Nahoo TV

@nahootelevision


Nahoo TV

11 Oct, 18:21


ትምህርት ሚኒስቴር የትምህርት መስክ የምርጫ መሙያ ጊዜውን ማራዘሙን አስታወቀ፡፡
በ2016 ትምህርት ዘመን የ12ኛ ክፍል ማጠቃለያ አገር አቀፍ ፈተና ወስደው ለትምህርት ሚኒስቴር ተጠሪ በሆኑ የመንግስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በመደበኛ እና በ 'Remedial' ፕሮግራም ለመከታተል የሚያስችል ማለፊያ ውጤት ያስመዘገቡ ተማሪዎች የተቋም እና የትምህርት መስክ ምርጫቸውን በየትምህርት ቤታቸው በተወከሉ መምህራን በኩል እስከ መስከረም 30 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ሞልተው እንዲጨርሱ መገለጹ ይታወሳል።
ይሁን እንጂ እስከ ትላንት መስከረም 30 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ሞልተው እንዲጨርሱ የተገለጸ ቢሆንም አንዳንድ ትምህርት ቤቶች “በሲስተም ችግር ምክንያት የተማሪዎቻችንን የትምህርት መስክ እና የዩኒቨርስቲ ምርጫ መሙላት ተቸግረናል” ብለዋል፡፡
በመሆኑም የትምህርት ሚኒስቴር የምርጫ መሙያ ጊዜውን እስከ መጪው ረቡዕ ጥቅምት 6 ቀን2017 ዓ.ም ድረስ ማራዘሙን ትምህርት ሚኒስቴር ይፋ አድርጓል።

Nahoo TV

11 Oct, 18:17


ግንባታ ሳያጠናቅቁ ቤቶችን የሚሸጡ ሪልስቴቶች የሚሰበስቡትን ገንዘብ በዝግ የባንክ ሂሳብ እንዲያስቀምጡ በአዋጅ ሊገደዱ መሆኑ ተሰማ፡፡
ያልተገነባ ቤት (ግንባታ ከማከናወናቸው በፊት) ቤት የሚሸጡ ሪል ስቴት አልሚዎች የሚሰበስቡትን ገንዘብ በዝግ አካውንት እንዲያስቀምጡ ሊገደዱ ነው፡፡ በተጨማሪ ግንባታው 80 በመቶ ላይ ያልደረሰን ቤት ለደንበኞች እንዳያስተላልፉ ሊከለከሉ መሆኑም ተሰምቷል።
ግንባታ ከማከናወናቸው አስቀድመው ቤት የሚሸጡ ሪል ስቴት አልሚዎች፤ ከደንበኞቻቸው የሚሰበስቡትን ገንዘብ በዝግ የባንክ አካውንት እንዲያስቀምጡ የሚያስገድድ ረቂቅ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቧል። አዲሱ ረቂቅ አዋጅ፤ ቤት ለመገንባት የመሬት የይዞታ ማረጋገጫ እና የግንባታ ፈቃድ ያላገኙ የሪል ስቴት አልሚዎች ደንበኞችን እንዳይመዘግቡ እና ቅድመ ክፍያ እንዳይሰበስቡም ይከለክላል።
“የሪል ስቴት ልማት እና የማይንቀሳቀስ ንብረት ግብይትና ግመታ” የተሰኘው ረቂቅ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው በትላንትናው እለተ መስከረም 30 ቀን 2017 ዓ.ም በተደረገው የህዝብ እንደራሴዎች አራተኛ ዓመት የሥራ ዘመን የመጀመሪያ መደበኛ ስብሰባ ላይ ነው።
በስብሰባው ላይ ከቀረቡት አራት ረቂቅ ሕጎች መካከል የሆነው ይህ አዋጅ፤ ከዚህ ቀደም ራሱን የቻለ ሕግ ላልነበረው የሪል ስቴት ቤቶች የግንባታ እና ግብይት ሂደት አዲስ እና አሳሪ አሠራሮችን ያስተዋወቀ ነው። እንደ ሕንጻ ያሉ የማይንቀሳቀስ ንብረቶች ያላቸው ዋጋ በመንግሥት እንዲሁም በግል ባለሙያዎች የሚገመትበትን እንዲሁም ግመታው አገልግሎት ላይ የሚውልበት አሠራርም በረቂቅ አዋጁ ላይ ተቀምጧል።
ከረቂቅ አዋጁ ጋር አብሮ ለምክር ቤቱ የቀረበው ማብራሪያ የሪል ስቴት ልማት፣ ግብይት እና የዋጋ ትመና “በቂ የሕግ ሥርዓት የሌለው በሕገ-ወጥ ደላሎዎች ተጽዕኖ ስር የወደቀ” እንደሆነ ያስረዳል። የሪል ስቴት ልማት ካለው የቤት ፍላጎት “በእጅጉ የራቀ” እንዲሁም “በሕገ-ወጥ መንገድ በሚንቀሳቀሱ ደላላ ተብለው በሚታወቁት አካላት” ተፅዕኖ ስር የወደቀ እንደሆነ በማብራሪያው ላይ ሰፍሯል።
አዲሱ ረቂቅ አዋጅ፤ በዚህ ዓይነት መልኩ ለግንባታ የሚውለውን ሀብት ማሰባሰብ የሚፈልጉ አልሚዎች አግባብ ካለዉ አካል ፈቃድ ማቅረብ እንደሚጠበቅባቸው ያሳስባ፤ ይህም ግዴታ መሆኑን ያብራራል።
የቅድመ ሽያጭ ዘዴን መጠቀም የሚፈልጉት ሪል ስቴት አልሚዎች፤ ከቤት ገዢዎች የሚሰበስቡት ገንዘብ የሚቀመጥበት የባንክ ሂሳብ እና የገንዘብ አወጣጥ ላይም አስገዳጅ አሠራር በረቂቅ አዋጁ ተጥሎባቸዋል።
አዲሱ ሕግ፤ ገንዘቡ የሚቀመጥበት ዝግ የባንክ አካውንት የሚከፈተው " አግባብ ባለው አካል ፈቃድ መሠረት " እንደሆነም ያስረዳል። በዝግ የባንክ ሂሳብ ገቢ የተደረገው ገንዘብ የሚለቀቅበት ሁኔታ ከረቂቅ አዋጁ መፅደቅ በኋላ በሚወጣ ደንብ ይወሠናል።
ከዚህም ባሻገር በቅድሚያ የተሸጠው ቤት ተገንብቶ ለተጠቃሚዎች እስከሚተላለፍ ድረስ የቤት የመሥሪያ ቦታው የይዞታ ማስረጃ " በሚመለከተው አካል እንዳይሸጥ፣ እንዳይለወጥ " እንደሚታገድ ረቂቁ ይገልጻል።

