ጎዶሎዋ ቀን
ምሽት ይመስለኛል እለቱ ቅዳሜ
እኔና አንቺን ይዛ ያዋየችን ጳግሜ።
የወርም ጎዶሎ ከጎዶሎም መካን
ፍሬ ያላፈራች የነጠፈች እርቃን።
የጊዜ ሰካራም ደንበርባራ በቅሎ
መጨበጥ አቅቷት የቆመች የኋሊት ቅርፅ አልባ አሎሎ።
ያ ናት ያቺ ማታ...........
እዮብ የረገማት ከቀናት ለይቶ
ከአምላክ ተቆጥቶ
ከራሱ ተጣልቶ
ልጁን ቤቱን አጥቶ
ንብረት ጤናዉ ጠፍቶ
ምሬትን የማያዉቅ አንደበቱ ከፍቶ
ትረገም ያላት ቀን ከቀናት ለይቶ።
አዎ ይግረምሽ ባይገርምሽ
እኔ ምጠላት ቀን ያቺ ናት አለምሽ።
ጨለማዬን መቅረዝ
ማጣቴን ለመዘዝ
ባዶነቴን ገልጠሽ
ዉስጤን አንጠፍጥፈሽ
ልቤን ወዲ.....ያ ጥለሽ
ጭልጭል ያለዉን ብርሀኔን ገፈሽ።
ደንገዝጋዛ ቤቴን
መፅናት የተሳነዉ ምርግ መሰረቴን
እያንገጫገጭሽዉ እያወዛወሽዉ
እያንከላወሽዉ እያንገዳገድሽዉ
ትርጉም ባጣ ስላቅ ሆዴን እያጮህሽዉ
ፍቅራችንን ናድሽዉ።
ህ...............
ባይደንቅም ይድነቅሽ
ጣዖቱ ግዑዝሽ አሳሳች ዉበትሽ
ሶምሶሙ አቋሜን እያንደረደረ
ደሊላ ልብሽ ላይ ሄዶ ተዘረረ።
ዳሩ ምን ያደርጋል
ድመት ብትመነኩስ
መሆኗ ልኩስኩስ አይቀርም ሆነና
አመለኛዉ ልብሽ ተነሳ እንደገና።
በጥርስሽ መሳቅሽ
በአይንሽ መግደልሽ
በአለንጋ ጣቶችሽ እኔን መዳበስሽ
በዘንፋላዉ ፀጉርሽ አይኔን መጋረድሽ
እሱም ነዉ ጥፋትሽ😳
ባትይም ልንገርሽ..........
አፍሽ ባያወጣም መዉደድሽን አፍርጦ
ይታየኝ ነበረ ፍቅርሽ ከአይኔ ፈጦ።
ባታምኚም አዉቃለሁ እሱ ነዉ ጦሰኛ
አንከላዉሶ አምጥቶ ያረገኝ ብቸኛ።
ተይኝ በቃ ተይኝ ከራሴ አታጣዪኝ
በለመደዉ እግርሽ ደርሰሽ አትከጅዪኝ።
ባታዉቂም ማወቄን ለኔ እንደማቶኚ
ጎዶሎ ቀኔ ነሽ በይ ከኔ ተሸኚ።
በትዝታ ወልዴ እንደተፃፈ✍
,,,,,,,,,,,,🌹❣🌹❣🌹❣🌹,,,,,,,,,,,
••●◉Join us share◉●••
https://t.me/YefikirGagata
━━━━━━✦🌹✿🌹✦━━━━━━