ETHIOPIAN BEST PHOTO AND ORTHODOX TEWAHDO MAZEMURE

@mertephoto


በዚኽ ቻናል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የተዘጋጁ መዝሙራት እንዲሁም ሥዕለ ቅዱሳን እና ምርጥ እና የሚመቹ ደስ የሚሉ ፎቶዎች ይለቀቅበታል
ማንኛውንም ሀሳብ አስተያየት ካለ እንዲሁም አንዲለቀቅ የምትፈልጉትን ፎቶዎች እና መዝሙሮችን በዚህ ሊንክ አድርሱን 👉👉👉 @Mtrsetbot👈👈👈

ETHIOPIAN BEST PHOTO AND ORTHODOX TEWAHDO MAZEMURE

07 Aug, 19:19


➣በሥራ ወይም በሌላ አጋጣሚ የዶሮ እርባታ ሥፍራዎችን፣ የቆዳ ፋብሪካዎችን፣ የእንስሳት እርባታና ተዋጽኦ ማቀነባበሪያ ቦታዎችን የመጎብኘት ሁኔታ አጋጥሞን  ከሆነ  መጥፎ ጠረኑ አፍንጫችንን እንድይዝ አስገድዶን ሊሆን ይችላል። በተለይም ራሳችንን እንደ ቀበጥ የከተማ ልጅ /City boy/ የምንቆጥር ከሆነ የመጥፎ ሽታውን ጠረን ለመቋቋም በጣም እንቸገራለን~እንዴውም "ኡፍፍፍፍ" እያልን እንጠየፋለን።

  ወዳጄ ሆይ~ እየሸተተን ያለው ግን አዛባና የዶሮ ኩስ ሳይሆን የገንዘብ /ዶላር ሽታ ነው። it's the smell of money. በዓለማችን የዚህን አዛባና ኩስ ሽታን ተቋቁመው ጠንክረው በመሥራት ወደ ከፍተኛ የብልጽግና ማማ ላይ የተፈናጠጡ አያሌ ባለጸጎች እንዳሉ ፎርቢስ ላይ ማንበብ ወይም በዙሪያችን ያሉትን ጥቂት ባለጸጎች መመልከት በቂ ነው። በከተሞች መንገድ ላይ የተከመረ ቆሻሻን በማጽዳት፣ እንደ ችቦ ብርሀን በመፈንጠቅ የሥራ ባህልና ሞራል ለገነቡልን ክብር ልንሰጣቸው ይገባል።

ከእውነተኛ ሀብት ጀርባ ሁልጊዜ ትልቅ ድካም፣ ትልቅ ትዕግስት፣ መጥፎ ጠረን የተሞላ የሥራ ቦታን መታገስ፣ እንቅልፍ የሚያሳጣ ረጅም የሥራ ሰዓት፣ ጅማት የሚያዝል ጡንቻ የሚያሸማቅቅ አድካሚ ሥራ፣ አዕምሮ የሚያነሆልል እሳቤ የሚጠይቅ ተግባር፣ የእጅ መዳፍ የሚገሸልጥ፣ የእግር ተረከዝ የሚሰነጥቅ፣ ጥፍርን የሚቀረድድ አድካሚ ሥራ መሥራት፣ ወገብ የሚያንቀጠቅጥ ተጋድሎ መፈጸም የግድ ይላል። በእንዲህ ያለ ድካም የሚገኝ ገንዘብ የኅሊና እርካታ፣ የሞራል ልዕልና ከምቾት ጋር ያጎናጽፋል። እንዲህ ባለ ሁኔታ የሚገኝ ሀብት ባለ ጸጋ ያደርጋል። ባለጸግነት የሞራል ልዕልና ደግሞ ትጋትን፣ ቅንነትና እውነትን ትይዛለች። ገንዘብ በስርቆትና መሰል በማጭበርበር ተግባራትም ሊገኝ ይችል ይሆናል። በዚህ መልኩ የተገኘ ገንዘብ ሀብታም ያደርግ ይሆናል እንጅ ባለጸጋ አያደርግም።