Nahoo TV

11 Oct, 18:14


የሽግግር ፍትህ ልዩ ችሎት በዚህ ዓመት ስራ እንደሚጀምር ጠቅላይ ፍ/ቤት አስታወቀ፡፡
የፌደራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት ቴዎድሮስ ምህረቱ በ2017 ዓ.ም የሽግግር ፍትህ ልዩ ችሎትን ስራ ለማስጀመር መታቀዱን አስታውቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ይህን ያሉት የፌደራል ፍርድ ቤቶች የ2017 ዓ.ም መደበኛ የዳኝነት ስራን ባስጀመሩበት ወቅት ነው፡፡
በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ባለፈው አመት የተስተዋሉ ግድፈቶች መኖራቸውን የተቆሙት አቶ ቴዎድሮስ በተያዘው ዓመት ችግሮችን ፈቶ ለመንቀሳቀስ እንደሚሰራም ጠቁመዋል፡፡
በተጨማሪም በ2017 ዓ.ም በልዩ ትኩረት ተቋማዊ ነፃነትን የጠበቀ የፍትህ ስርዓትን ማጠናከር፣ ለዳኞች ምቹ የስራ ሁኔታ መፍጠር፣ የተጠያቂነት ስርዓትን በአግባቡ መተግበር፣ የሽግግር ፍትህ ልዩ ችሎትን ማቋቋምና ሌሎችም የማሻሻያና አዳዲስ አሰራሮች በፍ/ቤቶች ይከወናሉም ነው ያሉት።

Nahoo TV

07 Oct, 09:10


በሀገሪቱ እየተስተዋለ ለሚገኘው የትምህርት ስብራት የቤተመፅሀፍት አቅርቦት ውስንነት እና የአጠቃቀም ክፍተት ዋንኛ ምክንያቶች መሆናቸው ተጠቆመ።

