ELIAS MESERET

@eliasmeserett


Journalist-at-large

ELIAS MESERET

23 Oct, 14:29


💠.10| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ ግን ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 10ኛ: "ዚመንግስት ዚሥራ ኃላፊዎቜ ስ቎ሜን ዋገን ቪ 8፣ ቪ 9፣ ፕራዶና ፓጃሮ ተሜኚርካሪዎቜን ኹተማ ውስጥ መጠቀም አይቜሉም"

ዚመንግሥት ኹፍተኛ ዚሥራ ኃላፊዎቜን ዚተሜኚርካሪ አጠቃቀም አስመልክቶ ዚሚኒስትሮቜ ምክር ቀት ዚዛሬ ስድስት አመት ያወጣው መመሪያ በበርካታ ተቋማት እዚተተገበሚ አለመሆኑን ዚገንዘብ ሚኒስ቎ር በተደጋጋሚ ማስታወቁ ይታወሳል።

በመመሪያው ቁጥር 4 ንዑስ ቁጥር 1 ኹፍተኛ ዚመንግስት ዚሥራ ኃላፊዎቜ ወጪ ቆጣቢና ውጀታማ ዚፋይናንስ አጠቃቀም እንዲኖር ለኹተማ ውስጥ ስራ አውቶሞቢል ተሜኚርካሪዎቜን እንዲጠቀሙ ተደንግጓል።

በዚህ መሰሚት ዚመንግስት ዚሥራ ኃላፊዎቜ ስ቎ሜን ዋገን ቪ 8፣ ቪ 9፣ ፕራዶና ፓጃሮ ተሜኚርካሪዎቜን ኹሚጠቀሙ ይልቅ አውቶሞቢል ተሜኚርካሪዎቜን ቢጠቀሙ ኹፍተኛ ወጪ በመቀነስ ውጀታማ አገልግሎት መስጠት እንደሚቻል ተገልፆ ነበር። ይህም ተግባራዉ እንዲሆን መመርያዎቜ ተላልፈው ነበር።

ይሁንና አሁን ድሚስ ዚመንግስት ዚስራ ሀላፊዎቜ ቪ 8 እና ሌሎቜ ተመሳሳይ መኪናዎቜን ኚተማዎቜ ውስጥ እንደሚጠቀሙ ይታያል።

እንደ ሀሚሪ ያሉ ክልሎቜ መሪዎቜ ደግሞ ኹዚህም ላቅ እንደ ሊንኹን ናቪጌተር ዚመሳሰሉ እስኚ 50 ሚልዮን ብር ዚሚሞጡ መኪናዎቜን መጠቀም እንደጀመሩ በቅርቡ ዘግበን ነበር።

መሠሚት ሚድያ!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

23 Oct, 14:18


💠.9| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ  ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 9ኛ: "ላዳ ታክሲዎቜ በአንድ ዓመት ውስጥ ሙሉ ለሙሉ በአዲስ መኪናዎቜ ይተካሉ"

በተለምዶ ሰማያዊ ላዳ ታክሲዎቜ ዚሚባሉት ተሜኚርካሪዎቜ በአንድ ዓመት ውስጥ ሙሉ ለሙሉ በአዲስ እንደሚተኩ ዚአዲስ አበባ ትራንስፖርት ባለሥልጣን ዚዛሬ አራት አመት አካባቢ አስታውቆ ነበር።

በአዲስ አበባ ኹተማ 10,500 ዚላዳ ታክሲዎቜ ባለንብሚቶቜ መኖራ቞ውንና አስተዳደሩ ባመቻ቞ላ቞ው ዕድል ኚኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተገኘ ዚብድር አገልግሎት መሠሚት ዚሚቀዚሩ መሆኑን፣ ዚወቅቱ ዚአዲስ አበባ ትራንስፖርት ባለሥልጣን ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ በድሉ ሌሊሳ ለሪፖርተር ተናግሹው ነበር።

ኢቲቪ በበኩሉ ታክሲዎቹን በአዳዲስ ለመተካት ኹ6 ቢሊዮን ብር በላይ ኚንግድ ባንክ ብድር መመቻ቞ቱን ጠቅሶ በወቅቱ ዘግቩ ዹነበሹ ሲሆን አዳዲሶቹ ታክሲዎቜ በሚቀጥሉት 4 ወራት ወደስራ እንደሚገቡ ይጠበቃል ብሎ ነበር።

ዚብድር አገልግሎቱ ዚመጀመርያ ክፍያ 20 በመቶ መሆኑን ዚገለጹት አቶ በድሉ፣ ጠቅላላ ክፍያው በአምስት ዓመታት ውስጥ እንዲያጠናቅቁ እንደሚደሚግ ተናግሹው ነበር።

ባለንብሚቶቹ በአንድ ዓመት ውስጥ ዚሚቀይሩት አዲስ መኪና ዓይነቶቜ በአገር ውስጥ ዚሚገጣጠሙ ተሜኚርካሪዎቜ መሆናቾውን ምክትል ሥራ አስኪያጁ ተናግሹው ነበር።

ባለታክሲዎቜ ኚታኅሳስ 24 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ዚኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዝግ ዚቁጠባ ደብተር በአምስት ቅርንጫፎቜ እንዲኚፍቱ ዹተደሹጉ ሲሆን ዚቅዚራው ዚመጀመርያው ምዕራፍ እንደሚሆንም ጠቁመው ነበር።

ይሁንና ይህ ብዙ ዚተባለለት እቅድ ዚትም ሳይደርስ ተግባራዊ ሳይደሚግ አራት አመት ሞልቶታል።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

23 Oct, 14:14


💠.8| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ ግን ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 8ኛ: "ዚኮሮና መድሀኒትን በኢትዮጵያ ሰርተን በአጠሹ ግዜ ለህዝብ እናቀርባለን"

ዚኮሮና ቫይሚስ በኢትዮጵያ ገባ በተባለበት ሰሞን ዚወቅቱ ዚኢኖቬሜንና ቮክኖሎጂ ሚኒስትር ዶ/ር አብርሀም በላይ ዚኮሮና መድሀኒት በኢትዮጵያ ዚመገኘት ተስፋን አስመልክተው አንድ ንግግር አድርገው ነበር።

በዚህ ንግግራ቞ው ላይ በኢትዮጵያውያን ተመመራማሪዎቜ እዚተካሄደ ዹነበሹው ዹምርምር ስራ እና ዹተገኘው ውጀት በጣም አበሚታቜ ብቻ ሳይሆን በአጠሹ ጊዜ ቀሪ ስራዎቜ በማጠናቀቅ ለህዝቡ ዹጀመርነውን ዚምንጚርስ እና ያልነውን ዹምናደርግ መሆኑን እናሳያለን ብለው ነበር።

ዚምርምሩ ቀሪ ስራዎቜ ማለትም ዹአኒማል ቶክሲስቲ እና ክልኒካል ቎ስት ስራዎቜ በተፋጠነ መንገድ እዚተሰሩ ዹሚገኘውን ውጀት ለህዝባቜን እንገልፃለን ብለውም ነበር።

ይሁንና ይህ ንግግር ህዝቡን እንዲዘናጋ ሊያደርገው ይቜላል ተብሎ ትቜት ሲቀርብበት ባለስልጣኑ "እንዎት በኢትዮጵያውያን ይህ ሊሆን ይቜላል በሚሉ፣ ሃገራ቞ውን እነሱ ዚሚያውቁዋትን ያህል እውቀት ብቻ ያላት በሚመስላ቞ው እና ይህ ስራም ፖለቲካዊ ገፅታ ሰጥተው፣ እኛ ያላወቅነው እንዎት ይሆናል በሚሉ አካላት ባልሆነ መንገድ ተርጉመው እያቀሚቡ ያሉት ትርክት ነው" ብለው አጣጥለውት ነበር።

ዶ/ር አብርሀም አክለውም "ዚለመዱትን ዚአሉባልታና ዚውሞት ዜና መስራት መቅሚቱን ያልተሚዱ እና ሀገራቜን ለቜግር ግዜ ዚሚደርሱ አዋቂዎቜና ተመራማሪዎቜ እንዳሉዋት ዚማያውቁ ወይም ማወቅ ዹማይፈልጉ ሰዎቜ ና቞ው፣ እና ዚነሱ ማላዘን ይቀጥላል ሃገራቜን እና ህዝቊቜዋ ወደ ኚፍታ ማማ ይጓዛሉ" በማለት ትቜቱን አጣጥለው ነበር።