በአገራችን ብዙ ሀብታሞች አሉ፤ ብዙ ባለጸጎች ግን የሉንም። ሀብታሞች ከባለጸጎች የሚለዩት ገንዘብ የሚያገኙት የሌሎችን በመቀማት፣ ጉልበት በመበዝበዝና እንዲሁም በማደህየት ሲሆን ባለጸጎች ግን ሀብትን በድካማቸው ይፈጥሩታል። ታላቁ የአሜሪካ የመኪና አምራች ኩባንያ ባለቤት ሚስተር ፎርድ ሥራውን የጀመረው አካፋና ዶማ በማምረት ነበር። ባለጸጎች ለሌሎች ይተርፋሉ እንጅ አይቀሙም።

ሀገራችን ባሳለፈቻቸው ሰላሳና አርባ ዓመታት የኢኮኖሚ ዕድገት ጭላንጭል ቢታይበትም በሞራልና በሕግ ባለመመራት ብዙ ባለ ሀብቶችን እንጅ ብዙ ባለጸጎችን አልታደለችም።

እነዚህ ድካምን ሳያዩ፣ ልፋትን ሳይቀምሱ ገንዘብ ያግበሰበሱ ባለሀብቶች የሀገሪቱን ኢኮኖሚያዊ መዋቅር ከማናጋታቸው በላይ በወጣቱ ሥነልቦና ላይ የፈጠሩት ጠባሳ በቀላሉ የሚታይ አይደለም። ከትንሽ ወደ ትልቅ፣ ከጠባብ ወደ ሰፊ፣ ከውድቀት ወደ ስኬት፣ ከኮረኮንች መንገድ ወደ ደልዳላ ጉዞ፣ ከመሳሳት ወደ መታረም፣ በመጨረሻም ከማጣት ወደ ማግኘት ከአካልና ከአዕምሮ ብስለት ጋር እንደሚታደግ ለወጣቶች ያስተማራቸው አርዓያ የሚሆናቸው አልነበረም።

  ትናንት ምንም ያልነበረው ሰው ድንገት ዛሬ በርካታ ሚሊዮን ብሮች፣ ብዙ ህንጻዎች፣ ቅንጡ ተሽከርካሪዎች፣ በርካታ ድርጅቶች እንዳሉት ይሰማሉ። በቃ የሀብት መንገድ አጭርና አቋራጭ ብቻ እንደሆነ፣ በድካም በጊዜ ሂደት መበልጸግ ሞኝነት እስኪመስላቸው ድረስ ስነ ልቦናቸውን የተጣመመ ሆኗል።

በጥቅሉ ከባለጸጎች ስኬት ጀርባ ብዙ የፈሰሰ ወዝ፣ የተንጠባጠበ ላብ፣ የተኮማተረ ጅማት፣ የታጠፈ አንጀት የተላጠ ትከሻ አለ። ከሀብታሞች ታሪክ ጀርባ ግን ቅሚያ፣ ጉልበት ብዝበዛ፣ ውንብድና እና ማጭበርበር አለ። ሀብት ከፈጠረው የቀላ ደረት፣ የወዛ ፊት ጀርባ የቆሸሸ ህሊና ሊኖር ይችላል።

ከህይወት ልምዴና ከመጽሀፉ ንባብ የተረዳሁት  "የገንዘብ ሽታ ፍልስፍና" ነገር ቢኖር~ የንጹህ ገንዘብ ሽታ የከብት አዛባ፣ የዶሮ ኩስ ሽታ ነው። የእውነተኛ ገንዘብ ጠረን የጭቃ፣ የኬሚካል፣ የጭስ፣ ከሰውነት ድካም የሚመነጭ የላብ ጠረን ነው። አሁን ሲገባኝ ለካ መጥፎ ሽታ የከብቶች አዛባ አይደለም፣ የዶሮ ኩስም አይደለም፣ የድካም ላብ ጠረንም አይደለም። መጥፎ ሽታ ድህነት ነው። መጥፎ ጠረን የሰው እጅ ማየት፤ ተቸግሮ ከሠው ፊት መቆም ነው። መጥፎ ቅርናት ማለት ስንፍናና ስርቆት ነው። ክርፋት ማለት ውድ ሱፍና ካራባት ለብሶ እንደ አገር እርዳታ መቀበል ነው።

#ችቦ መጽሀፍ~ዘር፣ ቋንቋ፣ ባህል፣ ሀይማኖት ቢለያየንም በዓለም ላይ ያለ ሁሉ የአንድ አዳምና ሄዋን ልጅ ነው። ትክክልና ስህተት /Right and wrong/ ለሁሉም ተመሳሳይ ነው።  በሞራልና በዕምነት ጎዳና ላይ ከሚያሳስቱን ይልቅ የሚያርሙን ይበልጣሉ። ከሚያሰናክሉን ይልቅ የሚያርሙን ይልቃሉ። ከዛህ ረገድ ከያዝነው መርህ መንሸራተት እንደሌለብን በአጽንኦት ይነግረናል። "Take care your self! Do not slide down from your principles!"

