ሚኪያስ ፈይሣ

@mikiyas_feyisa


ግጥም
ወግ
ሀሳቦች
ልቦለዶች
🤝 @mika145

ሚኪያስ ፈይሣ

23 Oct, 05:21


የእባዋን ጎርፍ አሳነሱት
መፀፀቷን አራከሱት
ገልጠው ሰው ፊት አነበቡ
የተዘጋው ምዕራፏን
ተንቀልቅላ ቤቱ ሄደች
እያነባች ይዛ አፏን
ሰውነቷን ተጠየፈች
የፀፀቷ ጅራፍ በዛ
ከጌታ ጋር አልተዋትም
እዛው ልቧን እንድትገዛ

የወገብ ላይ ውጋት ሆኑ
እንዳትቆም አሳቀቋት
በመጠየፍ አይን እያዩ
ቅን እምነቷን መነጠቋት
ውለው አድረውም
እንዲያው ናቸው
ሁሌ ግራ የሚሄዱት
ጥፋቷን ሰርክ እያነሱ
ንስሀዋን አከበዱት

አዎን ብዙ በድላለች
ሀጥዕ ሆና ጋለሞታ
ማንም ጣቱን እንዳይጠቁም
ከመጣች ግን ወደጌታ
ወርቅ ምንጣፍ ይዘርጋላት
ወደ ቤቱ እስክትገባ
ከግብዞች ፀሎት በላይ
ጌታ ይሰማል ንፁህ እምባ
ታሪክ ገጿ ምንም ይሁን
የትላንቷ ምንም ያክል
ማነው ሸክሟ በዝቷል ብሎ
እንዳትገባ ሚከለክል ?
.
አወሩባት ብዙ ነገር
.
አይን አውጣ ነች የማታፍር
አይተናታል ከዚህ ቦታ
ከጀርባዋ ይዘልፏታል
ታለቅሳለች በዝምታ
እንዲህ ሴት ነች
እንዲያ ሴት ነች
ክፉ ግብሯን ዘረዘሩት
ምንም ጥፋት እንዳልሰሩ
አሽሟጠጡ የተቀሩት

ምናለበት ሰው አይደለች?
ምናለበት ሰው አይደለች?

የልብሳቸው ጨርቃ ቢወልቅ
ቀሽም ቀሊል የሚሆኑ
ሱባኤዋን እስክትጨርስ
ገመናዋን ቢሸፍኑ
ባይፈርዱባት ምናለበት
በአደባባይ ለህዝበ አገር
የሀዲስ ኪዳን ሀጥያተኛ
በቃላት ነው የሚወገር?

ይበቃታል ህሊናዋ
ሰርክ አስታውሶ የሚቀጣት
ይበቃታል ህሊናዋ
በሀሳብ ማዕበል የሚንጣት
ይበቃታል ሰውነቷ
የሚቀፋት እንደ ሩቅ ሰው
ይበቃታል ይህ ጭንቀቷ
ውስጧን በልቶ የጨረሰው

አታድክሟት ደካማዋን
አትጨምሩት መከራዋን
አንድም የለም ከኛ መሃል
ችሎ ችሎ የማይደክም
እስቲ ተዋት ከአምላኳ ጋር
የሷን ህመም እሷው ታክም!

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

30 Sep, 18:34


አስጠነቆልኩባት


ዱር ገደል ወርጄ
ጠንቋይ ዘንዳ ሄጄ
መስተፋቅር ብቻ
ለሚጠነቁሉ.. ለታወቁ አባት
ጠጉሯን ይዤ ሄጄ.. አስጠነቆልኩባት

የታባቷንና
ለምን እኔ ብቻ ከርሷ መሄድ ማልተው
ለምን እኔ ብቻ ሳያት ምደሰተው
ለምን እኔ ብቻ በፍቅሯ ምቃጠል
ለምን እኔ ብቻ
ጡት እንዳየ ህፃን ላዩዋ ምንጠለጠል
ለምን እኔ ብቻ የ'ርሷም ዕጣ ይድረስ
የካበችው ገላ ከእግሬ ስር ይፍረስ
ለምን እኔ ብቻ
ለእርሷ ምንገበገብ በናፍቆት ምቀጣ
እርሷም በተራዋ ተንቀልቅላ ትምጣ

የታባቷን
በምዕናቤ እየሳልኩ
በፍቅሬ ተቃጥላ
ወደኔ ስትከንፍ ወደኔ ስትበር
እንደ ነብይ ቃል እጠብቃት ጀመር
ብጠብቅ .. ብጠብቅ
ብጠብቅም በጣም
ናፍቆቷ ነው እንጂ አካሏ አልመጣም
ጠንቋዩን አምኜ
ጠብቂያት
ጠብቂያት
በመጠበቅ ብዛት ጉልበቴ ቀለለ
ከመቅረቷ ይልቅ
በጠንቋዩ ስራ ቆሽቴ ድብን አለ