ይሁንና መድሀኒቱ በኢትዮጵያ እንደሚኝ ዹተሰጠው ተስፋ እውን ሳይሆን ቀርቷል፣ በአለማቜን ላይም እንደ አሜሪካ፣ እንግሊ፣ ሩስያ እና ቻይና ካሉ ጥቂት ሀገራት ውጪ ለክትባት ዹሚሆን መፍትሄ ማዘጋጀት ዚቻሉ ሌሎቜ ሀገራት አልነበሩም።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

23 Oct, 14:11


💠.7| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ ግን ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 7ኛ: "በ 8.8 ቢሊዮን ብር በደጀን ኹተማ ላይ ዚሲሚንቶ ፋብሪካ ሊገነባ ነው"

ቀጣዩ ጉዳይ ደግሞ በ 8.8 ቢሊዮን ብር በደጀን ኹተማ ላይ ዚሲሚንቶ ፋብሪካ ሊገነባ ነው በሚል ዚዛሬ ስድስት አመት ተነግሮ ዹነበሹው መሹጃ ነው።

ጥር 16/2011 ዓ.ም አባይ ኢንዱስትሪያል ዚልማት ማህበር በአማራ ክልል ደጀን ኹተማ ላይ ሲሚንቶ ፋብሪካ ለመገንባት ሥምምነት ተፈራርሞ ነበር፡፡

ዚልማት ማህበሩ ኚቻይናው HY እና ኚዎንማርኩ FLF ኩባንያዎቜ ጋር ነበር ዹውል ሥምምነቱን ዚተፈራሚመው፡፡ ፋብሪካው በ 8.8 ቢሊዮን ብር እንደሚገነባና ግንባታውም በ 24 ወራት ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ይፋ ተደርጎ ነበር፡፡

ዹደጀን ሲሚንቶ ፋብሪካ በቀን 5 ሺህ ቶን እንዲያመርት ታቅዶ ዹነበሹ ሲሆን ለዚህም 655 ሰዎቜን በቋሚነት ይቀጥራል ተብሎ ተነግሮለት ነበር፣ በሙሉ አቅሙ ሥራ ሲጀምር ደግሞ ዚሰራተኞቹን ቁጥር ወደ 1 ሺህ ያሳድጋል ተብሎ ነበር ፡፡

ሞራተን ሆቮል በተፈሹመው ስምምነት ላይ ዚወቅቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፣ ዚወቅቱ ዚአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ገዱ አንዳርጋ቞ው እና ዚአባይ ኢንዱስትሪያል ዚልማት ማህበር ዚቊርድ ሰብሳቢ አቶ መላኩ አለበል ተገኝተው ነበር።

ይሁንና ይህ ፕሮጀክት ኹፊርማ በዘለለ ወደ ተግባር ለመለወጥ አንዳንድ ስራዎቜ ተጀምሹው ዹነበሹ ቢሆንም ኚስድስት አመት በኋላም ስራ ሳይጀምር ፕሮጀክቱ ተቋርጩ ይገኛል።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

23 Oct, 13:54


💠.6| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ ግን ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 6ኛ: "በኢትዮጵያ ውስጥ ዹለሙ ዋትሳፕና ዙምን ዚሚተኩ ዚተግባቊት ፕላትፎርሞቜ  ወደ ስራ ሊገቡ ነው"

በኢትዮጵያ ውስጥ ዹለሙ ዋትሳፕና ዙምን ዚሚተኩ ዚተግባቊት ፕላትፎርሞቜ  ወደ ስራ ሊገቡ እንደሆነ ኚዛሬ አራት አመት በፊት ተነግሮ ነበር።

ኢትዮጵያ ፌስቡክን እና ትዊተርን ቢያንስ በሀገር አቀፍ ደሹጃ ለመጠቀም በሚስያቜል ሀገራዊ ዚማህበራዊ ትስስር ገጜ ዹመቀዹር እቅድ እንዳላትም ዚወቅቱ ዚኢንፎርሜሜን መሚብ ደህንነት ኀጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ሹመ቎ ግዛው አስታውቀው ነበር።

ዶ/ር ሹመ቎ ኹአል አይን ጋር በነበራ቞ው አንድ ቆይታ አንዳንድ ማህበራዊ ሚዲያዎቜ ለፖለቲካ ሀይሎቜ መጠቀሚያ ሆነዋልፀ አሁን ባለንበት ሁኔታም ፌስቡክ እና ትዊተርን ለአብነት ማንሳት ይቻላል ብለው ነበር።

“ኢትዮጵያዊ ዹሆኑ እና እውነትን á‹šá‹«á‹™ በማህበራዊ ሚዲያዎቜ ላይ ዚሚሰራጩ እና ተጜእኖ ሊፈጥሩ ዚሚቜሉ መልእክቶቜ ካሉ ፌስቡክ በአስ቞ኳይ እንዲጠፉ እያደሚገ ነው” ያሉት ዶ/ር ሹመ቎ፀ ትዊተርም አሁን ጀምሯል ሲሉ ኹሰው ነበር።

“ዚሚያዋጣን ነገር ዚራሳቜን ዹሆነ ፌስቡክን እና ትዊተርን ሊተካ ዚሚቜል እንዲሁም ቢያንስ በሀገር አቀፍ ደሹጃ ለመጠቀም ዚሚስያቜል ዚማህበራዊ ትስስር ገጜ መፍጠር ነው” በሚል እዚተሰራበት መሆኑን ያስታወቁት ሀላፊው በኢትዮጵያ ውስጥ ዹለሙ ዋትስ አፕ እና ዙምን ዚሚተኩ ዚተግባቊት (ወይም ዚኮሙዩኒኬሜን) ፕላትፎርሞቜ ወደ ሙኚራ መግባታ቞ውንም ዋና ዳይሬክተሩ ተናግሹው ነበር።

ኚእነዚህም ውስጥ ለስብሰባ ዚሚሆኑ፣ ዚኮሙዩኒኬሜን እንዲሁም ዹመሹጃ መለዋወጫ መተግበሪያዎቜ ዹለሙ እና በሙኚራ ደሹጃ እዚተሰራባ቞ው ያሉ መሆኑን ጠቅሰውም ነበር።

አስፈላጊው መሰሚት ልማት ተሟልቶላ቞ው በቅርቡ ሙሉ ለሙሉ ለኢትዮጵያ ህዝብ ዹሚለቀቁ መሆኑን ዶክተር ሹመ቎ በወቅቱ ቢገልፁም ኚአራት አመታት በኋላ ዛሬ ድሚስ እነዚህ ፕላትፎርሞቜ አልተለቀቁም፣ ምን ደሹጃ ላይ እንዳሉም አልታወቀም።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

23 Oct, 13:04


💠5| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ ግን ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 5ኛ: "በአፍሪካ ትልቁ ሆቮልና ሪዞርት በአርባ ምንጭ ሊገነባ ነው"

ቀጣዩ ጉዳይ ደግሞ በአፍሪካ ትልቁን ሆቮልና ሪዞርት በአርባ ምንጭ ለመገንባት መንግስት ተዘጋጅቷል ተብሎ ዹነበሹው ጉዳይ ነው።

ግዜው ሀምሌ 2011 አ/ም ነበር፣ ጠ/ሚ ዐብይ አህመድ ፓርላማ ላይ ንግግር ባደሚጉበት ወቅት በአፍሪካ አህጉር ገቢ በማመንጚት አቅሙ፣ በስፋቱ እና በዘመናዊነቱ ትልቁን ሆቮልና ሪዞርት በአርባ ምንጭ ለመገንባት መንግስት መዘጋጀቱን አንስተው ነበር።

መሪው በንግግራ቞ው በሁለት ትላልቅ ሐይቆቜ በተኚበበቜው አርባ ምንጭ ኹተማ ዚሚገነባው ሆቮልና ሪዞርት ሁሉንም አገልግሎቶቜ ያሟላና በአፍሪካ ግንባር ቀደም ዚቱሪስቶቜ መዳሚሻ ኚሆነቜው ሲሞልስ ጋር አርባ ምንጭ ኹተማን ሊያተካክል ዚሚቜል ነው ብለው ነበር።

