ዐውደ በረከት

@awde_beki


Bot -> @Awedebeki_bot

ዐውደ በረከት

13 Oct, 05:56


የገነትን ደጅ የከፈታት ማን ነው?

ያቺ በአባታችን አዳምና በእናታችን ሔዋን በደል ተዘግታ የነበረችውን የገነትን ደጅ ማን ከፈታት? ሱራፊ በእሳት ሰይፍ እየጠበቃት ተዘግታ የኖረችዋ የተድላ ደስታ ስፍራዋን ገነትን ማን ከፈታት? ሲል ሊቁ አባ ጽጌ ድንግል ይጠይቃል። እውነትም ግን በአምላክ ላይ በማመጽ በመፈንቅለ አምላክ ሙከራ ምክንያት የተዘጋችውን የገነትን ደጅ ማን ከፈታት? ሊቁ ጠይቆ ብቻ አያቆምም መልሱን አስቀድሞ ከላይ እንዲህ ሲል መልሶልናል፦ ከአንቺ ጽድቅ ውጪ የገነትን ደጅ የከፈታት ማን ነው። የገነት ደጅ የተከፈተው በእመቤታችን ጽድቅ መሆኑን አስረግጦ ይነግረናል።

ይህ ገነትን ያስከፈተ የቀድሞውን በደል የካሰ ጽድቅ እንዴት ያለ ነው? መልሱም ይኸውም ጽድቋ የማኀጸኗ ፍሬ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ስለምን ጽድቋ ብሎ ጠራው ከተባለም ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍሷም ነፍስን ነስቶ ከርሷ የነሰውንም ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍሶ በደሙ ማኀተምነት የገነት ደጅ ተከፍቷልና ጽድቅሽ ብሎ ጠራው። አንድም በንጽሕና በቅድስና ሆና ቢያገኛት በጽድቋ ምክንያት ከእርሷ ለመወለድ መርጧልና የአምላክ ከእርሷ መወለድ ከእግዚአብሔር ሁሉን ቻይነት ቀጥሎ የእርሷ በጽድቅ(በንጽሕና በቅድስና) መገኘት አስፈላጊ ነውና ጽድቅሽ ሲል ጠርቶታል። ይህ መዐዛ ቅድስናዋ መዐዛ ንጽሕናዋ የፍጥረታትን ንጉስ የገነትን ጌታ ወደምድር ሳበው። ከበደለው ከሰው ልጅ ጋርም አስታራቀው። የገነትን ፈጣሪ ወደዚህ ምድር ከሳበው ከሰው ጋር ካስታረቀው ከዚህ ከጽድቅሽ በቀር የገነትን ደጅ የከፈታት ማን ነው ሲል ነው ሊቁ።በዚህ ጽድቅሽም አዳም ወደ ቀድሞ ስፍራው ወደ አበባዋ ምድር ወደ ተድላዋ ስፍራ ገነት ተመለሰ እናታችን ሔዋንም አጥታው የነበረውን ገነት አግኝታለችና ከገነት ጣዕም የተነሳ በደስታ ዘለለች።

       ድንግል ሆይ እኛም ዛሬ በኃጢአታችን ምክንያት ዘወትር የምንዘጋትን የገነት ደጅ የሚከፍትልን ከአንቺ ጽድቅ በቀር ማን ነው? ስለዚህ ቸል አትበይን አትተይንም የገነትንም ደጅ ምሪን  መንገዱን ዘንግተናዋልና ፍለጋዋንም ጠቁሚን በዓለም ማዕበል በመባዘን መንገዷን ስተናልና። የገነትን ደጅ ዘግቶ የምትገለባበጥ ሰይፍ ሆኖ እንዳንገባ የሚከለክለን ኃጢአታችንንም ከእኛ አርቂልን ወደ ቀደመ ሥፍራችን እንገባ ዘንድ እንደ እናታችን ሔዋንም ከደስታ ብዛት ለመዝለል ያበቃን ዘንድ የገነትን ደጅ በጽድቅሽ ክፈቺልን የገነትን መዐዛዋን አሽትተን እንታደስ ዘንድ የገነትን ጣዕም አቅምሽን የገነትን ደጅ የሚያስከፍት ምንም ጽድቅ በእኛ ዘንድ የለምና።

     ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና የገነትን ደጅ ነገር እንመርምር የሊቁ ምሥጢር በዚህ ብቻ የሚያበቃ አልመሰለኝምና ግሩም የሆነውን ይህንን ምስጢር እንረዳ ዘንድ አምላካችንን እንለምነው የተሰወረውን የሚያውቅ ምስጢርን የሚገልጥ እርሱ ነውና እንማጸነው። ይህች የገነት ደጅ ሯሷ ድንግል ማርያም ናት። በር ከውጭ ያለው ወደ ውስጥ እንዲገባ ምክንያት እንዲሆን ከገነት ውጭ የነበርን እኛ በእርሷ ምክንያት ወደ ገነት ገብተናልና  ወደገነት የገባንባት የገነት ደጃችን እርሷው ናት። ጽድቅሽ ያለውም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ነው። ሊቁ"እንበለ ጽድቅኪ መኑ ለአንቀጸ ገነት ዘአርኀዋ" ማለቱ ፍጹም የሆነ የድንግልናዋን ነገር ማንሳቱ ነው። አስቀድሞ ሕዝቅኤል በትንቢቱ ከወደ ምስራቅ ያያት ከኃያላን ጌታ በቀር ማንም ያልገባባት በምስራቅ የተተከለችዋ ደጅ ገነቲቱ እመቤታችን ናት።

     ድንግለ ሆይ የገነትን መዐዛ እንናፍቃለንና የገነት መዐዛ የተባለ መዐዛሽን አሻችን በኃጢያት የከረፉውን ሰውነታችንን በመዐዛሽ ይታደስልን ዘንድ። በምልጃሽ ቁልፍነትም የገነትን ደጅ ክፈቺልን።

በጌጋየ አዳም ወሔዋን ሱራፊ ዘዐፀዋ
እንበለ በጽድቅኪ መኑ ለአንቀጸ ገነት ዘአርሃዋ
ተፈስሒ ድንግል መያጢተ አዳም እምጼዋ
በተዓምርኪ ውስተ ምድረ ነኪር አቲዋ
ከመ ጣዕዋ አንፈርዓፀት ሔዋ

ዲ/ን በረከት ንጉሴ

ዐውደ በረከት

05 Oct, 17:16


እንዴት ልከተልሽ?

የኔ እናት የጭንቅ ጊዜ ማለፊያዬ የመከራ ጊዜ መሸሻዬ ከስደቴ የማርፍብሽ ከሀዘኔ የምጽናናብሽ በጎዶሎዬ ሁሉ የምትሞይልኝ እናቴ የስደት ጉዞ መጀመርሽ እንዴት ያስደንቃል። ጨረቃን የተጫማሽ ስትሆኝ ስለሰው መዳን ስትይ በአሸዋው ግለት በባዶ እግርሽ መንከራተትሽን ሰምቶ የማይደነቅ ማን ነው? ለፍጥረት ሁሉ መጋቢ የሆነውን የሕይወት እንጀራን የተሸከመችው ድንግል ማርያም የተራበችውን ሔዋንን ታጠግብ ዘንድ በየሰው ቤት  ፍርፋሪን  ልመና ደጅ ጠናች። ሊቁ በቅኔቸው እንዲህ ብለው እንደተናገሩ፦
          "ማርያም ድንግል ዘኢትፈርህ ሐሜተ ፍርፋራተ ኀብስት ሰአለት በፍና እንዘ ትፀውር ሕብስተ፤ ሐሜት የማትፈራው ድንግል ማርያም የሕይወት እንጀራን ተሸክማ በመንገድ ላይ የእንጀራ ፍርፋሪን ለመነች።"

    የስደተኞች መጠጊያ ተሰደደች የሐዘንተኞች መጽናኛ አዘነች ለተራቡት የእንጀራ ገበታቸው እርሷ ተራበች የፊቷ ጸዳል ከፀሐይ ሰባት እጥፍ የሚያበራው  ያ ገጿ ስለሰው መዳን በግብጽ የአሸዋ ብናኝ ተሸፈነ ስለዚህ ስደትሽ ምን ማለት ይቻለኛል? ይህን ሀዘንሽን እንዴት መግለጽ ይቻላል? የመከራሽ መጠኑንስ ማንስ መረዳት ይችላል? ሊቁ በሰቆቃወ ድንግል ድርሰቱ እንደተናገረ የእመቤታችን መከራ በእንባ የሚጻፍ የሚያነበውም ወዮ እያለ የሚያነበው እንደሆነ ይናገራል ይህን የእመቤታችንን ሐዘን መረዳት የሚችለው የልብ ዐይን ያለው እንደሆነ ሲመሰክርም "ርእዮ ለይብኪ ዐይነ ልብ ዘቦ" ብሎ ተናግሯልና የልብ ዐይንን አድለሽኝ እያለቅስኩ አብሬሽ መሠደድን እመኛለሁ።