ወደ ጠንቋዩ ቤት
መብረር እየቃጣው እግሬ ተራመደ
እቅጩን ልነግረው
የርሱ ጥንቁልና ቁብ እንዳልፈየደ
ልጣላው ወስኜ
ከቤቱ ደርሼ አንኳኳው የምሬን
አልመልስም ካለ
"መስተፋቅር" ብሎ የበላኝን ብሬን

አልከፈት ብሎኝ
በርግጄ ስገባ ..ትግስቴ ተሟጦ
ጠንቋዩን አስተዋልኩ
ቆርጬ ያመጣሁት ፀጉሯ ላይ አፍጦ

አይ አለመታደል
ይህ ታታሪ ጠንቋይ
ስራን ከምንም ላይ ተነስቶ የፈጠረ
ፀጉሯ ጦስ ሆኖበት
ጥንቁልና ትቶ ከምንም ላይ ቀረ

"ፍቅሯ አደንዝዞት
እሷን አገኝ ብሎ
ጠንቁሎ ጠንቁሎ ..ከመጠንቆል ብዛት
መጠንቆያው ሲኒ..የሲኒ ጨብጥ ያዛት"
አያለ ይታማል

እኔ ግን እኔ ግን
የርሷ አለመምጣት
የብሬ መበላት ..ቅንጣቱን ሳይከፋኝ
እርሱን ማባበሉ ..በጣሙን አለፋኝ


ፍቅሯ ተምታቶበት
ፍቅሯ አጃጅሎት
በእርሷ ዘንዳ ሚኖር ሲሆን ቋሚ በድን
አማራጭ ስላጣን
ሌላ ጠንቋይ ጋራ ለማስጠንቆል ሄድን

*------------------*
@mikiyas_feyisa
(11-09-2015)
የቆየ ነው ደሞ😁🫡

ሚኪያስ ፈይሣ

18 Sep, 10:08


እንደ ተበዳይ አታልቅሺ
ለበደል ነበር አመጣጥሽ
ፀባይ አመልሽን ማጣፈጥሽ
እስስት ውስጥሽን መለወጥሽ

እንደ ንፁህ ሰው "እሪ" አትበይ
ባገር በሰፈር አታሳጂኝ
የሳልሽው ብረት በላሽ እንጂ
እቅድሽ ነበር ልትጎጂኝ

የዋህ አልነበርሽም እንዳሰብኩሽ
ጅል አልነበርኩም እንዳሰብሺኝ
አባዝተሽ ከኔ ለመውሰድ ነው
ሽሙንሙን ፍቅር የሰጠሺኝ

ፍቅርሽን ይዤ ዝም ብልሽ
ከእብድ አየሺኝ ከወንበዴ
ክፉ ሰው ሆንኩኝ ልትሄጂ ስል
ቀድሜሽ እኔ በመሄዴ

እሰይ ደግ አረኩ
የኔ አስመሳይ
ብትቀበሪም ፡ አላምንሽም
እምባሽ ላይ ሳቅሽ ይታየኛል
ውሸት አትፈሪም እየማልሽም
ድራማሽ ይብቃ ተነቃቃን
ከበቀል ጠጪ ከእልሁም
መለየት መርሳት እችላለው
እንደ ወንዶችሽ አይደለሁም!

እንዲያ ነው ብለሽ አውጂልኝ
ይሄ ጥቅስ አለ ከኔ ዘንዳ
"ደግ ነው በዳይ የሚያስለቅስ
ብፁዕ ነው ክፉ የሚጎዳ!"

እሰይ ..
እንኳን ጎዳሁሽ
@mikiyas_feyisa
@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

14 Sep, 17:18


..
ለገላዋ እራፊ ፡ ብጣሽ አልገዛሁም፤
እረዥም ታሪኳን ፡ ቁጭ ብዬ አልሰማሁም
ምኞት ፍላጎቷን ፡ ለይቼ አላወኩም
የእግሯን ወለምታ ፡ አሽቼ አላዳንኩም፤
አሞሌ ጭንቀቷን ፡ በሳቅ አላሟሟው፤
ያመቃትን ስቃይ ፡ ጠጋ ብዬ አልሰማው

ከድርብርብ ውጥረት
አስሮ ከደበቃት፤
ሽሮ ለመላቀቅ ፡ ቀልዴ ለሚበቃት
ማድያት ሽፍታ ፡
ሲያጨላልም መልኳን፤
ተራራ ሆኖብኝ ፥
"ምነው?" ማለት እንኳን
ፈገግታ እድሜዋን ፡ ጊዜ ሲከረክም፤
የትም እንደማትሄድ ፡ የኔን ብቻ ሳክም
ለእንስፍስፍ አንጀቷ ፡ ላይሆን መቀነቻ
ወኔዬም ፣ ጀብዱዬም ፡
"ወዳታለው" ብቻ።


ይቅርታ.. እማ።

@mikiyas_feyisa
@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

14 Sep, 04:06


...ለምን?
ስለማምን?