በጌድዮ ዞን ዲላ ከተማ በሀገሪቱ በአሳሳቢ ሁኔታ ላይ የሚገኘውን የትምህርት ስብራት ለማስተካከል ያለመ የፓናል ውይይት ተካሂዷል። በዚህ ውይይት ላይ የኢትዮጵያ ቤተ-መፃህፍትና ቤተ-መዛግብት አገልግሎት ተወካዮች፣ በዞኑ የሚገኙ የዘርፉ ሙሁራን፣ የዲላ ዩንቨርስቲ ፕሬዝዳንት እንዲሁም የዲላ ከተማ ትምህርት ፅ/ቤት ሀላፊዎች ተገኝተዋል።

በፓናል ውይይቱ ላይ በርካታ ጥናታዊ ፅሁፎች የቀረቡ ሲሆን፤ የሀገሪቱን የትምህርት ጥራት ያለበትን አሳሳቢ ሁኔታ የሚገመግሙ ናቸው። በሀገሪቱ የትምህርት ስርአት ላይ የተማሪዎች የቤተመፅሀፍት አቅርቦት ውስንነት እንዲሁም  የአጠቃቀም ክፍተት በትምህርት ስርአቱ ላይ አሁን ለተፈጠረው ክፍተት ሚናቸው የጎላ መሆኑም በቀረቡ ጥናቶች ተመላክተዋል።

ከዚህም ባሻገር በትምህርት ላይ የሚገኙ ታዳጊ ተማሪዎች የትምህርት እና ትርፍ ጊዜያቸውን የሚያሳልፉት በአላስፈላጊ ተግባራት መሆኑን ጥናታዊ ፅሁፎቹ በችግር ለይተዋል።

ይሁን እንጂ ማደግ ያልቻለው የሀገሪቱ የንባብ ባህልም፤ በትምህርት ዘርፉ ላይ እየታየ ላለው ውድቀት ሌላኛው ትልቅ ምክንያት መሆኑም በቀረቡ ጥናታዊ ፅሁፎች ተጠቁሟል።

አሳሳቢውን የሀገሪቱን የትምህርት ውድቀት ለማሻሻልም የንባብ ባህልን ማሳደግ፣ የቤተ መፅሀፍትን ስርጭት ማስፋፋት እንደሚገባ በፓናል ውይይቱ በቀረቡ ጥናታዊ ፁሁፎች ምክረሀሳብ ቀርቧል።

በተጨማሪም አየወደቀ የሚገኘውን የትምህርት ስርአት ለመታደግ ብሎም ሀገሪቱን ከገጠሟት ሁለንተናዊ ቀውሶች ለማትረፍ፤ ማህበረሰቡ ለትምህርት ዘርፉ ልዩ ትኩረትና ክትትል እንዲያደርግ ተጠቁሟል።

የፓናል ውይይቱ የኢትዮጵያ ቤተ-መፅሀፍትና ቤተ-መዛግብት አገልግሎት ከዲላ ዩኒቨርስቲ ጋር በትብብር ያዘጋጁት የንባብ ፌስቲቫል አንድ አካል ነው።

ዘገባው የባልደረባችን ማርቆስ ጎዴቦ ነው።

Nahoo TV

04 Oct, 15:35


እንኳን ለእሬቻ በአል በሰላም አደረሳችሁ።
Baga Ayyaana Irreechaa Nagaan Geessan !
ናሁ ቴሌቭዥን
Nahoo Television

