የህይወት ቃል / Word of life

@dailywordoflife


ይህ የቴሌግራም ቻናል በየእለቱ ህይወት ከሆነው ከእግዚአብሔር ቃል አጠር ያለ መልእክት የሚቀርብበት ነው። ይህንን ቻናል በመቀላቀልና አብረን ይህንን የህይወት ቃል እንድንመረምር እናድማችኋለን። ጥያቄ ወይም አስተያየት ቢኖራችሁ በዚህ አድራሻ ጻፉልን። @melakalex ወይም +254724416340

የህይወት ቃል / Word of life

23 Oct, 07:05


ቀን 1
ተስፋዬ በአንተ ላይ ነው
ብዙ ተስፋ አስቆራጭ ነገሮችን በምንሰማበትና በምናይበት በዚህ ዘመን እኛም ከመዝሙረኛው ጋር እንዲህ ብለን ልንጠይቅና ልናውጅ ይገባል:-
“ጌታ ሆይ፤ አሁንስ ወደ ማን ልመልከት? ተስፋዬ በአንተ ላይ ነው።” መዝ 39:7
ገንዘባችን፣ እውቀታችን፣ ሥልጣናችን፣ የዘር ሐረጋችን፣ የጦር ሃይላችን፣ ወዘተ… የዘላለም ተስፋ ጽኑ መሰረት ሊሆኑ ፈጽሞ አይችሉም።
ዘላለማዊ የሆነው፣ ሰማይና ምድርን የፈጠረው፣ ሁሉን በእጁ የያዘው ጌታ ብቻ የዘላለም ተስፋ ጽኑ መሰረት ነው። ይህ እውነት ሲገባን እንዲህ ብለን በእምነት እናውጃለን:-
‘ዐይኖቼን ወደ ተራሮች አነሣሁ፤ ረድኤቴ ከወዴት ይመጣል? ረድኤቴ ሰማይንና ምድርን ከፈጠረ፣ ከእግዚአብሔር ዘንድ ይመጣል።’ መዝ 121: 1-2
እርሱን ተስፋ የሚያደርጉ ሁሉ ደግሞ “ ኀይላቸውን ያድሳሉ፤ እንደ ንስር በክንፍ ይወጣሉ፤ ይሮጣሉ፤ አይታክቱም፤ ይሄዳሉ፤ አይደክሙም።” ኢሳ 40:31
ስንመረኰዘው እጅ ወግቶ እንደ ሚያቈስለው፣ የተሰነጠቀ ሸምበቆ በሆኑት ምድራዊ ነገሮች ላይ ተስፋችንን ከማድረግ ይልቅ፣ “የተቀጠቀጠውን ሸንበቆ በማይሰብረው፣ የሚጤሰውን የጧፍ ክር በማያጠፋው” የተስፋ አምላክ በእግዚአብሔር ላይ ተስፋችንን እንናድርግ።
እርሱም ፈጽሞ አይጥለንም።
አባት ሆይ፣ አይኖቻችንን ወደ አንተ በማንሳት ሁልጊዜ “ተስፋዬ ባንተ ላይ ነው” ማለት እንድንችል በጸጋህ እርዳን። አሜን።

የህይወት ቃል / Word of life

22 Oct, 03:29


አትፍራ፣ አትፍሪ፣ አትፍሩ

ላለፉት አርባ ቀናት በቅዱስ ቃሉ ውስጥ “አትፍራ፣ አትፍሪ፣ አትፍሩ” የሚሉትን ቃላት በያዙን ጥቅሶች ላይ እያሰላሰልን ስንጸልይ ቆይተናል። አምላካችን እግዚአብሔር በተለየ መንገድ ለልባችን እንደተናገረንም አምናለሁ። ታዲያ ይህንን ጥናት ስንቋጭ እግዚአብሔር አትፍሩ ሲለን ከሦስት ዋና ምክንያቶች የተነሳ እንደሆነ ልብ ልንል ይገባል።

1 ከእኛ ጋር ያለ አምላክ

እግዚአብሔር አትፍሩ የሚለን እርሱ ከእኛ ጋር ያለ አምላክ ስለሆነ ነው። አምላካችን አትፍሩ ሲለን ደጋግሞ የነገረን እውነት እርሱ መቼም የማይለየን፥ ሁልጊዜ አብሮን ያለ አምላክ መሆኑን ነው።