ሁሉም
የሚጥለኝ ፤
ድንበር ፡ ስለሌለኝ?

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

09 Sep, 10:33


አንቺ ?
አንቺ እንቁጣጣሽ
ምናባሽ ልትሰሪ መጣሽ?

አሁንም ግፍ አይበቃሽም
ዘንድሮም ለምለም ትያለሽ
ካቀፍሽው ቅጠል ባለፈ
የለመለመ ምን አለሽ?

ካቻምናም አምናም መተሻል
አቅፈንሽ አጥነን ደግሰን
አመትሽ ውበቱ ላይቆይ
እያደር ሊያተራምሰን

አንቺ ?
አንቺ እንቁጣጣሽ
ምናባሽ ልትሰሪ መጣሽ?

አምና ተስፋ አስደረግሺኝ
ደክሜ ቤቴን ሰራሁኝ
አልቅሼ ልገባበት ስል
ይፈርሳል ሁሉ ሰማሁኝ
አሁንም ተስፋ አልቆረጥኩም
ቃልሽን ስመላልሰው
አመትህ ተባርኳል ብለሽ
የላክሺኝ እንደ ሞኝ ሰው
ስታገል ከማይሽር ህይወት
መቀመቅ ነፍሴን ሲውጣት
ወደፊት ፈቀቅ እያልኩኝ
ሞት ልቤን እንዳይለውጣት

"አበባ አየሆሽ" አትበዪኝ
አበባ አልቸገረኝም
ዘፈንሽ አንገሽግሾኛል
ጨዋታሽ አይሰማኝም
በያመት ደምቀሽ ስትመጪ
ህፃን ልጅ ለምትመስዪው
ግጥሙን በምነግርሽ ቃል
ስትዘፍኚ አስተካክዪው

"የሀገሬ ልጆች ውጡ በተራ
ቅስም ሰብሬ ሰው እስክሰራ
እንኳን ሰውና የለኝም እድል
ሁሌ መጣለው አመት ላጎድል
አመት አጉድዬ ስገባ ቤቴ
ደስታ ይሰማታል የእንጀራ እናቴ"
አደዪ
የሞት ጉዳዪ
"ኡኡ" በዪ

እንደዚህ ብለሽ ዝፈኚ
ግጥሙን አስተካክለሽው
በቃ አንቺም እንዳገሬ ሰው
ጊዜን ነው የተማመንሽው?

"ሆ ብለሽ መጣሽ
ሆ ብለሽ
ሆ ብለሽ መጣሽ
ሆ ብለሽ"

ሆሆሆሆ!

አታፍሪም ደግሞ
ልክ እንደ ንፁህ እንዳልበደለ
ተስፋሽ ምስኪኑን እየገደለ
ከዘመን ዘመን ማትለወጪ
ጉድ ያዘለ አመት አቅፈሽ ምትሰጪ
ሆ ብለሽ መጣሽ?
ሆ ብለሽ ውጪ!

ለተድላ ሳይሆን
ለሞት ዋዜማ ፡ እያስጨፈርሺኝ
በመጣሽ ቁጥር
ሆ የምልልሽ ፡ ሞኝ አደረግሺኝ?

አሁን ንገሪኝ
ስለ አመትሽ
ይብስብኛል ወይስ ድናለው?
ዘፈኑን ተዪ ፡ ያንቺን ስሞታ ለምጄዋለው

ባለእንጀሮችሽ በተራ ገቡ
አዝማች አባትሽ ሌላ አገቡ
እንጨቱን ሰብረሽ ቤት እስክትሰሪ
ለእንጀራ እናትሽ ሳትናገሪ
እድጅ አድረሻል ኮከብ ስትቆጥሪ