መጥፎ በምንለው የአዛባ ሽታ፣ አስቀያሚ በምንለው የዶሮ ኩስ ጠረን ውስጥ ገንዘብ ይታፈሳል፣ ላብን በሚያንጠባጥብ ከባድ በምንለው ሥራ ውስጥ ወርቅና ዳይመንድ ይገኛል። ሽታውን ውደደው፣ ሽታው የገንዘብ /የዶላር ነው። it's the smell of money. Don't Worry!

እኔም ከዓመታት በፊት ቀለምና ቡርሽ አዋህጄ ስዕልና ጽሁፍ እየሰራሁ በነበረበት ወቅት የቅርብ ጓደኞቼ የቀለሙንና የማዋሀጃውን ኬሚካል ሽታ ይጠየፉት እንደነበረ አስታውሳለሁ። በበኩሌ የቀለሙን ሽታ ባልጠላውም የዶሮ ኩስ፣ የከብት ሽንትና አዛባ ባለበት ቦታ ሁሉ ሽታውን ለመቋቋም አፍንጫየን እይዝ ነበረ። ይሁን እንጅ  ከጥልቅ መረዳት በኋላ መጥፎ ጠረን ባለበት የሥራ ቦታ ሁሉ አፍንጫን መያዝ ሳይሆን አብሮ የመስራት ጥልቅ ፍላጎት አደረብኝ።

"ችቦ"

ETHIOPIAN BEST PHOTO AND ORTHODOX TEWAHDO MAZEMURE

27 Jul, 21:58


† #ሐምሌ ²¹ #እንኳን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም : ቅዱስ ዑራኤል እና ለቅዱሳኑ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን።

† ድንግል እመቤታችን እና ቅዱስ ዑራኤል፦ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት በዚህች ቀን ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ዑራኤል:-

1.ድንግል ማርያም በአካለ ሥጋ እያለች ወደ ሰማይ አሳርጓታል:: በሠረገላ ብርሃን ጭኖ: በክንፎቹም ተሸክሞ: አስቀድሞ ገነትን ቀጥሎም ሲዖልን አስጐብኝቷታል:: በዚህም ምክንያት እመ ብርሃን ስለ ኃጥአን የምታለቅስ: የምትለምንና የምትማልድ ሆናለች:: ለምናም አልቀረች የምሕረት ቃል ኪዳን ተቀብላለች::

2.ቅዱሱ መልአክ እመ ብርሃንን በስደቷ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ መርቶ አምጥቷታል:: በክንፉ ተሸክሞ: በአራቱም አቅጣጫ አዙሮ አሳይቶ አሥራት እንድትቀበል አድርጓል::

3.ጌታችን በተሰቀለ ጊዜ ደሙን በጽዋዕ አድርጐ በኢትዮጵያ ወንዞች ላይ አፍስሷል::

4.ለብዙ ቅዱሳን (አባ ጊዮርጊስን ጨምሮ) ጽዋዐ ልቡናን አጠጥቷል::

† ከእመቤታችን ድንግል ማርያም ጣዕሟን ፍቅሯን : ከቅዱሳኑ ሁሉ ጸጋ በረከትን እግዚአብሔር ያድለን::

