Wazema Media / Radio

@wazema_radio


Wazema Radio other contents are available either in our website/social media or FM radio stations in Ethiopia. www.wazemaradio.com

Wazema Media / Radio

22 Oct, 03:10


ለቸኮለ ማለዳ! ማክሰኞ ጥቅምት 12/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ የናይጀሪያ ባለሥልጣናት የሚያካሂዱበትን ስም ማጥፋት የአገሪቱ ፕሬዝዳንት እንዲያስቆሙለት በደብዳቤ መጠየቁን የአገሩቱ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ የናይጀሪያ አየር መንገድ ቢቋቋም ኢትዮጵያዊያን የአዲሱን አየር መንገድ የሃላፊነት ቦታዎች እንዲይዙ ታስቦ እንደነበር፣ የአየር መንገዱ ትርፍ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚሄድና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ታክስ እንደማይከፍል አድርገው የአገሪቱ ሲቪል አቬሽን ሚንስትር የሚያሠራጩት መረጃ እውነታነት እንደሌለው አየር መንገዱ መግለጡን ዘገባዎቹ ጠቅሰዋል። ሲቢል አቬሽን ሚንስትሩ ለምን ስሙን እንደሚያጠፉ ግልጽ እንዳልኾነለት የጠቀሰው አየር መንገዱ፣ የናይጀሪያ መንግሥት የአገሪቱን አየር መንገድ በጋራ ለማቋቋም በተደረሰበት ስምምነት ላይ ሃሳቡን በመቀየሩ ችግር እንደሌለበት ገልጧል ተብሏል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በ49 በመቶ ድርሻ የናይጀሪያ አየር መንገድን ለማቋቋም የደረሰበት ስምምነት መክሸፉ ይታወሳል።

2፤ መንግሥት የታክስ ገቢው ከጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት የሚኖረውን ድርሻ በ2016 ዓ፣ም ከነበረበት 6 ነጥብ 3 በመቶ በ2020 ዓ፣ም መጨረሻ ወደ 13 ነጥብ 2 በመቶ ለማድረስ ማቀዱ ተሰምቷል። ዋዜማ የተመለከተችው አንድ የገንዘብ ሚንስቴር ሰነድ፣ ገቢን ለማሳደግ የታቀደው የታክስ ፖሊሲዎችን በማሻሻል ተጨማሪ ገቢ በማግኘት ነው። መንግሥት እስከ 2020 ዓ፣ም ተግባራዊ የሚያደርጋቸው የታክስ ማሻሻያዎች፣ የታክስ ገቢው ከጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት የሚኖረውን ጥምርታ በ4 መቶኛ እንደሚያደርሱት ሰነዱ ይጠቅሳል። መንግሥት ወደፊት ለመጣል ካሰበው ታክስ መካከል፣ በተሽከርካሪ ዝውውር ላይ የሚጣል ታክስ አንዱ ነው።

3፤ በትግራይ ክልል ከሰሜኑ ጦርነት አስቀድሞ ለንግዱ ማኅበረሰብ ለተሰጡ ብድሮችና ወለዶች መንግሥት 'ፖለቲካዊ መፍትሔ' እንዲሰጥ ለመጠየቅ የፊርማ ማሰባሰብ እንቅስቃሴ እየተካሄደ መኾኑን ኢትዮጵያ ኢንሳይደር ዘግቧል። በክልሉ ከተሞች የተጀመረው የፊርማ ማሰባሰብ እንቅስቃሴ ዛሬ ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ መስማቱን ዘገባው አመልክቷል። ብሔራዊ ባንክ፣ ባንኮች በክልሉ ከጦርነቱ በፊት ለሰጧቸው ብድሮች የመክፈያውን ጊዜ እስከ ታኅሳስ 2017 ዓ፣ም እንዲያራዝሙ ቀደም ሲል ማዘዙ አይዘነጋም።

4፤ የአማራ ክልል ምክር ቤት አባል ዮሃንስ ቧያሌው፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ክርስቲያን ታደለና የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል ካሳ ተሻገር ትናንት ፍርድ ቤት ቀርበው ነበር። ፍርድ ቤቱ ዓቃቤ ሕግ ቀደም ሲል ክሱን አሻሽሎ እንዲያቀርብ በሰጠው ትዕዛዝ ላይ ውሳኔ ለመስጠት የተቀመጠ ቢኾንም፣ ዓቃቤ ሕግ ግን ክስ ማሻሻል የለብኝም በማለት የፍርድ ቤቱን ሂደት በጠቅላይ ፍርድ ቤት ለጊዜው አሳግዶታል። ፍርድ ቤቱ ይሻሻል ያለው ክስ፣ ዓቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ የተነሳ ሞተዋል ያላቸውን ከ1 ሺሕ በላይ ሰዎች ዝርዝርና አድራሻ እንዲገልጽ ነበር።

5፤ በመርካቶ ሸማ ተራ በተባለ አካባቢ ትናንት ምሽት የተነሳው ከፍተኛ የእሳት አደጋ በንብረት ላይ ጉዳት አድርሷል። በርካታ የእሳት አደጋ ተሽከርካሪዎችና ሠራተኞች የእሳት አደጋውን ለመቆጣጠር ከአራት ሰዓታት በላይ ከፍተኛ ጥረት እንዳደረጉ የከተማዋ ከንቲባ አዳነች አባቤ አስታውቀዋል። ከምሽቱ 1:00 ሰዓት ገደማ የተነሳውን የእሳት አደጋ ለመቆጣጠር የተቻለው፣ ከምሽቱ 5:00 ሰዓት በኋላ እንደነበር ታውቋል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

22 Oct, 01:47


#NewsAlert
ባንኮች ለሰራተኞቻቸው ለመኪናና ለቤት መግዣ በዝቅተኛ ወለድ ሰባት በመቶ ብድር ሲያገኙ ቆይተዋል። ይህ ማትጊያ በርካቶች የባንክ ዘርፉን እንዲቀላቀሉና በስራቸውም ላይ ለረጅም ጊዜ እንዲቆዩ ረድቷል።

ዋዜማ ባለፉት ቀናት ባሰባሰበችው መረጃ ይህ ለአመታት የዘለቀ ማበረታቻ በገበያ ወለድ ተመን ተሰልቶ ልዩነቱ ግብር ይጣልበታል።
የባንክ ስራተኞችም ለተበደሩት ገንዘብ የወለድ ልዩነቱ ደሞዛቸው ላይ ተሰልቶ ግብር እንዲከፍሉ ይገደዳሉ። ይህን ህግ ይዞ ብቅ ያለውና ባንኮችን እንዲያስፈፅሙ ያዘዘው የገቢዎች ሚኒስቴር ነው። ዋዜማ ያሰናዳችውን አስረጅ ዝርዝር ያንብቡት - https://cutt.ly/ceDyXSqz

Wazema Media / Radio

21 Oct, 16:26


ለቸኮለ! ሰኞ ጥቅምት 11/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ ሱዳን ለሳምንታት ዘግታው የቆየችውን የመተማ-ጋላባት መተላለፊያ ከዛሬ ጀምሮ እንደከፈተች የአማራ ክልል ቴሌቪዥን ዘግቧል። ኹለቱ አገራት በድንበሩ አከባቢ ያለውን ጸጥታ የሚጠብቅ ጊዜያዊ የጋራ የጸጥታ ኀይል እንደመደቡ ዘገባው አመልክቷል። የሱዳን ባለሥልጣናት የድንበር መተላለፊያውን የዘጉት፣ ባለፈው ወር በመተማ ከተማና አካባቢዋ በኢትዮጵያ መንግሥት ኃይሎችና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ግጭት መቀስቀሱን ተከትሎ ነበር። ድንበሩ በድጋሚ የተከፈተው፣ የመተማ ከተማ አስተዳደር አመራሮች ከሱዳኗ ገዳሪፍ ግዛት የድንበር ኮሚቴ ጋር ውይይት ካደረጉ በኋላ መኾኑን ዘገባው ጠቅሷል።

2፤ መንግሥት የመልቲ ሞዳል ትራንስፖርት ዘርፉን ለግሉ ዘርፍ ክፍት ሊያደርግ መኾኑን የማሪታይም ባለሥልጣን ባሠራጨው መረጃ አስታውቋል። ባለሥልጣኑ በተያዘው ወር ለሦስት የግል ኩባንያዎች የመጀመሪያውን ፍቃድ እንደሚሰጥና ኩባንያዎቹም በስድስት ወራት ውስጥ ሥራ መጀመር እንደሚጠበቅባቸው ገልጧል። በዘርፉ የአገልግሎት ፍቃድ ለማግኘት የጠየቁት ስምንት ኩባንያዎች ሲሆኑ፣ ፍቃድ የሚሰጣቸው ግን ፓናፍሪክ ግሎባል፣ ጥቁር አባይ ትራንስፖርት እና ኮስሞስ መልቲ ሞዳል ኦፕሬሽን የተሰኙ ኩባንያዎች ናቸው ተብሏል። እስካሁን የመልቲ ሞዳል ትራንስፖርት ዘርፉን በብቸኝነት ይዞት የቆየው፣ መንግሥታዊው የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክ ድርጅት ነው።

3፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ጠቅላይ ቤተክህነት በአዲስ አበባ አገረ ስብከት የተንሠራፋውን መስናና ብልሹ አሠራር እንዲያጣራ ያቋቋመው አጣሪ ኮሚቴ ሪፖርቱን ዛሬ ለቅዱስ ሲኖዶስ ማቅረቡን የቤተክርስቲያኗ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ አስታውቋል። አጣሪ ቡድኑ፣ በአዲስ አበባ አገረ ስብከት በአካል ተገኝቶ ማጣራት እንዳይችል እግር ስብከቱ ክልከላ ጥሎበት እንደነበር በሪፖርቱ መጥቀሱን መምሪያው ገልጧል። አጣሪ ቡድኑ፣ መረጃዎችን ለማሰባሰብ ተበዳዮችን በስልክና በአካል ማነጋገሩንና በሰነድ ማስረጃ አስደግፎ ሪፖርቱን እንዳዘጋጀና በጊዜያዊነትና በቋሚነት ችግሮቹን ለመፍታትና ያስችላሉ ያላቸውን የመፍትሄ ሃሳቦች እንዳቀረበ ተገልጧል። ቅዱስ ሲኖዶስ በሪፖርቱ ላይ ተወያይቶ ወደፊት ውሳኔ ይሰጣል ተብሏል።

4፤ የኢትዮጵያ የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት፣ ላለፉት ሦስት ወራት ከሐምሌ ወር ጀምሮ በተለይ በአማራ ክልል 548 ሺሕ 318 ዜጎች በወባ ወረርሽኝ መያዛቸውን ማስታወቁን ጠቅሶ ሪፖርተር አስነብቧል። በክልሉ በ2016 በጀት ዓመት ብቻ 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዜጎች የወባ በሽታ ሕክምና አግኝተዋል ተብሏል፡፡ በክልሉ በ2016 በጀት ዓመት እስከ ሰኔ ወር ድረስ የወባ ሥርጭት በ34 ወረዳዎች መታየቱንና ባለፈው ሳምንት ብቻ 51 ሺሕ 650 ሕሙማን ሕክምና እንዳገኙም ኢንስቲትዩቱ መናገሩን ዘገባው ጠቅሷል። በክልሉ የጤና ግብዓትን በማሠራጨት ረገድ የከፋ ችግር እንዳላጋጠመው የጠቀሰው ኢንስቲትዩቱ፣ ባለሙያዎችና መድሃኒት የጫኑ ተሽከርካሪዎች በነጻነት እንዲንቀሳቀሱ ተፋላሚ ወገኖች ትብብር ማድረግ እንዲቀጥሉ መጠየቁንም ዘገባው አመልክቷል። ወረርሽኙ፣ በደቡብ ኢትዮጵያና ኦሮሚያ ክልሎችም በከፍተኛ ደረጃ በዜጎች ላይ ጉዳት እያደረሰ ነው ተብሏል፡፡

5፤ እናት ፓርቲ፣ የላዕላይ ምክር ቤቱ አባላት እንደሆኑ ተጠቅሶ በፓርቲው ከፍተኛ አመራር ላይ ክስ አቀረቡ የተባሉ ግለሰቦች የሄዱበት መንገድ መዋቅሩንና የፓርቲውን መተዳደሪያ ደንብ ያልጠበቀ ነው ሲል ዛሬ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። በፓርቲው አመራር ላይ ክስና ውንጀላ ካቀረቡት መካከል፣ አንዱ ከፍተኛ የዲሲፕሊን ጥሰት ተገኝቶባቸው ርምጃ የተወሰደባቸውና ከብሔራዊ ሥራ አስፈጻሚነት የታገዱ እንደሆኑ ፓርቲ ገልጧል፡፡ ፓርቲው፣ ሌላኛው ከሳሽ አገር ውስጥ የሌሉና ካሁን ቀደም የቃል ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸው ናቸው ብሏል። ሆኖም ግለሰቦቹ ባነሷቸው፣ የመዋቅር፣ የመርህ፣ የሀብት አጠቃቀም፣ የሠራተኛ ቅጥርና የገቢ ምንጭ ጉዳዮች ዙሪያ ፓርቲው ወደፊት ተወያይቶ ዝርዝር ምላሽ እንደሚሰጥ ገልጧል። ባለፈው ሳምንት የተወሰኑ የፓርቲው ላዕላይ ምክር ቤት አባላት፣ በፓርቲው ውስጥ ብልሹ አሠራር ሰፍኗል በማለት ምርጫ ቦርድ ጣልቃ እንዲገባ ለቦርዱ የጻፉትን ደብዳቤ መመልከቷን ጠቅሳ ዋዜማ ዘግባ ነበር።