እኔ ምስኪኑ

ምን ያገባኛል ስላንቺ ኮከብ
ምን ያገባኛል የእንቅልፍሽ ማጠር
የኔ ችግር ነው ወሰን የሌለው
የኔ ስቃይ ነው የማይቆጠር

እህት አበባ ፡ እህት አበባ
እህት አበባ ስትልሽ ከርማ፤
ጥላሽ ብትሄድም በሀምሌ ጭለማ
እኔ ላይ "አዬዬ".. አትበዪብኝ፡
ለኔ አመቱ ነው የጨለመብኝ።

ተይ ባለጊዜ..
ተይ እንቁጣጣሽ..
ሀገር ጉድ አቅፈሽ ፥
ሁሌ እየመጣሽ፦

እንኩ አትበዪን፡

ሀዘን ቁስላችን ፡ ድኖ ሳይገግም፤
ካምናው የሚብስ
ሌላ አዲስ አመት ..አንፈልግም!

@mikiyas_feyisa
@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

08 Sep, 02:43


እግረ መንገድ ህይወት እየገፋው
በሞት ቀራንዮ እያለፍኩኝ ፤
እርቃኑን መስቀል ላይ የሰቀሉት
የቆሰለ ምስኪን ተዋወኩኝ።
ጠራኝ..
የከሰለ ፊቱን ፈገግ አርጎ
ከጎሮሮው ሲቃ እያማጠ፤
ልቤም የሰው ፍቅር የናፈቀው
እንዲሰማው ስሩ ተቀመጠ።

የቆዳው ሰንበሮች ቃል አላቸው
የችንካሩን ጥልቀት ሚዘክሩ
ከደረቀ ስጋው ክራር ሰርቷል
ተገትሮ ያለው ጅማት ክሩ

ከአይኑ ላይ በቀል አልነበረም
ተጎሳቁሎ እንኳን አለው ጸዳል
እንዴት ለገረፉት እጆች ሳይቀር
የሰው ልጅ ምህረት ይማልዳል?

ከፊትለፊት በኩል ተቀምጬ
ስለመስቀል ፍቅሩ እያግባባኝ
የታሪክ ፍሰቱን ተረድቼ
አንድ ነገር ብቻ ግራ ገባኝ
"የአይሁድ ንጉስ ነኝ ስላስባለ
ሊቀ-ካህናቱ ተቆጥተው
ከጌቴ ሴማኒ ቢወስዱትም
የርሱን ደቀ መዝሙር አስጠርተው
ቀድሞ እንደሚከዳው እያወቀ
የህወቱን ድቅድቅ ላበራለት
ለ 30 ዲናር ተስገብግቦ
እንዴት ለሸጠው ሰው ተሳመለት?

የጠቆረ መልኬን አስተውሎ
እንዳይ ገፈፈልኝ የአይኔን ቅርፊት
ከቦታው ላይ ሆኜ አስተዋልኩት
በዳይ ሆኖ ቆሞ ከህዝብ ፊት

ዝም ጭጭ ብሎ እንደ ሌባ
ዳኛው እፊት ቆሞ ሲያከራክር
እንዴት አልበገነም ላንዴም እንኳን
ያዳነው በርሱ ላይ ሲመሰክር
በቀል አይታይም ስቃዩ ውስጥ
ወደ መሰዊያው ጫፍ ሲንቀለቀል
ለወደዱት አይደል እንደ አለም
ለሚሰቅሉት ነበር የሚሰቀል

ሰው አጣሁኝ ብሎ የሚያፅናና
ውስጤ ለቂም በቀል ይሰናዳል፤
የገዳዩን መዳፍ እየሳመ
እርሱ እስከሞት ድረስ ሰው ይወዳል!።

"ማነው ይሄ?" አልኩኝ ተናድጄ
አፌ ለማጉረምረም ተዘጋጅቶ፤
እኔ ለእኔ መኖር ሲከረፋኝ፡
ምን ያደርግለታል ለሰው ሞቶ?
እንኳን ባዳ ቀርቶ የሩቁን ሰው
ያባቱን ልጅ ሳይቀር ለሚከዳ፥
ምንድነው ጥቅሙ የርሱ መሞት
እርቃኑን ተሰቅሎ ምድረበዳ?።

ዝባዝንኬ ኩርቱ የሆንኩት ሰው
መውደድ የገፈፈኝ መደበቄ፣
ፍቅሩ ያሰቀለው እመስቀል ላይ
የቆሰለ ምስኪን ተዋውቄ፤
ገርበብ ያለ በሬን ከፈትኩና
ከሰው መፈቀርን ብጠብቅም፧
የሚጠሉኝንም እስከመውደድ
አልበሰለም ነበር የኔ አቅም።