ETHIOPIAN BEST PHOTO AND ORTHODOX TEWAHDO MAZEMURE

09 Jun, 07:09


‹‹ሰላምን እተውላችኋለሁ፤ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ›› ዮሐ. ፲፬፥፳፯
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል ለሕዝቡ ‹‹ሰላምን እተውላችኋለሁ፤ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ…›› ብሎ በነገራቸው ቃሉ ሰላምን የሚሰጠው እርሱ እንደሆነ እንረዳለን፤ ይህም የተወልን ሰላም መንፍሰ ቅዱስ በመሆኑ መንፈስ ቅዱስ በአንድ ሰው ውስጥ ሲያድር የልብ ሰላምን ይጎናጸፋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሰላም ሲጽፍ እንዲህ ብሏል፤‹‹አእምሮውንም ሁሉ የሚያልፍ የእግዚአብሔር ሰላም ልባችሁንና ሀሳባችሁን በክርስቶስ ኢየሱስ ይጠብቃል፤›› (ዮሐ. ፲፬፥፳፯፤ ፊል. ፬፥፯)

ማንኛውም ዓይነት ውጫዊ ተጽእኖ ቢገጥመው ሰላም ያለው ሰው አይታወክም፤ አይጨነቅም ወይም አይረበሽም፡፡ የእርሱ ሰላም የሚመሠረተውም በእግዚአብሔር ጥበቃና እንክብካቤ፣ በሰው መተማመንና በእርሱ ቃል ኪዳኖች ላይ ባለው እምነት እንጂ ከውጪ ባሉ ሁኔታዎች ላይ አይደለም፡፡

እግዚአብሔር እስከ አለ እና እስከ ጠበቀን ድረስ ምንም ዓይነት ፍራቻ በውስጣችን ሊኖር አይገባም፤ ይህ በመሆኑም ነቢዩ ዳዊት እንዲህ በማለት ተናግሯል፤ ‹‹በሞት ጥላ መካከል እንኳ ብሄድ፤ አንተ ከእኔ ጋር በነህና ክፉን አልፈራም፤ በትርህና ምርኩዝህ እነርሱ ያጽናኑኛል፡፡›› የዳዊት ሰላም ምንጭ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር የመሆኑ እውነት ነው፡፡ (መዝ. ፳፪፥፬)

ሐዋርያት በታንኳ ሲጓዙ ጌታ ያንቀላፉ ስለመሰላቸው ሞገዱ ሲያናውጣቸው በጣም ተጨንቀው፤ ሰላማቸውን አጥተው ነበር፡፡ በእነርሱ ላይ የበረታው ውጪያዊው ሁኔታና የጌታ ሥራ ከእነርሱ ጋር ያለ መስሎ ስላልታያቸው ነው፡፡ ስለሆነም ጌታ ተነሥቶ ነፋሱን በመገሠጽ ሰላማቸውን መልሶላቸዋል፡፡

ውስጣቸው ጥብቅ ከሆነና በእምነታቸውም የጸናኑ ከሆኑ ከውጪ ያለ ምንም ዓይነት ነገር እንደማያናውጣቸው ነገራቸው፤ ነፋስና ጎርፍ እንዳልጣለውና በዓለት ላይ እንደተገነባው ቤተ እንዲሆኑም አዘዛቸው፤ ያም ቤት ውስጡ ጥብቅ ነበረና፡፡

ጠንካራ መርከብ በሚመታው ብርቱ ማዕበል ጉዳት ሊደርስበት አይችልም፡፡ መርከብ የሚጎዳው ወደ ውስጡ ውኃ የሚያስገባ ቀዳዳ ሲኖር ነው፡፡

ቅዱስ እንጦንስ ለልብ ሰላም ምሳሌ የሚሆን ሰው ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ አትናቴዎስ ስለ እርሱ ሲናገር፤ ‹‹መሪር ነፍስና የታወከ ሀሳብ ያላቸው ሰዎች ሁሉ የቅዱስ እንጦንስን መልክ ሲመለከቱ ልባቸው በሰላም ይሞላል›› ብሏል፡፡ (ፍኖተ አትናቴዎስ)

ሰላሙ የበዛለት ሰው ለሌሎች ሰላም መስፈን ምክንያት ይሆናል፤ ሰላም ስናገኝ በሥጋዊ ሆነ በመንፈሳዊ መንገድ ውስጥ በመልካም ጤንነት እንኖራለን፡፡ የክርስቲያኖች በሰላም በአንድነት ለመኖር ደግሞ የቤተክርስቲያን ሰላም ሊጠበቅ ይገባል፡፡