6፤ ዘለቀ ተመስገን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ኾነው እንደተሾሙ ኮሚሽኑ አስታውቋል። ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ፣ ዘለቀን የኮሚሽኑ ኮሚሽነር አድርገው የሾሟቸው፣ በቅርቡ የፍትህ ሚንስትር ኾነው በተሾሙት ሃና አርዓያ ሥላሴ ምትክ ነው።

7፤ የሱማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሞሐመድ ዛሬ ጅቡቲ ውስጥ ከፕሬዝዳንት እስማኤል ጌሌ ጋር በሱማሊያ የአፍሪካ ኅብረት የሽግግር ተልዕኮና ሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይተዋል። የአፍሪካ ኅብረት የሽግግር ተልዕኮ በቀጣዩ ታኅሳስ ከሱማሊያ እንደወጣ፣ የኅብረቱ ተተኪ ተልዕኮ ታኅሳስ 23 በአገሪቱ ሊሠማራ እንደሚገባና ለተልዕኮው አስተማማኝ የገንዘብ ምንጭ እንደሚያስፈልግ መስማማታቸውን ኹለቱ ፕሬዝዳንቶች ባወጡት የጋራ መግለጫ አስታውቀዋል። ከቅዳሜ ጀምሮ ኡጋንዳን፣ ቡሩንዲን፣ ጅቡቲን የጉበኙት ፕሬዝዳንት ሞሐመድ፣ ነገ ደሞ ወደ ናይሮቢ በማቅናት ከፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ ጋር እንደሚወያዩ ይጠበቃል። ኢትዮጵያ በፕሬዝዳንቱ የጉብኝት እቅድ አልተካተተችም። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

21 Oct, 03:08


ለቸኮለ ማለዳ! ሰኞ ጥቅምት 11/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻ አውጭ ግንባር (ኦብነግ)፣ የአገራዊ ምክክር ሂደቱ "አካታች" አለመኾኑንና "ግልጽነት የጎደለው" መኾኑን በመጥቀስ ከትናንት ጀምሮ በሂደቱ ተሳትፎውን ማቆሙን አስታውቋል። ኦብነግ፣ ገዥው ፓርቲ በስማሌ ክልል የምክክር ተሳታፊዎችን "በተናጥል መምረጡን"፣ "ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የደረሰበትን ስምምነት መጣሱን" እና "የተለያዩ ድምጾችን ማግለሉን" ትናንት ሌሊት ላይ ባወጣው መግለጫ ከሷል። የአማራ፣ ኦሮሚያና ትግራይ ተወካዮች በሌሉበትና ግጭቶች በቀጠሉበት ኹኔታ የሚካሄድ ምክክር፣ "የአንድ ወገን ብቻ" መኾኑ እንደማይቀር የገለጠው ኦብነግ፣ ሂደቱ "እውነተኛ ሰላም ሊያመጣ እንደማይችልም ገልጧል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ አገራዊ የምክክር ኮሚሽን ትናንት በሶማሌ ክልል የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ አስጀምሯል። የምክክር መድረኩ፣ 100 የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ወኪሎች፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የክልሉ መንግሥት ሕግ አስፈጻሚ፣ ሕግ አውጭና ሕግ ተርጓሚ አካላት፣ የልዩ ልዩ ማኅበራትና ተቋማትና የተጽዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች ወኪሎች የሚሳተፉበት የአጀንዳ ማሰባሰብ ምዕራፍ ነው፡፡ መድረኩ፣ በዋናው አገራዊ የምክክር ጉባዔው የሚሳተፉ ወኪሎችንም እንደሚመርጥ ይጠበቃል።

2፤ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጋሞ ዞን ጫሞ ሐይቅ ባለፈው ሳምንት ሐሙስ ከሰጠመችው ጀልባ ከሞቱት 13 ሰዎች መካከል የ12ቱን አስከሬን ማግኘቱን የዞኑ ፖሊስ እንደተናገረ ዶቸቨለ ዘግቧል። ከጀልባዋ ተሳፋሪዎቹ መካከል፣ ሦስቱ በሕይወት እንደተረፉ ቀደም ሲል እንደተገለጠ ይታወሳል። የቀን ሠራተኞችን ጨምሮ 16 ሰዎችንና ሙዝ ጭና የነበረችው ጀልባ ከመጠን በላይ በኾነ ክብደት የሰጠመችው፣ ከኮሬ ዞን ወደ አርባምንጭ ከተማ በመጓዝ ላይ ሳለች ነበር። 

3፤ ኢትዮ ቴሌኮም ትናንት እጅግ ፈጣኑን 5ኛ ትውልድ የሞባይል ኔትወርክ አገልግሎት በባሕር ዳር ከተማና አካባቢዋ አስጀምሯል። የ5ኛው ትውልድ ኢንተርኔት አገልግሎት የግብርና፣ ትምህርት፣ ጤና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ትራንስፖርት እና ቱሪዝም ዘርፎችን ይበልጥ ለማዘመንና ተደራሽ ለማድረግ እንደሚረዳ ኩባንያው ገልጧል። ኩባንያው ቀደም ሲል አገልግሎቱን በአዲስ አበባ፣ አዳማ፣ ጂግጂጋ፣ ድሬደዋ፣ ሐረር እና ሐሮማያ ከተሞች ማስጀመሩ አይዘነጋም።

4፤ የሱማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሞሐመድ በአገራቸው ለተሠማራው የአፍሪካ ኅብረት ተልዕኮ ወታደሮች ባዋጡ አገሮች በመዘዋወር መሪዎችን በማነጋገር ላይ ናቸው። ቅዳሜ'ለት በካምፓላ ከኡጋንዳው ፕሬዝዳንት ዮዌሪ ሙሴቪኒ ጋር በኅብረቱ ተተኪ ተልዕኮ ዙሪያ የተወያዩት ፕሬዝዳንቱ፣ ትናንት ደሞ ወደ ቡሩንዲ አቅንተዋል። ፕሬዝዳንቱ፣ ከቡሩንዲ ቀጥሎ ወደ ኬንያና ጅቡቲ ለተመሳሳይ ዓላማ ይጓዛሉ። ኢትዮጵያ በፕሬዝዳንቱ የጉብኝት እቅድ አልተካተተችም። ኢትዮጵያ ለተተኪው ተልዕኮ ወታደሮችን የማዋጣት ፍላጎት እንዳላት ባለፈው ሳምንት መግለጧ ይታወሳል።

5፤ የግብጽ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ባድር አብደላቲ፣ ግብጽ የሱማሊያን "ፍቃድ" እና "ሉዓላዊነት" በመላ የአገሪቱ ግዛት ተፈጻሚ እንዲኾን የማድረግ ሃላፊነት አለባት በማለት መናገራቸውን የግብጽ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። ኾኖም ግብጽ የሱማሊያን ሉዓላዊነት በምን መንገድ እንደምታስከብረው አብደላቲ ያብራሩ ወይም አያብራሩ ዘገባዎቹ አልጠቀሱም። አብደላቲ፣ የአፍሪካ ኅብረት ሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት ግብጽ በሱማሊያ የአፍሪካ ኅብረት ተተኪ ተልዕኮ ሥር ወታደሮቿን እንድታሠማራ ፈቅዷል በማለትም ተናግረዋል ተብሏል። ግብጽ በተተኪው ተልዕኮ እንድትሳተፍ ሱማሊያ ፍቃደኝነቷን አልገለጠችም የሚባለው መረጃ ሐሰት ነው ያሉት አብደላቲ፣ ኾኖም የግብጽ ወታደሮች የሚሠማሩት የተመድ ጸጥታው ምክር ቤት በሚያጸድቀው ማዕቀፍ ውስጥ ብቻ እንደኾነ ተናግረዋል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

19 Oct, 16:37


ለቸኮለ! ቅዳሜ ጥቅምት 9/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ የገንዘብ ሚንስትር አሕመድ ሽዴ፣ አዲሱ የመንግሥት ሠራተኞች የደመወዝ ጭማሪ ከጥቅምት ወር ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚሆን ዛሬ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል። ገንዘብ ሚንስቴር በማኅበራዊ ትስስር ገጹ ባሠራጨው የሚንስትሩ ማብራሪያ፣ የደመወዝ ጭማሪውን ተግባራዊ ለማድረግ ሚንስቴሩም ኾነ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኹሉንም ቅድመ ዝግጅቶች አድርገዋል ብለዋል። በክልሎች ለሚገኙ የመንግሥት ሠራተኞች የሚደረገውን የደመወዝ ጭማሪ፣ ፌደራል መንግሥቱ እንደሚሸን አሕመድ ተናግረዋል። አሕመድ፣ በመላ አገሪቱ ተግባራዊ ለሚኾነው የደመወዝ ጭማሪና የገንዘብ ምንዛሬ ለውጡ የሚያስከትለውን ጫና ለመቋቋም መንግሥት 300 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ በጀት ማዘጋጀቱን ገልጸዋል።

2፤ ዓለማቀፉ የገንዘብ ድርጅት፣ ለኢትዮጵያ የተራዘመ ብድር ለመልቀቅ ሲያደርግ የቆየውን ግምገማ ማጠናቀቁንና አገሪቱ የክፍያ ሚዛን ጉድለቷን ማስተካከል እንድትችል ባፋጣኝ 340 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ብድር እንዲለቀቅላት ከፍተኛ የሥራ አስፈጻሚ ቦርዱ መወሰኑን ድርጅቱ ባወጣው መግለጫ ገልጧል። የአገሪቱ የውጭ ምንዛሬ ክምችት እያደገ መኾኑን የጠቀሰው ድርጅቱ፣ ኾኖም አኹንም የውጭ ምንዛሬ ፍላጎቶች አልተሟሉም ብሏል። ጥብቅ የገንዘብ ፖሊስ መከተል፣ በማኅበራዊ ዋስትና (ሴፍቲ ኔት) ፕሮግራሞች ላይ ትኩረት ማድረግ፣ የውስጥ ገቢ የመሰብሰብ አቅምን ማጎልበት፣ በውጭ ምንዛሬ ተመን የብሄራዊ ባንክን ጣልቃ ገብነት በቀጣይነት ማገድና ለመንግሥት የገንዘብ ጉድለቶች ገንዘብ መልቀቅ ማቆም እንደሚያስፈልግ መክሯል። ድርጅቱ ባለፈው ዓመት ሐምሌ ኢትዮጵያ የክፍያ ሚዛን ጉድለቶችን ማስተካከል እንድትችልና የግሉ ዘርፍ መር ዕድገት እንድታስመዘግብ ለማገዝ፣ 3 ነጥብ 4 ቢሊዮን ዶላር ብድር ማጽደቁ ይታወሳል።

3፤ እናት ፓርቲ አመራሮች በድርጅቱ ውስጥ የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት ምርጫ ቦርድ ጣልቃ እንዲገባና ሕጋዊ ርምጃ እንዲወስድ መጠየቃቸውን ዋዜማ የፓርቲው ላዕላይ ምክር ቤት አባላት ለቦርዱ ካስገቡት ደብዳቤ ተመልክታለች። የላዕላይ ምክር ቤቱ አባላት፣ የፓርቲው ከፍተኛ አመራር ከመደበኛና ሕጋዊ መዋቅር ውጭ የኾነ አዲስ አወቃቀር ዘርግቶ “ጥያቄ የሚያነሱ” አባላትንና በማባረርና በማገድ ላይ ይገኛል፤ በፋይናንስ አሠራርና በሠራተኛ ቅጥር ዙሪያ ብልሹ አሠራር ሰፍኗል በማለት ከሰዋል። የምክር ቤቱ አባላት፣ የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ጠቅላላ ጉባዔ እንዳይካሄድ መንገድ ዘግቷል ሲሉ በደብዳቤያቸው ላይ ወቅሰዋል። የሥራ አስፈጻሚ አመራሮች በጉዳዩ ላይ ምላሽ እንዲሰጡ ዋዜማ ላቀረበላቸው ጥያቄ፣ ወደፊት ለኹሉም መገናኛ ብዙሃን ማብራሪያ እንደሚሰጡ በመግለጽ ምላሽ ሳይሰጡ ቀርተዋል። Link- https://cutt.ly/OeSJB1ym

