Alex Abreham በነገራችን - ላይ

@alexabreham


በገበያ ላይ የሚገኙ የአሌክስ አብረሃም መፅሐፍት ዝርዝር

1- አልተዘዋወረችም
2- ከዕለታት ግማሽ ቀን
3- ዙቤይዳ
4 - ዶክተር አሸብር
5 - እናት ሀገር ፍቅር
6 - አንፈርስም አንታደስም

💚💛❤️

አሌክስ ማለት በቃ አሌክስ ነው::
Contact me
@akexeth

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

20 Oct, 06:40


በዜሮ ...
(አሌክስ አብርሃም)

አንድ ጓደኛየ መንጃ ፈቃድ አውጥቶ መኪና መንዳት በጀመረ በመጀመሪያው ቀን በሰላም በእግሬ ከምሄድበት ጠራኝና
"ና ግባ አደባባዮን ላሻግርህ" አለኝ
"ግዴለም በእግሬ እሻገራለሁ" አልኩ። ነዝንዞ  አስገባኝና ጋቢና አስቀመጠኝ። ገና በሩን ከመዝጋቴ  ስለመኪና ባህሪና ስለአነዳድ ቴክኒክ ልቤ እስኪደክም ያስረዳኝ ጀመር። ያለምንም ዓላማ ከተማችንን አንድ ጊዜ  አዞረኝ። እስከዚህ ደህና ነበር።  "ይሄ ፍሬን ይባላል፣ ድንገተኛ ነገር ሰው ፣ አህያ ወይም  የተናኘ  ባል የሚነዳው መኪና ቢገቡብህ ማቆሚያ ነው"  አለና አጎንብሶ ፍሬኑንን ይፈልግ ጀመረ...(ተናኘ ሹፌር ያገባች የቀድሞ  ፍቅረኛው ናት) "እስክትፈልግ ግን ....ከማለቴ  ፍሬኑን አግኝቶ ባለ በሌለ ሀይሉ ረገጠው። ወደፊት ተወርውሬ የሆነ ነገር ጋር ተጋጭቸ ተመለስኩ። ዘና ብሎ "አሁን የገጨኸው ዳሽ ቦርድ ይባላል የትም አገር የሚያጋጥም ነገር ነው" አለና ቀጠለ። ደረቴን ደግፌ  እያሳልኩ ዝም አልኩ።

ብቻ እንዲህ አሰቃይቶኝ በመጨረሻ "አንዲት ብዙ ሹፌሮች ያልባነኑባት ቴክኒክ ላሳይህ ወደፊት ይጠቅምህ ይሆናል" አለኝ። ወይ እዳየ። ከዚህ ሁሉ ለዓመታት የነዳ ሹፌር ተደብቆ  ገና በአንድ ቀን ምን ተገልጦለት ይሆን እያልኩ ሳስብ በከተማችን አለ ወደሚባለው ቁልቁለት መንገድ ወሰደኝና "አሁን እዚህ ቁልቁለት ላይ ሞተሩን ታጠፋውና በዜሮ ትሄዳለህ ...መሪዋ ላይ ብቻ መጫወት ነው...ነዳጅ አተረፍክ ማለት ነው አባቴ" ብሎ ትልቅ ግኝት እንደነገረኝ አይነት በኩራት ሀሀሀሀሀ ብሎ ሳቀ። እኔ ግን ነፍሴ ተጨነቀች።  መኪናው ወደታች ፍጥነት እየጨመረ  መምዘግዘግ ጀመረ ። ወገኖቸ ባጭሩ ፍሬን ቢረግጥ ምን ቢረግጥ (እኔን ሁሉ እግሬን ቢረግጥ) መኪናው አልቆምም አለ። አታምኑኝም ዞር ስል የሹፌሩ በር ተከፍቶ አጅሬው ሲዘል ተገጣጠምን። ለደይቃወች ራሱን በሚነዳ መኪና ከተጓዝኩ በኋላ .... መኪናዋና እኔ ለግንባታ ፒራሚድ መስሎ  የተከመረ አሸዋና ጠጠር ክምር ጫፍ ላይ ጉብ አልን። እዚህ  ቴውድሮስ አደባባይ ያለውን የአፄ ቴውድሮስን የመድፍ ሀውልት ነበር የምንመስለው።

አሁን ያለንበትን የኑሮ ሁኔታ ሳየው፣  የሆነ ቴክኒክ ላሳያችሁ ብሎ ያሳፈረን ሹፌር ዘሎ የወረደ እስኪመስለኝ ቀላል እየተምዘገዘግን ነው?! ብቻ ማረፊያችንን ያሳምረው።

@AlexAbreham @AlexAbreham

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

20 Oct, 06:36


መዘበራረቅ

ዝብረቃ 1. 

ተኝታችሁ ከተስማማችሁ በኋላ ተንበርክካችሁ "ታገቢኛለሽ?" ማለታችሁ ትንሽ የቅደም ተከተል ችግር አለበት ልበል? ለፆለት የሚንበረከከው ወንድ ከዚህኛው መንበርከክ በቁጥር እያነሰ መምጣቱ እንዳያስቀስፈን ጓዶች።

ዝብረቃ 2.

ፊልሙን ለመስራት  1.5 ሚሊየን ብር አወጣን ካላችሁን በኋላ የዋናዋ  ገፀ ባህሪ ሰራተኛ እህት ልጅ  ሁና የተወነችው እንስት  የሽልማት መድረኮች ላይ 2.9999 ሚሊየን ብር የፈጀ ቀሚስ(አውትፊት ይሉታል)  ለብሳ የምትታይበት ሳይንስ ትንሽ ግራ ያጋባል። አንዳንዴ በውበትም በዋጋም ከፊልሙ የሚበልጥ ቀሚስ ስናይ የልብስ ሰፊወች አዋርድ እየመሰለን ተቸግረናል። ለነገሩ የትም አለም የተለመደ ነው።

የውጭ ዝብረቃ 3.

ኤለን መስክ የሚባል በቴክኖሎጅ ፍቅር ልብሱን ጥሎ ያበደ ሰውየ፣ የሆነ መሪ የሌለው መኪና እያስተዋወቀ ነው። በዓለም የመጀመሪያው ካለመሪ የሚንቀሳቀስ ነው አለ። እንኳን መኪና እእእእእ 😀 እሽ ይሁን።  የሆነ ሆኖ መኪናው እናንተ ቤታችሁ ተቀምጣችሁ ብቻውን ሄዶ ኡበር /ታክሲ/ ይሰራል ይሸቅላል ሲል ነበር። እና ሮቦቶች የሰወችን ስራ አይነጥቁም? ሲባል ምናለ? ይንጠቋ! ሮቦቶች ይሰራሉ ሰወች ዘና ብላችሁ የኪስ ገንዘብ እየተሰጣችሁ ትኖራላችሁ። ከመጠግረር ምን አላችሁ?

@AlexAbreham

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

17 Oct, 18:38


ችግራችሁን እያየን ያልደረስንላችሁ ይቅርታ!
ችግራችንን እያያችሁ ያልደረሳችሁልንም ይቅርታ!
(አሌክስ አብርሃም)

ፍቅር ብቻውን መልስ የሚሆንበት ጊዜ  ላይ አይደለንም።
በማንም ላይ መፍረድ ከባድ ነው። ሲቸገሩ መርዳት አለመቻል ከሚፈጥረው ህመም ለመራቅ ከምንወዳቸው  ወዳጆቻችን እንርቃለን። ዓይናቸው ውስጥ ያለውን ስቃይ ላለማየት ዓይናችንን እንሰብራለን።የአቅማችንን መደገፍ እንኳን ከአቅም በላይ ሆኗል። የተወለድንበት እና ያደግንበት ስር የሰደደ አብሮነት፣ መረዳዳት አሁን እግር ከወርች ካሰረን ኑሮ ጋር አብሮ አልሄድ ብሎ አስጨንቆናል። ረስተነው ወደወዳጆቻችን መንገድ ከጀመርን ፣ልንደውል ስልክ ካነሳን በኋላ ባዶ አይናቸው እጃችሁ ከምን ቢለንስ ብለን ተመልሰናል። ከመሄዳችን በላይ ምን ይዛችሁ መጣችሁ የሚለን አንደበታቸው ሳይሆን ኑሯቸው ሁኗል። የተጨነቀ መንፈስ፣ የተጨነቀ አየር። የማንንም እርዳታ የማይፈልጉ መንፈሰ ፅኑ ወዳጆቻችን ነገሮች ከአቅም በላይ ሆነውባቸው በዓይናቸው ባዶ ኪሳችንን ሲቃኙ ብናይ መርዳቱ ቢቀር አንታዘባቸውም። "እንትናም ተቸገረ?" ብለን አናሾካሹክም። ይገባናል ሰው ወደገደል ቢወድቅ አዳነውም አላዳነውም አጠገቡ ያገኘውን ሳርም ይሁን ቅጠል በደመነፍስ ጨምድዶ እንደሚይዝ። ሁላችንም ገደሉ ውስጥ ነን።ልብሳችንን አንቀው የሚማፀኑን እኛም የሌሎችን ልብስ አንቀን መንጠልጠላችንን ያውቃሉ። የመያያዙ መጨረሻ፣ የገደሉ ጫፍ የት እንደሆነ ማን ያውቃል?! እጃችን እየዛለ ነው። ደመነፍስ ላይ ነን። ማንንም ለመዳን እንይዛለን በማንም እንያዛለን።  ችግራችሁን እያየን ያልደረስንላችሁ ይቅርታ። ችግራችንን እያያችሁ ያልደረሳችሁልንም ይቅርታ። ሁላችንም ገደሉ ውስጥ ነን።

Alex Abreham

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

16 Oct, 14:18


‹‹አላውቅሽም››
------

ከቅርብ ጓደኛዬ ሳሮን ጋር ፊሊ ካፌ የተለመደው ቦታችን ተሰይመን እያወራን እያለ ስልኳን አሁንም አሁንም እያነሳች ሰዐት ስታይ፣
‹‹ምን ሆነሽ አስሬ ሰዐት የምታይው?›› አልኳት::
‹‹ብዙ መቆየት አልችልም፡፡ ከአስራ አንድ ተኩል በፊት ሆስፒታል መድረስ አለብኝ›› ብላ ስትመልስልኝ፣
ደንገጥ ብዬ ግማሽ የደረሰ የማኪያቶ ስኒዬን አስቀመጥኩና፤

‹‹ሆስፒታል? ምን ሆንሽ?›› አልኳት
‹‹ምንም አልሆንኩም›› አለች ቀኝ እጇን ወደ ታች አወናጭፋ፡፡ ‹‹ነገ በጠዋት ሰርጀሪ እደረጋለሁ፤ ሆድሽ ውስጥ የሆነ እጢ አለ፤ ቶሎ መውጣት አለበት ብለውኝ ነው፡፡ የአራት ሰዐት ፕሮሲጀር ነው፡፡ እዚያ ማደር አለብሽ ስላሉኝ እንዳልዘገይ ብዬ ነው…››