‹‹አቤቱ ጌታችን ሆይ፤ አንዲት ቅድስት ዓለማቀፋዊትና ሐዋርያዊት የሆነች ቤተ ክርስቲያንህን አስባት፤ በሰላምም ጠብቃት›› የሚለው ጸሎት ስለ ቤተክርስቲያን በየዕለቱ የሚጸለየውም ለዚህ ነው፡፡ ይህን ጸሎት ከሌሎች የንስሓ ጸሎቶች ሁሉ በፊት እንጸልየዋለን፡፡ በመሆኑም በሰርክ ጸሎት ማዕጠንት፤ በነግህ ጸሎት ማዕጠንት፤ ካህኑ በመሠቂያው ዙሪያ እየዞረ ዘወትር ሲጸለይም ይህን ጸሎት ይጸልያል፡፡

ቅዳሴ ከመጀመሩ በፊትና መባ ከመቅረቡ በፊት ደግሞ እንዲህ ብለን እንጸልያለን፤ ‹‹አንዲት፤ ቅድስት፤ ዓለማቀፋዊትና ሐዋርያዊት ለሆነችው የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ሰላምና ቅድስና አድላት፤›› ካህናት ሲሾሙም ይህን የዘወትር ጸሎት እንጸልያለን፡፡

ለንጉሥ በሚደረግ የዘወትር ጸሎት ውስጥም ‹‹አንዲት፤ ቅድስት፤ ዓለማቀፋዊትና ሐዋርያዊት ለሆነችው ቤተ ክርስቲያንህ ሰላም ልቡን ዳስሰው›› በማለት ስለ ቤተክርስቲያን እንጸልያለን፡፡

የቤተክርስቲያን ሰላም የአባቶቻችን ሐዋርያትና የቅዱሳን ሁሉ አንዱና ዋነኛው ጠቃሚ ጉዳያቸው ነበር፡፡ ለእነዚህ ሁሉ አባቶች ይህች ቤተክርስቲያን እስከ ሰማያዊው መንግሥት ድረስ የምትዘረጋ በምድር ያለች የእግዚአብሔር መንግሥት ምሳሌ ናት፡፡ የምትወክለውም የእምነትን ምንጭና እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር የመኖሩን እውነት ነው፡፡ አንድ ሰው በጸሎቱ ውስጥ ለራሱ ከሚያቀርበው ጥያቄ ይልቅ ለእርሷ ስለሚጠይቅ ሰላሟና ደኅንነቷ የእያንዳንዱ ሰው የጸሎት መሠረት ነው፡፡ ይህ ጥያቄ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባስተማረን ጸሎት ውስጥ የተመስጦአችን ማዕከል ስለሆነ ‹‹ስምህ ይቀደስ፤ መንግሥትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን…›› እያልን እንጸልያለን፡፡

ስለ ቤተክርስቲያን መጸለይ በምእመናን፣ በእረኞቹና በመጋቢዎቹ አንደበት ውስጥ ለብዙ መቶ ዓመታት የቆየ ታላቅ ጸሎት ነው፡፡ ራሳቸውን ከዓለም ለለዩ መነኮሳት በሚደረግ የቅዳሴ ጸሎት ውስጥ እንኳ ለቤተክርስቲያን ሰላም አንጸልያለን፡፡

የመናኞች ሁሉ ታላቅ አባት የሆነው የመጀመሪያው ባሕታዊ አባ ጳውሊ ቅዱሱን አባ እንጦንስን ስለ ቤተክርስቲያን ሰላም መጠየቁ እንደምን ያለ ድንቅ ነገር ነው፡፡ ይህን ጸሎት የምንጸልየው ከልባችን ነው፡፡ የምንጸልየው የቅዳሴ አንድ ክፍል አድርገን ሳይሆን እንደ ሕያውና እንደሚያቃጥል ስሜት እየሆነብን ነው፡፡ እያንዳንዱ ሰው ስሜቶቹን ሁሉ በዚህ ጸሎት ውስጥ በማደረግ ለቤተክርስቲያን መጸለይ ይገባል፤ እግዚአብሔር አምላካችን ሰላሙን ይስጠን፤ አሜን፡፡

ምንጭ፤ ‹‹መንፈሳዊ ቃላትና ጥቅማቸው- ክፍል አንድ፤›› በግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ፤ ትርጉም አያሌው ዘኢየሱስ

2,671

subscribers

1,285

photos

20

videos