Amba Digital - አምባ ዲጂታል @ambadigmedia Channel on Telegram

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

@ambadigmedia


አምባ ዲጂታል በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ መረጃ፣ ዘገባዎችና አተያዮችን የሚያቀርብ ዲጂታል የሚዲያ መድረክ ነው፡፡

Amba Digital - አምባ ዲጂታል (Amharic)

አምባ ዲጂታል በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ መረጃ፣ ዘገባዎችና አተያዮችን የሚያቀርብ ዲጂታል የሚዲያ መድረክ ነው፡፡ Amba Digital - አምባ ዲጂታል የሀገራችንን ጉዳይና ተመልከቱን እና ከነባር ሌሎች ዓለም የስናትን መጽሐፍና ዜናዎችን ማድረግ ይችላሉ፡፡ ይህ የድርጅቱ የህዝብ ተሸላሚ መረጃ መሆኑን ያረጋግጣል። ስለዚህ ከባህር የተለያዩ ዝርዝሮችን ይዘትና መረጃዎችን ለማወቅ እና ለመረጃዎች በታች ለማውጣት እንጠቀማለን፡፡

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

31 May, 09:01


ከሰላማዊ ማዕቀፍ ውጪ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የፖለቲካ ቡድኖችን መልሶ ሕጋዊ እውቅና እንዲያገኝ ያስችላል የተባለ የአዋጅ ማሻሻያ ወደ ፓርላማ ተመራ

አምባ ዲጂታል፤ ዐርብ ግንቦት 23፣ 2016 - የሚኒስትሮች ምክር ቤት ከሕጋዊ እና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ማዕቀፍ ውጪ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የፖለቲካ ቡድኖች መልሰው እንደ ፖለቲካ ፓርቲ ለመመዝገብ የሚያስችላቸውን ድንጋጌ የያዘ የአዋጅ ማሻሻያ ወደ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መርቷል፡፡

ምክር ቤቱ የአዋጅ ማሻሻያውን ተቀብሎ ወደ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመራው ዛሬ አርብ ግንቦት 23፣2016 ባደረገው ስብሰባ እንደሆነ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስታውቋል። ጽሕፈት ቤቱ ያወጣው መረጃ እንደሚያስረዳው ምክር ቤቱ በዛሬው ዕለት በአራት ረቂቅ አዋጆች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል።

የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በዛሬው ስብሰባ ውሳኔ እንደተላለፈበት በቀዳሚነት የጠቀሰው የኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ እና የምርጫ አዋጅ ማሻሻያ የቀረበበት በ2012 የወጣው የምርጫ ሕግ፤ እውቅና የተነፈጉ የፖለቲካ ፓርቲዎችን መልሶ ከመመዝገብ ጋር በተያያዘ ክፍተት ያለበት እንደሆነ ተጠቅሷል፡፡

“ከሕጋዊ እና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ማዕቀፍ ውጪ የቆዩ የፖለቲካ ቡድኖች በሰላማዊ መንገድ ለመንቀሳቀስ ፍላጎት በሚያሳዩበት ጊዜ እነዚህን አካላት ሕጋዊ የፖለቲካ ፓርቲ አድርጎ ለመመዝገብ የሚያስችል ሥርዓት በነባሩ አዋጅ ላይ አልተካተተም” ሲል በሥራ ላይ ያለው አዋጅ ላይ የታየውን ክፍተት ይገልጻል።

የሚኒስትሮች ምክር ቤት ዛሬ የመራው ማሻሻያ ላይ የፖለቲካ ቡድኖች “በሰላማዊ መንገድ ለመንቀሳቀስ እና ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማበርከት ፍላጎት በሚያሳዩበት ጊዜ” መልሰው ለመመዝገብ የሚችሉበትን ሥርዓት የሚዘረጋ እንደሆነም ተጠቅሷል።

ዛሬው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ስብሰባ ውሳኔ ላይ የተጠቀሰው የፖለቲካ ቡድኖች መልሶ የመመዝገብ ጉዳይ ከሕወሓት ዳግም ሕጋዊ እውቅና የማግኘት ጉዳይ ጋር በተያያዘ ውዝግብ ፈጥሮ ነበረ ጉዳይ መሆኑ ይታወሳል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት መቀስቀስን ተከትሎ የአመጻ ተግባር ላይ ተሰማርቷል በሚል የህወሓትን ሕጋዊ ሰውነት የሰረዘው ጥር 2013 ነበር።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

30 May, 11:36


አሜሪካ የጅዳው ድርድር እንዲቀጥል ያቀረበችውን ግብዣ የሱዳን ጦር ውድቅ አደረገ

አምባ ዲጂታል፤ ሐሙስ ግንቦት 22፣ 2016 - በሌተናል ጄነራል አብዱልፈታ አልቡርሃን የሚመራው የሱዳን መደበኛ ጦር አሜሪካ በጅዳ ከተማ ከፈጥኖ ደራሽ ኃይል ታጣቂዎች ጋር የሚደረገው ድርድር ይቀጥል ማለቷል ውድቅ አድርጎታል።

የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶንዮ ብሊንክን በዚህ ሳምንት ከአብዱልፈታ አልቡርሃንና ሌሎች የሱዳን መንግስት ባለስልጣናት ጋር በመከሩበት ወቅት ከፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ ጋር የሚደረገው ድርድር እንዲቀጥል ሃሳብ አቅርበው ነበር።

ነገር ግን የሱዳን ሉዓላዊ የሽግግር ምክር ቤት ምክትል ማሊክ አጋር በአሜሪካ የቀረበውን የድርድር ሐሳብ ውድቅ አድርገውታል። አጋር መንግስታቸው የድርድሩን ሐሳብ ውድቅ ያደረገው ሰላም በመጥላት ሳይሆን ድርድር ለማካሄድ ቅድመ ሁኔታ ማስቀመጥ አስፈላጊ በመሆኑ ነው ብለዋል። አጋር ቅድመ ሁኔታውን አልዘረዘሩም።

የሱዳን ተፋላሚ ኃይሎች ከባለፈው አመት ጀምሮ በሳዑዲ ያደረጉት ድርድር በአሜሪካና ሳኡዲ አረቢያ የሚመራ ነው። ድርድሩ በተደጋጋሚ ቢሞከርም ፍሬ አላፈራም።

አብዱልፈታ አልቡርሃን እና መሀመድ ሀምዳን ዳጋሎ የሚመሩት ጦር በሚያካሄዱት ጦርነት በርካታ ሱዳናዊያን ህይወታቸውን አጥተዋል።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

29 May, 12:37


የቀድሞው የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር አብደላ ሐምዶክ ወደ ሥልጣን የመመለስ ፍላጎት የለኝም አሉ

አምባ ዲጂታል፤ ረቡዕ ግንቦት 21፣ 2016 - አዲስ አበባ ውስጥ የሚገኙት የቀድሞው የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር አብደላ ሐምዶክ ወደ ሥልጣን የመመለስ ፍላጎት የለኝም ብለዋል፡፡