የምትለውን ማመን አቅቶኝ በግርምት እያየኋት፤

‹‹ነገ ጠዋት ሲሪየስ ሰርጀሪ እንዳለብሽ የምትነግሪኝ አሁን ነው?…ለዚያውም እንዲህ ቀለል አድርገሽ?›› አልኩ፡፡

የቀዘቀዘ ሻይዋን በዝግታ ማማሰሏን ሳታቋርጥ፤

‹‹ያው እኔን ታውቂኛለሽ፡፡ ደሞ ከባድ ነገር አይደለም እኮ…ያው ግድ ሆኖብኝ ነው እንጂ፡፡ ይልቅ ማታ የላኩልሽን መቅዲዬ የሰራችውን ቲክቶክ አየሽው?›› አለችኝ፡፡

-----
ከሶስት ወራት በኋላ ለምሳ ተቀጣጥረን ስደርስ ጠረጴዛው ተበታትነው የተቀመጡ መአት ወረቀቶች ታተራምሳለች፡፡ አንዱን በትኩረት አየሁት፤

‹‹ሉንዲን ዩኒቨርስቲ- ስዊድን›› የሚል ነገር አይኔ ገባ፡፡

‹‹ምንድነው ይሄ ሁሉ?›› አልኳት ስሜያት እንደተቀመጥኩ፡፡
‹‹እ…ወረቀቱ…? ሉንዲን ዩኒቨርስቲ ማስተርሴን ለመማር ሙሉ ስኮላርሺፕ አገኘሁ፡፡ ሚዲያና ፖለቲክስ ለሁለት አመት ልማር ነው፡፡ ከሃያ ቀን በኋላ እሄዳለሁ››
‹‹ምን….? ከሃያ ቀን በኋላ ስዊዲን ልትሄጂ መሆኑን ዛሬ ነው የምትነግሪኝ? ›› አልኳት በድንጋጤ፡፡
‹‹ያው እኔን ታውቂኛለሽ፡፡ ነገር ማካበድ አልወድም…በዛ ላይ ወሬን ወሬ ካላነሳው እንዴት አስታውሼ እነግርሻለሁ…? ገና እኮ ሃያ ቀን አለን…››

----
ከስዊዲን በተመለሰች በሳምንቱ ውጪ በመቅጠር ፋንታ የእናቷ ቤት ሄጄ እንዳገኛት ስትጠይቀኝ ግር ቢለኝም ሄድኩ፡፡

ወደ ሳሎኑ እንደገባሁ ባለ ሶስት መቀመጫው ሶፋ ላይ ጋቢ ተደርቦለት የተኛ ቆንጅዬ ብስል ቀይ ህጻን ልጅ አየሁ፡፡

ስድስት ወር ይሆነዋል፡፡

ሁለት ታላቅ እህቶቿ እዚያው ቤት ከእናታቸው ጋር ስለሚኖሩ ‹‹የማን ልጅ ይሆን?›› ብዬ አስቤ ሳልጨርስ ፣
ቡናዋን አቀራርባ ከተቀመጠችበት መጥታ ተቃቅፈን ከተሳሳምን በኋላ፤

‹‹የማነው ቆንጅዬ ልጅ?›› አልኳት ልጁን እያየሁ፡፡
‹‹የእኔ›› አለችኝ ፍርጥም ብላ፡፡
‹‹ምን?››
‹‹ምን ምን አለው? የእኔ ልጅ ነው››
‹‹ወልደሽው?››
‹‹አይ…እንደ እንቁላል ፈልፍዬው…
‹‹ሳሮን..ሲሪየስሊ…ምንድነው የምታወሪው?››
‹‹ልጄ ነው አልኩሽ…ከማስተርሴ ጋር አብሬ የሰራሁት…ይልቅ ፀሃይ መቶሻል መሰለኝ…ፊትሽ ከስሏል…ውሃ ላምጣልሽ? ››

ሳሮን በየጊዜው የምትጥላቸው ትልልቅ የዜና ቦምቦች እንዳስደነገጡኝ፣ በእርግጥ ጓደኞች ነን እንዳስባሉኝ ነው፡፡
ይሄኛው ግን ከሁሉ ከረረብኝ፡፡

ውሃ በብርጭቆ ይዛልኝ ስትመለስ፣
‹‹ልጅን የሚያህል ነገር አርግዘሽ ስትወልጂ…ይሄን ሁሉ ጊዜ ስናወራ ለጓደኛሽ እንዴት አንዴ እንኳን አትናገሪም?›› አልኩ ንዴቴን በሚያሳብቅ ድምፅ፡፡
‹‹ያው እኔን ታውቂኛለሽ፡፡ ነገር ማካበድ አልወድም…..›› የተለመደ መልሷን ቀጠለች፡፡

አሁን ግን ፣ ‹‹የለም አላውቅሽም›› ብለሻት ውጪ ውጪ አለኝ፡፡

By Hiwot Emshaw

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

11 Oct, 06:35


‹‹አስቴር አወቀ፣ ኤች አይ ቪ እና ሽምግልናዬ››
_________

(እንደእኔ) ካገቡ የቆዩ ሰዎች ስለ ዘንድሮ ልጆች የሽምግልና ዝግጅት በብዛት ሲያጉረመርሙ እሰማለሁ፡፡

የዘንድሮ የሽምግልና ድግስ የጥንቱን ባህል መሰረት ያደረገ ነው?
አይደለም::

ወጪው ከባድ ነው?
በጣም::

የድግሱ መጋነን በወጣቶች መሃከል ከባድ የፉክክር ስሜት ፈጥሮ ሊያገቡ ያኮበኮቡ ጥንዶችን ጋብቻ በወጪ ፍራቻ ሳቢያ ወደኋላ እያስባላቸው ነው?
ምናልባት::

ግን ይሄ ሁሉ እኛን ያገባናል?
አያገባንም፡፡

እኛ የዘመናችንን ኖርን፡፡

እኛም (እኛ ስል ባለፉት 20-15 አመታት ውስጥ ጎጆ የወጣን ሰዎችን ማለቴ ነው) ብንሆን ወላጆቻችን ባህሉን የጠበቀ ሽምግልና ነው ከሚሉት የሽምግልና ስርአት እንደዛሬዎቹ ልጆች እጅግ ባንርቅም ማፈንገጣችን ግን በጊዜው በሰፊው ተተችቷል፡፡

ለምሳሌ የእኔ ሽማግሌዎች አንድ ጊዜ ብቻ መጥተው እሺ እንዲባሉ መደረጉ ያናደዳቸው አክስቶቼ ዛሬም ድረስ ባሌን ሲያዩ፣

‹‹እሱማ አንዴ አራት ሰው ልኮ አፈፍ አደረጋት›› እያሉ ይሸነቁጡታል፡፡
ልክ እኔ ተስማምቼ አፈፍ እንዳልተደረግኩ ሁሉ፡፡
ሽምግልናው እናትና አባቴን ለማክበር ተከናወነ እንጂ እምቢ ቢሉም አመታት ቀድሞ ልቤን ከወሰደው ሰው አልለይ ነገር፡፡ ለዚያ ነው አይመላለሱ ተባብለን ባጭር የቀጨነው፡፡

ያሁኖቹ ወጣቶችም የራሳቸውን ነገር እያደረጉ ነው፡፡

ያም ሆነ ይህ፣ ሃምሳ ሽማግሌም ተላከ አራት፣ አምስት ሺህ ብር ወጣበትም አምስት ሚሊዮን ከሽምግልናውና ከከበረቻቻው፣ ከሆያሆዬውና ከድግሱ በላይ ትልቁ ነገር ሰላማዊ ትዳር ነው፡፡ በአሸወይና የቆመ ፣ በሽምግልናው ድግስ ስፋት የሚፀና ሶስት ጉልቻ የለምና፡፡

“ዛሬ በምን ትዝ ብሎሽ ነው በጥቅምት መባቻ ስለ ሽምግልና የምታወሪው?” ልትሉ ትችላላችሁ፡፡

ቅድም የአስቴር አወቀን ‹‹መዘዝ አለው›› ዘፈን ስለሰማሁ ነው፡፡

የአስቴር መዘዝ አለው (በእኔ እድሜ ያላችሁ ሰዎች እንደምታውቁት) ዩኤስኤይድ ሙዚቃን በመጠቀም ኢትዮጵያዊያንን ስለ ኤች አይቪ ለማስተማር ያሰራው አስደማሚ የሙዚቃ አልበም ላይ ያለ ድንቅ ዘፈን ነው፡፡

(ሁሌም የሚገርመኝ ነገር ይሄም ዘፈን ሆነ ሌሎቹ (የፍቅርአዲስ በድንገት…የቴዎድሮስ ፍቅሬ ሆይ… እና ሌሎቹም በዚህ አልበም የተካተቱ ዘፈኖች በግጥምና ዜማ ለዛቸውና የደረቀ የማስተማሪያ ዘፈኖች ባለመሆናቸው እስከዛሬ ድረስ ስለ ኤች አይ ቪ እንደተሰሩ ተረስቶ እንደ ጥኡም የፍቅር ዜማ የሚሰሙት ነገር ነው) ፡፡

ለማንኛውም እኔ እና ባሌ አስቴርን ከፍተን፣
‹‹አንድ ሰው ለአንድ ነው-
ትርፉ መዘዝ አለው›› ስንል ነው የዛሬ 17 ዓመት የነበረው ሽምግልናችን ትዝ ያለን፡፡

አሁን ደግሞ “እሱስ ይሁን ግን ኤች አይቪና ሽምግልና ምን አገናኘው?” ሳትሉ አትቀሩም፡፡

ባሌ ለቤቶቼ ሽምግልና ሲልክ ኤች አይ ቪ በሃገሩ ላይ እንደ ልቡ የሚፈነጭበት፣ ወጣቱን የሚያጭድበት፣ ጎልማሳውን አፈር የሚያለብስበትና ጨቅላዎችን ያለ አሳዳጊ ባዶ ቤት የሚያስቀርበት አስከፊ ጊዜ ነበር፡፡

ስለዚህ የዚያን ጊዜ ሽማግሌዎች ልጃችሁን ስጡን ብለው አባትና እናት፣ዘመድ አዝማድ ፊት ሲቀርቡ፣
ለመሆኑ ምን አለው?
ስራው ምንድነው?
በምን ያስተዳድራታል?
ቤትና መኪና አለው?
ከዚህ በፊት ትዳር ነበረው?