       ስደተኛይቱ ድንግል ሆይ በዚህ የመከራሽ ወቅት አብሬሽ መሠደድን እመኛለሁ። በስደትሽ እከተልሽ ዘንድ እሻለሁና እንዴት ልከተልሽ? በመከራዬ በሀዘኔ በችግሬ በጭንቀቴ ሁሉ እናቴ እንድልሽ በመከራ ጉዞሽ እንዴት ልከተልሽ? ከፊትሽ ቀድሜ ወደግብጽ ልሒድን? የበረኻውንስ ክበደት ተመልክቼ ልመለስን የመንገዱን ርዝመት ለክቼ ልንገርሽን? ከፊትሽ ቀድሜ ድንጋዮችን ላንሳልሽን? አቀበቱን ቁልቁለቱን የምትሔጂበት መንገዱን ላዘጋጅ? ሽፍቶች መኖራቸውንስ አይቼ ልምጣ? የግብጽ ሀገር ሰዎች ውሻ እንዳይለቁብሽ ቀድሜሽ ሔጄ ልመክትልሽ?ወይስ እግሬን ካንቺ ማስቀደሜን ልተው? በመከራዬ ቀን እናቴ ብዬ እንድጠራሽ በመከራሽ በስደትሽ እንዴት ልከተልሽ? እንደ አረጋዊዮሴፍ አብሬሽ ልከተል ዳገት ቁልቁለቱን  አብሬሽ ልንከራተትን? የበረሐውን ዋዕይ  የውሃውን ጥም የርኀብሽን መጠን ልካፈልን?አህያውን ልያዝ? በመከራዬ ቀን እናቴ እንድልሽ በመከራ ጉዞሽ እንዴት ልከተልሽ? ወይንስ እንደ ሠሎሜ ከኋላሽ ልከተል ስንቅሽን ልሸከም የረገጥሽውን ልርገጥ የሔድሽበትን ልሒድ የተጓዝሺውን ልጓዝን? በመከራሽ ሀገር በስደትሽ መንደር በእጄና በጀርባዬ ስንቅሽን ተሸክሜ ልከተልን? የሌሊቱን ቍር የቀኑንን ዋዕይ አብሬሽ ልካፈልን?እናቴ ሆይ መከራዬ የሚቀለው ባንቺው ነውና መከራሽን እንዴት ልካፈልሽ?እንደ ዮሳ ታምሜ በገሊላ ልቅርን አንቺን የመከተል አቅምን እስካገኝ ከህመሜ እስክድን ከአልጋ እስክነሳ በገሊላ ልቀመጥን? የሄሮድስን እቅድና ክፋት የሠልፈኛውን ዜና ይዤ ልድረስብሽን? ከስደት የማርፍሽ እናቴ በስደትሽ እንዴት ልከተልሽ? ከሀዘኔ የምጽናናብሽ እመቤቴ ሆይ ሀዘንሽን እንዴት ልካፈልሽ? ጭንቄን የማልፍብሽ መድኃኒቴ ሆይ ጭንቅሽን እንዴት ልጋራሽ? በመከራሽ ዘመን በስደትሽ ወቅት እንዴት ልከተልሽ?

      ሊቁ "ገብርኪሰ እመ ሀሎኩ በውእቶን ዓመታት እምፈተውኩ ይርከበኒ ምስሌኪ ስደት፤ እኔ አገልጋሽ ግን በእነዚያ ዓመታት ኑሬ ቢሆን ከአንቺ ጋር ብሰደድ በወደድሁ ነበር።" እንዳለ ካንቺ ጋር መሰደዱን እመኛለሁ በበረሓው የፀሐይ ሐሩር እንዳንቺ ልቃጠል። እንደ ሊቁ ምኞት የረገጥሽውን መሳም እመኛለው ያረፍሽበትን ዓለት መላስ እመኛለሁ የእንባሽ ጠብታ ያረፈባትን አፈር መብላትን እመኛለሁ። የገሊላ ሠዎች ሆይ እንቦሳይቱ ከበረቷ ወደየት ሔደች? ዜናዋን ንገሩኝ መንገዷን አሳዩኝ ወደ ሔደችበት ሁሉ በለቅሶ እከተላት ዘንድ የሔደችበትን ጠቁሙኝ የደረሠባን በልብ ዐይን አይቼ አለቅስ ዘንድ። የኢየሩሳሌም ቆነጃጅት ሆይ ማርያምን በቁስቋም ተራራ በጫካውም ካገኛችኋት በመከረኛ ዓለም በጭንቅ ያለሁ የጎስቋላ አገልጋዮን ልመናና ለቅሶ ትነግሯት ዘንድ በኃያሉ አምላክ ስም አምላችኋለሁ። በመከራዋ አብሬት ልሆን እመኛለሁና በስደቷ እንዴት ልከተላት? ሀዘኔን ጭንቀቴን መከራ ችግሬን ያቀለለችውና የምታቀለው እርሷ ናትና በስደቷ እንዴት ልከተላት?

"ድንግል ሆይ በመከራዬ ቀን እናቴ ብዬ እንድጠራሽ በመከራ ጉዞሽ እንዴት ልከተልሽ?"