“እግዚአብሔር ራሱ በፊትህ ይሄዳል፤ ከአንተም ጋር ይሆናል፤ ፈጽሞ አይለይህም፤ አይተውህምም፤ አትፍራ፤ ተስፋም አትቍረጥ።” ዘዳ 31፡ 8


2 በእኛ ደስ የሚለው አምላክ
እግዚአብሔር አትፍሩ የሚለን እርሱ በእኛ ደስ የሚሰኝ ስለሆነ ነው።
አምላካችን ከእኛ ጋር ያለ ብቻ ሳይሆን ደግሞ በእኛ ደስ የሚለው፣ ስለ እኛ የሚገደው፣ የእኛ ነገር ለእርሱ ሁሉ ነገሩ የሆነ አፍቃሪ አምላክ ነው። ለዚህ ነው “አትፍሩ” የሚለን።
“አትፍሪ፤
እጆችሽም አይዛሉ።
እግዚአብሔር አምላክሽ በመካከልሽ አለ፤
እርሱ ብርቱ ታዳጊ ነው፤
በአንቺ እጅግ ደስ ይለዋል፤
በፍቅሩ ያሳርፍሻል፤
በዝማሬም በአንቺ ላይ ከብሮ ደስ ይሰኛል።” ሶፎ 3፡ 16፣ 17

“የሰራን፣ የተቤዠን፣ በስማችን የሚጠራን፣ ለዐይኔ ብርቅ እና ክቡር ናችሁ” የሚለን አምላክ ደግሞ “አትፍሩ” ይለናል።


3 ለኛ ሁሉን በሁሉ የሚሆንልን አምላክ

እግዚአብሔር አትፍሩ የሚለን እርሱ ለእኛ ሁሉን በሁሉ የሚሆንልን አምላክ ስለሆነ ነው።
አዎ፣ ይህ ሁልጊዜ ከእኛ ጋር ያለ እና ደግሞም በእኛ ደስ የሚለው አምላክ ደግሞ ለእኛ ፍላጎታችንን ሁሉ አትረፍርፎ የሚሞላ ታላቅ አምላክ ነውና “አትፍሩ” ይለናል።

ጋሻ የሚሆነን፣ማዳኑን የሚያሳየን፣ ድልን የሚይቀዳጀን፣ የሚበቀልልን፣ መታመኛ ማምለጫ የሚሆንልን በእርግጥም ሁለመናችን ነው።

እንግዲያውስ እኛም እንደ መዝሙረኛው “ፍርሃት በሚይዘኝ ጊዜ እምነቴን ባንተ ላይ አደርጋለሁ” በማለት ፍርሃትን በእምነት ማሸነፍን ምርጫችን እናድርግ።

አባት ሆይ፣ ፍርሃት በሚይዘን ጊዜ እምነታችንን ባንተ ላይ ማድረግ እንድንችል ቃልህ ሁልጊዜ አቅም ይሁነን። አሜን።

የህይወት ቃል / Word of life

21 Oct, 03:41


ቀን 40
አትፍራ

“ሊደርስብህ ያለውን መከራ አትፍራ። እነሆ፤ ዲያብሎስ ሊፈትናችሁ አንዳንዶቻችሁን ወደ እስር ቤት ይጥላል፤ ዐሥር ቀንም መከራ ትቀበላላችሁ። እስከ ሞት ድረስ ታማኝ ሁን፤ እኔም የሕይወትን አክሊል እሰጥሃለሁ።”
ራዕይ 2፡ 10

ይህ መልእክት የተነገረው በብዙ ስደት፣ መከራና ችግር ውስጥ ያልፉ ለነበሩት ሰምርኔስ ለነበሩት አማኞች ነበር። ተናጋሪው ደግሞ "የመጀመሪያውና የመጨረሻው፣ ሞቶም የነበረውና ሕያው የሆነው" በማለት ራሱን ያስተዋወቀው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነበር። እንዲህም በማለት ነበር መልእክቱን የጀመረው:-