4፤ መንግሥት ጅቡቲ ወደብና ድሬዳዋ ላይ ተከማችተው የነበሩ በነዳጅ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎች እንዲገቡ መፍቀዱን ዋዜማ ገንዘብ ሚንስቴር ለጉምሩክ ኮሚሽን ከጻፈው ደብዳቤ ላይ ተመልክታለች። ሚንስትር አሕመድ ሽዴ የፈረሙበትና ለኮሚሽኑ የተጻፈው ደብዳቤ፣ የጉምሩክ ዲክላራሲዮን ተቀባይነት ባገኘበት ቀን በሚኖረው የውጭ ምንዛሬ ተመን ተሽከርካሪዎቹ ቀረጥና ታክስ ተከፍሎባቸው እንዲገቡ እንደተፈቀደ ይገልጣል። ሚንስትሩ፣ ተሽከርካሪዎቹ ሲገቡ መረጃቸው በጥንቃቄ እንዲያዝና የጉምሩክ ስነ ሥርዓት እንዲፈጸምባቸውም መመሪያ ሰጥተዋል። የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን በቅርቡ ለጠቅላይ ሚንስትር ጽሕፈት ቤት በጻፈው ደብዳቤ፣ በነዳጅ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎች እንዳይገቡ መመሪያ ከመውጣቱ በፊት የገዛቸውና እንዳይገቡ ተከልክለው ለረጅም ጊዜ ወደብ ላይ የተቀመጡ በርካታ ተሽከርካሪዎች ባፋጣኝ እንዲያስገባ መንግሥት እንዲፈቅድለት መጠየቁ እንደተዘገበ ይታወሳል።

5፤ በድሬዳዋ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ተዘዋዋሪ ችሎት ጥቃት ለመፈጸም ተንቀሳቅሰዋል ተብለው በተከሰሱ 60 የአልሸባብ አባላት ላይ እስከ ዕድሜ ልክ እስራት መጣሉን ፌደራል ፖሊስ አስታውቋል። ችሎቱ በኹለት የቡድኑ ከፍተኛ አመራሮች ላይ የዕድሜ ልክ እስራት ቅጣት ሲጥል፣ ቀሪዎቹ 56 ተከሳሾች ከ6 እስከ 18 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት እንደተቀጡ ገልጧል። የቡድኑ አባላት፣ በሐምሌ 2014 ዓ፣ም በ7 ተሸከርካሪዎችና በአራት ሞተር ሳይክሎች ከሱማሊያ በሌሊት ወደ ሶማሌ ክልል አፍዴር ዞን እንደገቡ ከክልሉ ጸጥታ ኃይሎች ጋር በተደረገ የተኩስ ልውውጥ የተማረኩ ናቸው። የ95 የቡድኑ አባላት ጉዳይ ገና በፍርድ ቤት ክርክር ላይ እንደኾነ ተገልጧል።

6፤ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጋሞ ዞን ጫሞ ሐይቅ ላይ ሐሙስ'ለት አንድ ጀልባ ተገልብጦ 14 ሰዎች የደረሱበት እንዳልታወቀ ፖሊስ ገልጧል። ጀልባው የተገለበጠው፣ 56 የቀን ሠራተኞችንና ሕገወጥ ሙዝ ጭኖ ከኮሬ ዞን ወደ አርባምንጭ ከተማ በመጓዝ ሳለ እንደኾነ ፖሊስ አስታውቋል። ከተሳፋሪዎቹ ሁለቱ በሕይወት የተረፉ መኾኑን የገለጠው ፖሊስ፣ ሌሎቹን የማፈላለጉ ጥረት እንደቀጠለ መኾኑን ተናግሯል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

19 Oct, 04:10


ለቸኮለ ማለዳ! ቅዳሜ ጥቅምት 9/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ በኦሮሚያ ክልል ከእርሻ መሬት ዓመታዊ ግብር ጋር የሚዳበሉ ሌሎች ግብሮች ከአቅም በላይ ለሆነ ወጪ እንደዳረጓቸው ዋዜማ ያነጋገረቻቸው አርሶ አደሮች ገልጸዋል። ላንድ የእርሻ መሬት 100 ብር የመሬት ግብር እንደሚከፍሉና ሌሎች ሃያ ያህል ክፍያዎች ግን ግብሩን ወደ 6 ሺሕ ብር እንዳሳደጉት አርሶ አደሮቹ ተናግረዋል። ከክፍያዎቹ መካከል፣ ለስፖርት፣ ለቀይ መስቀል ማኅበር፣ ለኦሮሚያ ልማት ማኅበር፣ ለሚሊሻ ጽሕፈት ቤት፣ ለባሕላዊ ፍርድ ቤት፣ ለወጣቶች መዋያ፣ ለቡሳ ጎኖፋ፣ ለሴቶች ሊግ፣ ለጤና መድኅን፣ ለመንገድና ጸጥታ የሚሉ እንደሚገኙበት ዋዜማ የተመለከተቻቸው የክፍያ ደረሰኞች ያመለክታሉ።

2፤ ብሄራዊ ባንክ፣ ንግድ ባንኮች የሚገጥማቸውን የጥሬ ገንዘብ እጥረት ለመፍታት አሻሽሎ ያወጣውን መመሪያ ይፋ አድርጓል። መመሪያው ያስፈለገው፣ የጥሬ ገንዘብ እጥረት የሚገጥማቸው ንግድ ባንኮች ከብሄራዊ ባንክ ሲበደሩ ግልጽና ተጠያቂነት ያለው አሠራር በማስፈለጉ እንደኾነ ባንኩ ገልጧል። ከባንኩ የገንዘብ ድጋፍ ማግኘት የሚችሉት ባንኮች፣ ጊዜያዊ የሆነ የጥሬ ገንዘብ እጥረት የገጠማቸው፣ በቀጣይነት አስተማማኝ ካፒታል መያዝ የሚችሉ፣ ችግራቸውን ለመፍታት ኹሉንም አማራጮች አሟጠው ስለመጠቀማቸው የሚያስረዱ፣ የመጠባበቂያ እቅዳቸውን ተግባራዊ አድርገው ችግሩን መቅረፍ እንዳልቻሉ ማስረጃ የሚያቀርቡና ተቀባይነት ያለው የእዳ ማስመያዣ ያላቸው እንደኾኑ አስታውቋል።

3፤ የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት፣ የመስከረም ወር የዋጋ ንረት 17 ነጥብ 5 መድረሱን አስታውቋል። የመስከረም ወር የዋጋ ንረት ከነኅሴ ወር አንጻር የጨመረው፣ በ0 ነጥብ 3 እንደሆነ ተቋሙ ገልጧል። የምግብ የዋጋ ንረቱ በነሃሴ ወር ከነበረበት 18 ነጥብ 8 በመቶ ወደ 19 ነጥብ 6 በመቶ ያሻቀበ ሲኾን፣ ምግብ ነክ ያልሆኑ ሸቀጦች የዋጋ ግረት ደሞ በ0 ነጥብ 4 ዝቅ ማለቱን የተቋሙ መረጃ ያመለክታል።

4፤ የአማራ ክልል ዳኞች ማኅበር፣ በክልሉ ዳኞችን "ያላግባብ ማሰር" እና "ማዋከብ" የተለመደ ክስተት ኾኗል ሲል ድርጊቱን አውግዟል። ባለፈው አንድ ዓመት ብቻ በኹሉም ዞኖች ከ35 በላይ ዳኞች "ያላግባብ" ታስረው እንደተፈቱ የገለጠው ማኅበሩ፣ የእስሩ ምክንያት "ከሥራቸው ጋር" የተገናኘ እንደኾነ ጠቅሷል። በባሕርዳር ፍርድ ቤቶች አራት፣ በሰሜን ሸዋ ዞን ቀወት ወረዳ ኹለት፣ በሸዋ ሮቢት ወረዳ አንድ እንዲኹም በደቡብ ወሎ ዞን ደሴ ከተማ አንድ ዳኛ ታስረው እንደሚገኙም ማኅበሩ አስታውቋል። ማኅበሩ፣ ዳኞቹ ባስቸኳይ እንዲፈቱና የክልሉ መንግሥትም ድርጊቱን ለማስቆም ርምጃ እንዲወስድ ጠይቋል።

5፤ የተመድ ስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን በጀኔቫ የኢትዮጵያ ቋሚ መልዕክተኛ የኾኑትን አምባሳደር ጸጋአብ ክበበውን ለሦስት ዓመታት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው ሁለተኛ ምክትል ሊቀመንበር አድርጎ መርጧል። የኮሚሽኑ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ በየዓመቱ የኮሚሽኑን እቅድና በጀት የሚያጸድቅ ሲኾን፣ በስደተኞች ጥበቃ ዙሪያ ኮሚሽኑንም ያማክራል። በተያያዘ፣ ኤርትራ ስደተኞችን አገር አልባ አድርጎ የሚቆጥረው ዓለማቀፍ አሠራር መቅረት እንዳለበት በዚሁ ስብሰባ ላይ በተወካይዋ በኩል አሳስባለች። ኤርትራ ስደተኞችን ዜጎቿ አድርጋ በመቀበል እኩል ጥበቃ እንደምታደርግና የዜግነት መብት እንደምትሰጥም ገልጣለች።

6፤ የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎትና የተመድ ስደተኞች ኮሚሽን በጋምቤላ ክልል ለሚገኙ ስደተኞች ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ለመስጠት ትናንት ምዝገባ መጀመራቸውን አስታውቀዋል። ስደተኞች ዲጂታል መታወቂያ ማግኘታቸው፣ የመረጃ ሥርቆትን እንደሚቀንስና ስደተኞች የባንክ ሒሳብ እንዲከፍቱ፣ ሲም ካርድና የንግድ ፍቃድ እንዲያወጡና የትምህርትና ጤና አገልግሎት እንዲያገኙ እንደሚያስችላቸው ድርጅቶቹ ገልጸዋል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

19 Oct, 03:17


ጅቡቲ የደረሰው ስንዴ ያለ ተጨማሪ ታክስ ክፍያ ወደ ሀገር እንዲገባ መንግስት ፈቀደ

ኢትዮጵያበ2015 ዓ.ም 30 ሚሊየን ኩንታል ወደ ውጪ የመላክ እቅድ የነበራት ቢሆንም በአመት ከ20 ሚሊየን ኩንታል በላይ ወደ ሀገር እየገባ መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ-
ዝርዝሩን ያንብቡት-
https://cutt.ly/AeSJ5XIo

Wazema Media / Radio

19 Oct, 02:35


እናት ፓርቲ ተከፈለ? ዝርዝሩን ያንብቡት- https://cutt.ly/OeSJB1ym

Wazema Media / Radio

18 Oct, 16:37


ለቸኮለ! ዓርብ ጥቅምት 8/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ የዓለም ምግብ ፕሮግራም፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የእርዳታ እህል እንደሚዘረፍ ለበርካታ ዓመታት ያውቅ እንደነበር በምርመራ ማረጋገጡን ሮይተርስ ዘግቧል። ድርጅቱ ርምጃ ያልወሰደው፣ መንግሥት በጦርነቱ ወቅት ወደ ትግራይ የሚገቡትን የእርዳታ ካሚዮኖች ቁጥር ሊቀንስ ይችላል በሚል ስጋት እንደነበር መረዳቱን ዘገባው ጠቅሷል። የተዘረፈው የእርዳታ እህል ለመንግሥት ወታደሮችና ለሕወሓት ተዋጊዎች እንደሚውል ይታወቅ እንንደነበርም ከአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት የውስጥ ሰነድ መመልከቱን ዜና ምንጩ አመልክቷል። ትግራይ ውስጥ የተዘረፈው የዕርዳታ እህል 450 ሺሕ ተረጂዎችን ላንድ ወር መመገብ የሚችል 7 ሺሕ ቶን ስንዴ እንደሆነ ከክልሉ ባለሥልጣናት መስማቱንም ዘገባው ጠቅሷል። ይህንኑ ተከትሎ፣ የአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት የዓለም ምግብ ፕሮግራምን በትግራይ ከዕርዳታ አከፋፋይነት ለማስወጣት አቅዷል ተብሏል።

2፤ በአማራ ክልል ሰሜን ጎጃም ዞን ደቡብ ሜጫ ወረዳ የመንግሥት ኃይሎች ከጥቅምት ወር መግቢያ ጀምሮ ፈጸሟቸው በተባሉ ጥቃቶች ከ100 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ቢቢሲ ዓይን እማኞችንና ነዋሪዎችን በመጥቀስ ዘግቧል። ጥቅምት 1 እኩለ ቀን ላይ በወረዳው ዋና ከተማ ገርጨጭ መሃል ገነት ጤና ጣቢያ ላይ በተፈጸሙ የድሮን ጥቃቶች፣ አንድ የዘጠኝ ዓመት ሕጻንንና የጤና ባለሙያን ጨምሮ ስምንት ሰዎች እንደተገደሉ ከነዋሪዎች መስማቱን ዘገባው አመልክቷል። ከጥቃቱ ከሰዓታት በኋላ በፋኖ ታጣቂዎችና በመንግሥት ኃይሎች መካከል ግጭት መካሄዱንና የመንግሥት ኃይሎች ቤት ለቤትና መንገድ ላይ በርካቶችን "እንደረተሸኑ” መረዳቱንም ዜና ምንጩ ጠቅሷል። ኢሰመኮ፣ ስለግድያዎቹ ሪፖርቶች ደርሰውት መረጃ እያሰባሰበ እንደኾነ ተናግሯል ተብሏል።