ዲ/ን በረከት ንጉሴ
#ጽጌ_Challenge 1

ዐውደ በረከት

28 Sep, 17:25


"ስለ እኔ እንዳታስብ"

         ስለ ህጻናት ስናስብ ከምንም ቀድሞ ትውስ የሚለን የዋኀነትና ንጽህናቸው ነው አብሮም ከዚህ የሚመነጭ ጥያቄያቸውና ሀሳቦቻቸው ሊዘነጉ አይችሉም። በአንድ የአሜሪካ ትምህርት ቤት ህጻናቱ ለእግዚአብሔር የጻፋትን ደብዳቤ እየተመለከትኩ ብዙዎች ከጥያቄዎቻቸው የተነሳ የዋኀነታቸውን እየተመለከትኩ ፈገግ ማለትን ሳልተው ከመካከል ያለውን ዳኒ የተባለ የ6 ዓመት ህጻን የጻፈውን ደብዳቤ ተመለከትኩኝ እንዲህ ይላል። "ውድ እግዚአብሔር ስለ እኔ እንዳታስብ እሺ። ሁል ጊዜ መንገድ ስሻገር ግራና ቀኝ በደንብ አይቼ ነው።"

       ተመልከቱት ይሔን የዋህ ህጻን ግራና ቀኝ አይቶ መሻገር ስለቻለ ብቻ እግዚአብሔር  የማያስፈልገው መስሎታል።እርሱን በመጠበቅ ስራ እንዳይበዛበት እግዚአብሔር እንዳይሰቸግርው ሰግቷል በዛ ላይ አሁን እንዳደገና ለራሱ መሆን እንደሚችል ተሰምቶታል፤ ስለዚህ  እግዚአብሔርን ሊያሳርፈውና በራሱ ሊንቀሳቀስ ስለፈለገ እግዚአብሔርን ስለእኔ እንዳታስብ የሚል መልዕክትን ለእግዚአብሔር  ልኳል።

           ይህን መልዕክት ከአንድ የ6 ዓመት ልጅ ያገኘነው በመሆኑ በየዋህነቱ ፈገግ ብለን ብናልፈው። ይህ ዓይነቱ የልጅነት ጠባይ በእኛ ህይወት ውስጥም በተደጋጋሚ ይስተዋላል። በአቅማችን በችሎታችን በእውቀታችን ተማምነን በዚህ ነገርማ እግዚአብሔር አያስፈልገንም በሚመስል መልኩ ፈቃደ እግዚአብሔር ሳንጠይቅ የወሰናቸው ያረግናቸው ነገሮች ሁሉ ስለእኔ እንዳታስብ ካለው የህጻኑ ደብዳቤ ጋር አንድ አይነት ነው። ስለዚህ ይህ አይነቱን የልጅነት ጠባይ እንሻርና ወደ አለማወቃችንን በመመለስ አንተ ምረኛ እንበል ሳበኝ ከአንተም ኋላ እከተላለው ብለን እግዚአብሔርን እናስቀድመው። ወደየትንም እንደሚያሰማራን እንማጸን ጌታዬ ሆይ ወደየትስ ታሰማራኛለህ እንበል።

