በዚያም ዘመን የነበሩት የኢትዮጵያ ጳጳሳት የነበሩት አባ ሚካኤልና አባ ገብርኤል የተባሉ ከንጉሡ ከዓፄ ዘርዐ ያዕቆብ ጋር ሆነው የምሕረት ቃል ኪዳን ለመቀበል በዚህች በግሸን ደብር ሱባዔ ገብተዋል፡፡ በሱባዔአቸውም በመጨረሻ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾ ‹‹ይህች ቦታ እኔ ተወልጄ ያደኩባትን ኢየሩሳሌምን ትሁን፤ የተሰቀልኩባትን ቀራንዮን ትሁን፤ የተቀበርኩባትንም ጎልጎታን ትሁን፤ በዚች ቦታ እየመጣ የሚማጸነውን ሁሉ ቸርነቴ ትጎበኘዋለች፤ ጠለ ምሕረቴም አይለይባትም፤ ከሩቅም ሆነ ከቅርብ መጥቶ የተቀበረ ኢየሩሳሌም እንደተቀበረ ይሁን›› የሚል የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ በዚያ ለተገኙት ምእመናን ሁሉ በጽሑፍ ካሰሙ በኋላ ጠቅላላ የግማደ መስቀሉንና የሌሎቹን ታሪካውያን ንዋያተ ቅዱሳትንም ዝርዝር ታሪክ የያዘውን መጽሐፈ ጤፉት ብለው ሰይመው ድንጋጌውን ሁሉ በመዘርዘር ለግሸን እግዚአብሔር አብ ሰጥተዋል፡፡
ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብም በዚህ ብቻ ሳይወሰኑ ዕሌኒ እኅታቸው የተሰኘችው በእመቤታችን ማርያም ስም ቤተ መቅደስ እንድትሠራ አዘው የእመቤታችን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር አብ ቤተ ክርስቲያን አጠገብ አሳንጻ ጥር ፳፩ ቀን ቅዳሴ ቤቱ ተከብሯል፡፡ ዓፄ ዘርዐ ያዕቆብም ይህችን ‹ደብር ደብረ ከርቤ› ብለው በመሰየም እንኳንስ ሰው የሠገረ ቆቅ፤ የበረረ ወፍ እንዳይገደል ዳሯ እሳት መካከል ገነት ትሁን ብለው ደንብና ሥርዓት በጤፉት መጽሐፍ ውስጥ አጽፈዋል፡፡
ከዚያም የሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም ሲመሠረት ሐይቅ ‹‹ደብረ ነጎድጓድ›› ተብሎ ሲሰየም ግሸን የሐይቅ ግዛት በመሆኑ ‹‹ደብረ ነጎድጓድ›› ተብሏል፡፡ በ፲፬ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመነ መንግሥት የክርስቶስ ግማደ መስቀሉ ግሸን ገብቶ ሲቀመጥ ‹‹ደብረ ከርቤ›› ተብሎ ተሰየመ፡፡ ከዐፄ ድልናአድ ዘመን ፰፻፹፮ዓ.ም እስከ ፲፩ኛው ክፍለ ዘመን በአሁኑ ስያሜ ‹‹ደብረ ከርቤ›› በመባል ይታወቅ ነበር። በዚህ ጊዜ የነበረው የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ መምህረ እስራኤል ዘደብረ ከርቤ ይባል ነበር። በመጨረሻም ከደብረ ከርቤ ‹ግሸን ማርያም› ተብሎ ተሰይሟል፡፡
ይህ ደብር የተቀደሰ በመሆኑ ከበረከቱ ለማካፈል ወደ በግሸን ማርያም ምእመናን በየዓመቱ መስከረም ፳፩ ቀን እየሄዱ በዓሉን ያከብራሉ፡፡
አምላካችን እግዚአብሔር ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፤ አሜን፡፡
ምንጭ፡- መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መጽሐፈ ጤፉት
mk