أحدث المنشورات من ✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞ (@tsehaye_tsidk) على Telegram

منشورات ✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞ على Telegram

✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞
👉ፀሐየ ጽድቅ
የሕይወት መብራት የጽድቅ ብርሃን

በዚህ channel ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቁ ትምህርቶች እና መዝሙሮች እንዲሁም ቅዱሳንን እንዘክራለን ስለቅዱሳን እንማማራለን ዕለታዊ ዜና ቤተ-ክርስቲያ ስንክሳር ግጻዌ ጥያቄና መልስ እንዲሁም በየእለቱ አጥንትን የሚያጠነክሩ መንፈስን የሚያለመልሙ ጽሁፎችን ወደ እናንተ እናደርሳለን፡፡
ቻናሉን ይቀላቀሉ
@Tsehaye_Tsidk
ሼር ያርጉ!!
1,809 مشترك
818 صورة
7 فيديو
آخر تحديث 12.03.2025 09:47

أحدث المحتوى الذي تم مشاركته بواسطة ✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞ على Telegram

✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

22 Feb, 19:51

221

#ዐቢይ_ጾም

" በወርኃ ጾም ከመልካም ኅሊና የሚመነጭ መልካም ስራ ማከናወን ግድ ይለናል፤  ምክንያቱም ጾምን የምንጾመው መልካም ኅሊና ኖሮን ለእግዚአብሔር ለመታዘዝና ለመገዛት ነው " - ቅዱስነታቸው

የጾመ ኢየሱስ ሱባዔ (ዐቢይ ጾም)ን አስመልክቶ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት መልዕክት አስተላልፈዋል።

ከቅዱስነታቸው መልዕክት ፦

" ጾመ ኢየሱስ እያልን በየዓመቱ የምንጾመው የታላቁ ጾማችን ዓላማ ዲያብሎስን ለማሸነፍ ነው፤ የዲያብሎስ ማሸነፊያ ስልት የመልካም ኅሊና ልዕልና ነው፤ ሰውነታችን በመብልና በመጠጥ ሲደነድን መልካም ኅሊና በውስጣችን ዓቅም ያጥረዋል፤ መልካም ኅሊና ሲያጥረን ዲያብሎስ ዘው ብሎ ይገባና ወደ ክፉ ኅሊና፣ ከዚያም ወደ ግብረ ኃጢኣት ይወስደናል፤ በዚህ ጊዜ እኛ ተሸናፊዎች እሱ ኣሸናፊ ይሆናል፤ በአንጻሩ ደግሞ ሰውነታችን ከመብልና ከመጠጥ ሲለይ መልካም ኅሊና፣ ቊጥብነት፣ ማስተዋልና ማመዛዘን በውስጣችን ትልቅ ጉልበት ያገኛሉ፤ እነሱ ጐለበቱ ማለት ዲያብሎስ መግቢያ አጣ ማለት ነው፤ እሱ ካልገባ ግብረ ኃጢኣት አንፈጽምም፤ በዚህ ጊዜ ዲያብሎስ ተሸናፊ እኛ ኣሸናፊዎች እንሆናለን፤ ስለሆነም ጾምን የምንጾመው በዚህ ስልት ዲያብሎስንና ግብረ ኃጢአትን ለማሸነፍ  ነው።

