መምህራን በ3 ይከፈላሉ
ኀጥአን መምህራን ፣ከሀድያን መምህራንና ደጋግ መምህራን ይባላሉ። የመጀመሪያዎቹ ኀጥአን መምህራን በሥጋ የደከሙ በኀጢአት የዛሉ ከጸሎት የሰነፉ ከአርዓያነት የራቁ ናቸው። እምነትና እውቀት ግን ያልተወሰደባቸው ማለት ነው። ፈጽሞ አይጸልዩም አይጾምም ማለታችን ግን አይደለም። በአዋጅ ሕግ ይገዛሉ በዶግማ በቀኖና ጸንተው ቢኖሩም በሕይወት ምሳሌ መሆን በአርዓያነት መጠቀስ ግን አይችሉም።
እነዚህ መምህራን ኀጠአን ቢሆኑም።ሰው ኀጢአት እንዲሰራ በአደባባይ አይሰብኩም በእግዚአብሔር ፊት ቢወድቁም ፈጽሞ ሕዝብ አያሰናክሉም።
በዓርዓያነት የሚጠቀስ ግብር ባይኖራቸውም ኀጢአትን አያደፋፍሩም።በድካማቸው ይሰቀቃሉ።
ያስተማሩትን ባለመኖራቸው ይጨነቃሉ።
ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ ከነዚህ መምህራን ቃሉን እንድንማር ከሕይወታቸው ደግሞ እንዳንማር አዞናል።
ስለምን ቢሉ
ለሰው የሚተርፍ ሕይወት የላቸውምና።
ቃሉን ግን እንዳያስተምሩ አልከለከላቸውም። ጸጋቸው ጨረሶ አልተገፈፈም። በጊዜው ለራሳቸው የማይጠቀሙ ቢሆኑም ሕዝቡን ለማዳን የቃሉ ማስተላለፊያ ያደርጋቸዋል። ከበሽተኛ ዶክተር መታክም እንደማይከለከል የዶክተሩም በሽታም መድኀኒቱ እንደማይበክለው ሁሉ ድክመታቸው ቅዱስ ቃሉን አያረክሰውም።
ባይመለሱ ጸጋቸውን ገፎ ከአገልግሎት ያርቃቸዋል።
እግዚአብሔር እስከተጠቀመባቸው ድረስ ግን እኛም እንጠቀምባቸዋለን። እግዚአብሔር ሲከለክላቸው ደግሞ እንከለከላለን።
እነርሱ የግል ኀጢአተኛ ስለሆኑ የእግዚአብሔር የማዳን ሥራ አይረክስም።እግዚአብሔር የዓለምን ድኅነት በቀያፋ በበለዐም አድሮ የእስራኤል ተስፋ ሲናገር እንደሰማነው ሁሉ።
አገልጋዩ የበቃ ባይሆን ራሱ ይከስማበል እንጅ የሌላውን መዳን አይከለክልም።
2ኛዎቹ ከሐዲያን መምህራን ይባላሉ።
እነዚህ በራሳቸው ማስተዋል የተደገፉ በራሳቸው መጠበብ የእግዚአብሔርን ቃል ያለአግባብ ተርጉመው የሚያስተምሩ ነውራቸውን እንደወንጌል የሚሰብኩ ቃሉን በአደባባይ የሚክዱ ናቸው።
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም ሐዋርያትን ሰብስቦ ከፈሪሳውያን እርሾ ተጠበቁ ሲላቸው ከትምህርታቸው ራቁ ማለቱ ነው። ዛሬ ዛሬ ከንፉቃን መምህራን ሕይወትን ከክሀድያን መምህር እውቀትን ለመሸመት መጣጣር መርዝ በማር በጥበጦ መጠጣት ለጤና ተስማሚ ነው እንደማለት ይቆጠራል።
በታጠበ ትሪ በተቀመመ ወጥ በተዋበ እንጀራ ቢቀርብም መርዝ መድኀኒት አይሆንምና።ከጥርጥር ሐሳባቸው ከሚበርዝ ተልኳቸው መጠበቅ የክርስቲያን ሁሉ ግዴታ ነው።
3ኛዎቹ እንደወርቅ የተፈተኑት ደግሞ ደጋግ መምህራን ይባላሉ።እነዚህ ደጋግ መምህራን እውቀታቸው እውቀትን ሕይወታየው ሕይወትን እየወለደ በእልፍ የሚባዙ የቃሉ ምሥክር ገድላት ናቸው። ከሚያስተምሩት የሚኖሩት ይበልጣልና ብዙውን በሕይወታየው ጥቂቱን በቃላቸው ያስተምራሉ። እነዚህን መምህራን ፈልጎ ያገኘ ነፍሱ ትረካለች ሕይወቱ ትቀደሳለችና ከሚኖሩበት ገዳም ከሚያስተምሩበት ጉባዔ ድረስ ተጉዞ በረከታቸውን መቀበል ምርቃታቸውን ማግኘት ያስፈልጋል።
ቅዱስ እግዚአብሔር ደጋግ መምህራን አያርቅብን።በያሉበት በረከታየው ይድረሰን።
https://t.me/dnhayilemikael