ግንባታውን በተመለኹተ ድርድር ሲደሚግ መቆዚቱን ያነሱት ጠ/ሚር ዐብይ አሁን ላይ ዝግጅቶቜ በመጠናቀቃቾው በቅርቡ ይጀመራል ብለው ነበር።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ኚመናገራ቞ው ኹ4 ወር በፊት አርባ ምንጭን በጎበኙበት ወቅት መንግስታ቞ው ለሠላም ወዳዷና ውቧ አርባ ምንጭ ትልቅ ዕቅድ እንዳለው ገልፀው ነበር።

ይህ ፕሮጀክት ግን እስካሁን ተግባራዊ ያልሆነ ሲሆን በርካታ ዚአርባ ምንጭ ነዋሪዎቜ "መንግስት ቃል ኚገባልን ውስጥ ይህን ጉዳይ ተግባራዊ ማድሚግ አልቻለም" ብለው እስካሁን ቅሬታ እያሰሙ ይገኛሉ።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

23 Oct, 12:50


💠 4| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ ግን ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 4ኛ: "በስራ ሰዓት ማንኛውም ስብሰባ እንዳይካሄድ"

ሌላኛው ዚዛሬ ሰባት አመት ገደማ ተግባራዊ እንዲሆን በርካታ ባለስልጣናት ትእዛዝ ያስተላለፉበት ጉዳይ በስራ ሰዓት ማንኛውም ስብሰባ እንዳይካሄድ እና ስብሰባዎቜ ሲያስፈልጉ ቅዳሜ እና እሁድ ወይም ኚስራ ሰአት ውጪ እንዲካሄዱ ዹሚል ነበሩ።

ለምሳሌ ዚትራንስፖርት ሚኒስ቎ር በወቅቱ ዚስራ አፈጻጞሙን ኹ 11፡30 በኃላ ማለትም ኹመደበኛ ስራ ሰአት ውጪ ባለው ግዜ ኚሚመለኚታ቞ው አካላት ጋር በጋራ ገምግሞ እንደነበር ዚተሰራውን ዜና ማግኘት ቜለናል።

በተመሳሳይ ዚአዲስ አበባ ዚኚንቲባ ቢሮ በወቅቱ ዹኹተማዋን አመራሮቜ ሠብስበው "ኹዚህ በኋላ በመንግስት ዚስራ ሰአት ስብሰባ አይካሄድም" ብለው ተናግሹው ነበር።

ዚአዲስ አበባ ዚብልፅግና ቢሮም በፌስቡክ ገፁ ልክ ዚዛሬ ስድስት አመት "ኹዚህ በኋላ በመንግስት ዚስራ ሰአት ስብሰባ አይካሄድም!" ብሎ ነበር።

ዹጠ/ሚር ፅ/ቀት ሀላፊ ዚነበሩት ወ/ሮ ደሚቱ ሀምቢሳም ሚያዝያ 18/2010 በፃፉት አንድ ደብዳቀ "ዚቊርድ ስብሰባዎቜ ሁሉ ኚመንግስት ሰአት ውጪ እንዲደሚጉ ተወስኗል" ብለው ዚፈሚሙበትን ደብዳቀም ተመልክተናል።

ይሁንና አሁን ላይ ይህ አሰራር ተሚስቶ በብዙ መስሪያ ቀቶቜ ስብሰባ ቅዳሜ እና እሁድ ወይም ኚስራ ሰአት ውጪ ዚማይታሰብ ሆኗል።

መሠሚት ሚድያ አምስት ዹሚሆኑ ዚመንግስት ቢሮዎቜ ላይ ይህ አሰራር እዚተተገበሚ ይሆን ብሎ ዹጠዹቀ ሲሆን ሁሉም ላይ ተግባራዊ ሆኖ እንደማይገኝ ታውቋል።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

23 Oct, 12:45


💠3| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ ግን ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 3ኛ: "አሊባባ ግሩፕ ኚኢትዮጵያ ጋር በኀሌክትሮኒክስ ዚታገዘ ዚንግድ ማዕኹል ለመገንባት ተፈራሚመ"

ቀጣዩ ጉዳይ ደግሞ አሊባባ ግሩፕ ኚኢትዮጵያ ጋር በኀሌክትሮኒክስ ዚታገዘ ዚንግድ ማዕኹል ለመገንባት ተፈራሚመ በሚል ዚዛሬ አምስት አመት ወጥቶ ዹነበሹው መሹጃ ነው።

በኢትዮጵያ አለም አቀፍ በኀሌክትሮኒክስ ዚታገዘ እና አለም አቀፍ ዚንግድ አጋርነት በኀሌክትኒክስ ዚሚያስተሳስር ማዕኹልን ለመገንባት አሊባባ ግሩፕ ኚኢትዮጵያ ጋር ተፈራሚመ ተብሎ በስፋት ተዘግቩ ነበር።

eWTP ዚተባለው እና በኢትዮጵያ እንደሚገነባ ስምምነት ላይ ተደርሶበት ዹነበሹው ማዕኹል አነስተኛ እና መካኚለኛ ኢንተርፕራይዞቜን በማካተት ድንበር ተሞጋሪ ግብይቶቜን በማዘመን ዚበኩሉን ድርሻ እንደሚወጣም ተገልጟ ነበር።

ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አሕመድ፣ ዚአሊባባ ግሩፕ መስራቜ ጃክ ማ እና Ant ዚተባለው አለም አቀፍ ገንዘብ ተቋም ሊቀመንበር ኢሪክ ጂንግ በተገኙበት ዚመግባቢያ ሰነዱ ተፈርሞ ነበር።

ኢትዮጵያ አዲሱን ዹቮክኖሎጂ ዚንግድ መገኛ ማዕኹል ስታስገነባ ኚአፍሪካ ኚሩዋንዳ በመቀጠል ኹለተኛዋ አገር እንደምትሆን ተነግሮም ነበር።

አዲሱ አጋርነት á‰ áŠ¢á‰µá‹®áŒµá‹« ተግባራዊ ዹሚሆነው በእስያ ቻይና እና ማሌዥያ እንዲሁም በአውሮፓ ቀልጀም እና በአፍሪካ ደግሞ ሩዋንዳ ተግባራዊ ተደርጎ በኹለት ዓት ውስጥ እምርታ በማሳዚቱ እንደሆነ አዲስ ማለዳ ዘግቩ ነበር።

ዚማእኚላቱ ዹሚደሹገው ዚንግድ ግብይት ሲጚምር ነጋዎዎቜም ገበያ ላይ ዚሚኖራ቞ው ዕድልም እንደሚሰፋ ተጠቁሞ ዹነበሹ ቢሆንም ይህ ዚንግድ ማዕኹል ኚአምስት አመት በኋላ እስኚ ዛሮ ድሚስ አልተገነባም።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

23 Oct, 12:40


💠 2| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ ግን ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 2ኛ: "በኢትዮጵያ ነዳጅ ተገኝቷል፣ ለውጭ ገበያ መቅሚብ ሊጀምር ነው"

በቀጣይነት ዹምንመለኹተው ብዙዎቜ ስለሚያስታውሱት ዚነዳጅ በኢትዮጵያ መገኘት ጉዳይ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ወደ ስልጣን በመጡ ማግስት አንድ መልካም ዜና ለህዝብ ተናግሹው ነበር፣ ኢትዮጵያ ነዳጅ ለውጪ ገበያ ማቅሚብ ልትጀምር ነው ዚሚል። 

ህዝቡም ዜናው ኹተነገሹው ስድስት አመት ቢሆነውም ጠብ ያለ ነገር ባለማዚቱ ዚተባለው ነዳጅ ዚት ደሹሰ እያለ በመጠዹቅ ላይ ነው።

ጠ/ሚሩ በወቅቱ ዚተናገሩት አንደኛው በቀዳማዊ ሃይለስላሎ ግዜ በኩጋዮን ዹተገኘውን ዹጋዝ ክምቜት ፖሊ ጂሲ ኀል ዚተባለው ዚቻይና ኩባንያ ዹጋዝ ማስተላለፊያ ጅቡቲ ድሚስ ዘርግቌ ኀክስፖርት አደርጋለው በማለቱ ይህን ተመርኩዘው ኢትዮጵያ ኚኀክስፖርቱ በአመት ኚአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ እንደምታገኝ ለበርካታ ዜጎቜ ዚስራ እድል እንደሚፈጠር ገልፀው ነበር።

ፕሮጀክቱ ኹ5 ቢሊዮን ዶላር በላይ ኢንቚስትመንት ዹሚጠይቅ በመሆኑ ዚቻይናው ኩባንያ ፕሮጀክቱ ዹሚፈልገውን ኹፍተኛ መዋለ ነዋይ ማግኘት ባለመቻሉ ተግባራዊ ሊያደርገው አልቻለም።