ሐምዶክ ይህን ያሉት እርሳቸው የሚመሩት የሱዳን ፖለቲካ ኃይሎች የፖለቲካ ጥምረት አዲስ አበባ ውስጥ እያካሄደ በሚገኘው ስብሰባ ላይ ነው፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር በዚህ ስብሰባ ላይ የእርሳቸው ፍላጎት የአገራቸውን ወቅታዊ ችግር መፍታት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሐምዶክ በስብሰባው ላይ ወደ ስልጣን የመመለስ ፍላጎት ካላቸው በሚል ጥየቄ እንደቀረበላቸው የገለጹ ሲሆን፣ እርሳቸው ግን ሌሎች ለቦታው ብቁ የሆኑ ፖለቲከኞች ስልጣን ላይ እንዲቀመጡ ጥቆማ መስጠታቸውን ገልጸዋል፡፡

ቀድሞው የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር ሀገራቸው የህልውና አደጋ እንደተጋረጠባት በመጥቀስ፣ አፋጣኝ መፍትሔ እንደሚያስፈልግ ነው የጠቆሙት፡፡

የሱዳን መደበኛ ጦር መሪ የሆኑት ሌተናል ጀነራል አብዱልፈታህ አልቡርሃን እና ጀነራል መሐመድ ሃምዳን ዳጋሎ የሚመሯቸው ጦሮች ውጊያ ውስጥ ከገቡ ከአንድ ዓመት በላይ ተቆጥሯል፡፡ በሁለቱ ጀነራሎች መካከል ሰላም ለማስፈን ሳኡዲ አረብያ እና አሜሪካ በተደጋጋሚ ጥረት ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡

የሱዳን ጦር መሪዎች ከዚህ ቀደም በሳዑዲ አረቢያ ጅዳ ከተማ በተወካዮቻቸው በኩል ለድርድር ቢቀመጡም ፍሬ አላፈራም።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

29 May, 07:55


ኮማንድ ፖስትና ብሔራዊ ደኅንነት ጣልቃ ቢገቡም የወርቅ ኮንትሮባንድ ሊቆም አልቻለም ተባለ

አምባ ዲጂታል፤ ረቡዕ ግንቦት 21፣ 2016 - በመከላከያ ኮማንድ ፖስትና በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ጭምር ክትትል ቢደረግም፣ በክልሎች እየጨመረ የመጣው የወርቅና የማዕድናት ኮንትሮባንድ ሊቆም እንዳልቻለ ተገለጸ፡፡

በማዕድናት ሕገ ወጥ ግብይት፣ ኮንትሮባንድና የፀጥታ ችግር ምክንያት በባለፉት ዘጠኝ ወራት ወደ ብሔራዊ ባንክ የገባው ወርቅ ሦስት ቶን ብቻ እንደሆነ፣ ይህም ከዕቅዱ 50 በመቶ ብቻ መሆኑ ታውቋል፡፡ የወርቅ ገቢም ከታቀደው 363 ሚሊዮን ዶላር 67 በመቶ ብቻ መሳካቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በመጋቢት ወር ብሔራዊ ባንክ የገባው ወርቅ 350 ኪሎ ግራም ሲሆን ይህም በ2014 መጋቢት ወር ከተገኘው 800 ኪሎ ግራም በእጅጉ ያነሰ ነው ተብሏል፡፡

በአገሪቱ ያሉ ወርቅ አምራቾች የባህላዊና የኩባንያ ተብለው ሲከፈሉ፣ በተለይ በባህላዊ አምራቾች የሚወጣው ወርቅ ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ ወደ ብሔራዊ ባንክ መግባት ያቆመ መሆኑን፣ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከታቀደው 2 ሺህ 306 ኪሎ ግራም ውስጥ 609 ኪሎ ብቻ (26 በመቶ) መቅረቡን መረዳት ተችሏል፡፡

በተለይ ኦሮሚያ፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ ጋምቤላና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልሎች ለብሔራዊ ባንክ ለማቅረብ ካቀዱት አንፃር የቀረበው እጅግ አናሳ መሆኑን፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው የማዕድን ሚኒስቴር ሪፖርት ያሳያል፡፡ ይሁን እንጂ ፈጽሞ ወርቅ ካላቀረቡት የትግራይ፣ የአፋር፣ የደቡብ ኢትዮጵያና የሶማሌ ክልል አንፃር የበፊቶቹ እንደሚሻል ሪፖርቱ ያሳያል፡፡

በኩባንያዎች ከቀረበው 2 ሺህ 400 ኪሎ ግራም ወርቅ ውስጥ ሚድሮክ ጎልድ በከፍተኛ መጠን ያቀረበ ሲሆን፣ ወደ ሥራ ገብተዋል የተባሉ ሌሎች ዘጠኝ የወርቅ ኩባንያዎች ሲደመሩ ያቀረቡት ከ100 ኪሎ ግራም በታች ነው፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ስቴላ፣ ዙምባራ፣ ኦሮሚያ ማይኒንግ ኤልኔት፣ ኢዛናና ኢትኖ ማይኒንግ የሚባሉት ይገኙበታል፡፡ በተለይ ኢዛና 375 ኪሎ ግራም አቀርባለሁ ቢልም ምንም ዓይነት ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ እንዳላስገባ በሪፖርቱ ተመላክቷል፡፡

ከወርቅ በተጨማሪም የታንታለም አፈጻጸም 40 በመቶ ብቻ የተሳካ ሲሆን፣ ኦፓል 49 በመቶ ነው፡፡ በአንፃሩ የሊትዬም፣ የጌጣጌጥና የኢንዱስትሪ ማዕድናት የወጪ ንግድ የተሻለ አፈጻጸም ታይቶበታል፡፡
አብዛኛው የባህላዊ አምራቾች ወርቅ በሕገወጥ ግብይትና በኮንትሮባንድ ከአገር የሚወጣ መሆኑን፣ በአንፃሩ ኩባንያዎች ደግሞ በፀጥታ ምክንያት ወደ ሥራ ሊገቡ እንዳልቻሉ ሪፖርቱ ያትታል፡፡

በተለይ በጋምቤላ፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ በኦሮሚያና በደቡብ አካባቢዎች በወርቅ ማውጫ አካባቢዎች በመከላከያ ሠራዊት እንዲጠበቁና የክልል መንግሥታት ከኮማንድ ፖስትና ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ጋር ተቀናጅተው እንዲሠሩ መደረጉ በሪፖርቱ ተመላክቷል፡፡

በእነዚህ ክልሎች ፕሬዚዳንቶች፣ የቢሮ ኃላፊዎችና የማዕድን ማውጫ አካባቢዎች አስተዳዳሪዎች ከኮማንድ ፖስት ኃላፊዎችና ከፌዴራል ተወካዮች ጋር ርብርብ እያደረጉ መሆናቸው ተገልጿል፡፡

ከሳምንታት በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በባህር ዳር የብልፅግና ፓርቲ ስብሰባ ላይ የወርቅና የማዕድናት ኮንትሮባንድ ከፍተኛ ደረጃ ላይ መድረሱን ገልጸው፣ በተለይ አሶሳና ሽሬ ከፍተኛ የሕገወጥ ወርቅ ዝውውር መተላለፊያ መሆናቸውን አስረድተው ነበር፡፡

በተለይ ሕገወጥ ወርቅ በሱዳን፣ በኬንያና በሶማሊያ ድንበሮች ከአገር በመውጣት በዋናነት ዱባይና ህንድ እንደሚደርሱ፣ እንዲሁም እስከ ኡጋንዳ ድረስ ከዚያም ወደ ዱባይ የሚያመራ ሰንሰለት እንዳለ ለዘርፉ ቅርበት ያላቸው ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡

በሕጋዊውና በጥቁር ገበያ መካከል ያለው የምንዛሪ ክፍተት ዋነኛው የችግሩ ምንጭ እንደሆነም በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡ ከጥቂት ወራት በፊት ብሔራዊ የማዕድን ልማት አስተባባሪ ኮሚቴ የተቋቋመ ሲሆን፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ከፍተኛ አመራሮችና የክልል ፕሬዚዳንቶች የኮሚቴው አባል ናቸው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ኮሚቴው በማዕድን አምራች አካባቢዎችና በማዕድን ኩባንያዎች ፕሮጀክቶች በመገኘት ምልከታና አሰሳ ካደረገ በኋላ፣ የማዕድናት ኮንትሮባንድን ለማስቀረት አዲስ የድርጊት መርሐ ግብር እያረቀቀ መሆኑን በሪፖርቱ ተጠቁሟል መባሉን የዘገበው ሪፖርተር ጋዜጣ ነው፡፡

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

28 May, 13:15


ቦይንግ ኩባንያ የአፍሪካ ቢሮውን በአዲስ አበባ ለመክፈት መወሰኑ ተሰማ

አምባ ዲጂታል፤ ማክሰኞ ግንቦት 20፣ 2016 - ግዙፉ የአውሮፕላን አምራጭ ቦንይንግ ኩባንያ የአፍሪካ ቢሮውን አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ለመክፈት ማቀዱን አሳውቋል።

ኩባንያው አዲሱን ዕቅዱን በድረ ገጹ ላይ ባወጣው መረጃ ይፋ አድርጓል።

ቦይንግ ኩባንያው የአዲስ አበባ ቢሮ ከመክፈቱ በፊት የቀድሞውን በፈረንሳይ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሄኖክ ሻውልን በማኔጂንግ ዳይሬክተርነት ሾሟል።

ሄኖክ ሻውል ቀድሞ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ውስጥ በከፍተኛ የኃላፊነት ደረጃ የሰሩ መሆናቸው ይታወቃል።

ቦይንግ ኩባንያ ዋና መቀመጫው በአሜሪካ ቨርጂንያ ግዛት ውስጥ ነው።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

26 May, 10:00


አምባሳደር ስለሺ በቀለን የሚተኩት ሌንጮ ባቲ እንደሚሆኑ ታወቀ

አምባ ዲጂታል፤ እሑድ ግንቦት 18፣ 2016 - በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው ሲያገለገሉ የቆዩትን ስለሺ በቀለ (ዶ/ር)ን የሚተኩት የወቅቱ የሳዑዲ ዐረቢያ አምባሳደር ሌንጮ ባቲ እንደሚሆኑ ታወቀ።

ይህንኑ አምባ ዲጂታል ለጉዳዩ ቅርበት ካላቸው ምንጮች ሰምቷል። የሌንጮ ባቲ የአሜሪካ አምባሳደርነት ሹመት ዜና የመጣው አምባሳደር ስለሺ በቀለ የመንግሥት የሥራ ኃላፊነት ለመልቀቅ ጥያቄ አቅርበው ተቀባይነት ማግኘታቸው ከተነገረ በኋላ ነው።

ስለሺ በቀለን (ዶ/ር) በመተካት በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው ይመደባሉ የተባሉት አምባሳደር ሌንጮ ባቲ በአሁኑ ወቅት በሳዑዲ ዐረቢያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ።

አምባሳደር ሌንጮ ባቲ በሳዑዲ አምባሳደርነት የተሾሙት በ2013 አጋማሽ ነበር።

ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ሥልጣን መምጣት በኋላ በአማካሪነት፣ በኋላ ደግሞ በአምባሳደርነት እያገለገሉ የሚገኙት ሌንጮ ባቲ፣ ቀድሞ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) አንደኛው ክንፍ አመራር ነበሩ።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

26 May, 06:34


አምባሳደር ስለሺ በቀለ ከመንግሥት ኃላፊነት ሊለቁ መሆኑ ተዘገበ

አምባ ዲጂታል፤ እሑድ ግንቦት 18፣ 2016 - በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው እያገለገሉ የሚገኙት የቀድሞው የውኃ ሀብት ሚኒስትር ስለሺ በቀለ (ዶ/ር) ከተሾሙበት የመንግሥት የሥራ ኃላፊነት ለመልቀቅ አቅርበው ጥያቄው ተቀባይነት ማግኘቱን የዘገበው ሪፖርተር ጋዜጣ ነው።

ስለሺ በቀለ (ዶ/ር) በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደርነት ሹመታቸው ብቻ ሳይሆን ሙሉ በሙሉ ከመንግሥት መዋቅር በመልቀቅ በግል ተቀጥረው በሙያቸው ለማገልገል ማቀዳቸውንም ዘገባው አመልክቷል።

ስለሺ (ዶ/ር) በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የሥልጣን ዘመን ወቅት የፓርቲ አባል ሳይሆኑ የመንግሥት መዋቅርን መቀላቀላቸው የሚታወስ ሲሆን፣ ከዚያ አስቀድመው በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በውኃ ምኅንድስና ሙያቸው በግል ተቀጥረው ሲያገለግሉ ነበር።

ሆኖም የአምባሳደር ስለሺ በቀለን መልቂቂያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ነብዩ ተድላ፣ ስለ ጉዳይ የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ገልጸዋል ተብሏል።

መንግሥት አምባሳደር ስለሺ ያቀረቡትን ጥያቄ ከመቀበሉ ባሻገር እርሳቸውን የሚተካ ሌላ አምባሳደር ለመመደብ መሰናዳቱንም የጋዜጣው ዘገባ ያመለክታል። አምባሳደር ስለሺ በቀለን (ዶ/ር) በመተካት በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው ይመደባሉ የተባለው በአሁኑ ወቀት በተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው እያገለገሉ የሚገኙት አምባሳደር ሌንጮ ባቲ ናቸው።

በአሜሪካን የኒውዮርክ ግዛት ውስጥ በሚገኘው በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋናው መሥሪያ ቤት፣ የማኅበራዊ ጉዳዮች ክፍል የኢኮኖሚና ዘላቂ ልማት አማካሪ ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩት አምባሳደር ስለሺ (ዶ/ር)፣ ለመጀመሪያ ጊዜ የኢትዮጵያ መንግሥት መዋቅርን የተቀላቀሉት በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ መምህር በነበሩበት ወቅት ወዳጅና ባልደረባቸው የነበሩት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ባቀረቡላቸው ጥሪ ነበር። 

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም አገራቸውን እንዲያለግሉ ያቀረቡላቸውን ጥሪ በመቀበል፣ ከተመድ የአማካሪነት ሥራቸው ለቀው ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት ስለሺ (ዶ/ር) የውኃ፣ መስኖና ኤነርጂ ሚኒስትር በመሆን የሥራ አስፈጻሚውን መንግሥት ለመጀመሪያ ጊዜ በጥቅምት ወር 2009 ተቀላቅለዋል። አምባሳደር ስለሺ በቀለ በተለይ በሕዳሴ ግድብ ተደራዳሪነት ይታወቃሉ።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