ከዚህ አኳያ ዲያብሎስን ለማሸነፍ መጾም ግድ ስለሆነ ጌታችን በከፈተልንና ባሳየን መንገድ እንጾማለን፤ እንግዲህ በወርኃ ጾም ከመልካም ኅሊና የሚመነጭ መልካም ስራ ማከናወን ግድ ይለናል፤  ምክንያቱም ጾምን የምንጾመው መልካም ኅሊና ኖሮን ለእግዚአብሔር ለመታዘዝና ለመገዛት፣ ከዚያም ከቃሉ በተነገረን መሠረት የተራቡትን ልንመግብ፣ የተራቈቱትን ልናለብስ፣ የተጣሉትን ልናስታርቅ፣ ፍትሕ ያጡትን ፍትሕ እንዲያገኙ ልናደርግ፣ ለንኡሳን የሕብረተ ሰብ ክፍሎች የተለየ ትኵረት ልንሰጥ፤ እኩልና ፍትሓዊ የሀብት ክፍፍል በሰው ልጆች መካከል ልናረጋግጥ፣ ሰብኣዊ ክብር እንዳይነካ ጦርነት፣ ጥላቻ፣ አደገኛ የቃላት ውርወራና መነቃቀፍ እንዲቀር ልናደርግ ነው ፤ በዚህ መንፈስ ጾሙን ከጾምን ጾማችን ግቡን መትቶአል፤ ዲያብሎስም ተሸንፎአል ማለት ነው፤ ስለሆነም በዚህ መንፈስ ጾሙን ልንጾም ይገባል፡፡

ወርኀ ጾሙን የተራበውን በመመገብ የተራቈተውን በማልበስ በኃላፊነት ያለን የኅብረተሰብ መሪዎችም ፍትሕንና እኩልነትን በማስፈንና ከነገሮች ሁሉ በፊት ለሰላምና ለአንድነት ቅድሚያ በመስጠት ጾሙን እንድናሳልፍ በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን። "

(የቅዱስነታቸው ሙሉ መልዕክት ከላይ ተያይዟል)

@Tsehaye_Tsidk
✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

22 Feb, 11:53

214

ምስጋና

ምስጋና ወደ ከፍታ መብረር ነው። በልባችን ያለውን እግዚአብሔር በሰማያት የምትኖር እንለዋለን። ምስጋና ወደ ከፍታ የምንበርበት መንኮራኩር ፣ መንፈሳዊ ሠረገላ ነው። የቅዱሳን ብቃት የምንለውም በተመስጦ መጥፋት ነው። ይህን ዓለም መተው ፣ ደመናትን ሰንጥቆ ሀገረ ሕይወት መንግሥተ ሰማያት መገኘት ነው። የተመስጦ ሕይወት የዓለምን ማቁሰል ፣ የሰይጣንን ጭካኔ የምንረሳበት ነው። ሰማይ እየደረሰ መመለስ የቻለ መራራው ጨርሶ አይመረውም። በምድር ጀምሮ በምድር መፈጸም ቀኑን ደመናማ ያደርገዋል። የምስጋና ክንፎች ወደ መንበረ ሥላሴ ያደርሳሉ። እዚያ ስንወጣ ትልቅ የሆነብን ነገር ሁሉ ትንሽ መረገጫ ይሆናል። ሁሉም ነገር ከምድር ሲያዩት ትልቅ ነው። ከሰማይ ሲያዩት ግን ትንሽ ነው። ምስጋና ወደ እግዚአብሔር መኖሪያ ወደማይዘጋው አደባባይ ፣ ግርዶሽ ወደ ሌለበት ቤት የሚወስድ ነው። ከጉዳያችን በላይ እግዚአብሔር ጉዳይ ሁኖ የምናመልከው የምስጋና ጣዕም ሲገባን ነው። ቤተ ክርስቲያን ለምስጋና ብቻ የምታሰለጥናቸው አዋቂዎች አሏት። በዓለም ላይም የምስጋና ትምህርት ቤት ያላት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ናት። የዋሸራው ቅኔ ፣ የቤተ ልሔሙ ድጓ ማስመስከሪያ ለስብሐተ ሥላሴ የተዘጋጀ ነው። ላለፉት ሁለት ሺህ ዓመታት የመዝሙር ዩኒቨርስቲ  ከፍታ የምታስመርቅ ይህች የበረሃ ጥላ የሆነች ቤተ ክርስቲያናችን ናት። ቀለሙ ዜማው በተመስጦ ይዞ ይጠፋል። በአንድ ቀለም ማታ የጀመረው ማኅሌት ይነጋል። በብዙ ግጥም ሳይሆን አንዱን ቀለም ሲያስተነትኑ ፣ ተመስጦው አልለቅ እያላቸው በጨለማ ሰዓት ጀምረው በንጋት ይላቀቃሉ። ምስጋናው እንደ ጎርፍ ነውና ማኅሌቱ ሲያበቃ ኪዳኑ ፣ ኪዳኑ ሲያበቃ ቅዳሴው ይቀጥላል። ሰማይንና ቀራንዮን በየዕለቱ የምትጋብዝ በአጭር ቃል የምትቀድስ ቤተ ክርስቲያን ናት። ማመስገን የራስን ፣ የዓለምን ፣ የክፋትን ግዛት ጥሶ ቀኙ ወደምታዝበት ከተማ መድረስ ነው።