ጌታዬ ሆይ ወደየት ታሰማራኛል? ሳበኝ ከአንተም ኋላ እከተላለሁ። ስለዚህም ስለ እኔ በመጨነቅ አንተ ምራኝ።

ዲ/ን በረከት ንጉሴ
መስከረም 18/2017     
https://t.me/awde_Beki

ዐውደ በረከት

24 Aug, 03:43


"እኔ ነኝ" ዩሐ 9፥9

ጌታችን ከቤተመቅደስ አስተምሮ ሲወጣ በመንገድ ሲያልፍ እውር ሆነ የተወለደውን አየ። ይህን ሰው ምራቁን እንትፍ ብሎ ጭቃ አድርጎ ዐይን ሠርቶ ሂዲና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ አለው ያም እውር ሒዶ ታጠበና እያየ ተመለሰ። በመንገድ በሚመጣበት ወቅት ቀድሞ ያውቁት የነበሩት ሠዎች 'ይህ በመንገድ ተቀምጦ ይለምን የነበረው አይደለምን? ' ብለው መጠየቅ ጀመሩ ገሚሶቹም እርሱ ይሆን አለ? ገሚሶቹ 'አይደለም እርሱን ይመስላል እንጂ'  አሉ፤ እርሱ ግን "እኔ ነኝ" አላቸው።
    ልክ እንደዚህ እውር ዛሬም በጨለማ የነበርኩ ሆኜ ሣለሁ ብርሃንህን አይ ዘንድ ውሣጣዊ ዐይኔን ብሩህ አርገህ ከጨለማ ያወጣኸኝ። ከድቅድቅ ጨለማ ወደ ሚደንቅ ብርሃን በፍቅርህና በምህረት የጠራኸኝ። ሥራዬ እጅግ የከፋ በበደሌ በሠው ሁሉ የታወቅኩ በመጨለማ መሆኔ ለሠው ሁሉ የተገለጠ እኔን በፍቅርህ  የሣብከኝ "እኔ ነኝ" መዓዛዬ በኀጢኣት የከረፋ ሆኜ ሣለሁ በነውሬ ብዛት መሽተቴን ሣትጠየፍ ወደእኔ መጥተህ ምዑዝ  የሆነ መዐዛህ የሠጠኸኝ በኃጢያት ባህር በጥልቁ ሠምጬ ሣለሁ የንስሐን ገመድ የምህረትህን እጅ ልከህ ከኀጢያት ያወጣኸኝ እኔ ነኝ።
      ሠዎች በቤትህ ለልጅነት መሾሜን በፍቅር መጠራቴን አይተው ይኸህ በጨለማ ህይወት ይኖር የነበረው አይደለምን ይላሉ። አዎን "እኔ ነኝ" የማይወጡትበት የኃጢያት ረግረግ የተዋጣኩ የማይነጋ በሚመስለው ጨለማ ውስጥ የተቀመጥኩ ብሆንም እርሱ ግን ሳይንቀኝ ወደ እኔ ቀረበ ፍቅሩና ቸርነቱን አበዛልኝ ከረግረጉ ጎትቶ ያወጣኝ ጨለማውን ገላልጦ ብርሃኑን ያበራልኝ "እኔ ነኝ"። የምህረቱና የቸርነቱ መጠን ማሳያ እኔ ነኝ። ሊቁ "ብዙ ኃጢያት ባለችበት የእግዚአብሔር ጸጋ ትበዛለች" ብሎ እንደመሠከረ ከሁሉ የበደልኩ ሆኜ ሣለ ከሁሉ ይልቅ የምህረትህን የችሮታህን ጸጋ ያበዛልኝ እኔ ነኝ።
        አሁንም በፍቅርህና በምህረትህ ጠርተኸኝ ከጨለማው አላቀኸኝ ብርሃንህን አሳይተኸኝ ዐይኔን አብርተህልኝ ወደ ጨለማው የምናፍቅ ከኀጢኣት ጽልመት አርቀህ ወደ ጸአዳነት መልሰኸኝ ማረፊያ አጥቼ ስዋልል የነበርኩትን በቤትህ አሳርፈኸኝ ተርቤ የነበርኩትን ሥጋህናን ደምህን መገበኸኝ ሁሉን ሰጥተኸኝ ሣለ አሁንም ከብርሃን ይልቅ ጨለማውን የምናፍቅ ከጽድቅ ብርሃን ይልቅ ጽልመትን የምመኝ ከዘላለም ማረፊያዬ ይልቅ ስደተኝነትን የምከጅል እንደ ግመል ሽንት ወደኋላ የምል ልጅህ እኔ ነኝ።
         ዛሬም ምህረትህ የሚያስፈልገኝ ጥሪህ የሚናፍቀኝ በቤትህ በቅጥርህ ሆኜ ባስቀመጥከኝ ያልተገኘው የጠፋው ባሪያህ  እኔ ነኝ። በቅዱሱህ ስፍራህ ያለውኝ ቅድስናን ግን ገንዘብ ማድረግ ያቃተኝ በብርሃን ሆኜ መንገዴ የጠፋብኝ። ብዙ የተቀበልኩ ብዙ የሚጠበቅብኝ ሆኜ ሣለው ምንም የሌለኝ  ከጽድቅ የተራቆትኩትኩኝ ባዶ እኔ ነኝ። ልክ እንደ ድሪሙ በቤትህ ሆኜ ዘወትር ከቅጥርህ ሣልጠፋ ነገር ግን ቆሻሻ በሆነ ህይወት በኀጢኣት ውስጥ የጠፋው በብርሃንህ ሥፍራ ብገኝም ኀጢኣቴና በደሌ አይኔን አዉሮኝ ጽድቅህንና ብርሃንህን ማየት የተሣነኝ ልጅህ እኔ ነኝ። አሁንም ምራቅህን ጥቅ ብለህ አንተን ማየት የሚችሉ ዓይንን ፍጠርልኝ። በፊቴ ላይ ቅዱስ ምራቅህን ጥቅ በልብኝ በፍቃዴ ያጠፋውትን ዓይኔንም አብራልኝ።

ዲ/ን በረከት ንጉሤ
በድጋሚ የተለጠፈ
https://t.me/awde_Beki

ዐውደ በረከት

28 Jul, 05:16


የአማረኛ መዝሙራት ስለእመቤታችን
#30Dayschallenge
https://t.me/awde_Beki

ዐውደ በረከት

13 Jul, 03:43


አልተወኝም ጌታ ለካስ ይወደኛል/2x/
ዛሬም ስበድለው ልጄ ነህ ይለኛል።


    ይህን መዝሙር የልጅነት ትውስታዬ ነው።ገና በህጻናት ክፍል ሳለሁ እንጥሌ እስኪታይ ድረስ ጮክ ብዬ እዘምረው ነበር፤ ያኔ ገና በደል ምን እንደሆነ ሳለይ በፊት የዛሬ በደሎቼ እየታዩኝ ነው መሰል እጅግ ከልቤ እዘምረው ነበር፤ አቤት ምን ያህል እወደው እንደነበር መርሐ ግብር መሪው መዝሙር ምረጡ ሲለን "እኔ. . . እኔ. . .  እኔ. . . " እያልኩ እጄን አይኑ ውስጥ ልከት ስደርስ 'እሺ በረከት ምረጥ' ይለኛል "አልተወኝም ጌታ" እል ነበር። ግን ዛሬስ?