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

28 Aug, 18:05


አንቺ እንደልማድሽ
ልጥፍ ደረቴ ላይ
እኔም አንቺን ውስድ
ወዲያ ወዲህ ሳላይ
እጆችሽ ከእጆቼ ፡ እንደተቋለፉ
አልባስሽ ከልብሴ ፡እንደተሰፋፉ
ነፍስሽ እና ነፍሴ ፡ እንደተቃቀፉ

ስታዪኝ በስስት ስመልስ በፍቅር
እንደድንገት ያየን ተገትሮ ይቅር።
ምድረ ብቸኛ ሰው
ምድረ ፍቅር አልባ
የኔና ያንቺን ጥምረት
በውበት ተከባ፤
እያየ ይድነቀው በቅናት ይቃጠል
ገላሽን አዝዬ እግርሽ ሲንጠለጠል
እያየ ይቃጠል።

የታባቱን ህዝቡ
የታባቱን ህዝቡ
እንድንለያይ ነው ምኞትና ሀሳቡ።

ነይ እንመርበት
ነይ እንድመቅበት
ሰው ቅናት አለበት

እኛ ብቻ እንሂድ
ሁለቴ ተራምደን አስሬ ስንቆም
ፍቅር ለጠፋበት
መንገድ ለመጠቆም
እኛ ብቻ እንሂድ በባዶው ጎዳና
ቀትር አይበግረን አንፈራ ደመና
እየተሳሳቅን
እየተናፈቅን
አይን እየሰረቅን
ስንላፋ ትንሽ ሲያፈጡብን ብዙ
ድንገት ስንሳሳም ገርሟቸው ሲፈዙ
እኛም ሳናቋርጥ ፍቅርን ስናደራው
በቅናት ሲወድቅ ህዝብ በየተራው

መዋደድ ላይገልፀን
የአለም ቃል ላይበቃን
በቀትር እንዳልዞርን
በሌት እየነቃን

በጨረቃ እኛው
እየተሳሳቅን
በጠዋትም እኛው
ጤዛ እየሰረቅን
በደስታውም እኛው
ተያይዘን ስንጨፍር
በሀዘኑም እኛው
ንፍሮ ስናነፍር

ፍቅር ገንዘብ ሆኖን
የስንቱን አይን ገዛን
"እነዛ" እየተባልን
በስንቱ አፍ በዛን
የጠፋው ስማችን
በቀል ላይመልሰው
በቅናት ላይ ጣድን
ስንቱን ነጠላ ሰው

የታባቱን ህዝቡ ....
የታባቱን ህዝቡ ....!
እንድንጣላ ነው
ምኞት እና ሀሳቡ።

ቢሳካለትና ..
ቢወርድለት ስልጣን፤
"ስታምሩ" ያለን ነው
ሰላም የሚያሳጣን።

አይገርምሽና
ልባቸውን ከፍተሽ ፡ ብታዪ የሁሉን፤
ሊለዩን ጥረዋል
"አይለያቹ" ያሉን!።

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

26 Aug, 01:31


.
.
.
ና አትበዪኝ ~ ምን ሰራለው?
አበሳሽን ፡ አቀላለው?

ና አትበዪኝ ~ ምን ልጠቅምሽ?
ስቃይሽን ፡ እንድደግምሽ?

ና አትበዪኝ ~ አልፈልግም!
ልሰባብርሽ ፡ ደግሞ ዳግም?

© @mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

24 Aug, 07:06


ለደግነቷ ምላሽ
ሳትጠብቅ፤
የልቧን ፍቅር
ካይኗ ሳትደብቅ፤
:
የአንጀቷን ሲቃ
ዜማ ለምቀኝ ፤
ያሳለፍኩትን
ሳትጠይቀኝ።

ፍርሃቴን አስራ
ድሌን ስትፈታ፤
አንዴም ሳትቆጥረው
እንደ ውለታ ።
:
እያሳመምኳት
እያዳነቺኝ፥
እየገፋኋት
እያቀፈቺኝ፤
እሷን የሚመስል ላላገኝ የትም፤
የሚገባትን ፡ አልሰጠዋትም!


@mikiyas_feyisa
@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

22 Aug, 14:36


..
ጭንቀቴ የታል?
የት ገባ?

አንተ ነህ አይደል፡
አባባ?
:
:
ሳልተነትነው፡
መአቴን ፤
እንዴት ሰማኸው፡
ፀሎቴን?።

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

21 Aug, 18:29









ዬኔ .. እኮ

ከጥርስሽ ስር ፥ ማጎብደዴ፤
መች ታውቂያለሽ
እንደበራው፡
ፅልመቴ ላይ .. ስቀሽ አንዴ!