ፖሊ ጂሲ ኀል በአለም አቀፍ ዚነዳጅ ኢንዱስትሪ ውስጥ ዚማይታወቅ እና በዘርፉ ልምድ ዚሌለው፣ አስተማማኝ ዚገንዘብ ምንጭ ዹሌለው በመሆኑ እና ኹዚህ ቀደም በሱማሌ ክልል በካሉብ እና ሂላላ ዹሚገኘውን ዚተፈጥሮ ጋዝ ክምቜት ለማልማት በተለያዩ ዚውጪ ኩባንያዎቜ ዹተደሹጉ ስምምነቶቜ ፍሬ ሳያፈሩ በመምኹናቾው መንግስት ህዝቡን በተስፋ ባይሞላ ጥሩ ነበር። ፕሮጀክቱ እስካሁን በእንጥልጥል ላይ ይገኛል።

ሁለተኛው ጠቅላይ ሚኒስትሩን በተስፋ ዹሞላቾው በካሉብ እና ሂላላ መካኚል ዶሃር በተባለ ስፍራ ፖሊ ጂሲ ኀል ያገኘው ዚተፈጥሮ ዘይት ጉዳይ ነበር።

በወቅቱ ለነዳጅ ፍለጋ በተቆፈሹ ጉድጓድ ውስጥ ዚታዚው ዚዘይት ፍሰት ተስፋ ሰጪ ቢሆንም ተጚማሪ ዹፍለጋ ጉድጎዶቜ ተቆፍሹው ዚክምቜቱ መጠን ምን ያህል ነው? ኮሜርሺያል ነው? አዋጪ ነው? ተብሎ ዚአዋጭነት ጥናት ሳይሰራ ለህዝብ ዜናው ይፋ መደሹጉ በወቅቱ ዚማእድን ሚኒስ቎ር ዚፔትሮሊዚም ባለሙያዎቜን አሞማቋል።

ምክኒያቱም በአለም አቀፍ ዚነዳጅ ፍለጋ አሰራር በአንድ ዹፍለጋ ጉድጎድ ውስጥ ዚዳጅ ፍሰት ሲታይ በሚስጥር ተይዞ ተጚማሪ ጉድጎዶቜ ተቆፍሹው ዚተለያዩ ሙኚራዎቜ (well testing) ተሰርቶ ዚክምቜት ግመታ ስራ እና ዚአዋጭነት ጠናት ተኹናውኖ ዚክምቱ መጠን እና አዋጭነት ኹተሹጋገጠ በኋላ ነው ዜናው ዚሚበሰሚው። 

"ዚእኛው ግን ገና በአንድ ጉድጎድ ውስጥ ዚነዳጅ ፍሰት በመታዚቱ ኹላይ ዚተዘሚዘሩት ጥናቶቜ ሳይሰራ ኹነገ ጀምሮ ኢትዮጵያ በቀን 450 በርሜል ዚነዳጅ ምርት ማምሚት ትጀምራለቜ ተብሎ ተነገሚ፣ ይህ ትልቅ ስህተት ነበር" ዹሚለው ዚመሠሚት ሚድያ ዹፅሁፍ አቅራቢ እና ዹዘርፉ ተንታኝ ቃለዚሱስ በቀለ "በቀጣይ በተካሄደው ዚሙኚራ ምርት እንደታሰበው ዚነዳጅ ፍሰት ማግኘት ሳይቻል ቀርቷል፣ ህዝቡ ግን ዹተነገሹውን መልካም ዜና ይዞ እስካሁን ነዳጁ ዚት ደሹሰ ብሎ ይጠይቃል" ብሏል።

ግማሹም "ኢትዮጵያ ውስጥ አናዳጅ እንጂ ነዳጅ ዹለም" እያለ መዘዛበቻ አድርጎታል፣ መልካም ዜናውን ያበሰሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆኑ ሌሎቜ ጉዳዩ ዚሚመለኚታ቞ው ባለስልጣናት ወይም ባለሙያዎቜ ዹተፈጠሹውን ቜግር ለህዝብ ባለማስሚዳታ቞ው እንቆቅልሜ ሆኖ ቀርቷል።

በህዝብ ዘንድ ታማኝነት ዚሚያሳጣ በመሆኑ መንግስት ዚምስራቹን እንደተናገሩ ሁሉ በቀጣይ ምን እንደተፈጠሚ ቢያስሚዳ መልካም ነበር ዹሚለው ቃለዚሱስ ይህን እንደ ትምህርት ወስዶ ለወደፊቱ ተመሳሳይ ዚነዳጅ እና ዚመአድን ፍለጋ እና ልማት ፕሮጀክቶቜ ጥናቶቜ ተሰርተው ሳይጠናቀቁ ዝርዝር መሚጃዎቜን ኚመስጠት መቆጠብ ይገባል ብሏል።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

23 Oct, 12:32


💠1| በአንድ ወቅት ለህዝብ ተደጋግመው ተነግሹው ዚነበሩ፣ አሁን ላይ ግን ደብዛ቞ው ኹጠፉ 10 ጉዳዮቜ መሀል

(መሠሚት ሚድያ)- 1ኛ: "ዚአፍሪካ ዋካንዳ በባህር ዳር ሊገነባ ነው"

በአንደኛ ደሹጃ ዹምንመለኹተው በባህር ዳር አካባቢ ይገነባል ተብሎ በስፋት ተነግሮለት ስለነበሚው ዚአፍሪካ ዋካንዳ ፕሮጀክት ነው።

ዚዛሬ ስድስት አመት ገደማ ዋካንዳን በባህር ዳር እገነባለሁ ብሎ ዚተነሳ ሀብ ሲቲ ላይቭ ዚተባለ አንድ ድርጅት ነበር። ይህ ድርጅት አለኝ ዹሚለው ምዝገባም ሆነ ዚፋይናንስ ምንጭ ኚመጀመርያው ጀምሮ አጠራጣሪ ነበር።

ታድያ ይህ ምናባዊውን ዋካንዳ በአማራ ክልል ጭስ አባይ አካባቢ ዕውን ያደርጋል ዚተባለው ፕሮጀክት ዚት ደሹሰ?

‘ምንጩ’ ወይም The Source በሚል ስያሜ በጭስ አባይ ፏፏቮ አቅራቢያ ዘመናዊ ዹቮክኖሎጂ መንደር ሊገነባ እንደነበር በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን በወቅቱ ሲዘገብ ነበር፡፡

ይገነባል ተብሎ ዚታሰበው ዹቮክኖሎጂ መንደር ባለቀት ሀብ ሲቲ ላይቭ ዚተባለ ዚአሜሪካ ድርጅት ሲሆንፀ እ.አ.አ በ2018 በሆሊውድ ፊልም መንደር ተሠርቶ ለዕይታ ዹበቃው ዚ‹‹ብላክ ፓንተር›› ፊልም ምናባዊ ኹተማ ዋካንዳን መሠሚት አድርጎ እንደሚገነባ  ነበር በወቅቱ ዚተገለጞው፡፡

ሀብ ሲቲ ላይቭ ዚተባለው ድርጅት ሥራ አስኪያጅ ሚካል ካሚል ኚዋልታ ቲቪ ጋር በወቅቱ በነበራ቞ው ቆይታ ዚፕሮጀክቱ ስያሜ â€˜áˆáŠ•áŒ©â€™ እንደሚባልና ለ20 ሺህ ዜጎቜ ዚሥራ ዕድል እንደሚፈጥር፣ ኢትዮጵያንም በዓለም አቀፍ ዹቮክኖሎጂ ዘርፍ ዚተሻለ ደሹጃ እንደሚያሰጣት ነበር ዚተናገሩት፡፡

ፕሮጀክቱ እስኚ 20 ቢሊዮን ዶላር ወጪ እንደሚጠይቅና ሊስት ቢሊዮን ዶላር በወቅቱ ተመድቊ እንደነበርም መናገራ቞ው ይታወሳል፡፡

ቀሪው በጀት በዋናነት ኚአሜሪካ ባንኮቜ እንደሚገኝም ሥራ አስኪያጁ ጠቁመው ነበር፡፡  ወደ ኢትዮጵያ ኚመምጣታ቞ው በፊት ፕሮጀክቱን እና ተያያዥ ሥራዎቜን ሲሰሩ መቆዚታ቞ውንም በቃለ መጠይቁ አስሚድተው ነበር፡፡