ተመስጦ ያስፈልጋል። ትዕግሥትን የምንለማመደው በተመስጦ ነው። ነገረ እግዚአብሔርን የምናጣጥመው በተመስጦ ነው። ቃሉን ከሕይወታችን ጋር በቅድስና ስናዋሕደው ፣ በተመስጦ ደግሞ ከመንፈሳችን ጋር እናዋሕደዋለን። ቃሉ ሲመጣ ቤታችንን ያንኳኳል ፣ ተመስጦ ደግሞ የእግዜርን ደጃፍ ማንኳኳት ነው። የሚመሰጥ ትውልድ እያጣን ነው። ስለዚህ መራርነት ፣ ሌላውን ማጥቃት ፣ ጭካኔ ፣ ያልተረጋገጠ እውቀት። ምስጋና በማይታዩ ክንፎች ወደ ላይ መብረር ነው።

እስትፋሳችሁ በአፍንጫችሁ ያደረችላችሁ አመሰግኑ! ተመስገን ተመስገን !

#ይቀላቀሉ!!
@Tsehaye_Tsidk
@Tsehaye_Tsidk
✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

20 Feb, 20:48

239

"...በጾማችን የነፍሳችንን ክፉ ልማዶች ካላስወገድን ከሥጋ መከልከላችን ብቻውን ምን ይጠቅመናል?

ስንጾም ውለን ጾም ከመግባቱ በፊት እንመገበው የነበረውን ምግብ ለውጠን መናኛ የሆነ የጾም ምግብ በማዕዳችን አቀረብን፡ ሆኖም ግን በጸሙ የምንመገበውን ምግብ እንደ ለወጥን ክፉ ግብራችንን እና ሕይወታችንንስ አብረን ለውጠናል ይሆን?

በእውነት እኔ ግን እንዲህ ያደረጋችሁ አልመሰለኝም፤ እንዲህ ከሆነ መጸማችሁ ጥቅሙ ምንድን ነው? ስለዚህ ከጾማችሁ ጋር ልማዳችሁንና ሕይወታቸሁን ወደ መልካምነት ትቀይሩ ዘንድ በተከታታይ እንድታስቡበት አደርጋችሁ ዘንድ ስለዚህ ነገር እናንተን ማስተማርንና መገሠጽን አላቋርጥም።

(ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ፣ ትምህርት በእንተ ምክንያተ ሐውልታት)

አስታውሱ

ዐቢይ ጾም (ጾመ ሁዳዴ)
የካቲት 17/2017 ዓም (Feb. 24/2025) ይጀምራል
✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

18 Feb, 15:49

288

ገድሉ ትሩፋቱ እንደአሸዋ የበዛለት ኤልያስ የሚባል አንድ ባህታዊ ነበር፤ በቅርብ የሚያውቁት ገዳማውያን "አባታችን አንተ ከኤልያስ በላይ ነህ፡፡'' ይሉታል።