"መከራህንና ድኽነትህን ዐውቃለሁ፤ " (ቁ 9)።

በእርግጥም እርሱ መከራችንንና ድህነታችንን የሚያውቀው፣ የእኛን ስጋ ወስዶ፣ በሁሉ እንደእኛ ተፈትኖ፣ ሃጢአታችንና ጠላታችን ዲያቢሎስ ሊያመጡ የሚችሉትን ከፍተኛ የመከራን መጠን ተጋፍጦ ነው። በጌተሰማኔ የመከራችንን ሙሉ ጽዋ ሊጠጣ በተሰናዳበት ጊዜ እንዲህ ብሎ ነበር:- "“ነፍሴ እስከ ሞት ድረስ እጅግ አዘነች፤ " (ማር 14:34)

አዎ፣ ጌታ መከራችንን ያውቀዋልና "አትፍሩ" ይለናል።
እርሱ እስከ ሞት ድረስ ታማኝ በመሆን ለሁላችንም የዘላለምን ህይወትን አዘጋጅቶልናል። እኛንም እስከ ሞት ድረስ ታማኝ እንድንሆን ሊያበረታን ይፈልጋል።

በህይወታችን እንዲመጡ በሚፈቅዳቸው መከራዎች፣ እምነታችን የበለጠ ጠንክሮ፣ የእርሱን ብሩቱ ክንድ ተለማምደን በመጨረሻ ያዘጋጅልንን የዘላለም ህይወት አክሊል ሊያጠልቅን የሚሻ ጌታ ነው። ለዚህ ነው "አትፍሩ" የሚለን።

አባት ሆይ፣ መከራችንን የምታውቅ፣ በመከራችን ከእኛ ጋር ሆነህ በድል ልታሻግረንና የዘላለምን ህይወት አክሊል ልትሰጠን እንደምትችል በማመን በፍርሃት ላይ ድል መንሳትን እንድትሰጠንና እስከ ሞት ድረስ ታማኝ ሆነን የምንቆምበትን ጸጋ እንድታበዛልን እንጸልያለን። አሜን።

የህይወት ቃል / Word of life

20 Oct, 03:42


ቀን 39
አትፍራ

ተወዳጁ የጌታ ደቀመዝሙር ከብዙ እንግልትና መከራ በኋላ በፍጥሞ ደሴት በግዞት ተወርውሮ ሳለ፣ የእምላክ የፍጥረትና የማዳን ስራው መታሰቢያ በሆነችው በጌታ ቀን፣ በሰንበት በአምልኮ መንፈስ ሳለ አስድናቂ ራእይን ተቀበለ። በራእዩ የተመለከተው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሲሆን፣ እርሱም እንዲህ አለው:- "አትፍራ"!
ለዚህም ምክንያቱን ሲሰጥ እንዲህ አለው፦ “የመጀመሪያውም የመጨረሻውም እኔ ነኝ፤ እኔ ሕያው ነኝ፤ ሞቼ ነበር፤ እነሆ፤ አሁን ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ሕያው ነኝ፤ የሞትና የሲኦል መክፈቻም በእጄ ነው።”

ይህ እንዴት ያለ ታላቅ የሚያጽናና የሚያበረታታ ቃል ነው!

የሞት ፍርሃት ውስጣችንን ሲያውከው፣ ይህንን የጌታችንን ድምጽ እንስማ። "አትፍራ! አትፍሪ!" "እኔ የሞትና የሲኦል መክፈቻ ቁልፍ አለኝ።"

ህይወት ሰጪ ከሆነው ከዚህ ጌታ በስተቀር ይህንን ማለት የሚችል ሌላ ማንም እንዲህ ማለት የሚችል የለም፦

““ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ በእኔ የሚያምን ቢሞት እንኳ በሕይወት ይኖራል፤ ” ዮሐ 11፡ 25

አባት ሆይ፣ በአንተ እጅ ውስጥ ያለውን የሞትና የሲኦል መክፈቻ ቁልፍ በማየት ከሞት ፍርሃት ነጻ እንድታወጣን፣ "በእኔ የሚያምን፣ ቢሞት እንኳን በህይወት ይኖራል" ብለህ የተናገረከውን ቃል በእምነት እንድጨብጥና በዚህ ተስፋ ደስ እንዲለን፣ ልባችንንም እንድታሳርፍልን እንጸልያለን። አሜን።