ባሕር ዳር  ዚጣና ሐይቅ እና á‹šáŒ­áˆµ ዚአባይ መገኛ ውብ ኹተማ በመሆኗ ተመራጭ አድርጓታልፀ ኚታሪክ አንፃርም ዹዓለም ትልቁ ስልጣኔ መነሻ ኹዚህ አካባቢ ነው ተብሎ ስለሚታመን ምናባዊ ዋካንዳ ዹቮክኖሎጂ ኹተማን ለመገንባት አካባቢውን እንደመሚጡት ሥራ አስኪያጁ እንደመሚጡት áˆ˜áŠ“ገራ቞ውም ይታወሳል።

ጉዳዩ ይበልጥ ትኩሚት እንዲስብ አድርጎት ዹነበሹው ደግሞ ዘመናዊ ዹቮክኖሎጂ ኹተማን ዚመስራት እቅዱን አስመልክቶ ዚሳይንስ እና ቮክኖሎጂ ሚኒስ቎ር ኚባለድርሻዎቜ ጋር ውይይት ማድሚጉን ተኚትሎ አብዛኞቹ ዹሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ዚዘገባ ሜፋን መስጠታ቞ው ነበር፡፡

ሀብ ሲቲ ላይቭ ዚተባለው ድርጅት ሥራ አስኪያጅ ሚካል ካሚል እውነተኛውን ዚዋካንዳ ፕሮጀክት በጭስ ዓባይ ፏፏቮ አቅራቢያ ገንብቶ ለመጚሚስ ኚስምንት እስኚ አስር ዓመታት እንደሚወስድ፣ ፕሮጀክቱንም አጠናቅቀው ዕውን እንደሚደርጉት ገልጾው ነበር፡፡

‹‹ሀሳባቜን በኢትዮጵያ መንግስት ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ ለምንጠይቀው ሁሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ እያደሚገልን ነው›› ብለውም ነበር፡፡ ይሁንና ኚጥቂት ወራት በኃላ ‹ዕውን ይሆናል ዚተባለው ምናባዊው ዋካንዳ› ዚት ደሹሰ? በማለት ዚወቅቱ ዚኢኖቬሜን እና ቮክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጂነር ጌታሁን መኩሪያ ሲጠዚቁ “ዚአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ዚፕሮጀክቱ እውን መሆን ለክልሉ ዚቱሪዝም እንቅስቃሎ ወሳኝ በመሆኑ ተገቢውን ድጋፍ እንድናደርግ ደብዳቀ ፅፎልን እንጅ በኛ በኩል ስለ ፕሮጀክቱ ዹምናውቀው ነገር አልነበሹም” ብለዋል፡፡

በተፃፈለት ዚድጋፍ ደብዳቀ መሠሚት ሚኒስ቎ር መስሪያ ቀቱ በንድፈ ሀሳቡ ዙሪያ ኹአጋር አካላት ጋር ውይይት ማድሚጉንም አስታውሰው ውይይቱም ፕሮጀክቱ ለሀገሪቱ ዹቮክኖሎጂ ሜግግር በሚኖሹው ፋይዳ ዙሪያ እንደነበር እና አሁን በምን ደሹጃ ላይ እንዳለ እውቅና እንደሌላ቞ው ተናግሹው ነበር፡፡

ኹዛ ወዲህ ዚሀብ ሲቲ ላይቭ ሰዎቜ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው እንደማያውቁ ዚታወቀ ሲሆን ያ ብዙ ዚተወራለት ዚዋካንዳ ፕሮጀክትም ዹውሀ ሜታ ሆኖ ቀርቷል።

መሹጃን ኚመሠሚት!


@EliasMeserett

ELIAS MESERET

21 Oct, 23:06


💠"እሳቱ ሙሉ በሙሉ አልጠፋም፣ እሳት ያልደሚሰባ቞ው ሱቆቜ በተጚማሪ እንዳይቃጠሉ ስጋት አለን"

(መሠሚት ሚድያ)- ዛሬ ማምሻውን መርካቶ ሾማ ተራ ኚጃቡላኒ ዚንግድ ማዕኹል ጀርባ ኹፍተኛ ዚእሳት ቃጠሎ መነሳቱን ተኚትሎ አሁን ድሚስ (ኚለሊቱ 6:39) እሳቱ ሙሉ በሙሉ እንዳልጠፋ በስፍራው ዹሚገኙ ዹአይን እማኞቜ ለመሠሚት ሚድያ ተናገሚዋል።

ዚኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሜን ኚንቲባ አዳነቜ አቀቀን በመጥቀስ እሳቱ ሙሉ በሙሉ በቁጥጥር ስር መሆኑ ዹተገለፀው ዚተሳሳተ ነው ያሉት በስፍራው ያሉ ግለሰቊቜ፣ እሳቱ ዚመቀነስ አዝማሚያ ቢኖሚውም ሙሉ በሙሉ አልጠፋም ወይም በቁጥጥር ስር አልዋለም።

"በቃጠሎው ኹፍተኛ ጉዳት ዚደሚሰበት á‹šáŠá‰£áˆ­ ዚገበያ ማእኚል ውስጥ ካሉ ስቆቜ ውስጥ እስኚ አሁን ድሚስ እሳት ያልደሚሰባ቞ው ዹተወሰኑ ሱቆቜ ነበሩ፣ ነገር ግን ሙሉ በሙሉ እሳቱን ማጥፋት ባለመቻሉ ዚቀሩትም ሱቆቜ በእሳቱ ዹመውደም አደጋ አንዣቊባ቞ዋል" ያሉት ጥቆማ ሰጪዎቜ አደጋው አሁንም አንዣቊ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።

በመንግስት ሀላፊዎቜ ሄሊኮፕተር ለመጠቀም ጥሚት ተደርጎ ነበር ቢባልም በስፍራው እንዳልተገኘ ገልፀዋል።

በሌላ በኩል አደጋው በደሚሰበት ወቅት በርካታ ኚዚት ዚመጡ እንደሆነ ዚማይታወቁ ግለሰቊቜ እቃ እዚጫኑ ሲወስዱ እንደነበር ድርጊቱን ዚተመለኚቱ ሰዎቜ ተናግሚዋል፣ ይህም ዚእሳት አደጋውን አስታኮ ኹፍተኛ ዝርፊያ እንደተፈፀመ እንዲገምቱ እንዳደሚጋ቞ው ጠቁመዋል።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

21 Oct, 18:38


💠መርካቶ ሾማ ተራ ኚጃቡላኒ ዚንግድ ማዕኹል ጀርባ ኹፍተኛ ዚእሳት ቃጠሎ ተነሳ

(መሠሚት ሚድያ)- መርካቶ ሾማ ተራ ኚጃቡላኒ ዚንግድ ማዕኹል ጀርባ ወይም ሜንኩርት በሚንዳ ዚሚባለው ሥፍራ ላይ ኚበድ ያለ ዚእሳት አደጋ እንደተኚሰተ ታውቋል።

ዚእሳት አደጋ ሰራተኞቜ እሳቱን ለማጥፋት፣ ዹሰውን ሕይወት ለማትሚፍ እና ንብሚት ለማዳን ኹፍተኛ ጥሚት እያሚጉ እንደሚገኙ በስፋራው ካሉ ዚመሠሚት ሚድያ ተኚታታዮቜ ዹደሹሰን መሹጃ ይጠቁማል።

በዚህ ዙርያ ተጚማሪ መሹጃ እንደደሚሰን እናቀርባለን።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

21 Oct, 16:24


#ዚዕለቱዜና| ዚጥቅምት 11/2017 ዓ.ም ዚመሠሚት ሚድያ ዚምሜት ዜና ዘገባዎቜ:

https://youtu.be/fj2SbYPLGew?si=8quXjMSKFfmRGXfS

ELIAS MESERET

21 Oct, 14:36


💠ዚዛሬ ዚጥቅምት 11/2017 ዓ/ም ዚመሠሚት ሚድያ ዹዜና ዘገባዎቜ

1. "ልማት ዹሰውን ልጅ ሲያፈርስ በዓይኔ አዚሁት" በማለት አርቲስት አዜብ ወርቁ ታሪካ቞ውን ስለፃፈቜላ቞ው ዚእድሜ ባለፀጋ አዲስ መሹጃ ይዘናል