3፤ ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ ፍትህ ሚንስትር ኾነው ለዓመታት ሲያገለግሉ የቆዩትን ጌዲዮን ጢሞቲዮስን የውጭ ጉዳይ ሚንስትር አድርገው ሾመዋል። ጌዲዮን ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ኾነው የተሾሙት፣ በቅርቡ የአገሪቱ ርዕሰ ብሄር ኾነው የተሾሙትን የቀድሞውን ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ታዬ አጽቀሥላሴ በመተካት ነው። ዐቢይ፣ በጌዲዮን ምትክ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ኾነው ሲያገለግሉ የቆዩትን ሃና አርዓያሥላሴን ፍትህ ሚንስትር አድርገው ሾመዋል። ዐቢይ፣ ናሲሴ ጫሊን ከቱሪዝም ሚንስትርነት ሥልጣን በማንሳት፣ በምትካቸው የመንግሥት ኮምንኬሽን ጉዳዮች ሚንስትር ደዔታ የኾኑትን ሰላማዊት ካሳን ሾመዋል። ጠቅላይ ሚንስትሩ፣ አዲሶቹን የሚንስትርነት ሹመቶች የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲያጸድቅላቸው ማቅረብ ይጠበቅባቸዋል።

4፤ በኦሮሚያ ክልል ሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዙን ሱሉለ ፊንጫ ወረዳ በእርሻ ሥራ ላይ የነበሩ ኹለት ወጣቶች በመንግሥት ወታደሮችና በኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ታጣቂዎች መካከል ትናንት ጧት ሲደረግ በነበረ የተኩስ ልውውጥ ተመትተው ሕይወታቸው ማለፉንና አንድ ሌላ ሰው መቁሰሉን ዋዜማ በአካባቢው ካሉ ምንጮቿ ሰምታለች። ወጣቶቹ ከአጎራባቾቹ ሆሮ እና ጉዱሩ ወረዳዎች ለእርሻ ሥራ የሄዱ መኾናቸውን የተናገሩት ምንጮቹ፣ አስከሬናቸው ዛሬ ረፋዱ ላይ ሱሉለ ፊንጫ ከሚገኘው የፊንጫ ስኳር ፋብሪካ ጤና ጣቢያ ወደ ትውልድ አካባቢያቸው እንደተወሰደ የዐይን እማኞች ለዋዜማ አረጋግጠዋል። በኹለቱ ኃይሎች መካከል ሰሞኑን በከባድ መሳሪያ የታገዘ ውጊያ ሲካሄድ እንደቆየና ከትላንት ሌሊት ከ9 ሰዓት ጀምሮ ያለማቋረጥ የተኩስ ልውውጥ ድምጾች ይሰሙ እንደነበርም ምንጮች አውስተዋል።

5፤ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት፣ የውስጥ ገቢውን ለማሳደግ ሲል በአርሶ አደሮች እንስሳት ላይ ግብር መጣሉን እንደሰማ ጠቅሶ ሸገር ዘግቧል። የክልሉ መንግሥት አዲሱን ግብር የጣለው፣ የተሻሻለውን ‘’የገጠር መሬት መጠቀሚያ ክፍያና የግብርና ሥራ ገቢ ግብር አዋጅ መሠረት በማድረግ እንደሆነ ዘገባው ጠቅሷል። አዲሱ ግብር የተጣለው፣ አርሶ አደሮች በንብረትነት በያዟቸው የዳልጋ ከብት፣ ጋማ ከብት፣ ፍየል፣ በግ እና ግመል ብዛት ላይ ነው ተብሏል። የክልሉ መንግሥት ይህንኑ ግብር ለመጣል፣ የአርሶ አደሮችን የቁም እንስሳት መቁጠር እንደጀመረም በዘገባው ተገልጧል። ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከተቋቋመ ወዲክ፣ በበጀት እጥረት ምክንያት ለመንግሥት ሠራተኞች ሳይቀር ደመወዝ ለመክፈል ተቸግሮ እንደቆየ ይታወቃል።

6፤ የኢትዮጵያ የሰነድ ሙዓለ ንዋይ ገበያ፣ ከናይሮቢ የሰነድ ሙዓለ ንዋይና ከአይ-አፍሪካ ኢንስቲትዩት ጋር እብሮ ለመስራት የሚያስችለውን የመግባቢያ ስምምነት ዜና ተፈራርሟል። ስምምነቱ፣ ኩባንያዎቹ ድንበር ዘለል ኢንቨስትመንት፣ የእውቀት ልውውጥና የአቅም ግንባታ ትብብር ለማድረግ የሚያስችላቸው ነው። የናይሮቢ የሰነድ ሙዓለ ንዋይ በአፍሪካ አንጋፋ ከሚባሉት ሙዓለ ንዋዮች አንዱ ነው። የኢትዮጵያ ሰነድ ሙዓለ ንዋይ ገበያ በቀጣዩ ወር መጀመሪያ ገደማ የመንግሥት ልማት ድርጅቶችን አክሲዮኖች በማገበያየት በይፋ ሥራ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

18 Oct, 04:18


ለቸኮለ ማለዳ! ዓርብ ጥቅምት 8/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ ገንዘብ ሚንስቴር፣ ስንዴ ጭነው ጅቡቲ ወደብና በጉምሩክ ቅርንጫፎች የቆሙ ተሽከርካሪዎች ተጨማሪ እሴት ታክስ ሳይከፈሉ እንዲገቡ ለጉምሩክ ኮሚሽን አቅጣጫ መስጠቱን ዋዜማ ተረድታለች። የኢትዮጵያ ዱቄትና የዱቄት ውጤቶች አምራቾች ማኅበር፣ ከውጭ የሚገባው ስንዴ ተጨማሪ እሴት ታክስ ይጣልበታል መባሉ፣ በስንዴ ዋጋ ላይ ተጽዕኖ ይፈጥራል በማለት መንግሥት መፍትሄ እንዲሰጥ ጥያቄ አቅርቦ ነበር። በስንዴ ላይ ተጨማሪ እሴት ታክስ ቢጣል፣ የአንድ ኩንታል ስንዴ ዋጋ ከ5 ሺህ 100 ብር ወደ 6 ሺህ ብር ሊያሻቅብ ይችል እንደነበር የማኅበሩ ምንጮች ለዋዜማ ተናግረዋል።

2፤ የትግራይ ነጻነት ፓርቲ፣ የሰሜን ምዕራብ ዞን አንድ አመራሩ ታፍነው ከተወሰዱ ከቀናት በኋላ ተገድለው አስከሬናቸው ወንዝ ላይ ተጥሎ እንደተገኘ ትናንት በሰጠው መግለጫ አስታውቋል። ፓርቲው፣ አባላቱ በሰሜን ምዕራብ ዞን የማዕድንና የመሬት ዝርፊያን በመቃወማቸው፣ አፈናና ማስፈራሪያ እየተፈጸመባቸው ይገኛል በማለት ከሷል። ፓርቲው፣ ከ18 በላይ አባላቱና አመራሮቹ እገታ፣ ማስፈራሪያና ድብደባ እንደተፈጸመባቸው ገልጧል።

3፤ የፌደራሉ የመጀመሪያ ፍርድ ቤት፣ በሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ወንጀል ጥፋተኛ የተባሉ 16 ተከሳሾች ከ1 እስከ 25 ዓመት በጽኑ እስራት እንዲቀጡ ትናንት ወስኗል፡፡ ከፍተኛ የእስር ቅጣት ከተፈረደባቸው መካከል፣ በ25 ዓመት ጽኑ እስራት የተቀጣው ተካ ወልደማርያም፣ 15 ዓመት እስራት የተፈረደባት ደመቀች ማጉጂ፣ 16 ዓመት የተፈረደበት ገብረትንሳኤ ሀጎስ እና 11 ዓመት ጽኑ እስራት የተፈረደበት መለሰ ካህሳይ ይገኙበታል። መሀመድ አሕመድ የተባለ የረዳት ሳጅን ማዕረግ ያለው የፖሊስ አባል ደሞ 6 ዓመት ተፈርዶበታል።

4፤ አገራዊ የምክክር ኮሚሽን፣ በአማራና ትግራይ ክልሎች ያሉት ወቅታዊ ኹኔታዎች ሥራዬን ባግባቡ እንዳላከናውን እንቅፋት ኾነውብኛል ማለቱን ዶቸቨለ ዘግቧል። ኮሚሽኑ፣ በአማራ ክልል አንጻራዊ ጸጥታ በሠፈነባቸው ወረዳዎች ተባባሪ አካላት የአጀንዳ መረጣ ተሳታፊዎችን ለመምረጥ ሙከራ ማድረጋቸውን መግለጡን ዘገባው አመልክቷል። ኾኖም የኮሚሽኑ አሰልጣኞችና ተባባሪ አካላት ተንቀሳቅሰው መስራት እንዳልቻሉ የጠቀሰው ኮሚሽኑ፣ አማራ ክልል በሂደቱ ሳይካተት አገራዊ የምክክር ጉባዔ ማካሄድ አስቸጋሪ መኾኑን ገልጧል ተብሏል።

5፤ እስራኤል በሶማሌላንድ ወታደራዊ ጦር ሠፈር የማቋቋም ፍላጎት እንዳላት ከምንጮች መስማቱን ጠቅሶ ሚድል ኢስት ሞኒተር ጋዜጣ ዘግቧል። እስራኤል በምላሹ፣ በሶማሌላንድ በግብርና፣ ኢነርጂና መሠረተ ልማት ኢንቨስትመንት ልትሳተፍ ትችላለች መባሉን ዘገባው አመልክቷል። እስራኤል በሶማሌላንድ ወታደራዊ ጦር ሠፈር እንድታቋቁም የግዛቲቱን መንግሥት የመግባባት ተልዕኮ የያዘችው የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች እንደኾነች ጋዜጣው ከዲፕሎማቶች መስማቱን ጠቅሷል። እስራኤል ሶማሌላንድ ውስጥ ጦር ሠፈር ለማቋቋም ፍላጎት ያሳየችው፣ ከየመን የሚሠነዘርባትን ጥቃት ለመቋቋም ነው ተብሏል።

6፤ የኬንያ የላይኛው ፓርላማ፣ በአገሪቱ ምክትል ፕሬዝዳንት ሪጋቲ ካሻጉዋ ላይ የቀረቡትን ክሶች መርምሮ ምክትል ፕሬዝዳንቱ ከሥልጣን እንዲነሱ ወስኗል። ከ66ቱ የምክር ቤቱ አባላት መካከል፣ 50 ያህሉ ታችኛው ፓርላማ በምክትል ፕሬዝዳንቱ ላይ ያቀረባቸውን ክሶች ተቀብለዋል። የፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ ምክትል ኾነው ከሁለት ዓመት በፊት በምርጫ የተመረጡት ጋሻጉዋ ከተከሰሱባቸው ወንጀሎች መካከል፣ ሕገመንግሥቱን መጣስና ሙስና ይገኙባቸዋል። በአገሪቱ ታሪክ ፓርላማው አንድን ምክትል ፕሬዝዳንት ከሥልጣን ሲያነሳ የመጀመሪያው ነው። ጋሻጉዋ በፓርላማው ውሳኔ ላይ ለፍርድ ቤት አቤት የማለት መብት እላቸው። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

17 Oct, 16:18


ለቸኮለ! ሐሙስ ጥቅምት 7/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻ አውጭ ግንባር (ኦብነግ) ከፌደራል መንግሥቱ ጋር ከስድስት ዓመት በፊት አሥመራ ውስጥ የተፈራረመውን የሰላም ስምምነት ለመገምገም ለጥቅምት 16 አስቸኳይ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ ጠርቷል። ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው፣ በአፍሪካ ቀንድ ባለው ወቅታዊ ኹኔታ ላይ ስትራቴጂካ ግምገማ እንደሚያደርግና የግንባሩ ጠቅላላ ጉባኤ የሚካሄድበትን ቀን ጭምር እንደሚወስን ግንባሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጹ ባሠራጨው መረጃ አስታውቋል።

