ግንባታ ሳያጠናቅቁ ቤቶችን የሚሸጡ ሪልስቴቶች የሚሰበስቡትን ገንዘብ በዝግ የባንክ ሂሳብ እንዲያስቀምጡ በአዋጅ ሊገደዱ መሆኑ ተሰማ፡፡
ያልተገነባ ቤት (ግንባታ ከማከናወናቸው በፊት) ቤት የሚሸጡ ሪል ስቴት አልሚዎች የሚሰበስቡትን ገንዘብ በዝግ አካውንት እንዲያስቀምጡ ሊገደዱ ነው፡፡ በተጨማሪ ግንባታው 80 በመቶ ላይ ያልደረሰን ቤት ለደንበኞች እንዳያስተላልፉ ሊከለከሉ መሆኑም ተሰምቷል።
ግንባታ ከማከናወናቸው አስቀድመው ቤት የሚሸጡ ሪል ስቴት አልሚዎች፤ ከደንበኞቻቸው የሚሰበስቡትን ገንዘብ በዝግ የባንክ አካውንት እንዲያስቀምጡ የሚያስገድድ ረቂቅ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቧል። አዲሱ ረቂቅ አዋጅ፤ ቤት ለመገንባት የመሬት የይዞታ ማረጋገጫ እና የግንባታ ፈቃድ ያላገኙ የሪል ስቴት አልሚዎች ደንበኞችን እንዳይመዘግቡ እና ቅድመ ክፍያ እንዳይሰበስቡም ይከለክላል።
“የሪል ስቴት ልማት እና የማይንቀሳቀስ ንብረት ግብይትና ግመታ” የተሰኘው ረቂቅ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው በትላንትናው እለተ መስከረም 30 ቀን 2017 ዓ.ም በተደረገው የህዝብ እንደራሴዎች አራተኛ ዓመት የሥራ ዘመን የመጀመሪያ መደበኛ ስብሰባ ላይ ነው።
በስብሰባው ላይ ከቀረቡት አራት ረቂቅ ሕጎች መካከል የሆነው ይህ አዋጅ፤ ከዚህ ቀደም ራሱን የቻለ ሕግ ላልነበረው የሪል ስቴት ቤቶች የግንባታ እና ግብይት ሂደት አዲስ እና አሳሪ አሠራሮችን ያስተዋወቀ ነው። እንደ ሕንጻ ያሉ የማይንቀሳቀስ ንብረቶች ያላቸው ዋጋ በመንግሥት እንዲሁም በግል ባለሙያዎች የሚገመትበትን እንዲሁም ግመታው አገልግሎት ላይ የሚውልበት አሠራርም በረቂቅ አዋጁ ላይ ተቀምጧል።
ከረቂቅ አዋጁ ጋር አብሮ ለምክር ቤቱ የቀረበው ማብራሪያ የሪል ስቴት ልማት፣ ግብይት እና የዋጋ ትመና “በቂ የሕግ ሥርዓት የሌለው በሕገ-ወጥ ደላሎዎች ተጽዕኖ ስር የወደቀ” እንደሆነ ያስረዳል። የሪል ስቴት ልማት ካለው የቤት ፍላጎት “በእጅጉ የራቀ” እንዲሁም “በሕገ-ወጥ መንገድ በሚንቀሳቀሱ ደላላ ተብለው በሚታወቁት አካላት” ተፅዕኖ ስር የወደቀ እንደሆነ በማብራሪያው ላይ ሰፍሯል።
አዲሱ ረቂቅ አዋጅ፤ በዚህ ዓይነት መልኩ ለግንባታ የሚውለውን ሀብት ማሰባሰብ የሚፈልጉ አልሚዎች አግባብ ካለዉ አካል ፈቃድ ማቅረብ እንደሚጠበቅባቸው ያሳስባ፤ ይህም ግዴታ መሆኑን ያብራራል።
የቅድመ ሽያጭ ዘዴን መጠቀም የሚፈልጉት ሪል ስቴት አልሚዎች፤ ከቤት ገዢዎች የሚሰበስቡት ገንዘብ የሚቀመጥበት የባንክ ሂሳብ እና የገንዘብ አወጣጥ ላይም አስገዳጅ አሠራር በረቂቅ አዋጁ ተጥሎባቸዋል።
አዲሱ ሕግ፤ ገንዘቡ የሚቀመጥበት ዝግ የባንክ አካውንት የሚከፈተው " አግባብ ባለው አካል ፈቃድ መሠረት " እንደሆነም ያስረዳል። በዝግ የባንክ ሂሳብ ገቢ የተደረገው ገንዘብ የሚለቀቅበት ሁኔታ ከረቂቅ አዋጁ መፅደቅ በኋላ በሚወጣ ደንብ ይወሠናል።
ከዚህም ባሻገር በቅድሚያ የተሸጠው ቤት ተገንብቶ ለተጠቃሚዎች እስከሚተላለፍ ድረስ የቤት የመሥሪያ ቦታው የይዞታ ማስረጃ " በሚመለከተው አካል እንዳይሸጥ፣ እንዳይለወጥ " እንደሚታገድ ረቂቁ ይገልጻል።