የህይወት ቃል / Word of life

19 Oct, 04:29


ቀን 38
አትፍራ

ሐዋርያው ጳውሎስ ለጌታ ለኢየሱስ ህይወቱን በመስጠት መታወቂያው ከአሳዳጅነት ወደ ተሳዳጅነት ከተለወጠበት ጊዜ ጀምሮ በብዙ መከራ ውስጥ ያለፈ ሰው ነበር። በእስያ ገጥሞት ስለነበረው ከባድ ፈተና ሲጽፍም እንዲህ ብሎአል:-
“በሕይወት ለመኖር እንኳ ተስፋ እስከምንቈርጥ ድረስ ከዐቅማችን በላይ የሆነ ጽኑ መከራ ደርሶብን ነበር። በርግጥም የሞት ፍርድ እንደ ተፈረደብን ይሰማን ነበር፤” (2 ቆሮ 1: 8፣ 9)

ታዲያ እንዲህ ካለው የሞት አደጋ ጌታ ደጋግሞ እንደታደገው ከምናነባቸው ታሪኮች መካከል በሐዋርያት ሥራ ምእራፍ 27 እና 28 ላይ በአገልግሎቱ መጨረሻ ወደ ሮም ባደረገው ጉዞ የገጠመው አንዱ ነው። ይህ የመርከብ ጉዞ እጅግ አስቸጋሪና ከባህሩ ላይ ከገጠማቸው ወጀብ የተነሳ መርከባቸው የተሰባበረችበት፣ ጳውሎስም የሞት አደጋን እንደገና ፊት ለፊት የተጋፈጠበት ጊዜ ነበር። ይሁን እንጂ፣ “አድኖናል፣ ያድነንማል” ያለው ጌታ ከጎኑ ሆኖ አበረታው። መልአኩንም በመላክ እንዲህ አለው:-

‘ጳውሎስ ሆይ፤ አትፍራ፤ በቄሳር ፊት መቆም ይገባሃል፤ ከአንተ ጋር የሚጓዙትንም ሰዎች ህይወት እግዚአብሔር አትርፎልሃል’ (የሐዋ 27: 24)

ጳውሎስም ይህንን ቃል ይዞ በአምላኩ ላይ ተስፋውን በማድረግ በመርከቧ ላይ የተጨነቁትን ሁሉ እንዲህ በማለት አጽናናቸው፡-
“ስለዚህ፣ እናንት ሰዎች ሆይ፤ አይዞአችሁ እርሱ እንደ ነገረኝ እንደዚያው እንደሚሆን በእግዚአብሔር አምናለሁና።”ቁ 25

እኛም ተስፋችንን "አትፍሩ"፡በሚለ ጌታ ላይ ስናደርግ ዛሬ የሚታወጁብን የሞት አዋጆች አያስደንግጡንም። ተስፋም አያስቆርጡንም። እኛ ፍርሃትን አሸንፈን ሌሎችንም "አይዞአችሁ" ብለን ማደፋፈር እንችላለን።

አባት ሆይ፣ አንተ በሕይወታችን ልትፈጽም የወደድኸውን አላማህን ሊያደናቅፍ የሚችል ምንም አይነት ኃይል እንደሌለ እንድናስተውልና "አትፍሩ" ስትለን በቃልህ በመታመን ሌሎችንም ማበርታት እንድንችል በጸጋህ እርዳን። አሜን።