ከሚሉት ጥያቄዎች አስቀድሞ የሚጠየቀው፣

‹‹ ህጋዊ ማህተም ያለበት ከኤ ች አይ ቪ ነጻ መሆኑን የሚያረጋግጥ ሰርተፍኬት ይዛችኋል ወይ?›› ተብሎ ነበር፡፡

ታዲያ ብዙ ወንዶች የሃሰት ማስረጃ እያስያዙ ሽማግሌዎች ስለሚልኩ ሃኪም ቤቶች ሰርተፊኬቱን በመላክ ፈንታ ‹‹የሚመለከተው ሰው›› መጥቶ እንዲያይ አዝዘው ነበር፡፡

‹‹ሮማንቲክ›› አይደለም ግን አስፈላጊ ነበር፡፡ ሰው ጊዜውን ነው የሚመስለው፡፡

እናም ይህንን የማይቀር መሰናክል ለማለፍ ሲል የዚያን ጊዜ ቦይፍሬንዴ ለኤች አይ ቪ ምርመራ ሲሄድ አብሬው ሄጄ ነበር፡፡
ቤተሰቤን ወክዬ (የአይጥ ምስክር ድምቢጥ ! ሃሃሃ)

ለክፉ የሚዳርግ የሰራው/የሰራነው ስራ ባይኖርም፣ በሽታው ‹‹በዚያ ነገር›› ብቻ ሳይሆን መምጫው ብዙ ነውና መፍራታችን አልቀረም፡፡

የ”ነጻ ነው” ሰርተፍኬታችንን ስናገኝ ግን…
አባቴ ከመፍቀዱ በፊት፣
ከሰርጉ በፊት፣
ከጫጉላው ሽርሽር በፊት የተጋባን መስሎን ደስ አለን፡፡

አሁን ስለ ምንከራየው ቤት ማሰብ ፣ አሁን የሶፋችንን ቀለም መምረጥ፣ አሁን ቤት ሳናስፈቅድና ሳንዋሽ ሁልጊዜ አብረን ማደር እንችላለን ተባባልን፡፡

ያ ነው የአስቴር ዘፈን- የኤች አይቪው ሰርተፍኬትና የሽምግልናዬ ግንኙነት፡፡

ለማንኛውም በጥቅምትና በመጪው የበልግ ወራት በሽምግልናም ሆነ ያለ ሽምግልና፣ ደግሳችሁም ሆነ ሳትደግሱ ጎጆ ለምትወጡ እዚሁ የአስቴር ዘፈን ላይ ባሉ ውብ ስንኞች መልካም ጋብቻ ልበላችሁ!

‹‹ከለመዱት ጠረን- ከወደዱት ጋራ
እምነት ፍቅር ካለ- ይገፋል ተራራ››

By Hiwot Emshaw

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

09 Oct, 15:35


እንውጣ
(በእውቀቱ ስዩም)

ወንድ ልጅ አይጣ! ምን አይጣ? ሚስት አይጣ! መልስ አይጣ! መውጫ አይጣ! ይልቁንም ገንዘብ አይጣ!

በቀደም እሁድ ለታ፥ ኤቲኤም ማሸኑ ላይ ሄጄ ተገተርኩ ፤ ዞር ብየ ታዛቢ መኖር አለመኖሩን ካረጋገጥኩ በሁዋላ” ሁለት መቶ ብር” የሚለውን አማራጭ ጨቆንኩት ፤ ማሽኑ ካርዴን መለሰልኝና “ ውድ ደንበኛችን፤ ለሁለት መቶ ብር ብለንማ በሰንበት መጋዘናችንን አንከፍትም! እባክዎ ባቅርቢያዎ ከሚገኝ የባንክ ዘበኛ ይበደሩ “ የሚል ጽህፈት ሰደደልኝ ፤

ከላይ ያለው ቀደዳ ሲሆን፥ ከታች ያለውን ግን የገሀዱ አለሜ ነጸብራቅ ነው!

ማርያምን ወንድ ልጅ አይጣ! ወንድ ልጅ በጣምም አያግኝ ! ሲያገኝ እንደኔ ጽጋበኛ ያለ አይመስለኝም! ከበቀደም ሁለት ቀን አስቀድሞ ልዝብ ሀብታም የሚያሰኘኝ ገንዘብ ሸቅየ ነበር፤ ሼክ አላሙዲን መክሰስ በሚበላበት ባርና ሬስቶራንት ገብቼ የምግብ ናዳ አዘዝሁ፤

ለማሳረጊያ ያዘዝኩት፥ ብርቱካን አናናስ እና ፓፓየ ጠረጴዛየ ላይ ተከማችቶ ያየ ሰው የሆነ የፍራፍሬ እርሻ የሚያስመርቅ የዞን ባለስልጣን ነው ምመስለው፤

ፈንጠር ብሎ የቀድሞ እግር ኳስ ተጫዋች የነበረ ሰውየ ተቀምጦ ያየኛል( ስሙን በሌላ ቦታ የገለጽሁት ሲሆን እዚህ ላይ አጅሬ እያልሁ እቀጥላለሁ)

አጅሬ ፈገግ ብሎ ሲያየኝ ከቆየ በሁዋላ “ ይሄን ያህል በምግብ ተጎድተሀል እንዴ ?” ብሎ ለከፈኝ ፤

እኔ ሰላማዊ ሰው ነኝ፤ አዝመራው የተባለ ዘመዴ ትዝ ይለኛል፤ ድሮ ከትምርት ቤት ስንመለስ የሰፈር ጎረምሶች አስቁመው ነገር ሲፈልጉን እኔ ከድብድብ ለማምለጥ ያሉ የሌሉ ዘዴዎችን ሁሉ አሟጥጬ እጠቀማለሁ፤ ጎረምሶቹ በለስላሳ ምላሴ ተማርከው በሰላም ሊያሰናብቱን ከጨረሱ በሁዋላ አዝመራው እመር ይልና ክምር እንዳየ ዝንጀሮ አንዱ ላይ ይወጣበታል ፤ ከቴስታ አቅም እንኳ ሶሰት አይነት ቴስታ ያውቅ ነበር፤ ሸራፊ ቴስታ- ማይግሪን የሚያስይዝ ቴስታ እና ለኮማ እሚዳርግ መርዘኛ ቴስታ-

ጎረምሶችን አሸንፎ ሲያበቃ የሚሸልላት አትረሳኝም፤

“ዘራፍ አዝመራ ! ( ከስሙ መጨረሻ ያለችውን “ው” ለቤት ምታት እንቅፋት ስለምትሆን ያስወግዳታል)
ቁመቱ አጣራ
ልቡ ተራራ”

ለወትሮው ሰላማዊ የነበርኩት ሰውየ ድንገት የአዝመራው መንፈስ ተጋባብኝ ፤ ብልጭ አለብኝ! በዚያ ላይ ለሁለት ወር የkick boxing ስልጠና መውሰዴ ተራራም ባይሆን የሰፈር ዳገት የምታክል ልብ አጎናጽፎኛል፤

ከለካፊየ ጋር ትንሽ የስድብ ልውውጥ ካደረግን በሁዋላ “ልብ ካለህ እንውጣ ! “ አልሁት፤ እሱ ግን ቸል ብሎኝ ድራፍቱን መቀንደሉን ቀጠለ፤ እኔ በዛቻየ ቀጠልኩ፤ አጅሬው ሰማኝ ሰማኝና በመጨረሻ በረጅሙ ተንፍሶ እንዲህ አለ፥

“ እንዲያው አሁን፥ አስሬ እንውጣ የምትለኝ ፤ ልትመታኝ ነው ብርድ ልታስመታኝ?”

By Bewuketu Siyoum

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

09 Oct, 06:45


‹‹ዐይኔ ያያል ዳቦ እንዳመጣሽ አውቃለሁ…ጥያቄዬ እሱ አይደለም›› አልኩ ትንሽ ገንፈል እያልኩ፡፡
‹‹እና ታዲያ ችግሩ ምንድነው?››
‹‹ችግር አላልኩም…ጥያቄ ነው ያልኩት››
‹እሺ ምንድነው ጥያቄሽ?››
‹‹በየት ሃገር ነው እንጀራ ከሩዝ ጋር የሚቀርበው?››

ልጅቱ ድምጽዋን ዝቅ አድርጋ ጥላኝ ለመሄድ እየተዘጋጀች..

‹‹ሆ…ስንት ዘመድ ያጣ እብድ አለ ባካችሁ›› ስትል ነገሩ ለየለት፡፡

ያበጠው ፈነዳ፡፡

ከዚያ የተፈጠረው ብዙ ነው ግን ለማሳጠር ያህል ልጅቱን ካልደበደብኩ አልኩ፤ ማኔጀሩ መጣ፤ ውጪ አለኝ፤ አልወጣም አልኩ፤ ከባድ ግርግር ሆነ፡፡ ፖሊስ መጣ፡፡

እና ምን ለማለት ነው…? ነገር ይገንብኛል፡፡

By Hiwot Emshaw

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

09 Oct, 06:45


‹‹ ነገር ይገንብኛል››

---=======------

‹‹ለትንሹም ለትልቁም ነገር አቃቂር ማውጣት ትወጃለሽ›› የሚሉኝ ሰዎች ብዙ ናቸው፡፡
‹‹ሊያውም ኢትዮጵያ ውስጥ እየኖሩ ሁሉን ነገር መተቸት…ሁሉ ነገር እንከን የለሽ እንዲሆን መጠበቅ አይከብድም?›› ይሉኛል፡፡

አንድ ሰው ኢትዮጵያ ውስጥ በመኖሩ ብቻ የተርመጠመጠ ነገር በቂው ነው ያለው ማነው?

…በቃ ለራሳችን የምንሰጠው ግምት ይህችን ታህል ነው?
…ለዚህ ይሆን አንድ ስፍራ ፀድቶና አምሮ ሲታይ፣
‹‹…ዋው ኢትዮጵያ አይመስልም›› የምንለው…?

እቅጩን ንገሪን ካላችሁ፤ “እኔን አቃቂር ታበዣለሽ” እያሉ የሚከሱኝ ሰዎች ኢትዮጵያ ውስጥ ስላለን ደህና ነገር አይገባንም በሚል የበታችነት ስሜት የሚሰቃዩ ሰዎች ናቸው፡፡

…እነሱ ለራሳቸው የሚሰጡት ግምት ከደረጃ በታች ስለሆነ፣ ያገኙትን ሁሉ ተስገብግበው ስለሚያነሱ፤ እንኩ የተባሉትን ሁሉ አጎንብሰውና በጀ ብለው ስለሚቀበሉ፣ የከፈሉበትን ነገር እንኳን ተሸቆጥቁጠው ተጠቃሚ ስለሆኑ፣ መራጭ ሳይሆን አግበሽባሾች ስለሆኑ….

እኔ ‹‹አረ ይሄ ነገር ከልክ በታች ነው›› ስል አፋቸውን ለትችት ያሞጠሙጣሉ፡፡
ለሽሙጥ የተሞረደ ምላሳቸውን ዘርግተው, ‹‹እስቲ ክፉ ክፉን ብቻ ማየት ትተሸ አይንሽ ለበጎውም ነገር ይከፈት›› ይላሉ፡፡

ደግሞ እኮ ነገር ይገንብኛል እነጂ ፣ ያን ያህል እንከን ፈላጊ ሰው ሆኜ አይደለም፡፡

ምሳሌ ልስጣችሁ፡፡

ባለፈው አንድ ቄንጠኛ ካፍቴሪያ (ስቀብጥ) ገብቼ ለአንድ ማኪያቶ 140 ብር እንደሚጠይቁ ሚኑውን ሳይ ብረዳም “አንዴ ገብቻለሁ” በሚል (የሃበሻ) ይሉኝታ አዘዝኩ፡፡

ማኪያቶው (ሶስቴ ፉት ብልለት በሚያልቅ መጠን እንስ ባለች ስኒ) ሲመጣ ባሬስታው በማኪያቶው አናት ላይ በአረፋ የሰራው የልብ ቅርፅ ወደ አንድ ጎን መንሻፈፉን ሳይ ተበሳጨሁ፡፡

አንዳንድ ሰው፣ ‹‹አሁን ይሄ ምኑ ያበሳጫል…አርፈሽ አትጠጪውም›› ሊል ይችላል…ግን እስቲ ትንሽ ረጋ ብላችሁ አስቡት፤ 140 ብር የተከፈለበትን ማኪያቶ ላይ ልብ የሚስል ባሬስታ የስእል ችሎታው ከአፈወርቅ ተክሌ ጋር ሊስተካከል አይገባም…?

