዲል ማሳመን እንደሚያስፈልገው አድርገን ማሰብ የለብንም። ይቅር ባይነት ባሕሪው ነው።
ይልቁን ክርስቶስ እንዲሠዋ ያስፈለገው የእግዚአብሔርን ጽድቅ ለመፈጸም ነው።
እግዚአብሔር ለሰው ምሕረት ሲያደርግ በሰው ኃጢአት ላይ በሕጉ መሠረት እንዲፈርድ ግድ ነው። ያለዚያ ግን ብይኑ ሕገ-ወጥ ይሆናል፤ ከእግዚአብሔርም ጻድቅነት ጋር ይቃረናል። ዳሩ ግን ሕጉ ሊጣስ አይቻልም፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ጻድቅ ነው። ጌታ ኢየሱስም ሕግን ሊፈጽም እንጂ ሊሽር አልመጣም። “እኔ ሕግንና ነቢያትን ለመሻር የመጣሁ አይምሰላችሁ፤ ልፈጽም እንጂ ለመሻር አልመጣሁም። እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይና ምድር እስኪያልፍ ድረስ፥ ከሕግ አንዲት የውጣ ወይም አንዲት ነጥብ ከቶ አታልፍም፥ ሁሉ እስኪፈጸም ድረስ” ይላል (ማቴ.5፥17-18)።
በመሆኑም እግዚአብሔር ሕጉ በሚጠይቀው መሠረት በክርስቶስ ሥጋ በሰው ኃጢአት ላይ ፈረደ።
“... እግዚአብሔር የገዛ ልጁን በኃጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ በኃጢአትም ምክንያት ልኮ አድርጎአልና፤ እንደ መንፈስ ፈቃድ እንጂ እንደ ሥጋ ፈቃድ በማንመላለስ በእኛ የሕግ ትእዛዝ ይፈጸም ዘንድ ኃጢአትን በሥጋ ኰነነ።” (ሮሜ.8፥3-4)
“የሕግ ትእዛዝ ይፈጸም ዘንድ” የሚለው ሕጉ የሚጠይቀውን የጽድቅ ፍርድ ማለት ነው። እሱን ክርስቶስ ለኃጢአተኛው ቤዛ ሆኖ (በሐዋርያው አገላለጽ “በኃጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ” ሆኖ) በመሞት ፈጽሞታል፤ “ኃጢአትን በሥጋ ኰነነ” የሚለው።
በዚህ ምክንያት፥ ሕጉ ሳይጣስ፥ እግዚአብሔር ጻድቅነቱን ጠብቆ በክርስቶስ የሚያምነውን ከኃጢአቱ ሊያጸድቀው ችሏል። “... በፊት የተደረገውን ኃጢአት በእግዚአብሔር ችሎታ ስለ መተው ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው፥ ራሱም (እግዚአብሔር) ጻድቅ እንዲሆን በኢየሱስም የሚያምነውን እንዲያጸድቅ አሁን በዚህ ዘመን ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው” ይላል (ሮሜ.3፥25-26)። የክርስቶስ ሞት አስፈላጊነት የማይታያቸው የእግዚአብሔርን ጻድቅነት የማያውቁና ያልተረዱ ናቸው።