25 May, 11:09


የትግራይ ኃይሎች በአላማጣ አቅራቢያ ከሚገኙ ሁለት አካባቢዎች እንዲወጡ ውሳኔ ማሳለፉን አሳወቀ

አምባ ዲጂታል፤ ቅዳሜ ግንቦት 17፣ 2016 - የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ኃይሎቹ እንዲወጡ ውሳኔ ያሳለፈው፣ በአላማጣ ከተማ አቅራቢያ በሚገኙት “ገርጃለ” እና “በቅሎ ማነቂያ” ከተባሉ ቦታዎች ነው።

የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር በፕሬዝዳንቱ ጌታቸው ረዳ አማካኝነት ትናንት አርብ ግንቦት 16፤ 2016 ባስተላለፈው መልዕክት ይህንኑ ገልጿል።  አቶ ጌታቸው ትላንት እኩለ ሌሊት ገደማ በይፋዊ የማህበራዊ ትስስር ገጾቻቸው አማካኝነት ባሰፈሩት በዚሁ መልዕክት፤  የትግራይ ኃይሎች ከ“ገርጃለ” እና “በቅሎ ማነቂያ” መንደሮች እንዲወጣ የተወሰነው ጊዜያዊ አስተዳደሩ ከፌደራል መንግስት እና ከአማራ ክልል “አስተዳደር” ጋር የደረሰበትን መግባባት “ለማክበር” ነው። 

የአማራ እና ትግራይ ክልሎች የበላይ አመራሮች የተካተቱበት ብሔራዊ ኮሚቴ፤ ባለፈው መጋቢት ወር አጋማሽ ገደማ ካደረገው ስብሰባ በኋላ በ15 ነጥቦች ላይ ከመግባባት ላይ ደርሶ ነበር ተብሏል። በሁለቱ ክልሎች መካከል “የወሰን ይገባኛል ጥያቄ የሚነሳባቸውን አካባቢዎች ጉዳይ ዘላቂነት ባለው መልክ እልባት ለመስጠት” የተቋቋመው ይህ ብሔራዊ ኮሚቴ፤ መግባባት ላይ ከደረሰባቸው ጉዳዮች መካከል አንዱ የተፈናቃዮች ጉዳይ እንደሆነ ምንጮቹ ገልጸዋል።

“ሁለት ወር ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ” እንዲፈጸሙ በብሔራዊ ኮሚቴው እቅድ ከተያዘላቸው ጉዳዮች መካከል፤ “ተፈናቃዮችን ወደ ቀድሞ አካባቢያቸው መመለስ” የሚለው “ቀዳሚ ስራ” እንዲሆን በመጋቢቱ ስብሰባ ላይ ከስምምነት ላይ ተደርሶ ነበር። በዚሁ ስብሰባ ላይ “ሁሉም ተፈናቃይ ያለ ቅድመ ሁኔታ እንደሚመለስ፣ በወንጀል የሚታማ ካለም በሂደት እና በማስረጃ ፌደራል መንግስት የሚከታተለው ስለሚሆን ወደቀዬው ከመመለስ የሚያስተጓጉል ምክንያት እንደማይኖር” በስብሰባው ላይ ከመግባባት ላይ ተደርሶ እንደነበር ኢትዮጵያ ኢንሳይደር ዘግቧል።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

24 May, 11:40


እያንዳንዱ ድሮን ታጥቆ የሚሰማራው ሚሳኤሎች ዋጋ 3.5 ሚሊዮን ብር እንደሚገመት ተዘገበ

አምባ ዲጂታል፤ ዐርብ ግንቦት 16፣ 2016 - በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች በሚካሄዱ ጦርነቶች እያንዳንዱ ድሮን ታጥቆ የሚሰማራው ሚሳኤሎች ዋጋ 3.5 ሚሊዮን ብር እንደሚገመት የጠቆመው ቢቢሲ በዘገባው ነው።

የዜና ተቋሙ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ በተለያዩ ማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ በኦሮሚያ ክልል ወለጋ ሆሮ ጉዱሩ ውስጥ የእርሻ ማሳ ላይ ወድቋል የተባለ ሰው አልባ አውሮፕላን (ድሮን) ተንቀሳቃሽ ምሥል እና ፎቶ በስፋት ሲሠራጭ እንደነበር በማስታወስ ምርመራ ማድረጉን ገልጿል።

የወደቀው ድሮን ባይራክተር ቲቢ 2 የተባለ ለወታደራዊ አገልግሎት የሚውል መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፣ ይህንኑ ከጦርነት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን ከሚተነትኑ ባለሙያዎችን አነጋግሮ ማረጋገጡን አስነብቧል።

ባለሙያዎች ሰው አልባ አውሮፕላኑ በመሳርያ ተመትቶ ስለመውደቁ የሚያሳይ ምንም ፍንጭ በምሥሉ ላይ እንደሌለ አረጋግጠዋል ብሏል።

የወደቀው ሰው አልባ አውሮፕላኑ አራት ተወንጫፊ ሚሳኤሎችን ወይንም ሮኬቶችን የመታጠቅ አቅምም እንዳለው የጠቆመው ቢቢሲ ከ5 እስከ 6 ሚሊዮን ዶላር ዋጋ የተተመነለት መሆኑን እና የሚያስወነጭፋቸው ሮኬቶች የእያንዳንዳቸው ዋጋ ከ 60,000 እስከ 100,000 ዶላር አንደሚገመት አመላክቷል።

ይህም ማለት እያንዳንዱ ድሮን ታጥቆ የሚሰማራው ሚሳኤሎች ዋጋ 3.5 ሚሊዮን ብር ይገመታል ማለት ነው ብሏል።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

23 May, 18:19


በኢትዮጵያ ጊዜያዊ የተኩስ አቁም እንዲደረግ የፖለቲካ ፓርቲዎች ኮከስ ጠየቀ

አምባ ዲጂታል፤ ሐሙስ ግንቦት 15፣ 2016 - በኢትዮጵያ ጊዜያዊ የተኩስ አቁም እንዲደረግ የፖለቲካ ፓርቲዎች ኮከስ የጠየቀው አዲስ ባወጣው መግለጫ ነው።

ኮከሱ በመግለጫው ዘላቂ ተኩስ አቁሙ ለዘላቂ ሰላምና መፍትሄ በነጻነት ለሚደረግ ሁሉን አቀፍ አሳታፊ፣ ሃቀኛና ተኣማኒ ብሄራዊ መግባባትና ዕርቅ መድረክ አስፈላጊ እንደሆነ ገልጿል።

የፖለቲካ ፓርቲዎች ስብስቡ ጊዜያዊ የተኩስ አቁም በአፋጣኝ ማድረግ ለነገ ይደር የማይባል አስቸኳይ ተግባር በመግለጽ፣ ለተግባራዊነቱ ኮከሱ ከራሱ አልፎ ሌሎችንም የማስተባበር ተልዕኮ ለመፈጸም ዝግጁ ነኝ ብሏል።

በሌላ በኩል ኮከሱ በቅርብ ቀናት በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኢትዮጵያን አስመልክቶ የሰጡትን መግለጫ አወድሷል። ኮከሱ የአሜሪካ መንግስት ከወትሮው በዲፕሎማሲ ቃላት የተድበሰበሰ አካሄድ  ወደ ሃቀኛ አረዳድና ግልጽ አገላለጽ መሸጋገሩ አበረታች እርምጃ ነው ብሎታል።