አለበለዚያ ለዚህች ፉት ሲሏት ጭልጥ ለምትል ተራ ማኪያቶ ይሄ ሁሉ ክፍያ ለምንድነው…ለጠማማ ልብ?

በማኪያቶው ጉዳይ የሆንኩትን ለጓደኛዬ ስነግራት፣
‹‹እዛ ቤት እኮ ማኪያቷቸው ምርጥ ነው፡፡ ዋናው መጣፈጡ ነው፡፡ ልቡን አትበይው›› ብላ ነገሩን አጣጣለችብኝ፡፡

‹‹ ሴትዮ…ያለነው 2017 ላይ ነው…ማኪያቶ መጣፈጥም ማማርም አለበት..በተለይ በዚህ ዋጋ›› ብያት ተነስቼ ሄድኩ፡፡

በዚህ ጠባዬ ሳቢያ የአዲሳባ ምግብ ቤቶች የእኔን ጨጓራ በመላጥ የሚደርስባቸው የለም፡፡

ባለፈው አንዱ ጋር ለቁርስ ገብቼ ፍርፍር አዘዝኩ፡፡ ሲመጣ ምን ሆኖ መጣ…?

ግማሾቹ እንጀራዎች በብረት ዘነዘና የተቀጠቀጡ ያህል ደቀው ቁሌቱ ውስጥ ቦክተዋል፤ ሌሎቹ ደግሞ በረጅሙ እንደተጠቀለሉ ሳይቆራረጡ ከቁሌቱ ሳይደርሳቸው ደረቅ ግንድ መስለው ተጋድመዋል፡፡

‹‹ ይሄንማ ፍርፍር ብዬ አልበላም›› ብዬ የነገርኩት አስተናጋጅ እንዳበድኩ ዓይነት ሲያየኝ መልሼ አፈጠጥኩበት፡፡

ማምረሬ ሲገባው ፍርፍር ብሎ ያመጣውን ነገር በሃፍረት ይዞ ተመለሰ፡፡

አንዴ ደግሞ ስለቸኮልኩ ራይድ ጠራሁ፡፡

ሲደርስ በጣም ፈዛዛ ወይን ጠጅ ቪትዝ ነው፡፡
አፕሊኬሽኑ ላይ ቀለሙ ‹‹ወይን ጠጅ›› ተብሎ ስለተመዘገበ ስጋት ሽው አለኝና ሳልገባ በፊት ጎንበስ ብዬ ለሹፌሩ ይሄንኑ ነገርኩት፡፡

ሳቁ እያፈነው፣ ‹‹ፀሃይ መቷት ነው›› ብሎ አቃለለው፡፡

የታርጋ ቁጥሩን አመሳክሬ ካየሁ በኋላ ስለቸኮልኩ ከነቅሬታዬ ገባሁ፡፡

መኪናዋ ውስጥ እንደገባሁ ከባድ እፍነትና ሙቀት ተቀበለኝ፡፡

ወቅቱ በጋ ነው፣ ሰአቱ ቀትር፡፡

ከስር የሚንቀለቀል እሳት፣ ከላይ የተቃጠለ ኩበት ተደርጎ አክንባሎ እንደተደፋበት ድፎ ዳቦ ሰራኝ፡፡

ዋናው መንገድ ላይ ስንወጣማ ባሰብኝ፡፡

‹‹በጣም ይሞቃል- ኤሲውን ታበራው?›› አልኩኝ ለታሪክ በሚቀመጥ ትህትና፡፡

በታላቅ መገረም፤ ‹‹ኤሲ ነው ያልሽው…እንዴ! ..ኤሲማ አላበራም ነዳጅ ይበላብኛል…ከፈለግሽ መስኮቱን ክፈቺው›› አለኝ፡፡

ሁኔታው ኤሲ እንዲከፍት ሳይሆን የኢትዮጵያን የአየር ንብረት ለውጥ ችግር እንዲፈታ የጠየቅኩት ነው የሚመስለው፡፡

እኔ የምለው…የምከፍለው ለነዳጁም አይደለም እንዴ…?.ደግሞስ መገናኛ መሃል መስኮቴን ከፍቼ “ስልኬን ብሉኝ “ የምል ጅል እመስለዋለሁ?

ሆ! ሰው ማፈር አቆመ እኮ እናንተ፡፡

ለዚህ ለዚህማ ባይመቸኝ እንኳን አንከውክዎ የሚያደርሰኝ ሚኒባሴ ምናለኝ፡፡

ከብሬም ከምቾቴም ሳልሆን ስልኬን ከድሮን ጥቃት እንደምጠብቅ ሁሉ ከልዬ መስኮቱን ከፈትኩና ሄድኩ እላችኋለሁ፡፡

እዚህ ሃገር ከፍለውም፣ መሰረታዊም ቢሆን ደህና ነገር መጠየቅ አበሳ ነው መቼስ፡፡

ብቻ አያችሁ አይደል…እኔ የአመክንዮ ሰው ነኝ..ቀበጥ አይደለሁ፣ ብዙ ነገር አልጠይቅም ግን ትንሽዋን ነገር እንኳን ስጠይቅ ቀይ ባህርን ለሁለት ክፈሉልኝ ብዬ የጠየቅኩ ያህል ይገንብኛል፡፡

ነገሬን ለማሳመን አንድ ሌላ ነገር ልጨምርላችሁና ልልቀቃችሁማ፡፡

ሰሞኑን ሰርግ ተጠርቼ ነበር፡፡ በሰርግ ወረቀት፡፡
ግን ቀረሁ፡፡ የቀረሁት ደግሞ እንዲሁ በትንሽ ጉዳይ አይደለም፡፡

የጥሪውን ወረቀት ከፍቼ ሳነበው የሚዘገንን ነገር አየሁ፡፡

ከሙሽሪት ስም በፊት በ‹‹ወይዘሪት›› ፈንታ ‹‹ወይዘሮ›› ብለው ፅፈዋል፡፡

ይቅርታ ግን…ሙሽራዋ በጋብቻ ላይ ጋብቻ እየፈፀመች ነው ወይስ ነገሩ እንዴት ነው…? በእኔ እይታ፣ ይሄ ትልቅና ይቅር የማይባል በአማርኛችን ላይ የተፈፀመ ወንጀል ነው…

‹‹ይሄንን ስህተት እንደ ዋዛ የሰሩ ሰዎችን ሰርግ ታድሜ ተጋቡ አልልም›› ስል ጓደኞቼ እንደ ንክ ሰው እያዩኝ ነበር፡፡

አልፈርድባቸውም፤ እንዲህ ያለው ስህተት በተጋቢዎቹ ላይ እያደር የሚያመጣውን መዘዝ ስላልተረዱት ነው፡፡

ለማንኛውም ከወረደው ሰው ጋር ሁሉ አልውረድ እንጂ ራሴን ማሻሻል የምጠላ ሰው ስላልሆንኩ ከትላንት በስቲያ ወደ አንዱ (ደህና የምለው) ምግብ ቤት ሄጄ ነበር፡፡

‹‹እስቲ ለ24 ሰአት ምንም እንከን ሳላይ፣ አቃቂር ሳላወጣ እንደ ሌላው ሃበሻ ልዋልና ልደር›› ብዬ ራሴን ልፈትን፡፡

ገባሁ፡፡ ተቀመጥኩ፡፡ የምፈልገውን ምግብ አዘዝኩ፡፡

ከአስር ደቂቃ በላይ ለማይፈጅ ምግብ 11 ደቂቃ አስጠበቁኝ (ቻልኩት)

የምጠጣው ነገር ቀድሞ ይምጣልኝ ብልም አስተናጋጇን ማስታወስ ነበረብኝ (እሱንም ቻልኩት)

ያመጣችልን የሚጠጣ ነገር ካዘዝኩት በተቃራኒ ቀዝቀዛ ነበር፡፡ እኔ የጠየቅኩት " ቀዝቀዝ" እንዲል ነበር። ሎሚ ረስታለች (ይህንንም ቻልኩት)

በመጨረሻ ምግቡ መጣ፡፡

የቀረበውን ነገር ሳየው ግን መቻል አቃተኝ፡፡

ከሩዝ በአትክልት ጋር እንጀራ አጃቢ ሆኖ መጥቶልኛል፡፡

ይሄን ጊዜ ያችኑ ቀልብ የሌላትን አስተናጋጅ ጠራሁና፣
በትህትና- በጣም በትህትና- ሩዜ ከእንጀራ ጋር የመጣበትን ምክንያት ጠየቅኳት፡፡

‹‹አንዳንድ ሰው እንጀራ ስለሚፈልግ ነው፡፡ በዚያ ላይ ዳቦም አምጥተንልሻል እኮ…በዳቦ መብላት ከፈለግሽ›› አለችኝ ዳቦና እንጀራው አጠገብ ለአጠገብ ተሰትሮ የተቀመጠበትን የእንጨት ትሪ እያሳየችኝ፡፡

ልክ እስካሁን ዳቦ መኖሩን እንዳላየሁት ሁሉ፡፡

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

06 Oct, 06:46


‹‹ዋለለ››
-----
(ክፍል ሁለት)

-------------------

ለብቻችን ሆነን ለማውራት ስንፈልግ ስንፈልግ የምናዘወትረውና ሰው የማይበዛበት ካፌ ቀጠርኩት፡፡

ቦታውን የመረጥኩት በነገርኩት ነገር ቢናደድ እንኳን ቤት ውስጥ ስላልሆንን እንደ አባትና እናቴ ወይ እንደልቡ እንዳያንባርቅብኝ ያግደዋል፣ ግን ደግሞ ሰው ስለማይበዛበት በማናውቃቸው ሰዎች ፊት ገመናችንን ለማስጣት እንገደድም ብዬ ነው፡፡

ብዬ ነበር፡፡

ግን ያላሰብኩት ሆነ፡፡

ቀድሜው ደርሼ ትንሽ እንደጠበቅኩት ሰማያዊ ሱፍ ግጥም አድርጎ ለብሶ መጣ፡፡
ግራ ተጋባሁ፡፡
አማን ሰርግ ወይ የስራ ኢንተርቪው ከሌለበት ሱፍ መልበስ ሞቱ ነው፡፡
ምን ተገኘ?
በእሱ አለባበስ ተገርሜ ሳላበቃ ገና ከመቀመጡ ለወትሮው ትእዛዛችንን ተቀብለው ለብቻችን የሚተዉን አስተናጋጆች ባልተለመደ ሁኔታ ወዲህ ወዲያ ውር ውር እያሉ ሲመለከቱን ይበልጥ ግራ ተጋባሁ፡፡

ምንድነው?

ግራ መጋባቱ ሳይለቀኝ ሰላም ካልኩት በኋላ ራሴን ወንበሩ ላይ አመቻችቼ እንዲህ አልኩት፤

‹‹አማንዬ ስማኝማ…የማናግርህ ትልቅ ጉዳይ አለ ግን ሳልጨርስ እንዳታቋርጠኝ እ?››

በቃኝ ስልህ እንዳትጮህ፣ እንዳትናደድ ማለቴ ነበር፡፡

ገና የምለውን ነገር ሳይሰማ ፊቱ በደስታ እያበራ፣ ‹‹ሄዋንዬ እሺ ወዳንቺ እንሄዳለን ግን መጀመሪያ ልነግርሽ የጓጓሁለት ነገር ስላለ ሳልፈነዳ በፊት እኔ ልቅደም?›› አለኝ፡፡

ምንድነው?