የህይወት ቃል / Word of life

18 Oct, 03:59


ቀን 37
አትፍራ
የአምላካችንን የማዳን ሃይል ለአለም የመመስከር ጥሪ በእርሱ ለሚያምኑ ሁሉ የተሰጠ ተልእኮ ነው። የላከን እርሱ ደግሞ ከእኛ ጋር እንደሚሆን፣ እንደሚያበረታንና እንደሚጠነቀቅልን ቃሉ ያስተምረናል። ለጳውሎስ በራእይ የተሰጠውም መልእክት ይህንን እውነት ያጸናልናል።
“ጌታም ሌሊት በራእይ ጳውሎስን እንዲህ አለው፤ “አትፍራ፤ ተናገር፣ ዝምም አትበል፤ እኔ ከአንተ ጋር ነኝና ማንም በአንተ ላይ ተነሥቶ ሊጐዳህ አይችልም፤ በዚህች ከተማ ብዙ ሰዎች አሉኝና።” የሐዋ 18፡ 9፣ 10
ከፍርሃት የተነሳ ዝም እንዳይል፣ ይልቁንም በዚያ ከተማ የምስራቹን ሊሰሙ የሚገባቸው ብዙ ሰዎች እንዳሉት ጌታ ለጳውሎስ በመንገር አደፋፈረው። "ማንም በአንተ ላይ ተነስቶ ሊጎዳህ አይችልም" በማለትም ዋስትና ሰጠው።
እርግጥ ነው፣ ጳውሎስ በአገልግሎት ዘመኑ ብዙ መከራ ደርሶበታል። ነገር ግን አንዳቸውም ያለ እግዚአብሔር ፈቃድ ወደ እርሱ አልመጡም። ጌታ መከራን ሲፈቅድ ለአላማው ሊጠቀምበት ነው።
ጳውሎስና ሲላስ ወደ እስር ቤት እንዲጣሉ ሲያደርግ፣ በእነርሱ ወደ እስር ቤት መግባት የእስር ቤቱ አለቃ እንዲድን ስለፈለገ እንጂ "ማንም በአንተ ላይ ተነስቶ ሊጎዳህ አይችልም" በማለት የገባውን ቃል መጠበቅ ተስኖት አይደለም። እንግዲያውስ እምነታችንን በጠራን በእርሱ ላይ አድርገን፣ እኛም የእርሱን የማዳን ሃይል እየጠፋች ላለችው አለም እንናገር። ዝምም አንበል!
አባት ሆይ፣ ተስፋ መቁረጥና ትርጉም አልባ ህይወት ምድራችንን በከበበት በዚህ ጊዜ ያንተን የማዳን ሃይል ከመናገር ዝም እንዳንል፣ ልባችንን በእምነት እንድትሞላው እንጸልያለን። አሜን።

የህይወት ቃል / Word of life

17 Oct, 03:51


ቀን 36
አትፍሩ
ደቀ መዛሙርቱ ከጌታችን ትንሳኤ በኋላ ደጋግመው የሰሙት መል እክት “አትፍሩ” የሚል ነበር። በተለይም ጌታችን ኢየሱስ ወደ አባቱ ከማረጉ በፊት በመጨረሻ የነገራቸው የምስራች ፍርሃትን እንዲያሸንፉ የሚረዳ ሆኖ እናገኘዋለን።
የአለምን ሃጢአት ተሸክሞ ቅጣቱ በመስቀል ላይ ከተቀጣና የሃጢአት መውጊያ የሆነውን ሞት በትንሳኤው ድል ነስቶ ከተነሳ በኋላ፣ ለተከታዮቹ እንዲህ አላቸው፦ "ስልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጥቶኛል"
ለመሆኑ ይሄ ስልጣን ምንድን ነው? እርሱ ፍጹም መለኮት እንደመሆኑ ቀድሞውንስ መች ስልጣን ጎደለውና አሁን ስልጣን ተሰጠኝ ያለው?
ይህ ስልጣን በሞቱና በትንሳኤው የተቀዳጀው በእርሱ አምነው ወደ እርሱ የሚመጡትን ሁሉ ፈጽሞ ለማዳን የሚችልበት ስልጣን ነው (እብ 7:25)። ይህ ስልጣን በራእይ 5 ላይ እንደምናነበው እንደበግ ከመታረዱ የተነሳ የተቀዳጀው ሰባቱን ማህተሞች ለመፍታት የሚያስችለው ስልጣን ነው።
እንግዲህ ጌታችን ስልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጥቶታልና “አትፍሩ” ይለናል።
በምድር ላይ ህይወታችን ቢሆን "በምድር ላይ ሁሉ ስልጣን" ያለው ህያው ጌታ ከእኛ ጋር አለ።
ለሰማዩ ተስፋችንም "በሰማይ ላይ ሁሉ ስልጣን" ያለው ይህ ጌታ በሰማያዊው መቅደስ ጠበቃችን ነው። ብቻ እምነታችንን በእርሱ ላይ እናድርግ፣ እርሱን የሃይላችን ምንጭ እናድርግ። ያን ጊዜ በፍርሃት ላይ ድልን እንቀዳጃለን።
አባት ሆይ፣ ስልጣን ሁሉ ያንተ በሆነው ላይ እምነታችንን እድርገን እንድንኖር፣ በዚህም ፍርሃትን በእምነት እንድናሸንፍ በጸጋህ እርዳን። አሜን።