       ትናንት ገና በደል ሳላውቅ ልቤ ንጹህ በሆነበት ዘመን በበደል ጉራንጉር በኃጢያት ጫካ ብጠፋም እንደማይተወኝ ብበድልም ልጄ ብሎ እንደሚጣራኝ እንዳልመሰከርኩ፤ ዛሬ ግን በበደል ስወድቅ በነውሬ ብዛት እንደማይተወኝ መመስከሩን ዘነጋሁት እንደውም ለአገኘሁት ሁሉ እግዚአብሔርማ ረስቶኛል ትቶኛል እያልኩ ለፍጡር ፈጣሪን አማው ጀመርኩ። ራሴው ብረሳው የረሳኝ መሰለኝ ቁጭ ብሎ በደጁ እንደሚጠብቀኝ ዘነጋው እንደ ጠፋው ልጅ አባት የንስሐ በሩን ከፍቶ ከደጁ ተቀምጦ ከእሩቅ አሻግሮ ይመጣ ይሆን እያለ እንደሚጠብቀኝ ዘነገውትና እሱማ ትቶኛል አልኩት በበደል ብዛት ዲዳ ሆኜ እንደሆነ ዘንግቼው አይሰማም አልኩት። እኔው ብተወው በእኔው ዐይን አየሁትና አይተወኝም ብዬ መመስከር አቃተኝ እንጂ በእውነት ግን እርሱ አልተወኝም።

     ለጊዚያዊ ደስታ፣ ክብር፣ ስልጣን ብዬ ችላ አልኩት ከእርሱ ይልቅ ገንዘብን አስበልጩና መርጬ ብተወዉ ጊዜ ረሳኝ አልኩት መኖሩን እንኳን ረስቼ በበደል ውስጥ ከመኖሬ ብዛት የበደልን መልክ ይዤ ተገኘሁና የእርሱን ብርሃን ማየት ቢያቅተኝ ትቶኛል አልኩ ሊቁ እንዳለ "ብዙ ኃጢያት ባለችበት የእግዚአብሔር ጸጋ ትበዛለች" እና የእኔ በደሌ ቢበዛ ኃጢአቴ ቢገዝፍም የፍቅርህ ጽናቱ እኔን መናፈቅህ ጨመረ እንጂ በፍጹም አልጎደለም ነበር፤ ነገር ግን ይህን የሚያይ የልብ ዐይን አጣሁና ህልውናህን ተጠራጠርኩ።ባይኖር ነው እንጂ ቢኖርማ መች ዝም ይል ነበር አልኩ ኃጢአት ጆሮዬን ደፍኖት ደንቆሮ መሆኔን ዘንግቼ። አንተ ግን ዛሬም ፍቅርህ ሳይጎል እኔን በመናፈቅና በመጠበቅ ዐይኖችህ በር በሩን ከማየት አልቦዘኑም።

        ታዲያ ለዚህ ወሰን ለሌለው ፍቅርህ ምንስ ማለት ይቻለኛል ምንስ እከፍልህ ዘንድ ይመጥናል። ብቻ አሁንም ልልህ የምችለው እስከዛሬ የተሸከምከኝ ፍቅርህን ያላጎደልክብኝ ብተውህም ያልተውከኝ ሆይ ዛሬም አትተወኝ ቸልም አትበለኝ። አንተ ኃጢአትን እንጂ ኃጢአተኛን መጠየፍ የሌለብህ ነህና አትናቀኝ። ከሰመጥኩበት የኃጢአት ባህር በፍቅርህ ገመድነት ወደ ጽድቅህ ሳበኝ። በንስሐ መንገድም ምራኝና እንደልጅነቴ አይተወኝም ጌታ እያልኩ ከፍ ባለ ድምጽ ልመስክርልህ።