@mikiyas_feyisa
@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

20 Aug, 11:15


ከአብራኳ ፡ በጣር ፡ ተወልጄ
አራዊት ፡ ዱሩን ፡ ተላምጄ
ከአፅናፍ ~ አፅናፍ ፡ ተሳድጄ

አቀበት ፡ ቋቷን ፡ አያለፍኩኝ
ሰርክ በስሟ ፡ እየማልኩኝ
ከደብሯ ስለት ፡ እየጣልኩኝ
በመስኳ ስከንፍ
እንደ ንስር ፤
ፀጋዋን መልመድ
የቁም እስር ፤
ፀጋዋን መራቅ
የቁም እስር፤

የጉርሻ ፍቅሯ
ልቤን አንቆት፤
እህል ስጎርስ
ሁሌ ናፍቆት፤
እህል ስቀምስ
ሁሌ ናፍቆት፤

እኔ ወንበዴ ፡ የደማስቆ
ደሟ ያሰረኝ ፡ እጄን አንቆ
እንደ ኢየሱስ ፡ ሳሳድዳት
የምትማርከኝ ፡ ያለ ጉዳት
ልቤ ሲያማትር ፡ ወዲያ ማዶ
የማትደነግጥ ፡ እንደ መርዶ

ከምድሯ ፡ በቃል ፡ ተፀንሼ
አፈር ፡ ኩበቷን ፡ ቀማምሼ
ከዋርካው ፡ ግርጌ ፡ አስነጥሼ

ክምር ፡ ተራራ ፡ ተንተርሼ
ግምጃዋን ፡ በአደይ ፡ አምነሽንሼ
ያሳር ፡ እትብቷን ፡ በጣጥሼ
ለሰላም ፡ ክብሯ ፡ እየሰጋው
ኤሎሄ ፡ እያልኩ ፡ እያነጋው

መጡና..

ውዳሴ ክብሯን መነጠቁኝ
ለኔ ፡ አደዬን ፡ ሊያሳውቁኝ
እኔን ፡ ከእምዬ ፡ ሊያናንቁኝ

የህዝቤን ክፋት ዘረዘሩ፥
ፀያፍ ሀሜቷን ተናገሩ፤
ዘረኝነቷን አሳበቁ፥
በኩራቷ ላይ ተሳለቁ፤
ቆሻሻ አላት .. ጋ ለ ሞ ታ፤
እድሜዋን ዛሯ ማይፈታ፥
ውርደት አረጓት የፈሪ ሞት፤
ፅላቷን ገፈው ወረቀ ታቦት፣

ምን ላድርግ እኔ
ስለ ስሟ?

ከዙፋን ፡ በግፍ ፡ ተወርውሬ
መቀመቅ ፡ መሃል ፡ ተቀብሬ
በደም ፡ መአበል ፡ ተነክሬ

ጠላት ፡ መርዶዋን ፡ ሲደጋግም
ነጎድጓድ ፡ ድምፁ ፡ ሲያስገመግም
ዝምብዬ ብቻ ፡ ስሯ ላዝግም?

የበታችነት ፡ የታወሰው
መልኳን ሲያጠለሽ ፡ ያገኛት ሰው
እምባዋን ሄጄ ልደባብሰው?

መርቅዞ አድሮ ፡ የሚያምሳት
እግሯን ሲያቃጥል ፡ የጭን እሳት
እይዞን እያልኩኝ ላስለቅሳት?።

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

18 Aug, 09:53


ክፋትን ያለየች ነፍሷ
የአለም ግፍ የተደበቃት
ፈንድቃ ያቀፈችው ሰው
ከምድር ሲጨፈልቃት
..
እንዳትሸሽ በሩ ተዘግቷል
የአቅሟን እየታገለች:
የማን ስም ጠርታ ትታደግ?
እኗቷ ጥላት ሄዳለች።

እንዳትጮህ አሸዋ ጎርሷል
ልጅ አፏ  የሳቀችበት፥
እንዳትሮጥ ተከምሮባት
ተሳቃ  ከቆመችበት፤
ያለአቅም ስቃይ ተግታ
እምባዋ ከአይኗ ሲረግፍ፥
ታላቋን ከማመን ውጪ
ዘመኗን ባልሰራችው ግፍ፤
ስትዳክር አላየቻትም
ለማቀፍ ምትሳሳ እናቷ፥
ብታይ ግን  ሰው ትሆን ነበር?
ደም ሲወርድ ፡ ከሰውነቷ? ።
..
ለእርሷ ነው  አሳር ምትበላው
ከሰው እጅ አልጠበቀችም፤
ኩርፊያዋ ፣ ሳቋ  አልበቃት፡
ምላሷን አልጠገበችም።
..
ቀን ያልፋል  ብላ ስትኖር፡
ሰርክ አዲስ የሚያሳቅቃት፥
ወጥመዱን ችላው ስትገፋ
ክፉ አለም ልጅም ነጠቃት።