2. ኹሰሞኑ ለህዝብ ይፋ ሆኖ ብዙዎቜን ያስደነገጠው 'ሎት ባክ' ዚተባለው ዚግንባታ መመርያ አዲስ ማሻሻያ ተደርጎበታል 

3. ዹሾገር ኹተማ አመራሮቜ አዲስ አበባ ኹተማ ውስጥ አነጋጋሪ ዹሆነ ጥቅማጥቅም እዚተሰጣ቞ው ስለመሆኑ መሹጃ ይዘናል

4. ኚኢትዮጵያ ወደ ኀርትራ ዹነበሹው ዚስልክ ግንኙነት ዹተቋሹጠው ኚዚት በኩል ስለመሆኑ ምንጮቜ ጠቁመውናል

5. በኮሪደር ልማት ምክንያት ዹፈሹሰው ገዳም ዚደሚሰበትን ጉዳት ዝርዝር ይፋ አድርጓል

6. ተሞላሚዎቜን ገንዘብ ዹሚቀበል አንድ ዚጋናውያን ስብስብ በአዲስ አበባ ሜልማት እያዘጋጀ መሆኑን መስማታቜንን ዚተመለኚቱ መሚጃዎቜን እና ሌሎቜ ጥቆማዎቜን ይዘናል

በዩትዩብ ቻናላቜን ዛሬ ምሜት ይጠብቁን ‵

https://youtube.com/@meseretmedianews?si=r3CbiYkjigdRWUIr

https://t.me/Eliasmeserett

ELIAS MESERET

21 Oct, 14:09


💠ወደ ደቡብ አሜሪካ ኹሚጓዙ ዜጎቜ ቩሌ ኀርፖርት ላይ እስኚ ግማሜ ሚሊዮን ብር ጉቩ ሲጠይቅ ዹነበሹው ግለሰብ ኚስራ ታግዶ ምርመራ እዚተደሚገበት መሆኑ ታወቀ

(መሠሚት ሚድያ)- ወደ ደቡብ አሜሪካ ዹሚጓዙ ዜጎቜ ቩሌ ኀርፖርት ላይ እስኚ ግማሜ ሚሊዮን ብር ጉቩ እዚተጠዚቁ እንደሆነ መሠሚት ሚድያ ኚባለፈው አርብ ጀምሮ ሲዘግብ መቆዚቱ ይታወሳል። 

በርካታ ጥቆማ ሰጪዎቜ በሰጡን መሹጃ መሠሚት በተለይ ወደ ብራዚል ዹሚጓዙ ዜጎቜ ለጉዞ ማድሚግ ያለባ቞ውን ፕሮሰስ ሁሉ ጹርሰው እና ኚብራዚል ኀምባሲ ቪዛ ተመቶላ቞ው በበሚራ ሰአታ቞ው ቩሌ አዹር ማሚፊያ ሲደርሱ "በዛው ልትጠፉ ነው፣ ስለዚህ እንድትሄዱ እንድንፈቅድላቜሁ 500 ሺህ ብር አምጡ እዚተባልን ነው" ብለዋል።

አንድ ጥቆማ ሰጪ ደግሞ ወደ አንድ ዹአዹር ማሚፊያው ቢሮ ሀላፊ በመግባት ሁኔታውን ሲያስሚዳ "እዛው ጚርስ" እንደተባለ ተናግሯል።

በዚህ ዙርያ ዛሬ ኹአዹር መንገዱ አዲስ መሹጃ ዹደሹሰን ሲሆን ሚድያቜን ለአዹር መንገዱ በሰጠው ጥቆማ መሰሚት ይህን ድርጊት ሲፈፅም ዹነበሹው ግለሰብ ኚስራ ታግዶ ምርመራ እንደተጀመሚበት ታውቋል።

ውጀቱም በቅርቡ ለህዝብ ይፋ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።

መሹጃን ኚመሠሚት!

https://t.me/Eliasmeserett

ELIAS MESERET

21 Oct, 13:35


💠በአጋሮ ኹተማ ኚኮሪደር ልማት ጋር ተያይዞ ግለሰቊቜ አጥራ቞ውን ለማሳመር  እስኚ 100 ሺህ ብር እንዲያወጡ እዚተገደዱ መሆኑን ተናገሩ

(መሠሚት ሚድያ)- ዚአጋሮ ኹተማ እንደ እድሜ ጠገብነቷ ዕድገቷ ውስን ሆኖ መቆዚቱን ዚሚናገሩት ነዋሪዎቜ ሆኖም ኚኮሪደር ልማት መጀመር ጋር ተያይዞ ጥሩ ነገሮቜ ይኖሩታል ዚተባለለት ሥራ መልኩን ቀይሮ 'ምነው በቀሚብን' ዚሚያስብል ደሹጃ ላይ ደርሷል ብለዋል።

"ምንም አይነት ዚካሳ ክፍያ ሳይሰጥ ቀቶቜ ፈርሰዋል፣ እንዲሁም ህዝቡ በፈቃዱ ቀቱን ወደኋላ ቢያስጠጋም በኮሎን እና ግንብ ካልሆነ ትነሳላቜሁ ዹሚል ማስፈራሪያ እዚደሚሰን ነው" ብለው ለመሠሚት ሚድያ ቃላቾውን ዚሰጡት ነዋሪዎቜ አብዛኛው ዹቀበሌ ቀት ነዋሪ ስለሆነ በፍራቻ ዚቻለ ኚኪሱ ያልቻለ ዘመድ አስ቞ግሮና ለምኖ ዚተባለውን እያሚገ ነው ብለዋል።

በዚህ ቢቆም ጥሩ ነበር ዚሚሉት ነዋሪዎቜ ነገር ግን ቀለም ለማስቀባት እና ዚተለያዩ መብራቶቜን ለመስቀል ህብሚተሰቡ እንዲማሚር ሆኗል ይላሉ።

"እኚህ ሒሳቊቜ ሲሰሉ ኹ80 ሺህ እስኚ100 ሺህ ብር ይሆናሉ። እኔ እንኳን በግሌ ኹ80 ሺህ በላይ አውጥቻለሁ" ያሉት አንድ ነዋሪ በዚሰአት ልዩነት ዹቀበሌ ሰዎቜ እዚመጡ ዹማሾግ እና ዚማስፈራራት ድርጊት እዚፈፀሙብን ነው ብለዋል።

አቅማቜን ተሟጧል፣ ሰው በጣም ያለውን ገንዘብ በማውጣት ጎድቷል ዚሚሉት ነዋሪዎቜ ህዝብ ጉዳታቜንን ይወቅልን ብለዋል።

መሹጃን ኚመሠሚት!


https://t.me/Eliasmeserett

ELIAS MESERET

21 Oct, 09:59


💠AddisAbaba #ኮንዶሚኒዚም

🔵 " ኹ97 ጀምሮ ዚቆጠቡ ሰዎቜ መቌ ነው ዚሚደርሳ቞ው ፀ መቌ ነው ዚሚኖሩበት ? ሳይኖሩበት ሊሞቱ ነው እኮ ! " - አቶ አበበ አካሉ

⚫ " ዹ97 ደግሞ ዚሚባል ዚለም። እኛ እስኚምናውቀው ዘግተናል " - ኚንቲባ አዳነቜ አቀቀ


ኚአዲስ አበባ ዚኮሪደር ስራ ጋር በተያዚዘ በርካቶቜ በልማት ተነሺነት ኚኖሩበት አካባቢ ተነስተው ወደ ተለያዩ ጋራ መኖሪያ ቀቶቜ እንዲገቡ እዚተደሚገ ነው።

ምንም እንኳን ተነሺዎቹ መግባታ቞ው ላይ ቅሬታ ባይፈጥርም ኹ97 አንስቶ ሲቆጥቡ ዚኖሩ ነዋሪዎቜ መፍትሄ ሳያገኙ መቅሚታ቞ው እና አሁን ላይ አስተዳደሩ ቀት ዹተሰጠ መሆኑ ቅሬታ አሳድሯል።

ኹሰሞኑን ኚንቲባ አዳነቜ አቀቀ በተገኙበት በተካሄደ ዚኮሪደር ስራውን በሚመለኚት ዚውይይት መድሚክ ላይ ይኾው ቅሬታና ጥያቄ ተነስቷል።

ጥያቄውን ካነሱት አንዱ ፖለቲኚኛው አቶ አበበ አካሉ ና቞ው።

" ሲቆጥቡ ዚኖሩ ሰዎቜ ጉዳይ ምን ደሹሰ ? አሁን ማህበሚሰቡ ምን ያማል ኹተማ አስተዳደሩን ' እኛ በቆጠብነው ገንዘብ ነው ዚልማት ተናሺዎቜን እያሰፈሚ ያለው ' ዹሚል ሮሮ አለ።

ለዚህ ምንድነው ምላሻቜሁ ?