2፤ ሂውማን ራይትስ ዎች፣ በኢትዮጵያ መንግሥት ኃይሎችና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል የሚካሄደው ግጭት በሱዳናዊያን ስደተኞች ደኅንነት ላይ ከባድ አደጋ መደቀኑን ዛሬ ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል። ድርጅቱ በቅርቡ ወደ ሱዳን የተመለሱ በርካታ ስደተኞች፣ መንግሥት እንዲመለሱ እንዳስገደዳቸው ነግረውኛል ብሏል። ባለፈው አንድ ዓመት ቢያንስ ሦስት ስደተኞች በታጠቁ አካላት ተገድለዋል ያለው ድርጅቱ፣ ኸሉም ወታደራዊ ኃይሎች በስደተኞች ላይ ጥቃት መፈጸም እንዲያቆሙ፣ ወደ ስደተኛ መጠለያዎች እንዳይገቡና ስደተኞች ሰብዓዊ ዕርዳታ እንዲደርሳቸው እንዲያደርጉም ጠይቋል። ዓለማቀፍ አጋሮች መንግሥት ለስደተኞች አስፈላጊውን ጥበቃ እንዲያደርግ፣ ስደተኞችን በግዳጅ መመለስ እንዲያቆምና ሰብዓዊ ድጋፎችን እንዲጨምር ግፊት እንዲያደርጉም ድርጅቱ ጥሪ አድርጓል። የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ግን፣ ስደተኞች በግዳጅ ወደ አገራቸው ተመልሰዋል መባሉን አስተባብሏል ተብሏል።

3፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ራስ ገዟ ሶማሌላንድ አዲስ አበባ ላይ ኢምባሲ እንድትገነባ በነጻ ቦታ ሰጥቷል። የሶማሌላንድ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ኢሳ ካይድ፣ ለግዛቲቷ በተሰጣት ቦታ ላይ ትናንት የኢምባሲውን የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠዋል። መንግሥት ለኢምባሲ መገንቢያ ቦታ መስጠቱቱ፣ በኢትዮጵያ እና ሶማሌላንድ መካከል ያለውን የኹለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ እንደሚጠናክረው የግዛቲቷ ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ገልጧል።

4፤ ፍሪደም ሃውስ የተባለው ዓለማቀፍ ተቋም ባወጣው መረጃ፣ ኢትዮጵያ በግጭቶችና በመንግሥት ውሳኔ ሳቢያ በአፍሪካ በይነ መረብ ነጻ ያልኾነባት አገር መኾኗን አዲስ ባወጣው ሪፖርት አመልክቷል። በጥናቱ ከተካተቱት አገራት መካከል፣ በኢንተርኔት ነጻነት ረገድ ድርጅቱ ከ100ው ለኢትዮጵያ የሰጣት ዝቅተኛው ደረጃ 27 ነው። ሪፖርቱ የኢትዮጵያ እና የሱዳን ባለሥልጣናት የብሄራዊ ደኅንነትና የጸጥታ ኹኔታዎችን እንደ ምክንያት በመጠቀም የኢንተርኔት ግንኙነቶችን እንደሚያቋርጡና የበይነ መረብ ጋዜጠኞችን እንደሚያሳድዱ የጠቀሰው ሪፖርቱ፣ ይህም ከፍተኛ የኢንተርኔት መብት ገደብ እንዳስከተለ ገልጧል። ይነ መረብ ጋዜጠኞችን ያሳድዳሉ ብሏል። ጥናቱ የተካሄደው፣ ኢትዮጵያን፣ ኬንያን፣ ሱዳንንና ኡጋንዳን ጨምሮ በ17 አገሮች ላይ ነው።

5፤ በአፋር ክልል አዋሽ አካባቢ ዛሬ ከቀኑ 6 ሰዓት ገደማ በሬክተር ስኬል 4 ነጥብ 7 የተለካ ርዕደ መሬት ተከስቷል። የርዕደ መሬቱ ንዝረት እስከ አዲስ አበባ ድረስ ተሰምቷል። የዛሬው ርዕደ መሬት ከመተሃራ ከተማ በቅርብ ርቀት በሚገኝ ቦታ ላይ የተከሰተ እንደነበር ዓለማቀፍ የርዕደ መሬት ተከታታይ ተቋማት አስታውቀዋል። ትናንት ምሽት 5 ሰዓት ገደማም፣ በሬክተር ስኬል 4 ነጥብ 6 የተለካ ርዕደ መሬት ተከስቶ እንደነበር ይታወሳል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጂኦፊዚክስና ስፔስ ሳይንስ፣ በአዋሽ ፈንታሌ እና ሳቡሬ ከተማ መካከል ላይ በመካሄድ ላይ ያለው የቅልጥ ዓለት እንቅስቀሴ እስካልቆመ ድረስ፣ የርዕደ መሬት ክስተቱ ይቀጥላል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጧል። የትናንቱም ኾነ የዛሬው ርዕደ መሬት በሰው ሕይወት ላይ ያስከተለው ጉዳት ይኑር ወይም አይኑር ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ሰዓት ድረስ አልተገለጠም።

6፤ የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ትናንት ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽን እና ከዓለማቀፉ የፍልሰት ድርጅት (አይ ኦ ኤም) ጋር በመተባበር በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከኩርሙክ ጊዜያዊ መጠለያ 300 ስደተኞችን ወደ አዲሱ ኡራ መጠለያ ማዛወሩን ገልጧል። ኡራ መጠለያ በቅርቡ ተገንብቶ ከተጠናቀቀ ወዲህ፣ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ድንበር ላይ ከሚገኘው የኩርሙክ የስደተኞች መቀበያ ጣቢያ የተዛወሩት ስደተኞች ብዛት 4 ሺሕ 500 ደርሷል። ሦስቱ ተቋማት እስከ ታኅሳስ መጨረሻ ድረስ 14 ሺሕ ስደተኞችን ከኩርሙክ ወደ ኡራ ለማዛወር አቅደዋል።

7፤ በዋናነት በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ላይ ጥገኛ ኾና የቆየችው ጅቡቲ 276 ኪሎ ዋት ኃይል የሚያመነጭ የጸሃይ ኃይል ማመንጫ ለመገንባት ከግብጽ ጋር ትናንት ስምምነት ተፈራርማለች። ግብጽ የጸሃይ ኃይል ማመንጫውን ወጪ ሙሉ በሙሉ እንደምትሸፍንና ራሷ እንደምትገነባው ተገልጧል። የጸሃይ ኃይል ማመንጫው ወደፊት እስከ 300 ኪሎ ዋት የማመንጨት አቅም እንዲኖረው ኾኖ ይገነባል ተብሏል። ጅቡቲ ከኹለት ዓመት በፊት የመጀመሪያውን የንፋስ ኃይል ማመንጫ መገንባቷ ይታወሳል። አገሪቱ በቀጣዮቹ 10 ዓመታት ውስጥ ሙሉ በሙሉ ወደ ታዳሽ ኃይል የመሸጋገር ዕቅድ አላት።

8፤ በሱማሊያ የአፍሪካ ኅብረት ተልዕኮ ትናንት በጁባላንድ ፌደራል ግዛት በታችኛው ጁባ አካባቢ በኪሲማዩ ወደብ የሚገኘውን አንድ ወታደራዊ ጦር ሠፈሩን ለሱማሊያ ጦር ሠራዊት አስረክቧል። የኅብረቱ ተልዕኮ ያስረከበው ወታደራዊ ጦር ሠፈር፣ የኬንያ ወታደሮች ላለፉት ዘጠኝ ዓመታት ሠፍረውበት የነበረ ወታደራዊ ጦር ሠፈር ነው። የኬንያ ወታደሮች አካባቢውን የተቆጣጠሩት፣ ከአልሸበብ ታጣቂዎች በማስለቀቅ ነበር። የኅብረቱ ተልዕኮ በሦስተኛው ዙር ብቻ እስካኹን 2 ሺሕ ወታደሮቹን ቀንሷል። የአፍሪካ ኅብረት ጦር በታኅሳስ መጨረሻ ከሱማሊያ ሙሉ በሙሉ ጠቅልሎ ይወጣል ተብሎ ይጠበቃል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

17 Oct, 03:10


በትግራይ አብዛኞቹ የመንግስት ተቋማት ለምን የፌደራሉ ሰንደቅ አላማ አይታይም? ክልሉ መልስ አለው- አንብቡት https://cutt.ly/ceSx3XFM

Wazema Media / Radio

16 Oct, 16:20


ለቸኮለ! ረቡዕ ጥቅምት 6/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ ኢትዮ ቴሌኮም 100 ሚሊዮን አክሲዮኖችን ለሽያጭ ማቅረቡን ማምሻውን የአክሲዮን ሽያጭ መጀመሩን ይፋ ባደረገበት መርሃግብር ላይ አስታውቋል። ኩባንያው ለኢትዮጵያዊያን ለሽያጭ ያቀረባቸው አክሲዮኖች እያንዳንዳቸው 300 ብር ዋጋ እንዳላቸው ገልጧል። አንድ ኢትዮጵያ መግዛት የሚችለው ዝቅተኛው የአክሲዮን ብዛት 33 ሲኾን፣ ከፍተኛው ደሞ 3 ሺሕ 333 አክስዮን እንደኾነ ኩባንያው አስታውቋል። ኩባንያው ዛሬ የጀመረው የአክሲዮን ሽያጭ፣ እስከ ታኅሳስ መጨረሻ ይቆያል ተብሏል።

2፤ በትግራይ ክልል በጦርነቱ ውድመት የደረሰበት የትምህርት ዘርፉን ለመልሶ ማገገሚያ 5 ነጥብ 65 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልገው ሪፖርተር ከክልሉ መንግሥት የጥናት ሰነድ መመልከቱን ጠቅሶ ዘግቧል። በመቀሌና በአምስቱ ዞኖች በ2 ሺሕ 54 ትምህርት ቤቶች ላይ በተደረገ ጥናት፣ 1 ሺህ 238 ትምህርት ቤቶች ከፊል ውድመት እንደደረሰባቸውና 575 ትምህርት ቤቶች ደሞ ሙሉ በሙሉ እንደወደሙ ሰነዱ ማመልከቱን ዘገባው ጠቅሷል፡፡ በማዕከላዊ ትግራይ ዞን ብቻ 195 ትምህርት ቤቶች ሙሉ ለሙሉ እንደወደሙ ተገልጧል። በተጠቀሱት አካባቢዎች በትምህርት ቤቶች ላይ የደረሰው ውድመት፣ በአማካይ 88 ነጥብ 27 በመቶ ነው ተብሏል። በክልሉ በጦርነቱ ከ10 ሺሕ በላይ መምህራን ሕይወታቸውን ማጣታቸው በትምህርት ዘርፉ ውድመት ላይ ባለፈው ሳምንት በተደረገ ውይይት ላይ መነሳቱን ምንጮች እንደነገሩት ጋዜጣው ጠቅሷል።

3፤ የሕወሓት ሊቀመንበር ደብረጺዮን ገብረሚካኤል፣ የትግራይ የጦርነት ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው ያልተመለሱትና በሌሎች ኃይሎች ቁጥጥር ሥር በሚገኙ አካባቢዎች የሚኖሩ ነዋሪዎች ለችግር የተዳረጉት፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ ክልሉን መምራት ባለመቻሉ ነው በማለት ወቅሰዋል። ደብረጺዮን ዛሬ መቀሌ ውስጥ ከንግድ ማኅበረሰቡ ተወካዮች ጋር ባደረጉት ውይይት፣ የትግራይ ሕዝብ ጥቅሞች አደጋ ላይ እየወደቁ ይገኛሉ በማለት ጊዜያዊ አስተዳደሩን ተጠያቂ አድርገዋል። እርሳቸው የሚመሩት የሕወሓት ክንፍ፣ ሕወሓት በጊዜያዊ አስተዳደሩ ውስጥ ያለውን ድርሻ ለማስተካከል እንጂ ለማፍረስ እንዳልተንቀሳቀሰም ደብረጺዮን ገልጸዋል። ሕወሓት በጊዜያዊ አስተዳደሩ ውስጥ ያሉትን ችግሮች ከፌደራል መንግሥቱ ጋር በመነጋገር እንደሚፈታ የገለጡት ደብረጺዮን፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ የግለሰብ ኩባንያ እንዲሆን አንፈቅድም በማለትም ተናግረዋል።

4፤ ኢዜማ፣ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጋርዱላ ዞን የመንግሥት ኃላፊዎችና የጸጥታ አካላት፣ አመራሮቼንና አባላቶቼን እያስሩ፣ እየደበደቡ እና እያሰቃዩ ይገኛሉ በማለት አዲስ ባወጣው መግለጫ ከሷል። የመንግሥት ጸጥታ አካላት ድርጊቱን የሚፈጽሙት፣ የተለያዩ የታጠቁ አካላት ለሚፈጽሟቸው ጥቃቶች ሕግ እናስከብራለን በሚል ሰበብ እንደሆነ ጠቅሷል። የመንግሥት ድርጊት አምባገነንነትን ለማስፈን የሚደረግ መወተርተርና ፓርቲዎች በሰላማዊ ትግል ተስፋ እንዲቆርጡ በማድረግ ወደሌላ መንገድ የሚመራ ነው በማለት አውግዟል። መንግሥት ከመሰል አፈናዎች እንዲታቀብና በእስር ላይ የሚገኙ አመራሮቹንና አባሎቹን በሕግ አግባብ እንዲለቅለትም ፓርቲው ጠይቋል።

5፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ዛሬ ከአዲስ አበባ ወደ ድሬዳዋ ሲጓዝ በነበረ በረራ ቁጥር ET248 በኾነ የመንገደኞች አውሮፕላን ላይ ጭስ መታየቱን አስታውቋል። አውሮፕላኑ ላይ ጭስ የታየው፣ ድሬዳዋ አየር ማረፍያ ለማረፍ በዝግጅት ላይ ሳለ እንደኾነ ገልጧል። አውሮፕላኑ በድሬዳዋ አየር ማረፍያ በሰላም ማረፋን የጠቀሰው አየር መንገዱ ጭሱ የተነሳበትን ምክንያት በማጣራት ላይ እንደኾነ ገልጧል።

6፤ ብሪታኒያ በሱማሊያ ለተሠማራው የአፍሪካ ኅብረት ጦር ማጠናከሪያ 7 ነጥብ 5 ሚሊዮን ፓውንድ ለግሳለች። የገንዘብ ድጋፉ በኅብረቱ የሽግግር ተልዕኮ ተሳታፊ ለኾኑ የኢትዮጵያ፣ ቡሩንዲ፣ ኡጋንዳ፣ ጅቡቲና ኬንያ ወታደሮች ደመወዝና ኅብረቱ በታኅሳስ መጨረሻ ወታደሮቹን ከአገሪቱ ሙሉ ለሙሉ ለማስወጣት የጀመረውን ጥረት ለማገዝ የሚውል እንደኾነ ብሪታንያ ገልጣለች። ብሪታኒያ፣ ዓለማቀፍ አጋሮች በጥር ወር በአገሪቱ ይሠማራል ተብሎ ለሚጠበቀው የኅብረቱ ተተኪ ተልዕኮ የገንዘብ ድጋፍ እንዲያደርጉም ከወዲሁ ጥሪ አድርጋለች። አፍሪካ ኅብረት በተተኪው ተልዕኮ አወቃቀር እና በጀት ዙሪያ በቀጣዩ ወር ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጸጥታው ምክር ቤት ሪፖርት ያቀርባል ተብሎ ይጠበቃል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

16 Oct, 03:19


ለቸኮለ ማለዳ! ረቡዕ ጥቅምት 6/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ የሰሜኑ ጦርነትና በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተከሰቱ ግጭቶች ባስከተሉት ጉዳት ላይ ገንዘብ ሚንስቴር ከዓለም ባንክ ጋር በመተባበር ያስጠናው ኹለተኛው ዙር የዳሰሳ ጥናት፣ በሚንስቴሩ እየተገመገመ እንደሚገኝ ዋዜማ ሰምታለች። የዳሰሳ ጥናቱ ቡድን፣ ጥናቱን አጠናቆ ለሚንስቴሩ ያቀረበው ባለፈው ሐምሌ እንደነበር ታውቋል። ጥናቱ የተካሄደው ከ2015 እስከ 2016 ዓ፣ም ሲኾን፣ ጦርነቱና ግጭቶች በግብርና፣ ቱሪዝምና ኢንዱስትሪ ዘርፎች፣ በኢነርጂና ዲጂታል መሠረተ ልማት፣ በመንግሥት አገልግሎቶችና በመኖሪያ ቤቶች ላይ በደረሱ ጉዳቶች ላይ ያተኮረ እንደሆነ ዋዜማ ከሚንስቴሩ ምንጮች ሰምታለች።

2፤ ኢትዮ ቴሌኮም ከዛሬ ጀምሮ 10 በመቶ ድርሻውን ለሕዝብ ይሸጣል ተብሎ ይጠበቃል። በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያንም ከኩባንያው ድርሻ እንዲገዙ ተፈቅዶላቸዋል። ኩባንያው 10 በመቶ ድርሻውን ለሕዝብ የሚሸጠው፣ በራሱ ቴሌብር መተግበሪያ አማካኝነት ነው። ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ሰዓት ድረስ ኩባንያው ምን ያህል ድርሻዎችን ለሽያጭ እንደሚያቀርብና ያንዱ የአክሲዮን ድርሻ ዋጋ ስንት እንደኾነ አልተገለጠም።

3፤ በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ደራ ወረዳ በመንግሥት ኃይሎችና በአማጺው የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት እንዲኹም በመንግሥት ኃይሎችና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ከመስከረም 27 ጀምሮ በተካሄዱ ግጭቶች ሰባት ሰላማዊ ሰዎች እንደተገደሉ ከአካባቢው ነዋሪዎች መስማቱን ጠቅሶ ቪኦኤ ዘግቧል። የአካባቢው ነዋሪዎች የሟቾቹን አስከሬኖች ጥቅምት 2 እንዳገኙ መናገራቸውን ዘገባው አመልክቷል። አንድ የአካባቢው አስተዳደር ባለሥልጣን ግን፣ በአካባቢው ምንም ውጊያ የለም በማለት ምላሽ መስጠታቸውን ዘገባው ጠቅሷል።

4፤ የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን፣ በአሜሪካ የልማት ተራድዖ ድርጅት ድጋፍ በዘጠኝ ክልሎች ተግባራዊ የሚደረግና ከ5 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት የተመደበለት የአደጋ ሥጋት አስተዳደር ሥርዓት ፕሮጀክት ይፋ አድርጓል። በ120 ወረዳዎች ተግባራዊ የሚደረገው ፕሮጀክት፣ ከ14 ሚሊዮን በላይ ወገኖችን ማዕከል ያደረገ እንደኾነ ኮሚሽኑ አስታውቋል። ፕሮጀክቱ አደጋ ከመከሰቱ በፊትና ከተከሰተ በኋላ በምን አኳኋን ማስተዳደር እንደሚገባ በተለያየ ሥልጠና የኅብረተሰቡን ንቃተ ሕሊና ከፍ ለማድረግ፣ የአደጋ ማስጠንቀቂያ፣ የምላሽና የትንበያ ሥርዓቶችን ለማጠናከርና አደጋዎችን በራስ አቅም ለመፍታት የሚያግዝ ነው ተብሏል።

5፤ ግብጽ ለሱማሊያ ጦር መሳሪያ መላክ ከጀመረች ወዲህ፣ ኢትዮጵያ በሱማሊያ ግዛት ውስጥ ያላትን የወታደር ብዛት ወደ 22 ሺሕ ማሳደጓን ከምንጮች መስማቱን ጠቅሶ የኢምሬቶች ጋዜጣ ዘ ናሽናል ዘግቧል። በግብጻዊያን ወታደራዊ አማካሪዎች የሚታገዙ የሱማሊያ ወታደሮች፣ ኢትዮጵያ ተጨማሪ ወታደሮችን ወደ አገሪቱ እንዳታስገባ ለመከላከል ወደ ድንበር መሠማራታቸውን ምንጮች እንደነገሩት ጋዜጣው ጠቅሷል። ግብጽ ባለፉት ሳምንታት፣ ወደ ሱማሊያ ወታደራዊ አማካሪዎችን፣ አሠልጣኞችንና የጸረ-ሽብር ኮማንዶዎችን እንደላከች የጠቀሰው ዘገባው፣ እስከ ታኅሳስ መጨረሻ በሺዎች የሚቆጠሩ ወታደሮቿን ታሠማራለች መባሉንም ገልጧል። ግብጽ፣ ሱማሊያ ውስጥ የወታደራዊ ተልዕኮዋን በማቋቋም ላይ እንደኾነችም ተነግሯል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

15 Oct, 16:44


ለቸኮለ! ማክሰኞ ጥቅምት 5/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ቢሮ፣ በሕዝብ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ ሚኒ-ባሶች፣ ሚዲ-ባስ ታክሲዎችና የከተማ አውቶብሶች ታሪፍ ላይ ከነገ ጀምሮ ተግባራዊ የሚኾን ከፍተኛ ጭማሪ አድርጓል። በዚህ መሠረት፣ 4 ብር ከ50 ሳንቲም የነበረው የምኒባስ ታሪፍ ወደ 10 ብር፣ 8 ብር ከ50 ሳንቲም የነበረው ታሪፍ ወደ 15 ብር፣ 13 ብር የነበረው ታሪፍ ወደ 20 ብር፣ 17 ብር የነበረው ታሪፍ ወደ 25 ብር እንዲኹም 21 ብር ከ50 ሳንቲም የነበረው ታሪፍ ወደ 30 ብር ከፍ ተደርጓል። ጭማሪ የተደረገበት ታሪፍ ተግባራዊ መኾን የጀመረው፣ ከጥቅምት 20፣ 2016 ዓ፣ም ጀምሮ ነበር። አዲሱ የታሪፍ ጭማሪ፣ "ወቅታዊ የነዳጅ የችርቻሮ ዋጋን" እና ሌሎች ቢሮው በስም ያልዘረዘራቸውን "አስተዳደራዊ ወጪዎች" ከግምት ያስገባ እንደኾነ ተገልጧል።

2፤ ብሔራዊ ባንክ፣ የንግድ ባንኮች የውጭ ምንዛሬ መግዣና መሸጫ መካከል ያለው ልዪነት ከሁለት በመቶ እንዳይበልጥ ዛሬ ባወጣው መመሪያ አሳስቧል። ባንኩ፣ ንግድ ባንኮች የውጭ ምንዛሬ መግዣ እና መሸጫ ዋጋቸውን በራሳቸው እና ከደንበኞች ጋር በሚስማሙበት መሠረት ኾኖ እንደሚቀጥል የገለጠው ባንኩ፣ ባንኮች ከውጭ ምንዛሬ ሽያጭ ጋር በተያያዘ የሚጠይቋቸውን ኮሚሽኖች እስከ ነገ ከውጭ ምንዛሬ መሸጫ ጋር ሳይደርቡ በተናጠል ለደንበኞች ማሳወቅ እንዲጀምሩ አዟል። ባንኮች የውጭ ምንዛሬ የሚገዙበትና የሚሸጡበት ዋጋ ከፍተኛ የኾነው፣ በሁለቱ ዋጋዎች መሃል ኮሚሽንና መሰል አገልግሎቶችን ከግምት ስለሚያስገቡ እንደኾነ ባንኩ ጠቅሷል። ይህንኑ ተከትሎ፣ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መሸጫ ዋጋውን በ8 ብር በመቀነስ፣ የአንድ ዶላር መግዣና መሸጫ የዋጋ ልዩነቱን ወደ ኹለት በመቶ በማውረድ፣ አንድን ዶላር በ113 ብር ከ13 ሳንቲም ሲገዛና በ115 ብር ከ39 ሳንቲም ሲሸጥ ውሏል።

3፤ በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ አርሲ አገረ ስብከት በ2016 ዓ፣ም 271 የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች መገደላቸውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ዜና ምንጮች ዘግበዋል። በዓመቱ፣ በአገረ ስብከቱ በሽርካ ወረዳ በ10 ቀበሌ ገበሬ ማኅበራት  91 ሰዎች ሲገደሉ፣ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ምዕመናን ከቤት ንብረታቸው እንደተፈናቀሉ አገረ ስብከቱ መግለጡን ዜና ምንጮቹ ጠቅሰዋል። በደጁ ወረዳ ቡርቃ ጉራቻ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አካባቢ 150 ምዕመናን፣ በጉሬ ደቢኖ ቅዱስ እግዚአብሔር አብ እና አርጆ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ30 በላይ ምዕመናን በተጠቀሰው ዓመት መገደላቸውንና 499 አባወራዎችና እማወራዎች ለስደት መዳረጋቸውን ዘገባዎቹ አውስተዋል።

4፤ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልላዊ መንግሥት፣ በዚህ ዓመት የቀድሞ ታጣቂዎችንና በግጭቶችና በጸጥታ መደፍረስ ሳቢያ ከቀያቸው ተፈናቅለው የነበሩ ዜጎችን ለማቋቋም ከ130 ሚሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ ማቀዱን እንደገለጸ ኢትዮጵያ ኢንሳይደር ዘግቧል። የክልሉ መንግሥት ካቢኔ ሥራውን በራሱ በጀት ማካሄድ እንደማይችል በማመን፣ ሃብት አሰባሳቢ ኮሚቴ ዕሁድ'ለት ማቋቋሙን መስማቱን ዘገባው አመልክቷል። በእርቅ ወደ ሰላማዊ ኑሮ የተመለሱ የቀድሞ ታጣቂዎች፣ በግብርና፣ በማዕድን ወይም ሌሎች በመረጧቸው የሥራ መስኮች እንዲሰማሩ  እንደሚደረግ የክልሉ ባለሥልጣናት መናገራቸውን ዘገባው ጠቅሷል። በ2016 በጀት ዓመት ብቻ፣ 9 ሺሕ 734 የቀድሞ ታጣቂዎችን የማቋቋም ሥራ ተሠርቷል ተብሏል። የቀድሞዎቹ አማጺዎች፣ የጉሙዝ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ እና የቤንሻንጉል ሕዝብ ነጻነት ንቅናቄ ከክልሉ መንግሥት ጋር የሰላም ስምምነት መፈራረማቸው ይታወሳል።

