የኬንያ መንግሥት በመዲናዋ ናይሮቢ ይኖሩ የነበሩ አራት ጥገኝነት ጠያቂ ቱርካውያንን በአስገዳጅ ሁኔታ ወደ አገራቸው እንዲመለሱ አድርጓል።
ይህ ድርጊትም ሰዎችን ነጻነታቸው እና ሕይወታቸው አደጋ ላይ የሚወድቅበት በመሆኑ ሁኔታው እንዳሳሰበው የመንግሥታቱ ድርጅት አስታውቋል።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ከፍተኛ የስደተኞች ኮሚሽን ከኬንያ ወደ ቱርክ የተመለሱት ስደተኞች ሁኔታ እንዳሳሰበው ገልጿል።
የመንግሥታቱ ድርጅት ይህንን መግለጫ ያወጣው በኬንያ መዲና ናይሮቢ ባለፈው አርብ ጥቅምት 08/2017 ዓ.ም. በርከት ያሉ ውጭ አገር ዜጎች መታገታቸውን ተከትሎ ነው።