ተስፋዬ በአንተ ላይ ነው
ብዙ ተስፋ አስቆራጭ ነገሮችን በምንሰማበትና በምናይበት በዚህ ዘመን እኛም ከመዝሙረኛው ጋር እንዲህ ብለን ልንጠይቅና ልናውጅ ይገባል:-
“ጌታ ሆይ፤ አሁንስ ወደ ማን ልመልከት? ተስፋዬ በአንተ ላይ ነው።” መዝ 39:7
ገንዘባችን፣ እውቀታችን፣ ሥልጣናችን፣ የዘር ሐረጋችን፣ የጦር ሃይላችን፣ ወዘተ… የዘላለም ተስፋ ጽኑ መሰረት ሊሆኑ ፈጽሞ አይችሉም።
ዘላለማዊ የሆነው፣ ሰማይና ምድርን የፈጠረው፣ ሁሉን በእጁ የያዘው ጌታ ብቻ የዘላለም ተስፋ ጽኑ መሰረት ነው። ይህ እውነት ሲገባን እንዲህ ብለን በእምነት እናውጃለን:-
‘ዐይኖቼን ወደ ተራሮች አነሣሁ፤ ረድኤቴ ከወዴት ይመጣል? ረድኤቴ ሰማይንና ምድርን ከፈጠረ፣ ከእግዚአብሔር ዘንድ ይመጣል።’ መዝ 121: 1-2
እርሱን ተስፋ የሚያደርጉ ሁሉ ደግሞ “ ኀይላቸውን ያድሳሉ፤ እንደ ንስር በክንፍ ይወጣሉ፤ ይሮጣሉ፤ አይታክቱም፤ ይሄዳሉ፤ አይደክሙም።” ኢሳ 40:31
ስንመረኰዘው እጅ ወግቶ እንደ ሚያቈስለው፣ የተሰነጠቀ ሸምበቆ በሆኑት ምድራዊ ነገሮች ላይ ተስፋችንን ከማድረግ ይልቅ፣ “የተቀጠቀጠውን ሸንበቆ በማይሰብረው፣ የሚጤሰውን የጧፍ ክር በማያጠፋው” የተስፋ አምላክ በእግዚአብሔር ላይ ተስፋችንን እንናድርግ።
እርሱም ፈጽሞ አይጥለንም።
አባት ሆይ፣ አይኖቻችንን ወደ አንተ በማንሳት ሁልጊዜ “ተስፋዬ ባንተ ላይ ነው” ማለት እንድንችል በጸጋህ እርዳን። አሜን።