5፤ የፌስቡክ ባለቤት ሜታ ኩባንያ የኢትዮ ቴሌኮም ደንበኞችን ተሞክሮ የሚያሻሽል የዳታ አጠቃቀም ፕሮግራም ተግባራዊ ለማድረግ መወሰኑን ኢትዮ ቴሌኮም አስታውቋል። ይህ የተገለጠው፣ የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ከሜታ-ፌስቡክ የመካከለኛው ምስራቅና አፍሪካ የንግድ ልማትና ስትራቴጂክ አጋርነት ዳይሬክተር ኃላፊዎች ጋር ውይይት ባደረጉበት ወቅት እንኾነ ኢትዮ ቴሌኮም ባሠራጨው መረጃ ገልጧል። የሜታ የዳታ አጠቃቀም ማሻሻያ ማዕቀፍ፣ ደንበኞች በሞባይል አካውንታቸው ውስጥ ሂሳብ ባይኖርም የሜታ-ፌስቡክ አገልግሎቶችን ለተወሰነ ጊዜ በነጻ መጠቀም እንዲቀጥሉና፣ እንደ ጤና፣ ትምህርት እና የሥራ ዕድሎች የመሳሰሉ ጠቃሚ መረጃዎችንም ከክፍያ ነጻ ለማቅረብ እንደሚያስችል ተገልጧል። ሜታ፣ የዳታ አጠቃቀም ማሻሻያ አገልግሎቱን ከመቼ ጀምሮ እንደሚጀምር ግን አልተገለጠም።

6፤ የትግራዩ ተቃዋሚ ፓርቲ ሳልሳዊ ወያነ፣ የመንግሥት ኮምንኬሽን ሚንስትር በቅርቡ "ወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሑመራ ዞን" የሚል ስያሜ መጠቀማቸውን አውግዟል። ፓርቲው የአካባቢው ስያሜ ምዕራብ ትግራይ ኾኖ ሳለ፣ ሕገመንግሥታዊ እውቅና የሌለው ሥያሜ መጠቀም ሃላፊነት የጎደለው ተግባር ብቻ ሳይኾን፣ የፕሪቶሪያውን የግጭት ማቆም ስምምነት የሚጥስ ነው በማለት ተችቷል። ድርጊቱ መንግሥት በአካባቢው ላይ በተፈጸመው "የዘር ማጥፋት" እና "የዘር ማጽዳት" ወንጀሎች ተጎጂ ለኾኑ ዜጎች እና ለጦርነት ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው መመለስ ግድ እንደሌለው የሚያሳይ ነው ያለው ፓርቲው፣ መንግሥት ከመስል የጦርነት ቃና ያለው ፕሮፓጋንዳ እንዲታቀብ ጠይቋል።

7፤ ንግድ ባንክ፣ ከዘመን መለወጫ ዋዜማ ወዲህ በነበሩት በዓላት ከ828 ቢሊዮን 549 ሚሊዮን ብር በላይ በዲጂታል የክፍያ አማራጮቹ መዘዋወሩን አስታውቋል። ባንኩ፣ ከነሐሴ 30፣ 2016 ዓ፣ም እስከ መስከረም 26፣ 2017 ዓ፣ም በነበረው ጊዜ ውስጥ በዲጂታል የክፍያ አማራጮች ከ145 ሚሊዮን በላይ ግብይቶች መካሄዳቸውን ገልጧል። በተጠቀሰው ጊዜ በዲጂታል የክፍያ አማራጮች ከተፈጸሙ ግብይቶች ውስጥ 84 በመቶ ያህሉ በሞባይል ባንኪንግ አማካኝነት እንደተከናወኑ የገለጠው ባንኩ ይህም በገንዘብ ሲሰላ ከ696 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ ነው ብሏል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

15 Oct, 02:50


ለቸኮለ ማለዳ! ማክሰኞ ጥቅምት 5/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ መንግሥት ከኢትዮ ቴሌኮም ኩባንያ የ10 በመቶ ድርሻ ሽያጭ ከ25 እስከ 28 ቢሊዮን ብር ገቢ እንደሚጠብቅ ዋዜማ ከምንጮቿ ሰምታለች። አንድ ሰው ከኩባንያው ሊገዛ የሚችለው ዝቅተኛ እና ከፍተኛ የአክስዮን መጠንም እንደተወሰነ ዋዜማ ተረድታለች። ከኩባንያው ድርሻ ለመግዛት የተፈቀደላቸው፣ ኢትዮጵያዊያንና በውጭ የሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ብቻ እንደኾኑ ምንጮች ገልጸዋል። ኩባንያው በቴሌብር አማካኝነት ነገ የ10 በመቶ ድርሻውን መሸጥ እንደሚጀምር ይጠበቃል።

2፤ በኦሮሚያ ከልል ሸገር ከተማ እንዳንድ ክፍለ ከተሞችና በሰሜን ሸዋ ዞን ሙሉ ለሙሉ ተቋርጦ የነበረው የደምጽና ኢንተርኔት አገልግሎት ትናንት ምሽት 12 ሰዓት ላይ መስራት መጀመሩን ዋዜማ ከምንጮቿ ሰምታለች፡፡ አገልግሎቱ ነሐሴ 30 ላይ ከተቋረጠ በኋላ በመሃሉ ለኹለት ቀናት ብቻ ተለቆ እንደነበር ምንጮች አስታውሰዋል፡፡ ኾኖም መንግሥት በዞኑ የሚንቀሳቀሱ አማጺዎች ለጠሩት የእንቅስቃሴ ማቆም አድማ ምቹ ኹኔታ ላለመፍጠር አገልግሎቱን ዳግም ማቋረጡን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

3፤ በአማራ ክልል በሰሜን ወሎ ዞን ዋና መቀመጫ ወልዲያ የመንግሥት ኃይሎችና የፋኖ ታጣቂዎች ከዕሁድ ምሽት ጀምሮ "ከባድ" የተኩስ ልውውጥ ማድረጋቸውን ቢቢሲ አማርኛ ነዋሪዎችን ጠቅሶ ዘግቧል። ኾኖም በተኩስ ልውውጡ በሰውና በንበረት ላይ የደረሰውን ጉዳት እንዳላወቁ ነዋሪዎች መናገራቸውን ዘገባው ጠቅሷል። የተኩስ ልውውጡ የተካሄደው፣ የፋኖ ታጣቂዎች በዕለቱ በመከላከያ ሠራዊት "ወታደራዊ ማዘዣዎች” ላይ ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ እንደኾነ መግለጣቸውን ዘገባው ጨምሮ አመልክቷል። የተኩስ ልውውጡ በዋናነት፣ ጎንደር በር እና መቻሬ በተባሉ ቦታዎች የተካሄደ እንደነበር ተነግሯል።

4፤ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ የሱዙኪ ኩባንያ ስፕሬሶ ተሽከርካሪዎች በመሪ ዘንጋቸው አካባቢ ችግር በመገኘቱ ማስተካከያ እንዲያደርጉ እንደተጠሩ ሪፖርተር ዘግቧል። ይህንኑ ማሳሰቢያ ያወጣው፣ የሱዙኪ ተሽከርካሪዎች ሕጋዊ አከፋፋይ ታምሪን ኩባንያ እንደኾነ ዘገባው አመልክቷል። የተሽከርካሪዎቹ ባለቤቶች ሪፖርተር ጋዜጣ ላይ የወጣውን የተሽከርካሪ ምርት ዘመንና የሻንሲ ቁጥር በማየት፣ ተሽከርካሪዎቻቸውን እንዲያስመረምሩ ኩባንያው ጥሪ አድርጓል።

5፤ የፌደራሉ ዐቃቤ ሕግ፣ የፐርTዝ ብላክ አክሲዮን ኩባንያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ፍስሐ እሽቱን ጨምሮ በ10 ግለሰቦችና ፐርፐዝ ብላክ ኢቲኤች ትሬዲንግ እና ኖትር ዲዛይን ሃ/የተ/የግ/ማኅበር ላይ ትናንት ክስ መመስረቱን ፋና ብሮድካስት ዘግቧል። ዓቃቤ ሕግ ክሱን የመሠረተው፣ ፐርፐዝ ብላክ ሜክሲኮ አካባቢ ባለ ሦስት መኝታ ቤቶችን በ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር እንደሚሸጥ በመቀስቀስና ግንባታ ሳይካሄድ ከ2 ቢሊዮን 234 ሚሊዮን በላይ ብር በመሰብሰብና ከፊሉን ገንዘብ ወደ ውጭ በማሸሽ ወንጀሎች እንደሆነ ዘገባው ጠቅሷል። ፍርድ ቤቱ፣ ከሳሽና ተከሳሽ በዋስትና ጥያቄ ዙሪያ የሚያደርጉትን ክርክር ለማዳመጥ ለጥቅምት 11 ተዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል ተብሏል፡፡ [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

14 Oct, 16:27


ለቸኮለ! ሰኞ ጥቅምት 4/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኮሬ ዞን ዛሬ ሰኞ ማለዳ ማንነታቸው ያልታወቁ ታጣቂዎች ሦስት አርሶ አደሮችን በጥይት መግደላቸውን ዶቸቨለ ዘግቧል። ታጣቂዎቹ ወደ እርሻ ሥራቸው በመሄድ ላይ በነበሩት አርሶ አደሮች ላይ ግድያውን የፈጸሙት፣ በጎርካ ወረዳ ኬሬዳ በተባለ ቀበሌ እንደሆነ ዘገባው አመልክቷል። ታጣቂዎቹ ከወረዳው አጎራባች ከኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ጉጂ ዞን ተሻግረው የገቡ እንደኾኑ የሟቾቹ ቤተሰቦች ተናግረዋል ተብሏል። ከምዕራብ ጉጂ ዞን የሚነሱ ታጣቂዎች በወረዳው በሰላማዊ ሰዎች ላይ ተደጋጋሚ ጥቃቶችን እንደሚፈጽሙ ሲዘገብ ቆይቷል።

2፤ ባለፈው ሳምንት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው የግንባታ ደረጃዎች ረቂቅ አዋጅ፣ ደረጃቸውን ያልጠበቁ ግንባታዎች በሚያከናውኑ የሥራ ተቋራጮች፣ ባለሙያዎችና አማካሪዎች ላይ ከእስራት እስከ ፍቃድ ማገድ የሚያስቀጣ መኾኑን ሪፖርተር ዘግቧል። አዋጁን ለማስፈጸም የሚወጡ ድንጋጌዎችን በሚጥሱ አካላት ላይ አስተዳደራዊ ዕርምጃ እንደሚወሰድባቸው በረቂቁ ላይ እንደተደነገገ ዘገባው አመልክቷል። ያላግባብ በተሰጠ የግንባታ ፍቃድ ላይ የግንባታ ተቆጣጣሪነት ግዴታውን ያልተወጣ ግለሰብ ከ5 ዓመታት እስከ 10 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ሊቀጣ እንደሚችል ረቂቁ ደንግጓል ተብሏል። ደረጃው የማይፈቅድለትን ወይም ተገቢው ፍቃድ ሳይኖረው ግንባታ ያካሄደ የሥራ ተቋራጭ ደሞ እስከ 10 ዓመት የሚደርስ ጽኑ እስራትና እስከ 10 ሺሕ የሚደርስ የገንዘብ መቀጫ እንደሚቀጣ ዘገባው ጠቅሷል።

3፤ ኢሕአፓ፣ የአዲስ አበባ የመንገድ ኮሪደር ልማት “ሕዝባዊ ቁጣ" ሊቀሰቅስ ይችላል ሲል ዛሬ በሰጠው መግለጫ አስጠንቅቋል። የኮሪደር ልማቱ የነዋሪዎችን “ሰብዓዊ መብቶች የጣሰ" መኾኑን የጠቀሰው ኢሕአፓ፣ የከተማዋ ልማትና ዕድገት ከነዋሪው "መብት መከበር” እና “ከጥቅሞቹ መጠበቅ” በተነጠለ ኹኔታ ሊታይ እንደማይገባ ገልጧል። የኮርደር ልማቱ፣ የበርካታ ነዋሪዎችን መኖሪያ ቤቶች፣ አነስተኛ እና ከፍተኛ የንግድ መደብሮች ማፍረሱን ኢሕአፓ በመግለጫው ጠቅሷል። ፓርቲው፣ የከተማዋ አስተዳደር ድርጊቶች፣ የነዋሪዎችን "ኹኔታ ያላገነዘቡ" እና ምቹ ጊዜን ያልጠበቁ” ናቸው በማለትም ወቅሷል።

4፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ በአፍሪካ የመጀመሪያውን ኤ350-1000 ግዙፍ የኤርባስ ኩባንያ የመንገደኞች አውሮፕለን በተያዘው ወር እንደሚረከብ መናገሩን ኢዜአ ዘግቧል። አየር መንገዱ አውሮፕላኑን "ኢትዮጵያ፤ ላንድ ኦፍ ኦሪጅንስ" በማለት እንደሰየመው ተግልጧል። አውሮፕላኑ፣ 400 መቀመጫዎች እንዳሉት የአየር መንገዱ ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው መግለጣቸውንም ዘገባው አመልክቷል። አየር መንገዱ ካለፉት ሰባት ዓመታት ወዲህ፣ የሃያ ኤ350- 900 የኤርባስ አውሮፕላኖች ባለቤት ኾኗል።