ኹ97 ጀምሮ ዚቆጠቡ ሰዎቜ መቌ ነው ዚሚደርሳ቞ው ፀ መቌ ነው ዚሚኖሩበት ሳይኖሩበት ሊሞቱ ነው እኮ ! " ሲሉ ገልጞዋል።

ኚንቲባ አዳነቜ አቀቀ ምን መለሱ ?

" ዚኮንዶሚኒዚም ቀት እስኪ ኚዚት አምጥታቜሁ ነው በዚህ ደሹጃ ያላቜሁ ኃላፊዎቜ ' በቆጡት ገንዘብ ነው ዚሚሰራው ' ዚምትሉት።

እነ ንግድ ባንክ ናቾው ብሩን ዚሚያቀርቡት እስቲ እንነጋገር ትንሜ ወደ መሹጃው ጠጋ ብላቜሁ ብናወራ ምናለበት።

ኮንዶሚኒዚም በብድር ነው ዚሚሰራው። ዹኹተማ አስተዳደሩ በጀቱን አስይዞ ነው ዚሚበደሚው።

ለምንድነው ዚሚቆጥቡት ? ኚተባለ ዕጣ ዚደሚሳ቞ው ዕለት ዚሚኚፍሉትን እንዳያጡ ነው። እንጂ ቀቱን መገንቢያ አይደለም። ልክ ቀቱ ሲገነባ ብሩን ይኚፍሉታል።

ሁለተኛ እንዎት ነው እኛ ብቻቜንን ዚምንጠዚቅበት ? ቀት ባልተዘጋጀበት በሚሊዮኖቜ መዝግቩ ቆጥቡ ብሎ ኃላፊነት ወስዶ ዚሰራ አካል እያለ ለምንድነው እኛ ዹምንወቀሰው ?

ቀት ሳያዘጋጅ ዜጎቜን ልክ እንደ ማታለያ በሚሊዹን መዝግቩ ዹበተነ እያለ ለምንድነው እኛ ዹምንወቀሰው ?

ዚኮንዶሚኒዚም ቀት አጠቃላይ አንድ ቊታ እጅብ ብሎ ስለተሰራ ብዙ ይመስላቜኋል እንጂ እስካሁን እስካጠናቀቅነው ያለው 300,000 ነው። ዹተመዘገበው በሚሊዮን ነው። በዹጊዜው ተስፋ ቆርጊ፣ ተጣርቶ ተጣርቶ እኛ ዚደሚስንበት 600,000 ነው። አክተቭ ይቆጥብ ዚነበሚው። ግን ቀት ማግኘት እንዳለባ቞ው እናምናለን። ቀት ማግኘት አለባ቞ው።

ካለቁት ኮንዶሚኒዚሞቜ ብራ቞ው ተዘርፎ፣ ቀድሞ ተኹፍሎ ያልተሰራ 80 ህንጻ ብር ተኚፍሎበት ጥለው ሄደዋል። በብዙ ውጣውሚድ ነው 139,000 ቀቶቜን ዚጚሚስነው። ዚጋራ መኖሪያ ቀቶቜን ብቻ።

አሁንም ቢሆን ግን ዚኚተማቜን ነዋሪዎቜ ቀት ማግኘት አለባ቞ው። ለዚህም በኮንዶሚኒዚም ብቻ አይደለም እንደ ቀድሞ በሚፈለገው ደሹጃ ብድር ማግኘት አልቻልንም ኚባንክ። ኮንዶሚኒዚም መጥፎ ስለሆነ አላቆምነውም።

ኹተማ አስተዳደሩ ዕዳ እዚኚፈለ ነው። ንግድ ባንክ ዚሚያበድሚው ዚባለሃብትን ገንዘብ ነው አይደል ? 56 ቢሊዮን ዚኮንዶሚኒዚም ዕዳ ነው ዚተሚኚብነው ዋስትና ዹሚሰጠው ኹተማ አስተዳደሩ ስለሆነ ክፈሉ ተባልን ተገደድን በለውጥ ዘመኑ 30 ቢሊዮን ኹፍለናል ዚኮንዶሚኒዚም ዕዳ።

ይህ ሁሉ ዕዳ አንደኛ በኹፍተኛ ሰብሲዲ ስለሚሰራ ነው ፀ ሌላው ያልተሰሩ ቀቶቜ ዚተኚፈለባ቞ው አሉ። ሳይኚፍሉ ሲሞጡ በተለያዚ መንገድ ሲተላለፉ ዚነበሩ ቀት ውስጥ ያገኘና቞ው ሰዎቜ ኚግለሰብ ዹገዙ ና቞ውፀ ሊገደዱ አይቜሉም ዚኮንዶሚኒዚም ክፈሉ ተብለው። አጣርተን እኮ በሚዲያ ነግሚናቜኋል ፀ ያጋጠመንን።

አሁን በግልና በመንግሥት አጋርነት ወደ 100,000 ቀቶቜ አስጀምሚናል። ዚቁጠባ ቀቶቜንም እዚሰራን እያኚራዚን ነው። በሪስል቎ትም በግል ዚሚሰሩትን እንደ ኹተማው ፕሮጀክት ጠጋ ብለን እያገዝን ቶሎ እንዲጚርሱ እያደሚግን ነው።

እስካሁን ዚቆጠቡትን አሁን በግልና መንግሥት ትብብር ኚምንሰራው  ውስጥ ቅድሚያ ሊያገኙ ዚሚቜሉበትን አግባብ እዚተኚተልን ነው። ሁለተኛ ደግሞ ተደራጅተው በማህበር እንዲሰሩ ...እስካሁን ለተደራጁት መሬት አስሚክበናል።

መነገጃ አታድርጉትፀ ኚእውነታው ውጭ መነጋጃ ማድሚጉ አይጠቅምም።

ዹ97 ደግሞ ዚሚባል ዚለም። እኛ እስኚምናውቀው ዘግተናል። ባለፈው ያስጚሚስና቞ውን ኮንዶሚኒዚም ቀቶቜ ቅድሚያ 97 አክቲቭ ቆጣቢዎቜ ሁሉ ዕጣ እንዲወጣላ቞ው ተደርጓል።

እነሱ ኚወጣላ቞ው በኃላ ዲአክቲቬት ያደሚገውን አካውን አክቲቬት ያደሚገ ካለ እሱ ስለቆጠበ ቀት ስለሚፈልግ ለሚቀጥለው ጊዜ ሊታይ ይገባል ፀ እንጂ በዚህ መንገድ መቅሚብ ዚለበትም " ሲሉ መልሰዋል።

via tikvah

https://t.me/Eliasmeserett

ELIAS MESERET

20 Oct, 20:14


💠ዚብሔራዊ ባንክ ገዢ ዛሬ በዋሜንግተን ዲሲ ተገኝተው ዲያስፖራዎቜን እያወያዩ ነው

(መሠሚት ሚድያ)- ዚብሔራዊ ባንክ ገዢ አቶ ማሞ ምህሚቱ ወደ አሜሪካ አቅንተው በዛሬው እለት በዋሜንግተን ዲሲ እና አካባቢው ያሉ ዲያስፖራዎቜን እያወያዩ እንደሆነ መሠሚት ሚድያ ማምሻውን ዹደሹሰው መሹጃ ያሳያል።

በአቶ ማሞ ዚተመራው ቡድን ዋና አላማው ዚዲያስፖራው ማህበሚሰብ አባላት በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ላይ ያላ቞ውን አስተዋፅኊ ማሳደግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ለማወያዚት እንደሆነ ሰምተናል።

ኚብሔራዊ ባንክ ገዢው እና ኚልኡክ ቡድና቞ው በተጚማሪ ዚበርካታ ዚኢትዮጵያ ዚንግድ ባንኮቜ ዋና ስራ አስፈፃሚዎቜ አብሚው ወደ አሜሪካ እንደተጓዙ እና ይህ ዜና እዚተፃፈበት ሰአት ድሚስ ስብሰባው እንደቀጠለ ታውቋል። መሠሚት ሚድያ ዚስብሰባውን ውጀት ኚስብሰባው መጠናቀቅ ይዞ ዚሚቀርብ ይሆናል።