በመሆኑም ላቀረበው ምክረ ሃሳብ ተፈጻሚነት ከኢትዮጵያ ህዝብ ሠላማዊ ትግል ጎን እንዲቆም፣ በተለይ በገዢው ፓርቲ፣ እንዲሁም በትጥቅ ትግል የተሰማሩ ኃይሎች ላይ አዎንታዊ ተጽዕኖ በማሳረፍ ዘላቂ ሠላምና የፖለቲካ መረጋጋት፣ አገራዊ አንድነትና ቀጣይነት ያለው ዕድገትና ልማት፣ ጤናማና በመከባበር ላይ የተመሰረተ  ማኅበራዊ ግንኙነት እንዲመሰረት  የወዳጅ  ገንቢ አስተዋጽኦ  እንዲያበረክት ጥሪ አቅርቧል።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

23 May, 08:56


በወልቂጤ የመሳሪያ ግምጃ ቤት ዝርፊያ መፈጸሙ ተዘገበ

አምባ ዲጂታል፤ ሐሙስ ግንቦት 15፣ 2016 - በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ ፖሊስ ጣቢያ በመሳሪያ ማከማቻ መጋዘን ላይ በተፈጸመ ዝርፊያ ቁጥሩ በውል ያልታወቀ የጦር መሳሪያ መወሰዱን የከተማው ሠላምና ጸጥታ ጽ/ቤትን ጠቅሶ በድረ ገጹ የዘገበው ዋዜማ ነው፡፡

ዝረፊያው የተፈጸመው ሰኞ ግንቦት 5፣ 2016 ከሌሊቱ 7 ሰአት አካባቢ እንደሆነ እና የዘራፊዎቹ ማንነት እስካሁን እንዳልታወቀም ጽ/ቤቱ አስረድቷል ነው የተባለው።

የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ሠላምና ጸጥታ ጽ/ቤት ኃላፊ ትዕግሥቱ ፉጄ እንደገለጹት፣ የተዘረፈው መሳሪያ እና ሌሎችም የተቋሙ መገልገያዎች ምን ያህል እንደሆኑ አልታወቀም፡፡

ከተዘረፉት የጦር መሳሪያዎች በተጨማሪ አንድ የፖሊስ ፓትሮል መኪናም እንደሚገኝበትና ዘራፊዎቹ “ቱሉ ላሜ” በሚባል የገጠር መንደር ውስጥ ጥለውት ሄደው መገኘቱን ተናግረዋል። መኪናው ምንም ጉዳት ሳይደርስበት ወደ ጣቢያ ተመልሶ አገልግሎት መስጠት መጀመሩንም ኃላፊው ጠቅሰዋል።

በዘረፋው ቁጥራቸው በርከት ያሉ ጠመንጃዎች እና ሌሎች የጦር መሳሪያዎች መወሰዳቸውን ለዋዜማ ያስረዱት ትዕግሥቱ፣ ድርጊቱን የሚያጣራ ኮሚቴ ተዋቅሮ ወደ ሥራ መገባቱንም ጠቁመዋል።

በእለቱ የነበሩ ተረኛ ጥበቃ የፖሊስ አባላት በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው እንደሚገኝና ወንጀሉን የፈጸሙ አካላትን አድኖ ለመያዝ ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝም አስረድተዋል መባሉን ዘገባው ያመለክታል፡፡

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

22 May, 12:01


ኢትዮጵያ የቆንስላ ጽሕፈት ቤቷን ወደ ኤምባሲ ማሳደጓ ተገለጸ

አምባ ዲጂታል፤ ረቡዕ ግንቦት 14፣ 2016 - ኢትዮጵያ በሶማሊላንድ፣ ሃርጌሳ የሚገኘውን የቆንስላ ጽሕፈት ቤቷን ሙሉ አገልግሎት ወደሚሰጥ ኤምባሲ ማሳደጓን የገለጹት የሶማሊላንድ የመረጃ፣ የባህል እና የብሔራዊ መመሪያ ሚኒስትር አሊ ሐሰን መሐመድ (አሊ ማርሃን) ናቸው፡፡

ሚኒስትሩ የኢትዮጵያ የቆንስላ ጽህፈት ቤት ሙሉ አገልግሎት ወደሚሰጥ ኤምባሲ ማደጉን አስመልክቶ ከፍተኛ ስፍራ በሚሰጠው ዕለት ፕሬዝዳንቱ ለሕዝባቸው ባደረጉት ንግግር ገልጸዋል ሲሉ ገልጸዋል ነው የተባለው፡፡

ፕሬዝዳንት ሙሳ ቢሂ አብዲ ሶማሊላንድ ነጻነቷን በማወጅ እንደ አገር የተመሠረተችበትን ዕለት ግንቦት 10/2016 33ኛ ዓመት ስታከብር ሃርጌሳ የሚገኘው የኢትዮጵያ ቆንስላ ጽህፈት ቤት ወደ ኤምባሲ ማደጉን ለመጀመሪያ ጊዜ መናገራቸውን በሶማሊላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የወጣው መረጃ ያስረዳል።

የሶማሊላንድ ባለሥልጣናት የሰጡትን መረጃ አስመልክቶ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃለ አቀባይ የሆኑትን አቶ ነብዩ ተድላ ጉዳዩ በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ሳምንታዊ መግለጫ ላይ ሊነሳ እንደሚችል ጠቁመው በአሁኑ ሰዓት ይህንን በተመለከተ የሚሰጡት መረጃ እንደሌላቸው ነግረውኛል ሲል ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ በቅርቡ የባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደርነት ሹመት ከሰጧቸው 10 ሰዎች መካከል በሶማሊላንድ የኢትዮጵያ ቆንስላ ልዑክ ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩት ደሊል ከድር ቡሽራ መካተታቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ግንቦት 7/2016 ያወጣው መረጃ ያሳያል።

ደሊል ከድር በሶማሊላንድ የኢትዮጵያ ልዑክ ሆነው ካለፈው ዓመት መጋቢት ጀምሮ ሲያገለግሉ እንደነበር መረጃዎች ያሳያሉ።
በሶማሊላንድ የሚገኘው የኢትዮጵያ ቆንስላ ጽሕፈት ቤት ወደ ኤምባሲ ከፍ ማለቱን በተመለከተ ከሶማሊያ በኩል አስካሁን በይፋ የተሰጠ አስተያየት የለም።

ሶማሊያ በኢትዮጵያ እና በሶማሊላንድ መካከል በፈረሙት የመግባቢያ ስምምነት ምክንያት ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ለማቋረጥ በመወሰን በአገሪቱ የሚገኙ የኢትዮጵያ አምባሳደር እና ዲፕሎማቶች ለቀው እንዲወጡ ማዘዟ እና አዲስ አበባ ያሉትን አምባሳደሯን መጥራቷ ይታወሳል።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

21 May, 17:10


በሀገሪቱ የሚካሄደው ጦርነት እንዲቆም ነእፓ ጠየቀ

አምባ ዲጂታል፤ ማክሰኞ ግንቦት 13፣ 2016 - ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ) የአምስት አመት ምስረታ ክብረ በዓሉን መጠናቀቅ አስመልክቶ በፓርቲው ዋና መ/ቤት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ በሀገሪቱ የቀጠለው ጦርነት እንዲቆም ጠይቋል።