5፤ ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ እና ሳፋሪኮም ኬንያ ኩባንያዎች፣ የኢትዮጵያ እና ኬንያ ደንበኞቻቸው ገንዘብ መላላክ የሚያስችላቸውን ስምምነት ተፈራርመዋል። ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ፣ መንግሥት ያካሄደው የውጭ ምንዛሬ ለውጥ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ገንዘብ በዲጂታል አማራጮች ወደ አገራቸው እንዲልኩ ባስቻለበት ወቅት መምጣቱ ስኬት እንደኾነ ጠቅሶ አድንቋል። የሳፋሪኮሙ ኤምፔሳ ከዓለማቀፉ የገንዘብ መላላኪያ አገልግሎት ሰጪ ኩባንያ ዳሃብሺል፣ በውጭ አገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን በኤምፔሳ አማካኝነት ኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገኙ ወዳጅ ዘመዶቻቸው ገንዘብ በቀላሉ ለመላክ የሚያስችላቸውን የአጋርነት ስምምነት ባለፈው ሰኔ መፈራረሙም አይዘነጋም።

6፤ የአሜሪካ መንግሥትና የሌሎች ምዕራባዊያን አገራት ባለሥልጣናት፣ ሱማሊያ ከኢትዮጵያ ጋር በገባችበት የባሕር በር ውዝግብ ሳቢያ ከአልሸባብ ጋር በምታደርገው ጦርነት ላይ ተጽዕኖ ማሳደሩ እንዳሳሰባቸው ዎል ስትሪት ጆርናል ዘግቧል። ምዕራባዊያን መንግሥታት፣ ሱማሊያ በውዝግቡ ላይ ከፍተኛ ትኩረት በማድረጓ፣ ጦር ሠራዊቷ በርካታ አካባቢዎችን ለአልሸባብ እየለቀቀ ነው የሚል ስጋት እንደገባቸው ዘገባው አመልክቷል። አሜሪካ ሱማሊያ ውስጥ የአገሪቱን ጦር ለማሰልጠን የሰፈሩት 450 ኮማንዶዎችም፣ ግብጽ ወደ ሱማሊያ መግባቷ ይበልጥ ከቡድኑ ጋር የሚደርገውን የጸረ-ሽብር ጦርነት ያወሳስበዋል ብለው እንደሰጉ ዘገባው ጨምሮ አውስቷል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

14 Oct, 02:36


ለቸኮለ ማለዳ! ሰኞ ጥቅምት 4/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ ኢትዮ ቴሌኮም ኩባንያ፣ 10 በመቶ ድርሻውን በራሱ የቴሌብር መተግበሪያ አማካኝነት ከረቡዕ ጀምሮ ለሕዝብ እንዲሸጥ መንግሥት መፍቀዱን ሪፖርተር ዘግቧል። መንግሥት እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው፣ ኩባንያው ድርሻውን በሙዓለ ነዋይ ገበያ ኩባንያ አማካኝነት እንዲሸጥ ያሳለፈውን ውሳኔ መቀየሩን ተከትሎ ነው። ኢትዮ ቴሌኮም ራሱ የአክሲዮን ድርሻውን እንዲያገበያይ የተፈቀደለት፣ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን የሰነድ ሙዓለ ነዋይ ግብይት አገናኝነት ፍቃድ የሰጠው በመኾኑ እንደኾነ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሩክ ታዬ መናገራቸውን ዘገባው ጠቅሷል። የሙዓለ ነዋይ ገበያው በይፋ ሥራ የሚጀምረው፣ በቀጣዩ ወር እንደኾነ ተገልጧል።

2፤ ደብረጺዮን ገ/ሚካኤል የሚመሩት የሕወሓት ክንፍ የጽሕፈት ቤት ሃላፊ ፈትለወርቅ ገ/እግዚአብሔር፣ ሕወሓት በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ላይ "መፈንቅለ ሥልጣን" አድርጓል የሚባለው ክስ ሐሰት ነው በማለት ማስተባበላቸውን ሕወሓት በማኅበራዊ ትስስር ገጹ አስታውቋል። ፈትለወርቅ፣ ከሥልጣን የማንሳት ርምጃ የወሰድነው፣ ሕወሓት በአስተዳደሩ ውስጥ ካሉት 14 ተወካዮች መካከል ከሕወሓት ባፈነገጡት 5ቱ ላይ ብቻ ነው ማለታቸው ተገልጧል። የጊዜያዊ አስተዳደሩን ርዕሰ መስተዳድር ጌታቸው ረዳ፣ የደብረጺዮን የሕወሓት ክንፍ በአስተዳደሩ ላይ መፈንቅለ ሥልጣን አካሂዷል በማለት መክሰሳቸው አይዘነጋም።

3፤ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን፣ ከዛሬ ጀምሮ በሶማሌ ክልል የአጀንዳ ማሰባሰብና የምክክር መድረኮችን እንደሚያካሂድ ትናንት አስታውቋል። ኮሚሽኑ ከክልሉ 104 ወረዳዎችና የከተማ አስተዳደሮች የተመረጡ የተለያዩ ኅብረተሰብ ክፍሎች ወኪሎች የምክክር መድረክ የሚያካሂደው፣ በጅግጅጋ፣ ጎዴ እና ዶሎ አዶ ከተሞች እንደኾነ ገልጧል። በአጀንዳ ማሰባሰቡ መድረክ፣ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የተለያዩ ተቋማትና የማኅበራት፣ የመንግሥት አስፈጻሚ አካላት ተወካዮች ይገኛሉ ተብሏል። ኮሚሽኑ፣ በአገራዊ ምክክር ጉባዔው የሚሳተፉትን የክልሉ ወኪሎችም ያስነርጣል ተብሏል። ኮሚሽኑ እስካኹን በኹለቱ የከተማ አስተዳደሮች፣ በአፋር፣ ሲዳማ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ ጋምቤላ፣ ሐረሬ፣ ሲዳማና ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደቶችን አጠናቋል።

4፤ የናይል ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ከትናንት ጀምሮ በይፋ ወደ ተግባር ገብቷል። ማዕቀፉ፣ የናይል ኮሚሽንን በማቋቋም የናይል ወንዝ አጠቃቀምና አስተዳደር በሕጋዊና ተቋማዊ ማዕቀፍ እንዲመራ የሚያስችል ነው። ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ፣ ማዕቀፉን ያልፈረሙ አገራት እንዲፈርሙ ጥሪ አድርገዋል። የማዕቀፍ ስምምነቱ ፈራሚዎች፣ ኢትዮጵያ፣ ኡጋንዳ፣ ሩዋንዳ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ታንዛኒያና ቡሩንዲ ናቸው። ላለፉት 14 ዓመታት ማዕቀፉ ወደ ተግባር እንዲገባ ከአስሩ ተፋሰስ አገራት የስድስቱ ፊርማ ያስፈልግ ነበር።

5፤ ግብጽና ሱዳን፣ የናይል ተፋሰስ አገራት የትብብር ማዕቀፍ ተፈጻሚ ሊኾንባቸው እንደማይችል በመግለጽ ውድቅ አድርገውታል። ኹለቱ አገራት፣ የትብብር ማዕቀፉ "ሙሉ መግባባት የሌለበት" እና "የዓለማቀፍ ሕግጋት መርኾዎችን ያላከበረ" መኾኑን ገልጸዋል። የትብብር ማዕቀፉ የናይል ተፋሰስ አገራትን "የሚወክል ተደርጎ ሊወሰድ አይችልም" ያሉት ግብጽና ሱዳን፣ የታችኛው ተፋሰስ አገራት ወደ መጀመሪያው የናይል ቤዚን ኢንሼቲቭ እንዲመለሱና ኹሉን አስማሚ ማዕቀፍ እንዲዘጋጅ ጥሪ አድርገዋል። [ዋዜማ]

Wazema Media / Radio

14 Oct, 01:12


የሰሜኑን ጦርነት ተከትሎ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ሲኖዶስ ተገንጥሎ የትግራይ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክህነት በሚል የተቋቋመው መንበረ ሰላማ በራያ አካባቢዎች መዋቅሩን እየተከለ መሆኑን ዋዜማ ተረድታለች። ዝርዝሩ ይኸው- https://tinyurl.com/mrxd4cnw

Wazema Media / Radio

12 Oct, 16:20


ለቸኮለ! ቅዳሜ ጥቅምት 2/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች

1፤ በትግራይ የሚገኙ ሰባት መንግሥታዊ ያልኾኑ ድርጅቶች ጥምረት ኹለቱን የሕወሓት ቡድኖች ለማሸማገል ጥረት እያደረጉ መኾኑን ሪፖርተር ዘግቧል። ጥምረቱ ለሽምግልናው የመጀመሪያውን ሕዝባዊ ጉባኤ መቀሌ ውስጥ ቅዳሜ'ለት ለማዘጋጀት አቅዶ እንደነበር የጠቀሰው ዘገባው፣ ኾኖም በኹለቱ ቡድኖች መካከል ውጥረቱ በመካረሩ ጉባዔው ሳይሳካ እንደቀረ የጥምረቱ አባላት መናገራቸውን ጠቅሷል። ጥምረቱ እስካኹን ኹለቱንም የሕወሓት ክንፎች ባንድ ላይ አቀራርቦ እንዳላናገረና በተናጥልም ቢኾን አንዳቸውም ለንግግር ዝግጁነታቸውን እስካሁን እንዳልገለጡ ተገልጧል። ጥምረቱ የተቋቋመው፣ ደብረጺዮን ገ/ሚካኤል የሚመሩት የሕወሓት ክንፍ ድርጅታዊ ጉባኤ ባካሄደ ማግስት ነበር።

2፤ የኢትዮ-ጅቡቲ ባቡር አክሲዮን ማኅበር፣ በባቡር ትራንስፖርት ለሚደርሱ ጉዳቶች የሚከፈለው ካሳ የባቡር ትራንስፖርት አዋጁ በሚፈቅደው መሠረት ብቻ እንዲፈጸም የባቡር መስመሩ ከሚያልፍባቸው ክልሎች መንግሥታት ጋር ከስምምነት ላይ እንደደረሰ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚ ታከለ ኡማ አስታውቀዋል። ታከለ፣ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የኢትዮ-ጂቡቲ የባቡር አክሲዮን ማኅበር በብዙ ሚሊዮኖች ብር "አላስፈላጊ" በኾነ አግባብ ካሳ ሲከፍል መቆየቱን ገልጸዋል። ኾኖም ይህንኑ "አግባብ ያልኾነ" የካሳ ክፍያ ለማስቅረት፣ በድሬዳዋ አስተዳደር፣ ከአፋር፣ ሱማሌ እና ኦሮሚያ ክልሎች ጋር ውይይቶች መካሄዳቸውን የገለጠት ታከለ፣ ማኅበሩ ከክልሎቹ ጋር የካሳ ክፍያዎችን በባቡር ትራንስፖርት አዋጅ መሠረት ተግባራዊ ለማድረግ ከስምምነት ደርሰናል ብለዋል።

3፤ የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን፣ ከሰኞ ጀምሮ በሶማሌ ክልል የአጀንዳ ማሰባሰብ የምክክር መድረክ እንደሚያዘጋጅ አስታውቋል። በአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደቱ እንደሌሎች ክልሎች ሁሉ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የኃይማኖት ተቋማት፣ ማኅበራትና የመንግሥታዊ አካላት ተወካዮች ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የአጀንዳ ማሰባሰቢያ መድረኩ የአገራዊ ምክክር ተሳታፊዎች ጭምር የሚመርጡበት ይኾናል። ኮሚሽኑ ባለፉት ጥቂት ወራት፣ በስድስት ክልሎች እንዲኹም በአዲስ አበባና ድሬዳዋ አስተዳደሮች የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደቶችን አጠናቋል።

4፤ ከኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኀን ባለሥልጣን ጋር ውዝግብ ውስጥ የገባው አሻም የግል ቴሌቪዥን ጣቢያ እስከ ጥቅምት 10 ድረስ ስያሜውን እንዲቀይር ባለሥልጣኑ እንዳሳሰበው ገልጧል። ጣቢያው ስያሜውን እንዲቀይር ባለፈው ሰኔ በፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ እንደታዘዘ አስታውሷል። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኀን ባለሥልጣን፣ አሻም እውነታነት የጎደላቸውን መረጃዎች ያሠራጫል በማለት ከቀናት በፊት "የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ" ሰጥቼዋለሁ ብሎ ነበር። አሻም በበኩሉ፣ ባለሥልጣኑ ለውንጀላው አንዳችም ማስረጃ አላቀረበም በማለት ውንጀላውን ውድቅ ማድረጉ ይታወሳል።  [ዋዜማ]