ይህ ቅዱስ አባት ''ኤልያስ እኮ አሞሮች የሚመግቡት ነቢይ ቅዱስ አባት ነው እኔ እኮ ምግቤን አሞሮች የሚቀሙኝ ሰው ነኝ" አለ ይላል ዜና ገድሉ። በረከቱ ይደርብንና

ክርስቲያናዊ ባሕርይ ይህ ነው፤ የክርስትና ባሕርይ የገባው ሰው ራሱን ከሌላው ጋርማወዳደር ማነጻጸር ያቆምና የቆመበትን ይመለከታል፤

በክርስትናው ባሕርይ ዝቅ ሳይሉ ከፍታ የለም ስለ ክርስቶስ ራስን ባዶ ማድረግ ሙሉ መሆን ነው። ስደተኛ መሆን ባለርስት መሆን ነው። ቅዱሳን መሬት የሚሆኑት (ራሳቸውን ዝቅ የሚያደርጉት) የቅድስናው ከፍታ ያለበትን ስለሚያውቁ ነው በረከታቸው ይደርብን!!!

   (አባ ገብረ ማርያም)
✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

17 Feb, 20:17

299

''ወዳጄ ሆይ! መንፈሳዊ ተጋድሎን አትፍራ፥ ከእርሱም አትሽሽ፡፡ ተጋድሎ ከሌለ ምግባር ትሩፋትም የለምና፡፡ እምነትና ፍቅርም ካልተፈተኑ በእውን ከአንተ ጋር ስለ መኖራቸው ርግጠኛ መኾን አይቻልምና፡፡ እነዚህ በርግጥ አንተ ገንዘብ አድርገሃቸው እንደ ኾነ የሚታወቀው መከራ ሲገጥምህ ነውና፡፡ ስለዚህ ተጋድሎን አትፍራ፥ ከእርሱም አትሽሽ።”

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

15 Feb, 07:30

344

“እናት ልጇን ዳዴ ስታስለምደው አስቀድማ እጁን ትይዘዋለች፡፡ እንዲሄድም ታደፋፍረዋለች፡፡ ትንሽ መሄድ ሲጀምር ትለቀዋለች፡፡ ትልቀቀው እንጂ ልቧ ሐሳቧ ሁሉ ግን ከልጇ ጋር ነው፡፡ ሊወድቅ ሲል ፈጠን ብላ ትደግፈዋለች፡፡

እግዚአብሔርም ለእኛ ለልጆቹ እንደዚህ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በእኛ እይታ ክፉ በሚመስሉ ሁኔታዎች እንድናልፍ ይፈቅዳል፤ ወርቅ ወርቅነቱ ይታወቅ ዘንድ በእሳት እንዲያልፍ፡፡ ነገር ግን ልክ እንደዚያች እናት በቅርብ ርቀት ሆኖ ይከታተለናል፡፡ ሐሳቡ ልቡ ሁሉ ከእኛ አይለይም፡፡ አንዳንድ ጊዜም ልንወድቅ እንችላለን፡፡ ነገር ግን መልሶ ያነሣናል፡፡ እዚህ ጋር መጠንቀቅ ያለብን ቢኖር በዚሁ የልምምድ ጊዜ ሰይጣን ያንን ሁናቴ ተጠቅሞ በክፉ ዐይን እንድናየው እንዳያስደርገን ብቻ ነው፡፡”

                   #ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ

@Tsehaye_Tsidk
@Tsehaye_Tsidk
✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

12 Feb, 09:31

351

#እየጾምኩ_ነው_የሚል_ሰው!