“የእርስ በእርስ ጦርነት ይቁም” በሚል መሪ ቃል ፓርቲው ያሰናዳው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የአምስት አመት ጉዞውን፣ ስኬት፣ ተግዳሮት እና ተሞክሮ የዳሰሰ ነበር።

በፓርቲው ሊቀንመንበር ዶክተር አብዱልቃድር አደም እና ሌሎችም ከፍተኛ አመራሮች የተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ከጦርነቱ በተጨማሪ ወቅታዊውን የኢኮኖሚ ጉዳይ አንስቷል።

ፓርቲው ኢትዮጵያ ካለችበት የኢኮኖሚ ቀውስ ትላቀቅ ዘንድ፣ መንግስት ጥልቅ የማክሮ ኢኮኖሚ እና የፊስካል ፖሊሲ ክለሳ እንዲያካሂድ፣ ውስን የሆነውን የሀገር ሀብት ለአብዛኛው ህዝብ አንገብጋቢ ባልሆኑ ፕሮጀክቶች ላይ ከማባከን ይልቅ የዜጎችን መሰረታዊ እና አጣዳፊ ችግሮች ሊፈቱ በሚችሉ የልማት ስራዎች እንዲያውል ጥሪ ቀርቦበታል።

በሌላ በኩል መንግስት ከዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማት (በተለይም ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት)  ብድር ለማግኘት የሚያደርገው ጥረት የኢትዮጵያን የረዥም ጊዜ ምጣኔ ሀብታዊ እድገት የሚያቀጭጭ እና ሀገርን ለከፋ የውጭ እዳ ጫና የሚዳርግ እንዳይሆን ተገቢውን ጥንቃቄ የሚዳርግ እንደሆነም ገልጿል።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

17 May, 08:12


ከ274 ሺህ በላይ የትግራይ ሠራዊት አባላት ትጥቅ ይፈታሉ ተባለ

አምባ ዲጂታል፤ ዐርብ ግንቦት 9፣ 2016 - ብሔራዊ የተሐድሶ ኮሚሽን ከ274 ሺህ በላይ የትግራይ ሠራዊት አባላት ትጥቅ ይፈታሉ ሲል አስታውቋል፡፡ ይህንኑ የብሔራዊ የተሐድሶ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ተስፋዓለም ይሕደጎ ለቢቢሲ ገለጸዋል፡፡

ጥቅ ይፈታል የተባለው የትግራይ ሠራዊት ከላይ ከትግራይ ኃይሎች ወታደራዊ ኮማንድ ጀምሮ እስከ ታች የተደራጀ ነው። አቶ ተስፋዓለም ይሕደጎ ትጥቅ የሚፈቱት 274 ሺህ 800 የትግራይ ሠራዊት አባላት መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

በዚህ ሳምንት መጀመርያ ላይ በተካሄደው ምክክር ላይ የፌደራል መንግሥት ተወካዮች፣ የትግራይ ጊዜያዊ መንግሥት አመራሮች እና የአፍሪካ ኅብረት የስምምነት ክትትል፣ አረጋጋጭ እና አስከባሪ ኮሚቴ አባላት መገኘታቸውን የብሔራዊ ተሐድሶ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ተመስገን ጥላሁን በኤክስ ገጻቸው አስታውቀዋል።

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ምክትል ፕሬዚዳንቶች እንዲሁም የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በዚህ ምክክር ላይ የትግራይ ተዋጊዎችን በመበተን እና ሁለንተናዊ በሆነ መልኩ ወደ ኅብረተሰቡ የማዋሃድ ፕሮግራም፣ ፕሮጀክቶች መንደፍ እንዲሁም የመጀመሪያው የትግበራ እቅድ ላይ ውይይት እንደሚደረግ ተጠቅሶ ነበር።

የትግራይ መንግሥት 50 ሺሕ የትግራይ ኃይል አባላትን ከጦሩ እንዳሰናበተ ተነግሯል። ኣላቱ ሲሰናበቱ አጭር ስልጠና፣ መሸኛና መቋቋምያ ተሰጥቷቸዋል ተብሏል፡፡

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

14 May, 11:55


በሰሜን ሸዋ ዞን በትምህርት ቤት በደረሰ የድሮን ጥቃት የአራት ሠዎች ሕይወት ማለፉ ተሰማ

አምባ ዲጂታል፤ ማክሰኞ ግንቦት 6፣ 2016 - በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ቀወት ወረዳ ተሬ ቀበሌ ጉሎ በተባለ ትምህርት ቤት እሁድ ግንቦት 4፣ 2016 በደረሰ የድሮን ጥቃት የወላጅ መምህራን ህብረት (ወመህ) ስብሰባ ላይ የነበሩ ሠላማዊ ሰዎች መገደላቸው ተሰምቷል፡፡ 

የዐይን እማኞችና የተጎጂ ቤተሰቦችን ጠቅሶ ቢሰ እንደዘገበው ከቀወት ወረዳ ዋና መቀመጫ ሸዋ ሮቢት በግምት 20 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በሚገኘው የጉሎ (ጎጥ) አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከቀኑ 7፡30 ገደማ ደርሷል በተባለው የድሮን ጥቃት አራት ሠዎች ሲገደሉ አምስት ሠዎች ደግሞ መቁሰላቸውን ተናግረዋል።

ጥቃቱ የደረሰው መምህራንና የአካባቢው ማህበረሰብ የወላጅ መምህራን ህብረት (ወመህ) ስብሰባ ላይ በነበሩበት ቅጽበት መሆኑን የተናገሩ አንድ የስብሰባው ተካፋይ፤ በጥቃቱ እሳቸውም ጭንቅላታቸው ላይ እንደቆሰሉ ገልጸዋል። ከሟቾቹ ውስጥ ሁለቱ የስብሰባው ተሳታፊዎች ሲሆኑ፤ ሁለቱ ደግሞ የት/ቤቱ ዙሪያ ላይ የነበሩ ሠላማዊ ሠዎች እንደሆኑ እማኙ ተናግረዋል።

በስብሰባው ላይ ተሳታፊ የነበሩና የአንዱ ሟች የቅርብ ቤተሰብ የሆኑ ግለሰብ፤ እርሳቸው ፈንጠር ብለው በመቆማቸው በፍንዳታው ግፊት መውደቃቸውን ገልጸው፤ ጥቃቱ ዱብዕዳ እንደሆነባቸው መናገራቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡

በአማራ ክልል በመንግሥት ኀይሎችና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ባለው ግጭት በተለያዩ ቦታዎች የድሮን ጥቃቶች የተፈጸሙ ሲሆን፤ ጥቃቶቹ የሠላማዊ ሠዎችን ሕይወት መቅጠፋቸውን የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች በተደጋጋሚ ገልጸዋል። ባለፈው ታህሳስ ወር የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በድሮን ጥቃቶች ንጹሃን እየተገደሉ ነው መባሉን አስተባብለዋል።

የመከላከያ ሠራዊት የድሮን ጥቃት የሚፈጽመው የፋኖ ታጣቂዎች “ስብስብ ዒላማ” ላይ መሆኑን በመጥቀስ “ሕዝብ ላይ ድሮን አይጣልም፤ አይተኮስም። መንደር ላይ እንኳ አይተኮስም። የጠላት ስብስብ ሲገኝ ግን ይተኮሳል" ማለታቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