‹‹ምን…ምንድነው ምታናግረኝ?›› አልኩ፡፡
አዲስ መጫወቻ እንደተገዛለት ህጻን ልጅ እየቦረቀ፣
‹‹የማወራሽ ትልቅ ነገር አለ›› አለኝ፡፡

ጌታ ሆይ!

‹‹ቪዛውን ሰጡህ?›› አልኩት አዎ ካለኝ እንዴት አድርጌ በቶሎ ማርሽ እንደምቀይር እያሰብኩ፡፡
‹‹አዎ ግን ስለ እሱ አይደለም የማናግርሽ!›› አሁንም ጥርሶቹ በሙሉ እስኪታዩኝ እየሳቀ፡፡

ስለ እሱ አይደለም?

እኔ የሚለኝን ነገር ለመረዳት ስባዝን የሚከተሉት ነገሮች በቅደም ተከተል ሆኑ፡፡

1ኛ- ቅድም ሲተራመሱ የነበሩት አራት አስተናጋጆች 40 ኢንች ቲቪ የሚያህል ፍቅር ስንጀምር የተነሳነው ሰልፊ ፎቶ ያለበት ኬክ እየተንገዳገዱ ተሸክመው መጡ፡፡
2ኛ- ቤስት ፍሬንዱ በትልቅ ስልኩ የሚሆነውን ሁሉ እየቀረጸና በጫት አረንጓዴ የሆኑ ጥርሶቹን ፈልቅቆ እያሳየ አጠገቤ መጥቶ ከነስልኩ መሽከርከር ጀመረ፡፡
3ኛ- ዛሬ እንለያይ ልለው የቀጠርኩት ቦይፍሬንዴ መሬት ላይ በግራ እግሩ ተንበርክኳል፡፡ በቀኝ እጁ ቀይ፣ ከፋይና ተከፍታ ቀለበት የያዘች ሚጢጢ ሳጥን ወደ ፊት አንከርፍፎ፡፡

ቀለበት! ባለ ፈርጥ የቃልኪዳን ቀለበት፡፡
እኔ ወንበሩ ላይ እንደተለሰነ ሰው በተቀመጥኩበት ‹‹ታገቢኛለሽ?›› ብሎ ጠየቀኝ፡፡

ያን ጊዜ ነው የወንዲ ማክ
“ታገቢኛለሽ ወይ” ሙዚቃ በካፌው ስፒከሮች ያለቅጥ ያንባረቀው፡፡

ዘፈኑ፣
‹‹ውዴ…እኔና አንቺ ለዚህ ቀን እንደርሳለን ብለሽ አስበሽ ታውቂያለሽ?›› ብሎ በንግግር ሲጀምር፣
ክው አልኩ፡፡ ህእ! አስቤ አላውቅማ!
ዝም ብዬ በተቀመጥኩበት ጓደኛው መቅረጹን ሳያቆም መጥቶ በግድ ጎትቶ አስነሳኝና የተንበረከከው አማን ፊት አቆመኝ፡፡

ቁልቁል ሳየው እንዲህ ብሎ ቀጠለ፡፡
‹‹ሄዋንዬ፣ ካናዳ ሄደን አዲስ ሕይወት እንድንጀምር እፈልጋለሁ፡፡ ቀለበት እንሰር፤ እንጋባና አብረን እንሂድ፡፡ እንውለድ፤ እንክበድ፡፡ ታገቢኛለሽ?››
ጌታ ሆይ!

ከባድ ወጥመድ ውስጥ ገባሁ፡፡ ለዚያውም በቪዲዮ የሚቀረፅ ወጥመድ ውስጥ፡፡

ዘፈኑ ሲሟሟቅ፣ ካፌው ውስጥ የነበረው ጥቂት ሰው ሁሉ ወደ እኛ ሲመለከት፣ የከበቡን አስተናጋጆች (ታሪካችንን ያውቁት ይመስል) እያሽቃበጡ ሲያጨበጭቡ፣ ጓደኛው ብዙ እንደተከፈለው የቪዲዮ ባለሙያ እየዞረን ሲቀርጽ፣ አማን አይን አይኔን ሲያየኝ እንደ መንቃት ይባስ ደነዘዝኩ፡፡

ልቤና መንፈሴ ዋለለ፡፡
ምን ባደርግ ይሻለኛል?
እምቢ ብዬ እዚህ ሁሉ ሰው ፊት ላዋርደው…ቅስሙን ልስበረው?
ቲክቶክ ላይ ሊለቀቅ የሚችል ቪዲዮ ላይ ‹‹እምቢ አላገባህም!›› ልበለው?
ወይስ በይሉኝታ እሺ ብዬው ራሴን የባሰ ማጥ ውስጥ ልክተት?

‹‹እ….ታገቢኛለሽ?›› አለ ደግሞ በልምምጥ፡፡

በተበታተነ ሃሳቤ መሃል አማንን አተኩሬ አየሁት፡፡

በድንገት ፊት ለፊቴ ተንበርክኮ ‹‹አግቢኝና ካናዳ ልውሰድሽ›› የሚለው ልለየው ያቀድኩት ቦይፍሬንዴ ብቻ እንዳልሆነ ተከሰተልኝ፡፡

ፊት ለፊቴ የተንበረከከው የማይደገምና ብዙዎች የሚመኙት፣ ብዙዎች መስዋእትነት የሚከፍሉለት፣ ንብረት ሸጠው የሚገዙት ታላቅ ከዚች ሃገር የማምለጥ እድል ነው፡፡
ስራ ለመሄድ የታክሲ ወጪዬን እንኳን የማይሸፈን አስር ሺህ ብር ደሞዝ እየተቀበልኩ እየኖርኩ እንዲህ ያለውን ታላቅ እድል እምቢ ብዬ ብገፋ የእግዜርን ዐይን መውጋት አይሆንም?

እምቢ ብለው፣ እማዬ ቆዳዬን ነው የምትገፈው፡፡
ጓደኖቼ እብድ ነሽ ይሉኛል፡፡ የአማን ዐይኖች ያረፉባት የልብ ጓደኛዬ ደግሞ ይሄንን እድል ብታገኝ ከመቀበል አልፋ ለማንኛውም ብላ (ለቀብድ እንዲሆን ) መንታ ታረግዝለት ነበር፡፡

ስለዚህ እሺ ልለው ወሰንኩ፡፡

ነገር ግን አማንን አግብቼ ካናዳ ብሄድ መንገድ የለመዱ አይኖቹ ሌሎች ሴቶችን ሲቃኙ፣ ጓደኞችና ኳስ ጨዋታን ደጋግሞ ከእኔ ሲያስቀድም፣ ከእሱ በስተቀር ሌላ ሰው በማላውቅበት ሃገር በብቸኝነት ሲያቆራምደኝ ታየኝና ‹‹እሺ›› የምትለዋ ቃል ከንፈሬን አልፋ መውጣት አቃታት፡፡

ቢሆንም እሺ አልኩት፡፡

የከበበን ሰው ሁሉ በሆታ ሲያጅበን፣ ካናዳን ከመርገጤ ታናሽ እህቴን ቶሎ ወስጄ እንደምፈታው እያሰብኩ ነበር፡፡

Hiwot Emshaw

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

05 Oct, 15:08


‹‹ዋለለ››
(ክፍል አንድ)
----------------

ከቦይፍሬንዴ ጋር መለያየት የነበረብኝ ከስድስት ወራት በፊት ነበር፡፡ ግን ይሄው ደህና ከጀመረ በኋላ አለ ቅጥ እንደተንዛዛውና ለዛውን እንዳጣው ሰው ለሰው ድራማ ነገሮችን ስጎትት ስጎትት እዚህ ደረስን፡፡

ለምን በጊዜ መቁረጥና መለያየትን ፈራሁ?

ምነው እንደ ትዕግስት ዋልተንጉስ ሰራሽ አትበሉኝና፤ ይሄ ጠባዬ ከልጅነት ጊዜ ጠባሳዬ ጋር ይገናኝ ይመስለኛል፡፡

ሰውን ፊት ለፊት ገጥሞ በግልጽ ማውራትና ያበጠን ማፈንዳት ክፉኛ እፈራለሁ፡፡ ሰዎች ከጣራ በላይ እየጮሁ ሲያወሩ ሁለመናዬ ይረበሻል፤ ጠብ ያርደኛል፡፡

እናቴ አባቴ ላይ በሆነው ባልሆነ ትጮህበት ነበር፡፡

አለ አይደል…ለምን ማታ የተቃጠለውን የመኝታ ቤት አንዱን አምፖል ወዲያው አልቀየርከውም ብላ ድምፅዋ አድዋ ተራሮች ድረስ እስኪሰማ ታምባርቅበታለች፡፡ እሱም የዋዛ አይደለም- መልሶ ያምባርቅባታል፡፡ ያን ጊዜ ሽንቴ ሊያመልጠኝ ይዳዳል፡፡

በእንዲህ ሁኔታ ሲጯጯሁ በነበረ ጊዜ ሁሉ እንደኔ በፍርሃት የምትርደውን ታናሽ እህቴን ይዤ ወደ መኝታ ክፍላችን እሸሽና በሩን ዘግቼ ክፍላችን ራስጌ ጠረጴዛ ላይ ያለችው ቴፕ ውስጥ ያኘሁትን ሲዲ አለ ቅጥ ከፍ አድርጌ እከፍትና ከጩኸትና ስድባቸው ልከልላት እሞክራለሁ፡፡

እኔን የሚከላከልልኝ ሰው ግን አልነበረልኝም፡፡ ያን ጊዜ ጭንቅላቴን እግሮቼ መሃል ድፍት አድርጌ ጆሮዎቼን በሁለት እጆቼ ለመሸፈን እየሞከርኩ ፣

ለምን ቀስ ብለው አያወሩም?
ለምን እንዲህ ከሚጮሁ ነገሮችን በውስጣቸው ችለው በዝምታ አያሳልፉም? እል ነበር፡፡

ለዚህ ይመስለኛል ሁለት አመት ተኩል አብሬው ከቆየሁት ቦይፍሬንዴ ጋር ሲሆን ከዐመት፣ ቢያንስ ከስድስት ወራት በፊት መለያየት ሲኖርብኝ እስከዛሬ ነገሮችን ችዬ የከረምኩት፡፡

ያለ ነገር አይደለም ልለየው የምፈልገው፡፡ ምክንያቶች አሉኝ፡፡ ሁለቱ አንኳር ችግሮቼ እነዚሁና!