ተወዳጆች ሆይ! የምታደምጡ ብቻ አትኹኑ፤ ያስተማርኳችሁን ትምህርት ለሌሎችም በማስተላለፍ መምህራን ትኾኑ ዘንድ - ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “አንዱ ሌላውን ያንጸው” (1ኛ ተሰ.5፥11)፤ ዳግመኛም “በፍርሐትና በመንቀጥቀጥም የራሳችኁን መዳን ፈጽሙ” ብሎ እንደ ተናገረው በስሕተት ጐዳና ያሉትን ታድኑ ዘንድ መረባችሁን ጣሉ ብዬ እማፀናችኋለሁ (ፊልጵ.2፥12)፡፡ ይህን ስታደርጉ ቤተ ክርስቲያን ከመቼውም ጊዜ በላይ ትሰፋለች፤ እኛም ይህን ዐይተን እጅግ ደስ እንሰኝባችኋለን፡፡ እናንተም ለወንድሞቻችሁ፣ ለእኅቶቻችሁ ባሳያችሁት ፍቅር በሰማያት ዘንድ ታላቅ ማዕረግና ክብር ታገኛላችሁ፡፡ እንደምታውቁት የእግዚአብሔር ፈቃድ እያንዳንዱ ክርስቲያን ስለ ራሱ መዳን ብቻ እንዲያስብ አይደለም፤ ወንድሙንም እንዲያንጽ ነው እንጂ፡፡ ሲያንጸውም በቃል ብቻ አይደለም፤ በተግባርም ጭምር እንጂ፡፡ የእግዚአብሔር ፈቃዱ እያንዳንዳችን በአኗኗራችን ክርስቶስን መስለን ታምነን እንድንኖርና ፍጥረት ኹሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንዲገቡ ማድረግ ነው፡፡ ይኸውም ሰዎች ከምንናገረው በላይ የምንኖረውን ስለሚያምኑና ስለሚማርካቸው ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ በተዋቡ ቃላት ስለ ይቅርታ ብንናገር ነገር ግን በሕይወታችን እጅግ ቂመኞችና ይቅርታን የሚቀበል ልብ የሌለን ከኾነ ቃላችንና ሕይወታችን ስላልተስማማላቸው ሰዎች የምንለውን ነገር አያምኑንም፡፡ የምንናገረውንና የምናስተምረውን የምንኖረው ከኾነ ግን ያምኑናል፡፡ እውነቱን ለመቀበልም አይቸገሩም፡፡ በቃል መነገሩ፣ በልብ መታሰቡ፣ በቅዱሳት መጻሕፍት መዘገቡ ከፍ ከፍ ይበልና ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ ያለውን ክርስቲያን እንዲህ ሲል አመስግኖታል፡- “ #የሚያደርግም_የሚያስተምርም_እርሱ_ንዑድ_ክቡር_ነው ” (ማቴ.5፥19)፡፡

እንግዲህ ጌታችን ሲያስተምር በተግባር የሚሰጠውን ትምህርት በቃል ከሚሰጠው ትምህርት ይልቅ እንዳስቀደመው ታስተውላላችሁን? አያችሁ! ከተግባራችን በኋላ ቃላችን ባይከተል እንኳን ሰዎችን ወደ እውነት (ኢየሱስ ክርስቶስ ) ለማምጣት በቂ ነው፡፡

ስለዚህ በቃላችን ከመናገር በላይ በተግባር ክርስቲያኖች መኾናችንን እናሳያቸው፡፡ እንደዚህ ካልኾነ ግን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ሲል ይወቅሰናል፦ “ #አንተ_ሌላውን_የምታስተምር_ራስህን_አታስተምርምን ?” (ሮሜ.2፥21)፡፡

አንድ ሰው መንፈሳዊ ሕይወቱ የተስተካከለ መኾን እንደሚገባው ለመምከር የምናስብ ከኾነ እኛው ቀድመን የራሳችንን ሕይወት በተግባር ልንስተካከል ይገባናል፡፡ ይህን የምናደርግ ከኾነ የምንሰጠው ምክር ተአማኒነት አለው፡፡ የሌሎች ሰዎች ነፍስ መዳን የሚያስጨንቀን ከኾነ ከምንም በፊት እኛው ራሳችን ስለ ራሳችን መዳን እንጨነቅ፡፡ ሌሎች ሰዎች ራሳቸውን መግዛት እንዲችሉ የምንሻ ከኾነ ከማንም በፊት እኛው ራሳችን ያንን አድርገን እናሳያቸው፡፡ ትክክለኛ ጾም ማለትም ይኸው ነው፡፡ ለተወሰነ ሰዓት ከምግበ ሥጋ የመከልከላችን ዓላማም ራሳችንን መግዛት እንድንችል ነው፡፡