14 May, 11:16


የቀድሞ ተዋጊዎችን ትጥቅ የማስፈታት የቅድመ ማስጀመሪያ ውይይት መርሃ ግብር በመቐለ ተካሄደ

አምባ ዲጂታል፤ ማክሰኞ ግንቦት 6፣ 2016 - የቀድሞ ተዋጊዎችን ትጥቅ የማስፈታት፣ ወደ ህብረተሰቡ የማቀላቀል እና መልሶ የማቋቋም የቅድመ ማስጀመሪያ ውይይት መርሃ-ግብር በትግራይ እየተካሄደ ይገኛል።

የቀድሞ ተዋጊዎችን ትጥቅ የማስፈታት፣ ወደ ህብረተሰቡ የማቀላቀል እና መልሶ የማቋቋም የቅድመ ማስጀመሪያ ውይይት ትላንት ግንቦት 5፣ 2016 በመቐለ ከተማ መጀመሩን የገለጹት የብሔራዊ ተሐድሶ ኮሚሽን ኮሚሽነር ተመስገን ጥላሁን ናቸው፡፡

በውይይቱ ላይ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ባለሥልጣናት ተገኝተዋል፡፡ ከተገኙት መካከል ሌተናል ጄነራል ታደሰ ወረደ እና ሌተናለ ጄነራል ጻድቃን ገብረትንሳዔ ይጠቀሳሉ፡፡ የትግራይ ከልል ግዚያዊ አስተዳደር እና የፌደራል መንግስት ተወካዮችም በመርሀ ግብሩ ላይ ተገኝተዋል።

በተጨማሪም የአፍሪካ ህብረት የሰላም ስምምነቱ ተቆጣጣሪ ኮሚቴ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተወካዮች ተገኝተዋል ተብሏል፡፡

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

14 May, 05:33


የኦፌኮ ሊቀመንበር መረራ ጉዲና ከማይክ ሐመር ጋር ተወያዩ

አምባ ዲጂታል፤ ማክሰኞ ግንቦት 6፣ 2016 -  የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ሊቀመንበር ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና ከአሜሪካ የምሥራቅ አፍሪካ ልዩ መልዕክተኛ አምባሳደር ማይክ ሐመር ጋር ተወያይተዋል።

ከፕሮፌሰር መረራ ጋር ውይይት ያካሄዱት የአሜሪካ የምሥራቅ አፍሪካ ልዩ መልዕክተኛ አምባሳደር ማይክ ሐመር፣ ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ በኬያያ፣ ጅቡቲ እና ኢትዮጵያ የሚያደርጉትን ጉዞ መጀመራቸው ይታወቃል።

መረራ ከማይክ ሐመር ጋር በነበራቸው ውይይት፣ የኢትዮጵያን ወቅታዊ ፖለቲካዊ ችግሮች አንስተዋል ተብሏል። የኦፌኮ ሊቀመንበር ለችግሮቹ መፍትሔ ለማበጀት ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ገዥው ብልጽግና ፓርቲ ላይ ግፊት እንዲያደርግ ጠይቀዋል።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

13 May, 14:44


በደቡባዊ የኢትዮጵያ ክፍል በሳምንት ልዩነት ከፍ ያለ መጠን ያለው የመሬት መንቀጥቀጥ መከሰቱ ተሰማ

አምባ ዲጂታል፤ ሰኞ ግንቦት 5፣ 2016 -  በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደቡብ ኦሞ ዞን በሬክተር ስኬል 4.8 ሆኖ የተመዘገበ የመሬት መንቀጥቀጥ መከሰቱን የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጂኦፊዚክስ፣ ህዋ ሳይንስ እና አስትሮኖሚ ኢንስቲትዩት አስታውቋል።

በበና ፀማይ ወረዳ የተከሰተው ይህ የመሬት መንቀጥቀጥ አጎራባች በሆነው አሪ ዞን እንዲሁም ባለፈው ሳምንት ተመሳሳይ ክስተት ያስተናገደው የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልሉ ዳውሮ ዞን ጭምር የደረሰ እንደሆነ ነዋሪዎች እና ባለስልጣናት ተናግረዋል።

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ትናንት እሁድ ግንቦት 4፣ 2016 የተከሰተውን የመሬት መንቀጥቀጥ የመዘገበው ከሌሊቱ 6 ሰዓት ከ36 ደቂቃ ላይ እንደሆነ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሶሲሞሎጂ ትምህርት ክፍል ኃላፊ ፕሮፌሰር አታላይ አየለ መናገራቸውን ቢቢሲ ዘግቧል።

የመሬት መንቀጥቀጡ በሬክተር ስኬል 4.8 ሆኖ መመዝገቡን የሚያስረዱት ፕሮፌሰር አታላይ፤ ይህ መጠን “መካከለኛ” የሚል ደረጃ የሚሰጠው መሆኑን ገልጸዋል። የትላንቱ የመሬት መንቀጥቀጥ ልኬት ባለፈው ሳምንት በዳውሮ ዞን ከተመዘገበው 3 ሬክተር ስኬል ከፍ ያለ መሆኑን የሶሲሞሎጂ ትምህርት ክፍል ኃላፊው አስታውሰዋል።

“ይን [የመሬት መንቀጥቀጥ] ዝቅተኛም፣ ከፍተኛ አይባልም። መካከለኛ ነው። [የሚያስከትለው] ውድመት እና ጥፋት ግን እንደ አካባቢው ቅርበት [የሚወሰን] ነው። ይህ ከተማ ውስጥ ቢፈጠር ብዙ ጉዳት ያደርሳል” ሲሉ የክስተቱ ሊያደርስ የሚችለውን የጉዳት ጠቅሰዋል።

ፕሮፌሰር አታላይ እንደሚገልጹት ክስተቱ የተመዘገበው በደቡባዊ የኢትዮጵያ ክፍል “ወይጦ ድልድይ ፖሊስ ጣቢያ” በተባለ አካባቢ ነው።

“ወይጦ” የተባለው አካበቢ የሚገኝበት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደቡብ ኦሞ ዞን በና ፀማይ ወረዳ ብራይሌ ታዳጊ ከተማ ስራ አስኪያጅ አቶ ኦይታ ኡኖ ትናንት ሌሊት የመሬት መንቀጥቀጥ ማጋጠሙንም ማረጋገጣቸውም በዘገባው ተመላክቷል።

የመሬት መንቀጥቀጡ “በተከታታይ ሁለት ጊዜ” መከሰቱን የሚናገሩት ዋና አስተዳዳሪው፤ ክስተቱ “አስደንጋጭ” እንደነበር ገልጸዋል።
“ብዙዎቻችን በህይወት እንተርፋለን ብለን አልጠበቅንም ነበር” ሲሉም በሰዓቱ የተሰማቸውን አጋርተዋል።

በናይ ፀማይ ወረዳ የሚገኝበት ደቡብ ኦሞ ዞን ካሉት ስድስት ወረዳዎች እና አንድ የከተማ አስተዳደር ውስጥ በስድስቱ ውስጥ የመሬት መንቀጥቀጥ መከሰቱ እንደተረጋገጠ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ ለቢቢሲ ተናግረዋል። እስካሁን ድረስ ከአንድ ወረዳ መረጃ እንዳልደረሳቸው የጠቀሱት ዋና አስተዳዳሪው፤ መረጃ በተገኘባቸው መዋቅሮች ጉዳት አለመመዝገቡን ገልጸዋል።