አንደኛ- ለእኔ የሚሆን ጊዜ የለውም፡፡ የማስበውን ያህል፣ የማስብለትን ያህል አያስበኝም፣ አያስብልኝም፡፡ ከሥራ እና ከእንቅልፍ የተረፈውን ሰዐቱን በተቀዳሚነት የሚሰጠው ለሁለት ነገሮች ነው፡፡ ለእግር ኳስና ለጓደኞቹ፡፡ እኔ የትርፍ ጊዜ ሥራው፣ ትዝ ስለው ጊዜ የሚሠጠኝ ነገር ነኝ፡፡

ወንድሙ ጅራ፣
‹‹የእኔ ጉዳይ የኔ ኑሮ ካሁን በኋላ፣
ያንቺ ሆኗል የኔ ፍቅር የኔ ወለላ፣
ቅድሚያ የምሰጥሽ ከምንም፣
ለእኔ በምድር ላይ ያለሽ ጉዳዬ ነሽ›› ብሎ ሲዘፍን ደሜ የሚንተከተከው ለዚህ ነው፡፡

ሁለተኛ- ዐይኖቹ ቅብዝብዝ ናቸው፡፡

እዚህም እዚያም ሌላ ያያሉ፡፡

ቆንጆ ሴትን በመስገብገብ ሰርቀው ይቃኛሉ፡፡ ሌላ ሴት ያያል ስላችሁ ዝም ብሎ መንገድ ላይ፣ በየካፌው ብቻ እንዳይመስላችሁ፡፡ እነዚሁ ቀበጥባጣ ዐይኖቹ ስንቱ ሴት ላይ ነጥረው ሲያበቁ የልጅነትና የልብ ጓደኛዬ ላይም አርፈዋል፡፡

እርግጥ ነው እሱ በለመደው ምኞቱ ይመልከታት እንጂ በሁለቱ መሃከል ምንም የተፈጠረ አይመስለኝም፡፡ ቆይቶ ግን፣ ‹‹እኔ ግን አስተያየቱ ስለሚደብረኝ አብሬያችሁ ባልሆን›› ስትለኝ ሃፍረት አንገቴን አስደፋኝ፡፡ ያኔ ነበር ልለየው የሚገባኝ ግን እንዳልኳችሁ ሁኔታን ተጋፍጦ ማለፍ ስለማይሆንልኝ ታስሬ ቆየሁ፡፡

ለዚህ ነው ነፃነት መኮንን የምትባል የዘጠናዎቹ ዘፋኝ፣
‹‹ከእኔ ምን አጥተህ ነው- ከእኔ ምን ጎድሎህ ነው፣
ዐይንህ ታዲያ ሌላ የሚያየው -መንገድ መንገድ ያሰኘው›› የሚል በልጅነቴ የሰማሁት ዘፈን ዛሬ ደርሶብኝ ሲገባኝ የተብሰለሰልኩት፡፡

ይህንን ጉዳይ ይበልጥ ያወሳሰበውን ነገር ደግሞ ልንገራችሁ፤ ቦይፍሬንዴ እንዲህ በብዙ ነገር ስሜቴን ይጉዳው፣ ጨጓራዬን ይላጠው እንጂ ደህና ጎን የለውም ለማለት አልችልም፡፡

ይንከባከበኛል፡፡ ጊዜውን እንጂ ገንዘቡን አይሰስትም፡፡ ሁልጊዜ በአበባና በተለያዩ ስጦታዎች እንዳንበሸበሸኝ ነው፡፡ አንዳንዴ ደግሞ ያለ ምክንያት፣ ሳይጠየቅ፣ ሳይጠበቅበት የሚገርም ነገር ያደርጋል፡፡ ለምሳሌ ቤት ደብሮኝ ቁጭ ብያለሁ ምናምን ስለው ቻኖሊ ሄዶ የምወደውን ኑድልስ አሰርቶልኝ ቤት ድረስ ያመጣልኝና ስሞኝ ይሄዳል፡፡

ደስ አይልም?

የዛሬ ዘጠኝ ወር አባቴ ሲሞትም ካጠገቤ አልተለየም፡፡ ቀን በሉት ሌሊት በሉት እጄን ይዞ ትከሻዬን እየደባበሰ ሲያፅናናኝ፣ ነገሮችን ሲያስተካክልና ስርአት ሲያሲዝ፣ እኔንም፣ እናቴንም፣ እህቴንም አንደኛ ዘመድ የተባለ ሰው ካደረገው በላይ ሲንከባከብና ሲያፅናናን ከረመ፡፡

ይሄን ሁሉ ሲያይ የሰነበተው እድርተኛ፣ ጎረቤትና ዘመድ አዝማድ፣ ‹‹ይሄማ ብረት መዝጊያ ነው›› ብሎ የምስክር ወረቀት ሰጠው፡፡
በዚያች ሰሞን ለነበረው ቦይፍሬንድነቱ ያ የምስክር ወረቀት ቢያንስበት እንጂ አይበዛበትም ግን…..እንዳልኳችሁ ሁልጊዜ እንደዚህ አይደለም፡፡ ያ ነው ናላዬን የሚያዞረው፡፡ አንዱን ይዞ ወጥ ሰው ቢሆንማ ምንኛ በቀለለኝ፡፡

አባቴን አፈር ባቀመስን በሶስተኛው ወር፣
‹‹የካናዳ ቪዛ ፕሮሰስ ከጀመርኩ ሶስት ወር ሆነኝ፡፡ እያለቀልኝ ነው፡፡ ከተሳካልኝ የምመለስ አይመስለኝም›› አለኝ፡፡
ከጀመርኩ፡፡ እያለቀልኝ ነው፡፡ ከተሳካልኝ፡፡ የምመለስ አይመስለኝም፡፡
አያችሁት አይደል!

የእሱ ነገር እንዲህ ነው፡፡

ራሱን ብቻ ነው የሚያስበው፡፡ አንድም ቦታ ስለ እኔ አላሰበም፡፡ እቅዱ ውስጥ አልደመረኝም፡፡

ልክ እንዲህ ሲለኝ በቃ እንለያይ ማለት ነበረብኝ ግን መልሼ ሳስበው ቪዛ አግኝቶ በቅርቡ መሄዱ ላይቀር ለምን አፌን አበላሻለሁ …? ለቅሶው ላይ እንደዛ ሲሆንልኝ ያየስ ሰው ምን ይላል…ልታግስና ካናዳ ወስዳ ትገላግለኝ ምናምን ብዬ ዝም አልኩ፡፡

ዝም ብልም ራስ ወዳድነቱ ለእሱ የነበረኝን ስሜት ከፍቅር ወደ ተራ ጓደኝነት፣ ከተራ ጓደኝነት ደግሞ ወደ ‹‹መቻል›› በፍጥነት ያወርደው ጀመረ፡፡

‹‹በቅርብ ይሄድና ሁሉ ነገር ያበቃለታል›› ብዬ መጠበቄን ቀጠልኩ፡፡

ግን አልሄደም፡፡

ጭራሽ የዛሬ ወር የቪዛ ፕሮሰሱ እንዳሰበው እንዳልሄደለትና ተጨማሪ መረጃ አሟላ ብለው እንደጠየቁት፣ በዚህ ምክንያት ከዘገየ ለአንድ ዐመት እዚሁ እንደሚቆይ አይነግረኝም?

ኤጭ!

ለዚህ ነው ዛሬ የመጣው ይምጣ ብዬ እንለያይ ልለው የቀጠርኩት፡፡ ከዚህ በላይ መጠበቅ አልፈልግም፤ አልችልም፡፡

ይቀጥላል . . .
Hiwot Emshaw

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

05 Oct, 07:34


ባሻዬ! ከሚስትህ ጋር ኳስ ጨዋታ አትመልከት ብዬ ከአንዴም ሁለቴ መክሬህ ነበር። ዛሬ ለ3ኛ ጊዜ ልንገርህ።

የማንቼን ጨዋታ ለማየት ትናንት ማታ ቁጭ ባልኩበት ሚስቴ ከባድ ጥያቄ ጠየቀችኝ፣

"ስንት ደቂቃ ነው የሚጫወቱት?"

"በመጀመሪያ 45 ደቂቃ"

"ለምን 45 ደቂቃ ሆነ?"

በጥያቄዋ ደንግጬ ትንሽ ካሰብኩ በኋላ፣

"ሜዳ ውስጥ ያለ ማቋረጥ የሚንቀሳቀሱ 45 ድቡልቡል ነገሮች ስላሉ ነው"

"ምንድን ናቸው?"

"በአንዱ ቡድን ውስጥ 11 ተጫዋቾች ስላሉ በሁለቱም ቡድኖች ውስጥ 22 ተጫዋቾች ይኖራሉ። እያንዳንዱ ተጫዋች ሁለት ሁለት የዘር ፍሬ ስላለው በአጠቃላይ 44 ድቡልቡል የዘር ፍሬዎች በከባድ እንቅስቃሴ ላይ ይገኛሉ"

"አንድ ይጎድላል እኮ!"

"አንዷማ ኳሷ ነች"

Tesfaye Hailemariam

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

04 Oct, 05:25


ታሪክን ወደ ሁዋላና ወደፊት
(በእውቀቱ ስዩም)

ያልተበረዘውን የኢትዮጵያ ታሪክ የሚያነብ ሰው ፥ መጀመርያ የሚመጣለት ስሜት “ wtf ? ምን ጉድ ነው ?” የሚል ነው ፤ ለምሳሌ ነገስታት አንድ ልማድ ነበራቸው ፤ልክ ዙፋን ላይ ሲወጡ ልጆቻቸውን እና ወንድሞቻቸውን ሰብስበው ከመዲናቸው ራቅ ያለ ማጎርያ ቦታ ያስቀምጧቸዋል፤ የማጎርያው መልክአምድር ለማምለጥ አይመችም፤ ከዚያም አልፎ፤ በንቁና አስፈሪ ዘበኞች ይጠበቃል፤ በአክሱም ዘመን ደብረዳሞ የልኡላን ማጎርያ ሆኖ አገልግሏል፤ የሸዋ ነገስታት በተራቸው ሲገዙ፤ ለዚህ ተግባር የመረጡት ቦታ፥ ወሎ ዛሬ ግሼን ማርያም የምትገኝበትን አምባ ነበር፤ የጎንደር ነገስታት በበኩላቸው ዘመዶቻቸውን “ወህኒ” ወደ ተባለ ስፍራ ማጋዝ ጀመሩ፤ ወህኒቤት የሚለውን ቃል የወረስነው ከዚህ ስፍራ ነው ፤ ወህኒ በመሰረቱ የፖለቲካ እስር ቤት ሲሆን ፥የመጀመርያው የፖለቲካ ወንጀል ከንጉስ መወለድ ነበር፤

ንጉሱ ድንገት ወራሹን ሳያሳውቅ በጦር ሜዳ ይገደላል እንበል፥ አንዱ የቤተመንግስት መኮንን ብድግ ይልና አንዱን ልኡል ከማጎርያ ቤት አውርዶ ዙፋን ላይ ያወጣዋል፤ ሌላው የጦር አዝማች ደግሞ የኔን ምርጫ ካላነገስኩ ሞቼ እገኛለሁ ብሎ ይነሳል፤ ባንጋሾች መካከል የሚደረገው ፉክክር መዲናይቱን ባንዴ ወደ ፍርስራሽ እና ያስከሬን ክምር ይቀይራታል::

የቀድሞ ሰዎች እንዲህ አይነቱን ብሄራዊ አደጋ ለመቀነስ የፈጠሩት “ዘዴ “ የንጉስን ሞት መሰወር ነበር ፤ የንጉስ ሞት ቀርቶ ህመሙ እንኳ ለህዘብ ይፋ አይደረግም፤ በዘመነ መሳፍነት ጊዜ ፥ የየጁው ራስ አሊ ሲሞት ፤ አንድ አሳባቂ ( የዘመኑ ፓፓራዚ) ወሬውን አሾለከው፤ ወድያው የረጋው አገር መላወስ ጀመረ፤ ጉዳዩ ያሳሰባት አንዲት አልቃሽ እንዲህ ብላ ገጠመች፥

“ እሻ እሻ ነው እንጂ የእስራኤልን ሞት
እንዲያልቅሰው አሊን ለምን ቀበሩት “

“ እሻ እሻ “ ማለት ዝም በሉ ጸጥ በሉ ማለት ነው ፤ በዘመኑ የንጉስ ወገን ነን የሚሉ ሰዎች ዘራቸውን ከሰለሞን ስለሚመዝዙ “ እስራኤል “ በሚል የወል ስም ይታወቃሉ፤
በግጥሙ መስመር ላይ ያለው ህብረቃል “ እንዲያልቅሰው “ የሚል ነው፤ ሰሙ “ እንዲህ አልቅሰው “ ሲሆን ወርቁ “ ሰው እንዲተላለቅ” የሚል ትርጉም አለው ፤

ባጭሩ አልቃሺቱ፥
“ ህዘብ እንዳይተላለቅ
የንጉስ ሞት ይደበቅ “ ማለት ነው የፈለገችው ፤

ከጥንት እስከዛሬ አገረ -መንግስታችን የሚቆመው ባንድ ሰው ትከሻ ላይ ነው ፤ መሪ ሲታመም አገር ይታመማል፤ መሪ ሲሞት አገር በጥቂቱ ይሞታል፤ ይህንን መለወጥ የሚቻለው እንዴት ነው? የማይሞቱ ተቋሞችን በመገንባት ፤ የማይታመሙ ህጎችን በመመስረት? ወይስ ሌላ መላ አለ?