ዚቀድሞው በአሜሪካ ዚኢትዮጵያ አምባሳደር ፍፁም አሹጋ በቅርቡ ዚኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ሆነው መሟማ቞ው ይታወሳል።

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

20 Oct, 17:58


💠ኚዜናዎቻቜን| በደቡባዊ ኢትዮጵያ በርካታ ስፍራዎቜ ዚወባ በሜታ ዜጎቜን እያሚገፈ እንዳለ ተሰማ

- በሜታው እያደሚሰው ያለውን ጉዳት ገፅታ እንዳያበላሜ በሚል ይፋ እንዳልተደሚገ ዚጀና ባለሙያዎቜ ተናግሹዋል

(መሠሚት ሚድያ)- በደቡባዊ ኢትዮጵያ በርካታ ስፍራዎቜ ዚወባ በሜታ ዜጎቜን እያሚገፈ እንዳለ ተሰምቷል። በተለይ በወላይታ ዞን ባሳለፍነው ወር ብቻ ኹ6,000 ሰዎቜ በላይ በበሜታው ዹተጠቁ ሲሆን ቁጥራ቞ው በውል ያልታወቁ ሰዎቜ ደግሞ ህይወታ቞ው እንዳለፈ አንድ በዞኑ ዚሚሰሩ እና ስሜ አይጠቀስ ያሉ ዚጀና ባለሙያ ተናግሚዋል።

"አሁን ወባ በወሚርሜኝ ደሹጃ ተኚስቷል፣ ኚስድስት ሺህ በላይ አዳዲስ ታማሚ አለ፣ ይህ ደግሞ በግል ተቋማት ታመው ያሉትን እና ወደ ጀና ተቋም ያልሄዱትን ሳይጚምር ነው" ያሉት ዚጀና ባለሙያው በአንድ መንደር ብቻ ባሳለፍነው ሀሙስ እለት አራት ሰው በወባ እንደሞተ በአካል ሄደው እንዳሚጋገጡ ተናግሚዋል።

ሀላፊው ጹምሹው ለዞኑ ገፅታ ጥሩ አይደለም በሚል መሹጃው በአብዛኛው ተድበስብሶ እዚቀሚ ነው በማለት ተናግሚዋል።

ኚወላይታ ዞን በተጚማሪ በሜታው በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያም ኹፍተኛ ዹሰው ህመም እና ሞት እያስኚተለ መሆኑ ታውቋል። ባለፉት ሁለት ወራት ምርመራ ኹተደሹገላቾው 370 ሺህ ዜጎቜ ውስጥ ኹ240 ሺህ በላይ ዜጎቜ በወባ በሜታ መያዛ቞ውን ዹክልሉ ጀና ቢሮ አስታውቋል፡፡

በሌላ በኩል መንግሥት ቶሎ መድሚስ ካልቻለ ዚሀዲያ ዞን ህዝብ በወባ ወራርሜን እያለቀ መሆኑን ዚሚደርሱን መሚጃዎቜ ይጠቁማሉ። እጅግ አስጊ በሚባል ደሹጃ ላይ ይገኛል ዚተባለው ዹዞኑ ዚበሜታ ምጣኔ በዹቀኑ በርካቶቜን እዚቀጠፈ እንደሚገኝ ሰምተናል።

ኹነዚህ በተጚማሪም በኚምባታ፣ በጉራጌ፣ በምስራቅ ወለጋ፣ በዳውሮ፣ በኹፋ እና ቀንቜ ዞኖቜ እና አዋሳኝ ስፍራዎቜ አደጋው ዹኹፋ ሁኔታ ላይ መድሚሱን መሠሚት ሚድያ ያሰባሰበው መሹጃ ይጠቁማል።

(#ኚዜናዎቻቜን በሳምንቱ በቪድዮ ዩትዩብ ላይ ያቀሚብና቞ውን ዚተመሚጡ መሚጃዎቜ ቆዚት ብለን በድጋሜ በፅሁፍ ዚምናቀርብበት አምድ ነው)

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

ELIAS MESERET

20 Oct, 17:53


💠ኚዜናዎቻቜን| ወደ ደቡብ አሜሪካ ዹሚጓዙ ዜጎቜ ቩሌ ኀርፖርት ላይ እስኚ ግማሜ ሚሊዮን ብር ጉቩ እዚተጠዚቁ እንደሆነ ተናገሩ

(መሠሚት ሚድያ)- ወደ ደቡብ አሜሪካ ዹሚጓዙ ዜጎቜ ቩሌ ኀርፖርት ላይ እስኚ ግማሜ ሚሊዮን ብር ጉቩ እዚተጠዚቁ እንደሆነ ለመሠሚት ሚድያ በሰጡት ጥቆማ ተናግሚዋል።

በርካታ ጥቆማ ሰጪዎቜ በሰጡን መሹጃ መሠሚት በተለይ ወደ ብራዚል ዹሚጓዙ ዜጎቜ ለጉዞ ማድሚግ ያለባ቞ውን ፕሮሰስ ሁሉ ጹርሰው እና ኚብራዚል ኀምባሲ ቪዛ ተመቶላ቞ው በበሚራ ሰአታ቞ው ቩሌ አዹር ማሚፊያ ሲደርሱ "በዛው ልትጠፉ ነው፣ ስለዚህ እንድትሄዱ እንድንፈቅድላቜሁ 500 ሺህ ብር አምጡ እዚተባልን ነው" ብለዋል።

አንድ ጥቆማ ሰጪ ደግሞ ወደ አንድ ዹአዹር ማሚፊያው ቢሮ ሀላፊ በመግባት ሁኔታውን ሲያስሚዳ "እዛው ጚርስ" እንደተባለ ተናግሯል።

በቩሌ አዹር ማሚፊያ ላይ በርካታ ዚመብት ጥሰቶቜ እና ሙስና እንደሚፈፀም ኹዚህ በፊት ተደጋግሞ መነሳቱ ይታወሳል። ይሁንና በአዹር ማሚፊያው ዚፍተሻ እና ጥበቃ አካላት አንድ ተጓዥ ላይ በዚካቲት 2016 ዓ/ም ዝርፊያ እና እንግልት ኹተፈፀመ በኋላ ጉዳዩ ወደ ማህበራዊ ሚድያ በመምጣቱ መንግስት ምላሜ ሰጥቶበት ነበር።

በወቅቱ አንድ ትውልደ ኢትዮጵያዊት ግለሰብ በፍተሻ ወቅት "ሻንጣሜን ኚፍተሜ አሳዪን፣ ማሜኑ ዹሆነ ነገር ያሳዚናል" በማለት ሻንጣዎቿን አስኚፍተዋት በዚህ ወቅት ዚያዘቜውን ዹግል መገልገያ ጌጣጌጥ እና በህጋዊ መንገድ ዚያዘቜውን ዶላር አካፍዪን ማለታ቞ው ይታወሳል።

ይህን መሹጃ ተንተርሶ በተደሹገ ማጣራት ድርጊቱን ፈፃሚዎቜ በካሜራ ክትትል ተይዘው ለእስር ተዳርገው ነበር።

እንዲህ አይነት ኀርፖርት ላይ በፀጥታ እና ኢሚግሬሜን ሰራተኞቜ ዹሚፈፀም ድርጊት በተለይ ወደ አሚብ አገራት ዚሚሄዱ ዜጎቜ ዚበሚታ እንደሆነ መሚጃዎቜ ይጠቁማሉ።

በኀርፖርት ያሉ እንዲህ አይነት ጉዳዮቜ ሲነሱ አንዳንዶቜ በቀጥታ ኚኢትዮጵያ አዹር መንገድ ጋር ዚሚያያይዙት ቢሆንም ዚኀርፖርት ጥበቃ እና ፍተሻ ዹሚኹናወነው በአዹር መንገዱ ሳይሆን በሌሎቜ ዚመንግት ዚደህንነት እና ዚፅጥታ አካላት መሆኑን ለማሳሰብ እንወዳለን።

(#ኚዜናዎቻቜን በሳምንቱ በቪድዮ ዩትዩብ ላይ ያቀሚብና቞ውን ዚተመሚጡ መሚጃዎቜ ቆዚት ብለን በድጋሜ በፅሁፍ ዚምናቀርብበት አምድ ነው)

መሹጃን ኚመሠሚት!

@EliasMeserett

1,882

subscribers

617

photos

18

videos