ስለዚህ እየጾምኩ ነው የሚል ሰው ካለ ከምንም በፊት፡-  #ትዕግሥተኛ ፣ #ልበ_ትሑትና  #የዋህ ፣ #እግዚአብሔርን_የሚፈራ_ልቦና_ያለው፣
#የፍትወታትን_ጅረት_ከኹለንተናው_የሚያስወግድ ፣ #ዘወትር_በልቡናው_ዕለተ_ምጽአትን_የሚያስብ ፣   #በእግዚአብሔር_የፍርድ_ዙፋን_ፊት_እንደሚቆም_የማይረሳ ፣ #በፍቅረ_ንዋይ_ወጥመድ_ተይዞ_ምጽዋትን_የማይጠላ ፣ #ወንድሙን_ከልቡ_የሚወድ_ይኹን ፡፡ እውነተኛ ጾም ማለት ይኼ ነውና፡፡

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ

#ይቀላቀሉን!!
@Tsehaye_Tsidk
@Tsehaye_Tsidk
✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

11 Feb, 12:25

293

"እንግዲህ ከወዴት እንደ ወደቅህ አስብ ንስሐም ግባ የቀደመውንም ሥራህን አድርግ፤ አለዚያ እመጣብሃለሁ ንስሐም ባትገባ መቅረዝህን ከስፍራው እወስዳለሁ።"
(የዮሐንስ ራእይ 2:5)


አምላከ ቅዱሳን ዘውትር ለንሰሐ የነቃ ልቦናን ያድለን!!....❤️‍🩹🙏
✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

02 Feb, 14:57

49

ሸጋ መልዕክት አላት፦

አባት ልጁ ከቤት ወጥቶ መኪና እንዳይገጭበት፣ ወድቆ እንዳይሰበርበት፣ ድንገት በአከባቢው የሚያልፉ ከብቶች ገፍተው እንዳይጥሉበት መውጫው በሩን ይዘጋበታል፡፡ ይኼኔ ልጁ በሩ ለምን እንደተዘጋበት አያውቅም፤ ልጅ ነውና፡፡ አባቱ የጠላው መስሎትም ምርር ብሎ ሊያለቅስ ይችላል፡፡ ማልቀስ ብቻ አይደለም፤ ቂምም ሊይዝበት ይችላል፡፡ አባቱ ግን በሩን የዘጋበት ምክንያት ያውቃል፤ ጠልቶት ሳይሆን ይጐዳበታልና ልጁ ቢያለቅስም አይከፍትለትም፡፡

እውነተኛው አባታችን እግዚአብሔርም አንዳንድ ጊዜ የማይጠቅሙን ይልቁንም ክፉኛ ሊጎዱን የሚችሉ በሮችን ይዘጋብናል፡፡ ከእውቀት ከፍለን የምናውቅ ልጆቹ ነንና አባታችን ለምን እንደዘጋብን ለጊዜው አይታወቀንም፤ ብቻ የከለከለን ይመስለናል፡፡ በመሆኑም ቂም ልንይዝበት ልናማርረውም እንችላለን፡፡ እርሱ ግን ይታገሠናል፤ ለእኛ የሚያስባት መልካሚቱን በር እርሱ ያውቃታልና ይከፍትልናል፤ በእኛ እይታ መልካም የምትመስለንን ነገር ግን ክፉይቱን በር ይዘጋብናል፡፡

ቅዱስ አባት ሆይ ስለ ከፈትክልን ብቻ ሳይሆን ስለ ዘጋህብንም በር እናመሰግንሃለን፡፡ አሜን!