Bewuketu Siyuom

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

03 Oct, 10:47


‹‹እናትህ----››
----------------

አዲስ አበባ፡፡ የመንግስት ትምህርት ቤት፡፡ ዘጠነኛ ከፍል ታሪክ ክፍለ ጊዜ፡፡

‹‹ቲቸር…እንቅልፍ ሊወስደን እኮ ነው…ትንሽ ነቃ እንድንል እያደረጉ አስተምሩን እንጂ…››አለ ናትናኤል ዴስኩ ጠረጴዛ ላይ ተኝቶ እያዛጋ፡፡

ቲቸር በላይነህ አይናቸው ደም ለበሰ፡፡

‹‹ይሄ ቲክቶክህ መሰለህ…? ትምህርት ነው አንተ ደደብ!›› አሉ በንዴት፡፡
‹‹አትሳደብ ሰውዬ…!››አለ ናትናኤል ከተኛበት ቀና ብሎ፡፡
ቲቸር በላይነህ ለወትሮም የማይፈታው ግንባራቸው ታይቶ የማይታወቅ ግንድ ግንድ የሚያካክል የደም ሥር አበቀለ፡፡
‹‹ውጣ አንተ ዱርዬ.! ውጣልኝ!›› አሉ በጩኸት፡፡

የዛሬ ልጆች፡፡ የዘንድሮ ተማሪዎች፡፡ ታላቅ አያከብሩ፡፡ አስተማሪ አይፈሩ፡፡ በእኛ ጊዜ ቢሆን እንዲህ የተናገረ ተማሪ ተመንግሎ ነበር ከትምህርት ቤት የሚባረረው…ሊያውም አርባ ተገርፎ…ሊያውም ቀኑን ሙሉ እጅ በጆሮ ይዞ እያሉ ያስባሉ፡፡

የበሰበሰ ጊዜ፡፡

ይሁን ብቻ፡፡ አንድ አመት ነው የቀረኝ በጡረታ ልገላገል፡፡ ከዚህ ሲኦል ላመልጥ፡፡ የማያልቅ ስራ፡፡ ሆድ እንኳን የማይሞላ ደሞዝ፡፡ እነዚህ ስድ ለወላጅ ያስቸገሩ አግድም አደግ ልጆች፡፡ ትምህርት አይገባቸው፡፡ መምህር አያከብሩ፡፡ በእኛ ጊዜ እኮ አስተማሪ በሽቶ እግሬን እጠበኝ ቢል እንኳን እናጥብ ነበር፡፡

የበሰበሰ ጊዜ፡፡

ቲቸር በላይነህ ናትናኤል ከዴስኩ ተነስቶ በሩ ጋር እስኪደርስ ይሄን ሁሉ አሰቡ፡፡

ናትናኤል በሩ ጋር ሲደርስ ክፍል ውስጥ ያሉት ልጆች ጩኸት በረታ፡፡

‹‹ዝም በሉ ብያለሁ እናንተ ደግሞ! ›› ሲሉ ግን ድንገት ረገበ፡፡
ያኔ ነው ጆሯቸውን ያደማው ነገር ከናትናኤል አፍ በለሆሳስ ሲወጣ የሰሙት፡፡
‹‹እናትህ…››

ንዴት የሚደርጋቸውን አሳጣቸው፡፡ አፋቸውን ከፍተው ሊናገሩ ሞከሩ ግን ቃላት ማውጣት አቃታቸው፡፡

ህመም ብቻ፡፡ ቀሳፊ የደረት ላይ ህመም፡፡

ደረታቸውን እንዳቀፉ የሲሚንቶው ሊሾ ወለል ላይ ዝ-ር-ግ-ፍ አሉ፡፡

በወደቁበት ከበው የሚያዩዋቸውና የሚንጫጩትን በርካታ ተማሪዎች ፊቶች ይመለከታሉ፡፡ በጡረታ ለመገላገል ይሄ አመት ብቻ ነበር የቀራቸው፡፡

ራሳቸውን ለመሳት ሲቃረቡ፣ አንዴ አፉን በእጁ ሸፍኖ በከባድ ድንጋጤ የሚያያቸው ናትናኤልን አንዴ ደግሞ የክፍሉ ኮርኒስ ጥግ ላይ ተስሎ የሚገኘውን ከሰላሳ አመታት በፊት ያረፉት የእናታቸው ውብ መልክና ‹‹ና ልጄ!›› በሚል የተዘረጉ ሁለት ቀጫጭን
ክንዶቻቸውን እያዩ እንዲህ አሉ፡፡

‹‹እናቴ…እማዬ…እማዬ…!››

ተማሪዎቹ ግራ በመጋባት ይባስ ተንጫጩ፡፡

ቲቸር በላይነህ እንስፍስፍ እናታቸውን ሲመለከቱ ተማሪያቸው ናትናኤል የሰደባቸው አፀያፊ ስድብ እንደቅድሙ አላናደዳቸውም፡፡

ይልቁንም ከወዲያኛው ዓለምም ልጇን ለመቀበል የማይደክም እጆችዋን የምትዘረጋውን እምዬን በእንዲህ ያለ ስድብ በማርከሱ አዝነውለት ነበር፡፡

Hiwot Emshaw

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

02 Oct, 06:53


‹‹ውድድር››
————————-

‹‹ባይሽ ባይሽ ቁምነገር አጣሁብሽ›› ብሎ ስለተወኝ ከተለየሁት የቀድሞ ፍቅረኛዬ ጋር ከዓመት ተኩል በኋላ በአጋጣሚ ባንክ ተገናኝተን ነው፡፡

ብዙም ሳይዘገይ በሌላ እንደተካኝ ሰምቻለሁና፤ ከሰላምታ በኃላ፣

‹‹አዲሷ እኔ እንዴት ናት?›› አልኩት፡፡

‹‹በጣም ደህና ናት ግን ፈፅሞ እንዳንቺ አይደለችም›› አለኝ፡፡

ይሄ ጭካኔው አሁንም አልለቀቀውም፡፡ አሁንም ራሱ የሰጠኝ ያልሻረ ቁስሌ ውስጥ እንጨት ይሰዳል፡፡

‹‹ደህና ናት›› ብሎ መተው ማንን ገደለ?

‹‹ፌስቡክ እና ኢንስታግራም ላይ ብፈልጋት ብፈልጋት ላገኛት አልቻልኩም…የገጠር ልጅ ናት እንዴ ?›› አልኩት በጭካኔ አፀፋውን ለመመለስ ነገር አድርቼ፡፡

የተወጋ ሰው መልሶ የመውጋት መብት የለውም ?

እኔ ፌስቡክ እና ኢንስታግራምና ላይ ተደምሮ ከዘጠና ሺህ በላይ ተከታይ እንዳለኝ ያውቃል፡፡ ቲክቶኬም በፍጥነት እያደገ ነው፡፡

ስሜቴን እንደ ጎዳው ስሜቱን ጎዳሁት ብዬ እርካታዬን አጣጥሜ ሳልጨርስ..
ድንገት ካገኘኋት እንዲህ እላታለሁ ብሎ አጥንቶ ሲያፈላልገኝ የከረመ በሚያስመስል ፍጥነትና ቅልጥፍና፣

‹‹ያዲሳባ ልጅ ናት ግን የማያውቃት ተከታይ ሳይሆን ከልጅነት እስከ እውቀት የሚያውቋት ጓደኞች፣ ከሩቅ ኑሮዋን እያዩ የሚያደንቋት የማታውቃቸው ሰዎች ሳይሆኑ ሁሉንም የምትካፈላቸው ወዳጆች፣ በፎቶና በቪዲዮ አይተዋት የሚሻፍዱባትና ወዲያው ከነ መኖሯ የሚረሷት ሺህ ወንዶች ሳይሆኑ ልቡን እንቺ ብሎ ያስረከባት እጮኛ ስላላት የእኔዋ ኢንስታግራምና ፌስቡክ ላይ አትገኝም፡፡ ለዚህ ነው አንቺን አትመስልም ያልኩሽ›› አለኝ፡፡

ይሄ ሰውዬ ከዚህ ሁሉ ሃተታ ከባንኩ ጥበቃ ጠመንጃ ተውሶ ተኩሶ የማይገድለኝ ለምንድነው ?

ፊቱ ላይ ያለው የ‹‹ልክ ልኳን ነገርኳት›› የደስታ ስሜት አቃጠለኝ፡፡

ጉዳዬን ሳልጨርስ ከእምባዬ እየታገልኩ ከባንኩ ሮጨ ወጣሁ፡፡

Hiwot Emshaw

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

26 Sep, 13:24


‹‹እዛ ነገር ላይ አሪፍ ከሆንሽ …››
(አሌክስ አብርሃም) ማስታወሻ

‹‹ወይኔ ይሄ ባል አይደለም  እናትኮ ነው  እናት... ›› ትለኛለች  በተገናኘን ቁጥር ! ስለባሏ አውርታ አትጠግብም ! አንዴ ከጀመረች ሰው የሚሰለች አይመስላትም ! ጧት ተነስቶ  ቁርስ ሰርቶ ፣ ልጆቹን አለባብሶ …በቃ መንገድ ላይ ሲያልፍ ልብስ ካየ  ለራሱ እንኳን አይገዛም …ልበሽ ነው ይመርብሽ ነው …ፀጉርሽን ተሰሪ ነው …አመመኝ ካልኩ ቀድሞ ነው የሚታመመው …ማታ  ከስራ ሲወጣኮ ብታየው  በቃ ብን ብየ የምጠፋበት ነው የሚመስለው ወደቤት ነው …እንደውም ባለፈው ወደቤት ሲመጣ ከፍጥነት በላይ ነድቶ ትራፊክ ፖሊስ ሲያስቆመው ምን ቢል ጥሩ ነው?