ህፃን ነች እቅፍ ማትሞላ
እንደ አራስ ፊቷ ያባባል፤
እንኳንስ የጭንቋ ሲቃ
እምባዋ ከልብ ይገባል፤

አትችልም ቁጣ መቋቋም፡
ፍቅር ነው የተማረችው፥
ተራራ ሚገፋን ጉልበት ፡
በምን ሀይል ተቋቋመችው?።

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

17 Aug, 19:10


-
ጥርስሽ አይደል የሚያስጠላው
አስር ጊዜ አትቦርሺው፤
አይንሽ አይደል የሚያስጠላው
ዙሪያ ኩሉን አታዳርሺው፤
ገላሽ አይደል የሚቀፈው
ነጭ ሎሽን አታብሺው፤
ከናፍርሽ ያምራል እንዲው
እርጥብ ቅባት አታቅምሺው፤
ህሊናሽ ነው የቀፈፈኝ ..
.. ወይራ ነገር አጫጭሺው!

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

16 Aug, 18:25



..ሀዘን እጄን አልመራኝም፥
ሀሴት መንገድ አልጠቆመኝ፤
ጥርሴን ንፋስ አልነካውም፡
ወይም ነፍሴን አላመመኝ፤
ከሀዘን ደስታ ያልተጋባ..
ሳቅም ለቅሶም ያልተባለ፤
በደስታና ሀዘን መሃል፦
ስሜት አልባ ፧ ህይወት አለ።

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

15 Aug, 17:30


ንጉሱ ፡ ክብር ፡ ይገባዋል!

ኢትዮጵያን በክብሯ ያስቀመጠ
ምስቅልቅል ምድሯን የለወጠ
የህዝቧን ወኔ ያነሳሳው
የዘመን ሀረግ የማይረሳው

ንጉሱ ክብር ይገባዋል!

ግምጃዋን በአደይ ያሳመረው
መልኳ ላይ ውበት የጨመረው
የድንግል ክብሯን ብፅዕና
እስከሞት ድረስ የሚያጸና

ንጉሱ ክብር ይገባዋል!

ተባይ ቅሪቷን ያስወገደ
ህዝቦቿን ከልብ የወደደ
ወዳጅ ጠላቷን የለያየ
እንዳትቀጸፍ የፀለየ

ንጉሱ ክብር ይገባዋል!

ወርቅ፣ዝና፣ክብር የማይለውጠው
መልኳን በብርሃን ያንቆጠቆጠው
ልቧ ቢጨልም ግድ የማይሰጠው!

ንጉሱ ክብር ይገባዋል!

ይኸው..
ንጉሱ ክብር ይግባውና ፦

ቤተስኪያን ሳይሆን መዳፍን ሳምን
ሰላም ቅንጦት ነው እድገት አለምን
እንደ ምቀኞች ሳንሞት ጃጀን
ለሬሶች እንኳን ጥላ አበጀን

... ንጉሱ ክብር ይግባውና ፤

ነፃ ሰው ሆንን የማንቀጣ
አንመለስም ከቤት ስንወጣ
የበታች የለም ሆነን የበላይ
ሁሉም መብት አለው
በነፍሳችን ላይ!

... ንጉሱ ክብር ይግባውና ፤

ከጉድ ወተናል ከእንጦሮጦስ
አሰረን እንጂ የነእንትና ጦስ
ብንበደለም በሀይል አንገፋም
ለኛ ብሎ ነው ንጉስ ቢያጠፋም

... ንጉሱ ክብር ይግባውና ፤

ትዕግስት አደለን የመቻል አቅም
አስክሬን ስናይ አንሳቀቅም
የሚሞት ስናይ አንሳቀቅም
አያስፈራንም የለቅሶ ድንኳን
ኢትዮጵያ አይደለን
እየሞትን እንኳን!