Nahoo TV

03 Oct, 09:09


በኢሬቻ ሆራ ፊንፊኔ በዓል አከባበር ወቅት ለተሽከርካሪ ዝግ የሚሆኑ መንገዶች ይፋ ሆኑ
በርካታ ህዝብ የሚታደምበት የኢሬቻ ሆራ ፊንፊኔ በዓል መስከረም 25 ቀን 2017 ዓ/ም በአዲስ አበባ ይከበራል፡፡
በዓሉ በሠላም እንዲከበር የፀጥታ አካላት ትኩረት ሰጥተው ወደ ተግባር በመግባት እየሰሩ መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅሶ በተለይ በዓሉ ወደሚከበርበት ስፍራ የሚመጡ ታዳሚዎች ለጋራ ደህንነት ሲባል ፍተሻ መኖሩን ተገንዝበው አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉ ተጠይቋል፡፡
በመሆኑም የኢሬቻ ሆራ ፊንፊኔ በዓል ተከብሮ እስከሚጠናቀቅ
• ከቅዱስ ኡራኤል አደባባይ ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ቅዱስ ኡራኤል አደባባይ ላይ
• ከቦሌ አቅጣጫ ወደ መስቀል አደባባይ ለሚመጡ ተሽከርካሪዎች ኦሎምፒያ አደባባይ ላይና ታች እንዲሁም ግራና ቀኝ
• ከመስቀል ፍላወር ወደ ኦሎምፒያ የሚወስደው መንገድ ጋዜቦ አደባባይ ላይ
• ከአጎና ሲኒማ ወደ መስቀል አደባባይ ለከባድ ተሽከርካሪ አጎና ሲኒማ አጠገብ እንዲሁም ለቀላል ተሽከርካሪ ጥላሁን አደባባይ (አራተኛ ክፍለ ጦር ላይ)
• ከለገሀር መብራት ወደ መስቀል አደባባይ ለገሀር መብራት ላይ
• ከቴሌ ማቋረጫ ወደ ስታድዮም ለሚጓዙ ቴሌ ማቋረጫ
• ከራስ ሆቴል ወደ ስታድዮም ለሚመጡ ተሽከርካሪዎች ራስ ሆቴል ላይ
• ከሃራምቤ መብራት ወይም ከአምባሳደር ሲኒማ ወደ መስቀል አደባባይ ሃራምቤ መብራት ላይ
• ከብሔራዊ ቤተ መንግስት ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ብሔራዊ ቤተ መንግስት አጠገብ
• ከካዛንቺስ ሼል ወደ ባምቢስ የሚወስደው መንገድ ካዛንቺስ ሼል አጠገብ እንዲሁም
• ከጁፒተር ሆቴል ወደ ECA የሚወስደው መንገድ ባምቢስ ሳልኮት ህንፃ አጠገብ
ከመስከረም 24 ቀን 2017 ዓ/ም ከቀኑ 6፡00 ሰዓት ጀምሮ ፕሮግራሙ እስከሚጠናቀቅ ድረስ መንገዶቹ ለተሽከርካሪ ለጊዜዉ ዝግ እንደሚሆኑ አስታውቋል፡፡
በአዲስ አበባ ዙሪያ ከሚገኙ የሸገር ከተማ አካባቢዎች በርካታ ህዝብ በዓሉን ለማክበር ከዋዜማው ጀምሮ ወደ ከተማችን የሚገባ በመሆኑ መላው ህብረተሰብ ተገቢውን አክብሮት በመስጠት የእንግዳ ተቀባይነት እሴታችንን አጉልቶ ሊያሳይ እንደሚገባ የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውሶ በዓሉ በሚከበርበት ዙሪያ እና በአካባቢው በግራና በቀኝ ለረጅምም ሆነ ለአጭር ጊዜ ተሽከርካሪ አቁሞ መሄድ ፍፁም የተከለከለ መሆኑን ገልጿል፡፡

Nahoo TV

02 Oct, 09:24


ኢሕአፓ በትግራይ ክልል ይፋዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ መጀመሩን አስታወቀ፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ሰሞኑን ባወጣው እና ለጣቢያችን በላከወው ወቅታዊ መግለጫው፣ እንደ አንድ አገራዊ ፓርቲ በትግራይ ክልል ውስጥ ድርጅታዊ እንቅስቃሴ መጀመሩን አስታውቋል፡፡
ኢሕአፓ ‹‹ኅብረ ብሔራዊ ኢሕአፓ ዛሬም የትግራይም ጭምር ነው›› በሚል ርዕስ ባወጣው መግለጫ፣ ፓርቲው በትግራይ ክልል ውስጥ እንደ አንድ አገራዊ ፓርቲ መከሰቱ፣ እና ሥራውን ለመጀመር መቻሉ ለመላው ኢትዮጵያውያን እንደ አንድ ትልቅ ተስፋ የሚቆጠር ነው ብሏል፡፡
ፓርቲው በመግለጫው የኢሕአፓ አባላት በትግራይ ክልል ከሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር መልካም ግንኙነትን እንዲፈጥሩ ለማስቻል እየሠራ ነው፡፡ ከመላው የትግራይ ወጣቶች ጋር ለመሥራትም ጥሪ አቅርቧል፡፡
በወታደራዊ ደርግ የስልጣን ዘመን ተቋቁመው ከፍተኛ የፖለቲካ ትግል ሲያደርጉ ከነበሩ ፓርቲዎች ውስጥ አንዱ ኢሕአፓ እንደነበረ ያስታወሰው መግለጫው፣ የትግራይ ወጣቶች ከምሥረታው ጀምሮ በወቅቱ በነበረው ትግል ውስጥ የነበራቸውን ከፍተኛ ሚና ዘርዝሯል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎች ተደራሽነቱን ለማስፋት ባለው ድርጅታዊ ዕቅድ መሠረት ጠንክሮ እየሠራ መሆኑን የገለፀው ኢሕአፓ፣ ከትግራይ ክልል በተጨማሪ በቅርቡ በጋምቤላ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሊከፍት መሆነኑን አስታውቋል፡፡
ፓርቲው በትግራይ ክልል ዋና ከተማ መቐለ የመጀመሪያ ቅርንጫፉንና ዋና ጽሕፈት ቤቱን የከፈተ ሲሆን፣ በቀጣይ በአዲግራትና በአክሱም ከተሞች ተጨማሪ ጽሕፈት ቤቶች ለመክፈት በዝግጅት ላይ እንደሆነ ገልጧል፡፡ በክልሉ በሰባት አባላት ኮሚቴ ተቋቁሞ የአመራርና የአባላት ምርጫ ተደርጎ በይፋ ሥራ መጀመሩንም ፓርቲው አስታውቋል፡፡