አልተወኝም ጌታ ለካስ ይወደኛል/2x/
ዛሬም ስበድለው ልጄ ነህ ይለኛል።



በዲ/ን በረከት ንጉሴ
በድጋሚ የተፖሰተ
https://t.me/awde_Beki

ዐውደ በረከት

06 Jul, 04:59


ወደ እኔ ና ሳበኝም

           በህይወታችን አንዳንድ ጊዜ አለ አይደል? ሁሉ ነገር የሚደራረብባችሁ ዙሪያው ጨላማ የሚሆንባችሁ መከራው ሁሉ የሚከብዳችሁ ሸክም ሁሉ የሚጸናባችሁ ጊዜ አለ አይደል? ልክ እሱ ጊዜ ላይ ሆኜ በጣም ስጨነቅ ለአንድ ወዳጄን አማከርኩት እርሱም ይህን ጥቅስ ጠቅሶ ሊያጽናናኝ ሞከረ “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ።” ማቴ 11፥28 ውስጤ በጥያቄ ተወጠረ ደካማ መሆኔን ተርድቶ ሸክሜ መክበዱን አውቆ ሳለ እንዴት ወደእኔ አይመጣም? እንዴት ወደ እኔ ና ይለኛል? በእኔ ደካማነት ያውም ሸክሜ ከብዶ  እንዴት እርሱ ድረስ ችዬ እሄዳለሁ? የሚል ጥያቄ ውስጤን ይንጠው ጀመረ።

            ጌታዬ ሆይ አንተ ወደ እኔ ና አቅሜን ታውቀው አይደል፤ አንተ ጋር እንዴት እደርሳለሁ? ሸክሜንስ ታውቀው አይደል እንዴት እችለዋለሁ? እኔ ግን እንደ ጴጥሮስ በማዕበል ውስጥ ሆኜ "ጌታ ሆይ አድነኝ" ስል እጣራለሁ። ጴጥሮስን እጁን ስበህ የማዕበሉን ሸክም አቅልለህ እንዳወጣኸው እኔንም ሸክሜን አቅልለህ ወደ አንተ ሳበኝ። ጌታዬ ሆይ ሳበኝ ሸክሜንም አራግፍልኝ ያኔ ሸክሜ ቀሏልና ከአንተ ኋላ እሮጣለሁ። ስምህ እንደሚፈስ ሽቱ ነውና ስምህን በላዬ ላይ አፍስልኝ ደናግል በወደዱህ መውደድም ልውደድህ። ጌታዬ ሆይ ሰሎሞን በመኃልየ መኃልዩ "ስምህ እንደሚፈስ ሽቱ ነው፤ ስለዚህ ደናግል ወደዱህ።" እንዳለ እንደደናግሉ ያለ ፍቅር በእኔ ልብ የለም። የተገዛውላቸውና  የማደርጋቸው ሥጋዊ ምኞቶቼ ሸክም ሆነው ከብደውኝ ወደ አንተ መድረስ አልቻልኩምና ሸክሜን አራግፈህ ሳበኝ በእራሴ ወደአንተ መምጣት አይቻለኝምና።

             ጌታዬና መድኃኒቴ ሆይ ማቴዎስን ከቀራጭነቱ ሸክም አላቀህ ተከተለኝ እንዳልከው እኔንም ሸክሜ አላቀህ ተከተለኝ በለኝ። ወደቤቴ ግባና እንደዘኪዮስ ዛሬ ለዚህ ቤት መዳን ሆኗል የሚል ቃልን አሰማኝ። ይህን ለማድረግ ዛፍ ላይ መውጣት ካለብኝም እንደ ዘኪዮስ ምድራዊ በሆነ በሾላ ዛፍ ላይ ያይደለ ሥሮቿ በምድር ቅርንጯፋ በሰማይ የሆነችውን ዛፍ/ሀረግ/ እናትህን እርሷን ተጠግቼ በእርሷ አማላጅነትም ተንጠላጥዬ አንተን ለማየት ተስፋ አደርጋለሁና ጌታዬ ሆይ ወደ እኔ ና ዛሬ በቤትህ እውል ዘንድ ይገባኛልም በለኝ።

         ይህን እያሰብኩ ወደተነሳሁበት ጥቅስ ኀሊናዬ መለሰኝ “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ።” ማለቱ ለካ የሚያሳየው ቅርብ መሆኑን ነው። ኑ ማለቱም እንዳግዛችሁ ፍቀዱልኝ ሲል ነው ለካ! ጌታዬ ሆይ አንተ በሁሉ የሞላህ አይደለህ የትም ብሔድ አንተ ከእኔ ጋር ነህ ስለዚህ ጌታ ሆይ አድነኝ ሳበኝም ሸክሜንም አራግፈህ አሳርፈኝ። ይኸው ፍቃዴን ሰጥቼሀለሁ ጌታዬ ሆይ አሳርፈኝ።