@mikiyas_feyisa
@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

14 Aug, 16:57


...
ሲስቁብኝ የነበሩት
ተረባርበው ሲጠይቁኝ፥
ሲያንቋሽሹኝ የነበሩት
ተጸዳድተው ሲጠብቁኝ፤

ክ.ር.ስ.ት.ና.ን ተጣረስኩኝ
ውስጥ ህመሜ ላይነቀል ፤
ቅንጣት ጥቅም ባይጨምርም
ይጣፍጣል ፡ ለካ ፡ በቀል።

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

13 Aug, 10:40


ትወዳለች ለጊዜያት
ጣፋጭ ስሜት ይሰማታል
ውሎ ሲያድር መላመዱ
የእውነት ፍቅር ይመስላታል።

በአጭር ጊዜ ሳታስበው
ሁሉም ነገር ጣራ ይነካል
በመሃል ግን እንዳልነበር
የደራው ቤት ይታወካል

ምን አገኘው ውስጥ ልቧን?
መሃላቸው ምን ጦስ ገባ
መልስ ላይሆን መነፋፈቅ
እርቅ ላይሆን ማውረድ እምባ።
ስታስበው በኋላ ላይ
ስታስበው በረድ ሲል
ያመነችው ሀሰት ነበር
ቁርጥ እውነት የሚመስል

የታወከው ጠርቶ ሲታይ
የጋረዳት ሲያቀረቅር
የተሰማት ኦና ነበር
ያንሳፈፋት ባዶ ፍቅር።

@mikiyas_feyisa

ሚኪያስ ፈይሣ

11 Aug, 18:49


...
ከጎኔ በተቀመጠችበት ደረቴ ላይ ልጥፍ ብላ አብራኝ ልብወለድ የምታነብ ልጅ ነበር የምፈልገው። የኔዋ ግን እንኳን መጽሀፍ ገልጣ ልታነብ ይቅርና የመጽሀፍ መደርደሪያዬን ስትይ እራሱ ወደላይ ሊላት ይደርሳል። በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ የምትስቅ ፣ የምትፍለቀለቅ ፣ ጥርሷን መክደን ነውርን ከመክደን በላይ የሚከብዳትን ልጅ ነበር የምፈልገው። የኔዋ ግን በትንሽ በትልቁ ማኩረፍ ይቀናታል። እዚች ግቢ የማትባል ትንሽዬ ፉገራ እርሾ እንደበዛበት ሊጥ ኩፍ ያደርጋታል።
ከሀገር ሀገር አብራኝ የምትዞረውን ፣ በየጉራንጉሩ ፣ በየጫካው ፣ በየዋሻው ከአጠገቤ የማላጣት ፣ በየህንፃው ጫፍ ፣ በየተራራው አናት ላይ አብራኝ ወደታች የምትመለከተውን ልጅ ነበር የምፈልገው። እርሷ ግን በተቃራኒው ጉዞ የሚባል ነገር አትወድም። መኪና ድምፁን በሰማች ቁጥር ሆዷን ባርባር ይላታል። 150km ተጉዛ ከምታየው ውብ የተፈጥሮ ሀይቅ ውስጥ ከመዋኘት በላይ ሙዚቃ እስከጫፉ በልቅጦ ሻወር መውሰድ ያስደስታታል። ደምጿን እሰማና ለራሴ እገረማለው። የአስቴር አወቀን ዘፈን ረጋ ባለ ድምጿ የምታንጎራጉርልኝን ሴት ነው እስከዛሬ የምስለው። እርሷ ግን ይኸው ከኔ እኩል የአብዱኪያር "መርካቶ ሰፈሬ"ን አብራ እየጮኸች የምትዘፍን ልጅ ሆና አገኘኋት። አሁን አብራኝ ያለችው ልጅ እስከዛሬ እንደምፈልጋት በአይምሮዬ ከሳልኳት ልጅ ጋር በፍፁም አይገናኙም። የኔዋን የበለጠ ወድጃታለው። የማትወደውን ልቦለድ መጽሀፍ በግድ ቁጭ አድርጌ ታሪኩን መተረኩ ደስ ይለኛል። ትንሽዬ ቀልድ ኩፍ የሚያስብላት እሷን ማባበሉን ለምጄዋለው። የአብዱኪያርን ሙሉ አልበም ከእርሱ ድምፅ በላይ በርሷ ድምፅ ለምጄዋለው። እርሷን ትቼ የhawai ደሴቶች ላይ ከምዝናና ይልቅ እርሷን እያየው ዳሎል በእሳት ብቃጠል እመርጣለው። እስከዛሬ በምናቤ ያሰብኳት ልጅ አይደለችም። እርሷ ልጅ እራሷ ብትመጣም እንኳን የእርሷን ቅንጣት ያህል ቦታ አልሰጣትም። የኔዋን አይምሮዬ perfect ብሎ ከፈጠራት ልጅ በላይ ወድጃታለው። ፍቅር ባሰቡት መልክ ሰፍሮ አያውቅም። አስበውት የማውቁትን ተፈጥሮ ለዘመናት ሲጓጉለት ከነበረው ጸባይ በላይ ሊወዱት ይችላሉ።

@mikiyas_feyisa