"እኔ ለስንታችሁ ዋ ብዬ ልሙት…?"
የጎንደር ቀጠና የአማራ ፋኖ ውጊያ እንደዶፍ ዝናብ መውረዱን ቀጥሏል፡፡ የትግል መዝገብ ማስታወሻችን እንደሚያረጋግጠው ያለፉት ሃምሳ አንድ ቀናት ያለማቋረጥ ውጊያ ተካሂዷል፡፡
ከሐምሌ 26/2016 እስከ ነሐሴ 25/2016 ድረስ ለአንድ ወር የቀጠለው ‹‹ዘመቻ አይሸሽም›› እጅግ ስኬታማ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ያ ዘመቻ የመተማውን ድል ያመጣ፣ የፋኖን ድል ዓለማቀፋዊ ሚዲያዎች ሳይቀር የዘገቡለት እንደነበር ይታወሳል፡፡
በመቀጠል የመጣው ዘመቻ ‹‹ዘመቻ ኖላዊት ዘገየ›› ነበር፡፡ ይህ ዘመቻ ለተከታታይ አምስት ቀናት ቀጠሎ ደምቢያ ሰቀልት ላይ የምዕራባዊያን ኢምባሲዎችና ዲፕሎማቶች በወታደራዊ አታሼዎቻቸው ትንታኔ ያሰሩበት ታላቅ ወታደራዊ ድል ተመዘገበ፡፡
አዲሱን የድል ዓመት ከተቀበልን ጀምሮ ከመናገሻ ጎንደር በመቶ ኪሎ ሜትር ራዲየስ 12 ቦታዎች ላይ መደበኛ የጦር አውደ ውጊያ ተካሂዶ የፋኖ የውጊያ ልኬት ስታንዳርድ የተቀመጠበት ድል ተመዘገበ፡፡
ይህ ድል፣ የዓለም ቀይ መስቀል ማኀበር Geneva, Switzerland, በሚገኘው ዋና መቀመጫው ቢሮ ጠረጼዛው ላይ የአማራ ፋኖ ጎንደር ዕዝ ዓለማቀፍ የጦር ሕግን ያከበረ፡- የምርኮኛ ተረከቡኝ ጥያቄ አጀንዳን ያስቀመጠ፣ የአማራ ትግል የመጨረሻው ከፍታ የታየበት ሆነ፡፡
የጎንደር ፋኖ በአደረጃጀት መለያየት የትግል ዓላማ ልዩነት ሳይፈጠርባቸው የድሉን መለኪያ ከፍ አድርገው ሰቀሉት፡- ስሜናዊው የጎንደር ግዛት ደባርቅ፣ ዳባት፣ ገደብየ፣ አምባጊዩርጊስ፤ በምዕራባዊው የጎንደር ቀጠና ድፍን አርማጭሆ፣ መተማና ረዥሙ የሱዳን መዋሰኛ መስመር እስከ ቋራ ጥግ፤ ምስራቃዊው የጎንደር ቀጠና ኪንፋዝ በገላን ይዞ በለሳ መና መቀጣ ቆላ ሐሙሲት ተከዜ ጫፍ፤ ወደደቡባዊው የጎንደር ግዛት ጋይንት፣ ስማዳ፣ ሰዴ ሙጃ፣ ጉና፣ እስቴ ሁለቱም ወረዳዎች፣ ደራን አካልሎ፣ በማህደረማርያም እስከ ደብረታቦር ጫፍ የደረሰው ድል እጅን በአፍ ያስጫነ ነበር፡፡
ይህ ድል አሁን ድረስ መነጋገሪያ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ በየቀኑ የማስታወሻ መዝገቤ ላይ የማሰፍራቸው የፋኖ ድሎች የዘመናችን የጀግንነት ፊደል በሥም ይገለጽ ቢባል የማን ተፅፎ የማን ሊቀር ነው በሚል ጭንቀት ውስጥ እገባለሁ፡፡
ለካ ወድዶ አይደለም… ፋሲል ደመወዝ ‹‹እኔ ለስንታችሁ ዋ ብየ ልሙት…?›› ያለው… የደረሰበት ያውቀዋል!!
በድል ቁንጣን ስላጨናነቁን ፋኖዎቻችን የጦር ሜዳ ውሎና ጀብዷቸው፡- ለትውልዱ መማሪያ፤ ለእውነተኛ የአማራ ብሔረተኝነት ግንባታ መሠረት አድርገን እንጠቀምባቸዋለን!!
ለሁሉም በጎንደር ቀጠና ቢፃፍ በቴራ ባይት የሚለካ የድል ታሪክ መሰራቱ ቀጥሏል!!
ብዙዎች መረጃው ያላቸው አልመሰለኝም ሁሉም የጎንደር ቀጠና የገጠር ቀበሌዎች ነጻ ወጥተዋል፡፡ ይህ መረጃ መናገሻ ጎንደርን ጨምሮ ለከተሞች የሚቀርቡ የገጠር ሳተላይት ቀበሌዎችን ጨምሮ ነው፡፡ ቀዩን መስመር ሳይጨምር ጎንደር ቀጠና 19 ወረዳ ሙሉ በሙሉ፤ 21 ወረዳዎች ደግሞ በከፊል በፋኖ ቁጥጥር ስር ናቸው፡፡ የብልጽግና አራዊት ሰራዊት በዋና ዋና የዞን ከተሞች ተከማችቶ ይገኛል፡፡ በጠላት እጅ የሚገኙ የወረዳ ከተማ አስተዳደሮች በማንኛውም ጊዜ በፋኖ ቁጥጥር ስር ሊውሉ የሚችሉ እንደሆነ በተደጋጋሚ ውጊያዎች ታይቷል፡፡
እንደታች ጋይንት፣ ስማዳ፣ ሰዴ ሙጃ፣ እስቴ፣ ቋራ፣ ኪንፋዝ በገላ፣ በለላ ቆላው፣ …ባሉ ነጻ ወረዳዎች ለአማራ የቁርጥ ቀን ልጅ ፋኖ ሕዝባዊ የድጋፍ ሰልፎች ተካሂደዋል፡፡ የማዘጋጃ ቤት፣ የፍርድ ቤትና ሌሎች ማኀበራዊ ተቋማት አገልግሎት መስጠት የተጀመረባቸው ወረዳዎችም አሉ፡፡
የፋኖ አስተዳደራዊ ተቋም ምሁራንን ጭምር የሚያቅፍ በመሆኑ ነጻ በወጡ ወረዳዎች የምሁራን ሚና ጨምሯል፡፡ አማራ አሁን ትክክለኛውን የፖለቲካ ቁመና የሚያገኝበትን መዋቅር ከታችኛው የቀበሌ መዋቅር ጀምሮ በመዘርጋት ላይ እንደሆነ በጎንደር ቀጠና እያየን ነው፡፡
በቀጣይ የሌሎች የአማራ ግዛት ቀጠናዎችን መረጃ አጠናቅሬ እመለሳለሁ…
ያየነውን እንመሰክራለን! የምናውቀውን እንናገራለን!
©የፈራ ይመለስ