“በጌታ የተቀበልኸውን አገልግሎት እንድትፈጽሙው ተጠንቀቅ።” ቆላስይስ 4፥17

ዲ/ን በረከት ንጉሴ
https://t.me/awde_Beki

ዐውደ በረከት

29 Jun, 03:56


ፍቅርኪ እሳት

      አባታችን አዳም በበደሉ ምክንያት ከገነት ሲወጣ ከተረገመው እርግማን መካከል  ምድር እሾህና አሜኬላን ታበቅልብሃለች የሚል ነው። ይህንን አባቶቻችን ሲተረጉሙ ምድር የተባለ ከምድር አፈር የተበጀ የአዳም ስጋ ሲሆን እሾህና አሜኬላ የተባሉ ደግሞ ፍትወታት እኩያት ኃጣውዕ መሆናቸውን አስተምረውናል። በዚህ የቤተክርስቲያናችን ትርጓሜ መሰረት ኃጢአት እሾህ ተብሎ ይጠራል።የምንሰራው በደል በሰውነታችን ላይ እሾህ እንደሚሆን ምን ያክሎቻችን እናውቅ ይሆን? ይህንን ትርጓሜ ስስማ ነፍሴ እጅግ ተጨነቀች በበደሌ የተነሳ  እሾህ ተብዬ ልጠራ የሚገባኝን መሆኔን ባስብ ጊዜ ልቤ ደነገጠብኝ።

           ከዚህ ሀዘን የሚያጽናናኝ ባገኝ ብዬ ህሊናዬን ከወዲያ ወዲህ ሳባዝን የአባታችን የአባ ጽጌ ድንግል ጸሎት  ትውስ አለኝ ሊቁ እንዲህ ሲል እመቤታችንን ይማጸናታል፦"ሦከ ኃጢአትየ ያውዒ ፍቅርኪ (ጽጌኪ) እሳት፤ የኃጢአቴን እሾህ ፍቅርሽ ያቃጥልልኝ።" ሊቁ ቀድሞ በአዳም እርግማን ምክንያት ወደ ሰው ልጅ የመጣው  የኃጢአት እሾህ የጠፋው በእመቤታችን መሆኑን በማመን በፍቅሯ እሳትነት የከበደውን እሾሁን በደላችንን ታጠፋልን ዘንድ ይማጸናል። እኛም የሊቁን ልመናን ልመናችን በማድረግ ለመጸለይ እንበቃ ዘንድ አስቀድመን ፍቅሯ በልቦናችን ላይ ይሳል ዘንድ እንማጸናል። የድንግል ማርያም ፍቅር ልብን ብቻ ሳይሆን ኃጢአትንም የሚያቃጥል  ነውና የእርሷን ፍቅር እንማጸናለን።

         ወዳጄ ሆይ የእመቤታችን ፍቅር ቀላል አይምሰልህ  ያለ ጥርጥር እመቤታችንን መውደድ እግዚአብሔርን የመምሰል ህይወት ነው። እርሱ እግዚአብሔር ንጽህናዋን ባየ ጊዜ ውበቷን ወዶ ከላይ ከአርያም ወደ ምድር የመጣው በትህትናም የተገለጠው ድንግል ማርያም የምትወደድ ሆና በመገኘቷ ነው። ስለዚህ እርሱ በወደዳት ልክ መውደድ እንኳ ቢያቅተን በአቅማችን በመውደድ እርሱን ወደ መምሰል እናድጋለን። ተወዳጆች ሆይ አሁንም ደግሜ እላለሁ የእመቤታችን ፍቅር ቀላል አይምሰላችሁ። ፍቅሯ ሐዋርያትን ለስብከት አትግቷል ሰማዕታትን ለሰይፍ ጻድቃንን ለምነና ያበቃ ኃያል ነውና ። በእርሷ ፍቅር የሰከረ ሰው ምን ያስፈራዋል  አምላክን በፍቅር ማሸነፍ የቻለ  የእርሷ ፍቅር ምነን ይሳነዋልና?

           ስለዚህ እንዲህ ስንል እንማጸናለን፦ ጌታ ሆይ የእናትህን ፍቅር በልቦናችን አሳድርብን አንደበታችንንም ለምስጋናዋ አሰልጥነው ዘወትርም በፍቅሯ እሳትነት የተሟሟቅን የታቃጠልን አድርገን። ፍቅሯ ከኀሊናችን አይነጠል ከሀሳባችን አይለይ ዘወትር እርሷን በማፍቀር እንኖር ዘንድ የበቃን አድርገን። በፍቅሯ እሳትነትም የኃጢያአታችንን እሾህ ታንድድልን።

                      ድንግል ሆይ ለፍቅርሽ አትጊን

ዲ/ን በረከት ንጉሴ

"በጌታ የተቀበልኸውን አገልግሎት እንድትፈጽመው ተጠንቀቅ"

https://t.me/awde_Beki

ዐውደ በረከት

28 Jun, 04:49


አበው ስለእመቤታችን
የመጨረሻ ቀን
#30Dayschallenge

ዐውደ በረከት

27 Jun, 03:21


አበው ስለእመቤታችን
Day 29
#30Dayschallenge

ዐውደ በረከት

26 Jun, 04:56


አበው ስለእመቤታችን
Day 28
#30Dayschallenge

ዐውደ በረከት

25 Jun, 03:36


አበው ስለእመቤታችን
Day 27
#30Dayschallenge

ዐውደ በረከት

24 Jun, 03:18


አበው ስለእመቤታችን
Day 26
#30Dayschallenge

1,123

subscribers

300

photos

14

videos