Nahoo TV

02 Oct, 09:23


የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተጠናቀቀው የ2016 በጀት ዓመት 14 ሚሊየን መንገደኞችን ያጓጓዘ ሲሆን ለዚህምየደህንነት መስሪያ ቤቱ ሚና ከፍተኛ እንደነበር ተገለፀ፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ያስተናገዳቸው 14 ሚልዮን መንገደኞችና በርካታ ጭነቶች ያለ ምንም የደኅንነት ስጋቶችና ክፍተቶች እንዲጓጓዙ በማድረግ ረገድ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ሚና ከፍተኛ እንደነበር ተመላክቷል፡፡
ለዚህ ስኬት የላቀ አስተዋፅኦ ላበረከቱ የአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ አመራሮችና አባላት እንዲሁም ባለድርሻ አካላት እውቅና እንደተሰጣቸው የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አስታውቋል፡፡
አገልግሎት መስሪያ ቤቱ ለመገናኛ ብዙኃን በላከው መረጃ እንዳመለከተው፤ ተቋሙ ከተሰጡት ቁልፍ ተልዕኮዎች ውስጥ በኢትዮጵያ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪው ደኅንነት የተረጋገጠ እንዲሆን ማድረግ ነው፡፡
በዚህም በአፍሪካ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ የጎላ ስም ያለው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ያስተናገዳቸው 14 ሚልዮን የሀገር ውስጥና ዓለምአቀፍ መንገደኞችና ትላልቅ ጭነቶች ያለ ምንም የደኅንነት ስጋቶችና ክፍተቶች እንዲጓጓዙ ማድረግ ተችሏል፡፡
ተቋሙ የአቪዬሽን ደኅንነትን ለማረጋገጥ የሚሠማሩ ባለሙያዎችን በማሰልጠን፣ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ሥራ ላይ በማዋልና በተጓዦችና በንብረቶች ላይ ተገቢውን የደኅንነት ፍተሸ በማድረግ በ2016 በጀት ዓመት ምንም አይነት የደኅንነት ስጋቶች እንዳይኖሩ ማድረጉን አገልግሎት መስሪያ ቤቱ ጠቁሟል፡፡
በአቪዬሽን ኢንዱስትሪው የደኅንነት ዘርፍ ለተገኘው ስኬትና በደኅንነት ልዩ ኦፕሬሽን ዋና መምሪያ በኩል ለተገኘው እመርታ ርብርብ ላደረጉ የሥራ ክፍሎች፣ ሠራተኞችና ባለድርሻ አካላትም ምስጋና አቅርቧል፡፡
የደኅንነት ልዩ ኦፕሬሽን ዋና መምሪያ ባለሙያዎች በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የአቅም ግንባታ ሥልጠናዎችን እንዲያገኙ መደረጉንም አገልግሎቱ አስታውቋል፡፡ በአዲስ አበባ የተካሄደው 37ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ፣ ሃይማኖታዊና ህዝባዊ ባዕላትን ከበርካታ ሀገራት የመጡ የሀገር መሪዎችን እንዲሁም ቁልፍ የመንግሥት ተቋማት እና አመራሮችንና በአስተማማኝ ሁኔታ በመጠበቅ በደኅንነቱ መስክ የተገኙ የዓመቱ ስኬቶች እንደሆኑም ጭምር መግለፃቸውን መረጃው አመልክቷል፡፡