በደህና ቆዩልኝ ❤️‍🩹 🤗
✞ ፀሐየ ጽድቅ ✞

31 Jan, 19:40

110

በቤተ ክርስቲያን 5 አይነት አክሊላት አሉ
1 አክሊለ ሰማዕት
ይህ አክሊል ሰማእታት በተጋድሎ የሚያገኙት አክሊል ነው ቅዱስ ጳውሎስም ስለዚህ አክሊል ሲናገር ሃይማኖቴን ጠብቄለው ሩጫዬን ጨርሻለው ወደፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል ብሎ ጠቅሶታል
2 ጢሞ 4+6-7
በተመሳሳይ ባለራዕዩ ቅዱስ ዮሐንስም እስከሞት ድረስ የታመንክ ሁን የሕይወት አክሊል እሰጥሃለው ብሎ የተናገረው ስለ ሰማእታት አክሊል ነው ራዕ 2+10 ክርስቶስም አክላሎሙ ለሰማእት ተብሏል እመቤታችንም አክሊለ ሰማእት ትባላለች

2 አክሊለ ሶክ (አስኬማ መላእክት)
ይሄ አክሊል የአባ እንጦንዮስ አክሊል ሲሆን መነኮሳት የሚያደርኩት አክሊል ነው ይሄ አክሊል በምንኩስና ዓለምን ከናቁ በኋላ የሚገኝ ነው ክርስቶስ በዕለተ አርብ የተቀበለው አክሊለ ሶክ የሚታሰብበት ሲሆኔ ይሄን አክሊል ያደረጉ መነኮሳት እንደ መላእክት በንጽሕና በቅድስና ስለሚኖሩ አስኬማ መላእክት ተብሏል

3 ተክሊል (የተክሊል አክሊል)
ይህ አክሊል በድንግልና ኑረው ለሚጋቡ ኦርቶዶክሳውያን የሚደረግ የድንግልና ምልክት የሆነ አክሊለ ከብካብ ነው ደናግል ላልሆኑ ፈጽሞ የማይደረግ ነው

4 አክሊለ ነገሥት ይህ አክሊል ለነገሥታት ብቻ የሚደረግ ነው ሰሎሞን ሲነግሥ ሲቀባ የተደረገለት አክሊል ነው አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው ወአክሊሉ ለሰሎሞን የሰሎሞን አክሊል ነሽ ብሎ የተናገረው የነገሥታት አክሊል እመቤታችን እንደሆነችና ነገሥታት ሲነግሢ ተቀብተው አክሊል እንደሚያደርጉ ለመግለጽ ነው

5 አክሊለ ካህናት
ይህ አክሊል በክህነት የሚያገለግሉ ካህናትና ዲያቆናት የሚያደርርጉት አክሊል ነው
ክህነት ለሌለው ፈጽሞ የማይደረግ ሲሆን የካህናት አክሊል አሰራሩ ከላይ 4 ማዕዘን ሲሆን የዲያቆናት አክሊለም በአሰራር ከካህናት የተለየ ክብ ነው ዲያቆን የቄሱን አክሊል ፈጽሞ ማድረግ አይችልም አምስቱ አክሊላት እነዚህ ናቸው
አሁን አሁን ግን የካህኑን እና የዲያቆኑን አክሊል ሴቶች ሳይቀር አድርገውት እየታየ ስለሆነ እጅግ የሚያሳዝን ነው
ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እየተጣሰ ቸል ተብሎ እየታየ ነው ስለዚህ የሊቃውንት ጉባኤ ይሄን ጉዳይ እልባት ሊሰጥበት ይገባል
መጋቤ ሐዲስ ሄኖክ ፈንቴ