ባለፈው ዓመት ከደቡብ ኦሞ ዞን ተነጥሎ በዞንነት በተዋቀረው አሪ ዞንም የመሬት መንቀጥቀጡ መሰማቱን የዞኑ የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን መምሪያ ኃላፊ አቶ ታምራት ተስፋዬ ተናግረዋል።

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

13 May, 06:36


በራያ የተቋረጡ የሕዝብ አገልግሎቶችን ለማስጀመር ፌደራል መንግሥት እና የትግራይ ክልል ውይይት እያደረጉ መሆኑ ተሰማ

አምባ ዲጂታል፤ ሰኞ ግንቦት 5፣ 2016 -  የትግራይ ክልል ጊዜያዊ  አስተዳደር በቅርቡ በተቆጣጠረው የራያ አካባቢ መስረታዊ የሕዝብ አገልግሎቶችን ለማስጀመር ከፌደራል መንግስቱ ጋር ውይይት እያደረገ መሆኑንና በመግባባት እየሰራ እንደሆነ ተሰምቷል፡፡

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የደቡብ ትግራይ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ሃፍቱ ኪሮስ፣ በራያ አካባቢዎች መሰረታዊ የሚባሉ ግልጋሎቶችን ማለትም ትምህርት ቤቶችን፣ ባንኮችን፣ እንዲሁም የጤና ተቋማትን እና የመንግሥት መስሪያ ቤቶችን ወደ ሥራ ለማስገባት ከፌደራል መንግሥቱ ጋር ውይይት ጀምረናል ማለታቸውን ዋዜማ ራድዮ ዘግቧል፡፡

አገልግሎቶችን ለማስጀመር የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር በተናጠል እንቅስቃሴ ጀምሯል ያሉት አስተዳዳሪው፣ ለአብነትም መድኀኒቶችን ወደተለያዩ አካባቢዎች ማሰራጨት እንደጀመረ ጠቅሰዋል ነው የተባለው፡፡ 

አስተዳዳሪው፣ ከጦርነቱ ቀደም ብሎ የነበሩ የመንግሥት ሰራተኞች ወደ ሥራ እንዲመለሱ እያደረጉ መሆኑን ጠቅሰው፣ የአካባቢውን የህዝብ ስብጥር ለመቀየር እና ለፖለቲካ ዓላማ ከተለያዩ የአማራ ክልል አካባቢዎች በመንግሥት ሠራተኛነት ስም የተመደቡ ከ4 ሺሕ በላይ ሰዎች ሲቀሩ የቀድሞ ሠራተኛ አገልግሎት እንዲጀምር እያደረግን ነው ብለዋል።

አስተዳዳሪው ጦርነቱን ተጠቅመው “ሕገ-ወጥ አስተዳደር” መስርተው ነበር ያሏቸው እና አሁን ፈርሰዋል የተባሉት ኃይሎች፣ የአካባቢውን የመማሪያ መጽሐፍት እንዲሁም ካርታ ቀይረው ነበር ሲሉ ወቅሰዋል።

በፌደራሉ የትምህርት ሥርዓት መሰረት ትምህርት ቤቶችን ለማስጀመር ጥረት እየተደረገ እንደሆነ ሃፍቱ ኪሮስ ተናግረዋል።
በቅርቡ በሕወሓት ታጣቂዎች እና በአካባቢው ሚሊሻዎች መካከል የተፈጠረውን ግጭት ተከትሎ፣ የማንነትና የወሰን ጥያቄ በሚነሳባቸው የራያ አካባቢዎች ሁሉም የአገልግሎት መስጫ ተቋማት ዝግ መሆናቸውን፤ እንዲሁም መደበኛ እንቅስቃሴዎች በአብዛኛው መስተጓጎላቸውም በዘገባው ተጠቅሷል፡፡

Amba Digital - አምባ ዲጂታል

10 May, 11:45


ከቀሪና ድጋሚ ምርጫው አስቻይ ሁኔታ የለም ያሉ ሁለት የፖለቲካ ፓርቲዎች ራሳቸውን ማግለላቸው ተነገረ

አምባ ዲጂታል፤ ዐርብ ግንቦት 2፣ 2016 -  እናት እና የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ፓርቲዎች ምርጫ ባልተካሄደባቸው እና በድጋሚ ምርጫ በሚካሄድባቸው አራት ክልሎች ሰኔ 9፤ 2016 ከሚካሄደው ምርጫ ራሳቸውን ማግለላቸውን አስታውቀዋል፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ 6ኛው ጠቅላላ ምርጫ ባልተካሄደባቸው የቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ አፋር፣ ሶማሌ እና ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች በሚገኙ 28 የምርጫ ክልሎች ምርጫ ለማካሄድ የካቲት 22፤ 2016 የጊዜ ሰሌዳ አውጥቷል።

ሰኔ 9 ይካሄዳል የተባለውን ምርጫ ለማካሄድ “አስቻይ ሁኔታ” የለም ያሉት ፓርቲዎቹ፤ አስቻይ ሁኔታ እስኪፈጠር ድረስ ምርጫው እንዲዘገይ ለብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ጥያቄ ማቅረባቸውን ጠቅሰዋል።

ፓርቲዎቹ ከሌሎች ሁለት ፓርቲዎች ጋር የካቲት 25 ለምርጫ ቦርድ በጻፉት ደብዳቤ “ትክክለኛ ምርጫ ለማድረግ የማያስችሉ” ያሏቸውን ነጥቦች አንስተው ቦርዱ ውሳኔውን ዳግም እንዲያጤነው መጠየቃቸውን የቢቢሲ ዘገባ ያመለክታል፡፡

ሆኖም በቀሪና ድጋሚ ምርጫ በሚደረግባቸው አካባቢዎች እንንቀሳቀሳለን ያሉት ሁለቱ ፓርቲዎች ቦርዱ “ማስተካከያ” ባለማድረጉ በምርጫው አንሳተፍም ሲሉ አስታውቀዋል።
ፓርቲዎቹ ለውሳኔያቸው አገሪቱ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ላይ መሆኗ እንዲሁም የጸጥታ ችግርን እንደ ምክንያት አንስተዋል። የእናት ፓርቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሰይፈ ሥላሴ አያሌው የአገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ በመጥቀስ ወደ “ሕገ-መንግሥታዊ ስርዓት” ስትመለስ ምርጫው መካሄድ አለበት ብለዋል።

ምርጫው ይካሄድባቸዋል በተባሉ ክልሎች ያለው አሁናዊ የሠላምና የጸጥታ ሁኔታ አስተማማኝ አይደለም የሚሉት ፕሬዘዳንቱ ለምርጫው “አጃቢ” መሆን አንሻም ሲሉ ራሳቸውን ማግለላቸውን መናገራቸውን ዘገባው ጠቅሷል።

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ቀሪና ድጋሚ ምርጫ በሚያካሂድባቸው ክልሎች የእጩዎችን ዝርዝር ይፋ አድርጓል። ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአፋር አምስት፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ 21፣ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ደግሞ አምስት እጩዎች ተመዝግበዋል።

ለክልል ምክር ቤት በአፋር 73፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ 198፣ በሶማሌ 22፣ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ደግሞ 10 እጩዎች ቀርበዋል።