የህይወት ቃል / Word of life

16 Oct, 06:57


ቀን 35
አትፍሩ

ከባዶው መቃብር የሚመነጨው የትንሳኤው ሃይል በፍርሃት ላይ ድል የሚያቀዳጀን ለምናምን ሁሉ የተሰጠ ብርታታችን ነው። ጴጥሮስ የፍርሃት ሰለባ ሆኖ "ሌሎች ሁሉ ቢክዱህ እኔ ግን ህይወቴን አሰጥሃለሁ" በማለት የፎከረው ፉከራ ሁሉ ውሃ በልቶት፣ ከአንድም ሶስት ጊዜ፣ ሊያውም በተራ ሰዎች ፊት "ኢየሱስን ፈጽሞ አላውቀውም" እያለ በመማልና በመገዘት ካደው። ፍርሃት ጴጥሮስን ጉድ ሰራው።

ይሁን እንጂ፣ ጌታችን ሞትን ድል ነስቶ ከተነሳ በኋላ፣ ጴጥሮስም ይህንን የትንሳኤ ሃይል በእምነት በህይወቱ እንዲሰራ ከተቀበለ በኋላ፣ ፍርሃቱ በእምነት ድፍረት ተተካ። በገረድ ፊት የካደውን ኢየሱስ፣ በአለቆች ፊት ሰበከው። ብዙ ማስፈራሪያ፣ ግርፋትና እስራት ቢደርስበትም፣ ሞትን ከምንም ሳይቆጥር፣ በሞት ላይ ድል የነሳውን ጌታ በጨለማ ለሚሄድ ህዝብ ለማሳውቅ ራሱን መስዋእት አደረገ። ይሄ ሁሉ የሆነው በትንሳኤው ሃይል ህይወቱ በመለወጡ ነበር።
እኛም ይህንን የትንሳኤውን ሃይል እንድለማመድ፣ በፍርሃታችን ሁሉ ላይ ድልን እንዲያቀዳጀን በእምነት ወደ እርሱ እንቅረብ።

አባት ሆይ፣ "ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ ለሕያው ተስፋና ለማይጠፋ፣ እድፈትም ለሌለበት፣ ለማያልፍም ርስት እንደ ምሕረትህ ብዛት" ስላደምከን እናመሰግንሃለን። ዛሬ ይህንን ያነተን ሃይል በእምነት በህይወታችን እንድለማመድ እርዳን። አሜን።

የህይወት ቃል / Word of life

15 Oct, 04:56


ቀን 34
አትፍሩ
በውሃ ላይ መራመድ በራሱ አንድ ትልቅ ተአምር ነው። በውሃ ላይ የምትንሳፈፈውን ጀልባ እንኳን ሊያሰምጥ እየተገለባበጠ ባለ ማእበል ላይ መራመድ ግን የተአምርም ተአምር ነው!
ጌታችን ኢየሱስ በማእበሉ ላይ እየተረማመደ ልትሰምጥ ጫፍ ላይ በደረሰችው ታንኳቸው ውስጥ ወዳሉት በጭንቀትና በፍርሃት ወደተሞሉት ደቀመዛሙርቱ መጣ። እነርሱም የሚያዩትን ማመን አቅቶአቸው የበለጠ ፈሩ። ያን ጊዜ ነበር "እኔ ነኝ፣ አትፍሩ" ያላቸው።
ትናትና፣ ዛሬ እስከ ለዘላለም ያው እና ሕያው የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ዛሬም
እኛንም ባሰጨነቀን በማኛውም ወጀብ ላይ እየተራመደ ወደ እኛ መቅረብ ይችላል። እንዲህም በማለት ድምጹን ያሰማናል፦ "እኔ ነኝ፣ አትፍሩ" ።
“በምድር ላይ ከሚሆነው ነገር የተንሳ፣ የሰዎች ልቦች በፍርሃት ምክንያት ይወድቃሉ። ነገር ግን በእግዚአብሔር የሚያምኑ ሁሉ በወጀቡ መካከል እንዲህ የሚለውን ድምጹን ይሰማሉ:- “እኔ ነኝ፣ አትፍሩ” Signs of the Times, October 9, 1901.
አባት ሆይ፣ በእርግጥም አንተ አስጨናቂውን ወጀብ መረማመጃህ የምታደርግና ልጆችህን ለመታደግ የምትፈጥን አባት ነህና ስምህ የተመሰገነ ይሁን። ባንተ ላይ መታመናችንን እንድናደርግ እርዳን። አሜን።

