ህይወት አዙሪት ናት።ረጅም ርቀት የተጓዝክ ቢመስልህ የምትጨርሰው ከጀመርክበት ነው።ራቁትክን ትወለዳለህ እርቃንህን ወደ መቃብር ትወርዳለህ።በጥርስ ዐልባው ድድህ እየጋጥክ ትጀምራለህ ጥርሱን ባረገፈው ድድህ እያልጎጠጎጥክ ትጨርሳለህ።የህይወት ትግል እየዳህ ትጀምራለህ አጎንብሰህ ትጨርሳለህ።ዘመንም ተምኔታዊ ነው።መስከረም ጥቅምት ብሎ ያስጀምርህና መስከረም ብሎ ይመጣብሀል።ሰኞ ማክሰኞ ብለህ ተጉዘህ እንደገና ሰኞ ትላለህ።ሕይወት አዙሪት ናት!መጀመሪያህ መጨረሻህ ነው።የጀመርክበትን አትርሳ መጨረሻህ ነውና።የጀመርክበትን አትናቀው ትጨርስበታለህና።ተራ ሰው ሆነህ ትጀምራለህ ተምረህ እውቀት ብትጨምር ነግደህ ሀብት ብታገኝ ተሹመህ በህዝብ ላይ ብትሰለጥን ክቡረ ክቡራን ሆነህ የወርቅ ካባ ብትለብስ የምትጨርሰው እንደ ተራ ሰው አፈር ለብሰህ ነው።
ባለማወቅ ትጀምራለህ በመዘንጋት ትጨርሳለህ ዕውቀት አላመጣህምና ዕውቀትም ይዘህ አትሄድም።በለቅሶ ትጀምራለህ በጭንቅ ትጨርሳለህ።በሰው እቅፍ ትጀምራለህ በሰው ሸክም ትጨርሳለህ።
ገፅ 314_315
ከመርበብት
በዶ/ር አለማየሁ ዋሴ