የህይወት ቃል / Word of life

14 Oct, 03:46


ቀን 33
አትፍሩ

ይህ ዘመን ከቁጥጥራችን ውጪ የሆኑ ብዙ አስጊ ነገሮች እለት እለት እየጨመሩ የሰውም ልብ በፍርሃት የሚርድበት ዘመን ነው። ታዲያ በዚህ ዘመን፣ ለፍጥረቱ የሚጠነቀቅ አምላክ፣ አባታችን በሰማይ እንዳለ ማወቁና በእርሱም ዘንድ ዋጋችን የከበረ እንደሆነ መረዳቱ እጅግ ወሳኝ ነገር ነው። በእርግጥም እርሱ ስለ እኛ እንደሚገደው በማመን፣ በነገር ሁሉ እርሱን በመታመን ፍርሃትን ድል ነስተን ልንኖር እንችላለንና እንዲህ ይለናል፦

“በአንድ ሳንቲም ከሚሸጡት ሁለት ድንቢጦች አንዲቷ እንኳ ያለ አባታችሁ ፈቃድ ምድር ላይ አትወድቅም። የራስ ጠጕራችሁ እንኳ አንድ ሳይቀር የተቈጠረ ነው። ስለዚህ አትፍሩ፤ ከብዙ ድንቢጦች ይልቅ ዋጋችሁ የከበረ ነው።”

ዋጋ አውጥታ በአንድ ሳንቲም ለመሸጥ የግድ ሁለት መሆን ያለባት (በሌላ አነጋገር በሰው ዘንድ ምንም ዋጋ የሌላት) አንዲት ድንቢጥ በእግዚአብሔር አይን የምትታይ ከሆነ እንግዲያውስ እኛ የዐይኑ ብሌን የሆንንማ የራሳ ጠጉራችን እንኳ አንድ ሳይቀር የተቆጠረ ሲሆን ያለ እርሱ እውቅናም ያቺ አንዲት ጠጉር አትወድቅም።

ከዚህ በተጨማሪም ወደ እኛ የሚመጣው ነገር በእርሱ እውቅና የሚመጣ ብቻ ሳይሆን እኛን የሚነካን በቅድሚያ እርሱን ነክቶት ነው ። የጌታ ቃል እንዲህ ይላልና:- “የሚነካችሁ የዐይኑን ብሌን ይነካል፤” ዘካ 2:8
በእርግጥም እንደ ዐይኑን ብሌን የሚያየንን አምላክ ሳይነካ እኛን የሚነካን አንዳች ነገር የለም። ችግራችን፣ ስቃያችን፣ ሃዘናችን፣ ጭንቀታችን ሁሉ እኛን ከመንካቱ በፊት እርሱን በቅድሚያ ይነካዋል።

በኢሳ 63:9 ላይ ይህንን እውነት በማስረገጥ እንዲህ ተጽፎአል:- “በጭንቃቸው ሁሉ ተጨነቀ፤ የፊቱም መልአክ አዳናቸው፤ በፍቅሩና በምሕረቱ ዋጃቸው፤ በቀደመው ዘመን ሁሉ አነሣቸው፤ ተሸከማቸውም።” የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ለዚያ ማረጋገጫችን ነው። እንዴት ያለ ድንቅ አፍቃሪ አምላክ ነው እኛ የምናመልከው! ስሙ ይባረክ።

አባት ሆይ፣ ሁሉን በምትገዛና በምትጠነቀቅልን በአንተ በአምላካችን ላይ ያረፈ ልብ ይኖረን ዘንድ እምነታችንን አጠንክርልን። አሜን።