‹‹ትንሽ ካመሸሁ የሚስቴ ምላስ  ሳማ ነው  አለው ?››

‹‹ሒድ ወደዛ  ሞዛዛ ‹ ሚስቴ ናፍቃኝ ነው›  ብሎ  ትራፊክ ፖሊሱን አሳቀው ሂሂሂሂ …ወንዶች ብዙ ነገር ከሱ መማር ትችላላችሁ ….ፀጉሬን ሁሉ ይሰራኛል ብልህ ታምናለህ ….?!>>  እና ሞልቀቅ ብላ …<<የኔ ጀግና እዛ ነገር ላይስ ቢሆን አንበሳኮ ነው>>  ከእኔ አልፋ ፌስቡክ ላይ  ባሏን ….ሰማይ ስታደርሰውና  ሆድ ለባሰው ባለትዳር ሁሉ  ምክር ስትሰጥ  ትውላለች ….የበሉት የጠጡት .. ባሏ የተነፈሰው ያስነጠሰው ሁሉ አይቀርም  ….እንደጉድ ትፅፈዋለች ! ባሏም እሷም ጓደኞቸ ናቸው ! በተቃራኒው ባሏ ፌስቡክ የሚባል ነገር ይዘፈንበት ይለቀስበት አያውቅም ! የስራ ሰው ነው ! ወሬው ቁጥብ ለዛውም ስለስራ ብቻ ! አለፍ አለ ከተባለ ስለልጆቹ ትምህርት !

   አንድ ቀን ታዲያ  ባሏ እፈልገሃለሁ አለኝ …ንጭንጭ ብሎ
‹‹ምነው በሰላም ?››  አልኩ! ሰዓቱ የስራ ሰዓት ስለነበር ግርር ብሎኝ ! 
‹‹ባክህ ምን ሰላም አለ ይች ልጅ አስመረረችኝ …››
‹‹  የቷ ልጅ? ዛሬም ስልክህን ሰበረችው? ›› ብየ ሳኩ... ትልቋ ልጁን ነበር ያሰብኩት
‹‹ስለእናቲቱ ነው የማወራህ ›› አለ በስጨት ብሎ ተገናኘን !

‹‹ ጓደኛ ነህ … ሚዜ ለመሆን ከመንከርፈፍ ተው አትሆንህም ብትለኝ  ምን ነበረበት  …?›› አለ እንባ እየተናነቀው …ጉድ ፈላ አልኩ !

‹‹ማለት …››

‹‹ስማኝ ስማኝ …አታቋርጠኝ … እኔ ያገባሁት እሷን ነው ወይስ የፌስቡክ ጓደኞቿን ?… እኔኮ እቤት ውስጥ ለስሙ እኖራለሁ …ለስሙ ገመናየን ለመሸፈን የቤት ኪራይ እከፍላለሁ እንጅ ''ኦፊሻሊ'' በረንዳ አዳሪ ነኝ …አላፊ አግዳሚው ምን እንደምበላ …ምን እንደምለብስ …ስተኛ ምን ፒጃማ እንደምለብስ …ልጆቸ ጋር ምን እንደማወራ … ወጣ ብየ ቤተሰቤ ጋር የት እንደምዝናና አገር ነው የሚያውቀው … አዲስ ልብስ ገዝቸ ለብሸው ስወጣ ጓደኞቸ ኦ ይሄን ነገር ከዚህ በፊት ለብሰኸ አይቸዋለሁ ልበል ? ይሉኛል …ያው ፌስቡክ ላይ እሷ ለጥፋው ነው ….ምንድናት ?…ጋዜጠኛ ናት ሚስት ?… የራሷንም የቤተሰቧንም ገመና አደባባይ ላይ በማስጣት በላይክና ኮሜንት ነፍሷን የምታስታምመው ለምንድነው …?ትዳራችን ደብሯታል …?››

‹‹እሱ እንኳን በትዳሯ መደሰቷን በቤተሰቧ መኩራቷን ለማሳየት ይመስለኛል …ስንቷ ናት የባሏን ፎቶ መለጠፍ ቀርቶ አግብቻለሁ ማለት የምታፍር ...?›› አልኩ …

‹‹  ኩራት እንደአፋልጉኝ  ማስታወቂያ  ፎቶህ በየአደባባዩ ስለተለጠፈ ነው እንዴ ….ይሄ እንደውም  በትዳር አለመደሰት አለመርካትና ይሄን መሰላቸት  በዚህ ለመሸፈን የሚደረግ ጥረት ነው ! ሰው እንዴት የምኝታ ቤቱን ፎቶ ይለጥፋል? …ህዝቡኮ አብሮኝ አንሶላ ውስጥ መግባት ነው የቀረው …. ልጆቸ ራሳቸው ሰለቻቸው …ሲስቁ ፎቶ ፌስቡክ ላይ …ሲያለቅሱ ፎቶ ፌስቡክ ላይ …ውጤታቸው ዝቅ ሲል የፈተና ወረቀታቸው ፎቶ ፌስ ቡክ ላይ …አጥፍተው ሲቀጡ ፎቶ ፌስቡክ ላይ ….ወድቀው ሲፈነከቱ ከሆስፒታል ቀድማ ፎቷቸውን ፌስቡክ ላይ …አከራያችን ኪራይ ዘገየብኝ ሲሉ አገር ይስማ ፌስቡክ ላይ …..ሌላው ይቅር በየወሩ ደመወዝ ስቀበል አዋጅ ፌስቡክ ላይ ‹‹ዛሬ የደመወዝ ቀን ነው ፈታ ልንል ነው ›› ምንድነው ይሄ ?…እንቁልልጭ ነው ?…ትዳር እንደፌስቡክ ብሎክ አድርገህ አትገላገል ነገር !መሮኛል !

‹‹መነጋገር እና ነገሮችን በልክ ማድረግ ነው ...ቀላል ነው ….››

‹‹ትቀልዳለህ ?  ልጆች  ወለድን …ስንት ዓመት ተናገርኩ … አጉል ተናንቀናል …በተናገርኳት ቁጥር  ሁለት ቀን ሶስት ቀን ኩርፊያዋ አይጣል ነው …ቤቱ መቃብር ቤት ነው የሚመስለው ! ታውቃለህ ኩርፊያ አልወድም ነፍሴ ይጨንቃታል ...እቤት ስገባ ጧት ቁርስ የተበላበት ሰሃን ተከምሮ ነው የሚጠብቀኝ …ስለሚደብረኝ  ደክሞኝ ከስራ መጥቸ አጥባለሁ …ሳጥብ ፎቶ አንስታ ‹‹ውዱ ባለቤቴ እቃ በማጠብ ሲረዳን ›› ትላለች … ላይክና ኮሜንት ይጎርፋል ‹‹ዋው ›› ይባላል ….እኔም በውስጤ ርግማንና እንባ ይጎርፋል …

ማታ ጉልት ብላ ስልክ ስትጎረጉር እስከእኩለ ሌሊት አትናገር አትጋገር …ልጆቹን ራሱ ስለምታመናጭቃቸው ነገ ስንት ስራ እያለብኝ …እነሱን የቤት ስራ ሳሰራራ …ሳስተኛ አመሻለሁ … ቀና ብላ ስታየን ፎቶ ታነሳና ‹‹ማሚ ራት እስከምታዘጋጅ አባትየው ልጆች ሲያስጠና ›› ብላ ትለጥፋለች …እንኳን ራት ወፍ የለም … ‹‹ለምሳ የተሰራ ወጥ አለ ፍቅር.... አሙቅና ብሉ ›› ትልቅ ስራ እንደሚሰራ ሰውኮ ነው በቃ ቢዚ የምትሆነው !

ልጆች ተኝተው … በቃ ብቻችንን ሁነን እጠብቃታለሁ እንቅልፍ እያዳፋት  ቫዘሊኗን ተደፍልቃ መጥታ ትወድቃለች …ጎኗ አልጋ እንደነካ የለችም  እንቅልፍ ! ይታይህ አብሪያት ጊዜ ማሳለፍ እፈልጋለሁ … ጧት ስነሳ እንደተጋደመች ነው …ተነስቸ እየተነጫነጭኩ ያደረ ነገር ካለ ቀምሸ እወጣለሁ …! ልጆቸ ራሳቸው ተጎዱ ….ከስራ ስመጣ ስሞታ ነው … ቴሌቪዥን ከፍታ ትጥዳቸዋለች አይናቸው ቡዞ ነው የሚጠብቀኝ  ! ጭራሽ ፌስቡክ ላይ ስለልጅ አስተዳደግ ፌስቡክ ላይ ካልመከርኩ ስትል ታገኛታለህ !

ልጆቸ ቴሌቪዥን ላይ ከመጎለታቸው የተነሳ ይሄው ዜና እንደሙዚቃ ...አንባቢው ጋር አብረው ማነብነብ ሁሉ ጀምረዋል !  ወይ አታጫውታቸው … ወይ ይዛቸው አትወጣ … በዚህ ቀልቧ ይዛቸው ብትወጣም ስልኳን ስትጎረጉር መኪና ውስጥ ነው የምትማግድብኝ !  መረረኝ …››  ብሎ ትክዝ አለ ….አይኔ ሸሚዙ ላይ አረፈ አንዱ ቁልፍ ተበጥሷል …ባለፈው ሚስቱ ይሄንንም ሸሚዝ  ፖስት አድርጋው ነበር  ‹‹ወንዶችኮ ኬርለስ ፍጥረቶች ቁልፉ ተበጥሶ ለብሶት ስራ ይሄዳል እንደፈረደብኝ ልትከል ›› ብላ እስካሁን ቁልፉን አልተከለችውም !

‹‹… በእውነት ስልችት ነው ያለኝ … ፌስቡክ መጠቀም ይቅርና ማንበብና መፃፍ የማትችል ሴት ባገባሁ ብየ እመኛለሁ ! ጉራ ብቻ … ከማንኪያ እስከሶፋ አንጀቴን አስሬ አንዲት ነገር ልግዛ …ብራንዱን ፎቶ እያነሳች መለጠፍ እና መጎራት ነው ! ይሄ ነው ቤተሰብ …ይሄ ነው በቃ ሕይዎት …. የሁለታችንም  ጓደኛ  ነህ አንድ ነገር በላት …አለበለዚያ  የእኔና የእሷ እህል ውሃ አበቃ …ብሎኝ ቻው እንኳን ሳይለኝ ተነስቶ ሄደ !

በተቀመጥኩበት  የፌስቡክ አካውንቷን  ቸክ አደረኩ  ከሶስት ደይቃ በፊት  ከሰፊ አልጋ ምስል ጋር እንደዚህ የሚል ፅሁፍ ለጥፋለች

((ባልሽን እዛ ነገር ላይ ካስደሰትሽው  ትዳርሽ ገነት ይሆናል  ሂሂሂ ))

@AlexAbreham

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

26 Sep, 07:58


የሆነ ቀን ሶስት ቲሸርት ከድሬዳዋ አመጣችልኝ ። የገዛችልኝ ቲሸርት ቀለም እና ስታይል ያምራል።ልጅ እያለሁ ለበዓል ልብስ ሲገዛልኝ እንደሚሰማኝ አይነት ደስ አለኝ ፦

የሆነ ቀን በስልክ እየተወራጨው ሳወራ ቀስ አድርጋ ስልክ ያልያዘውን እጄን ይዛ አይበሉባዬን ዳበሰቺው እያረጋጋቺኝ ነበር

የሆነ ቀን ተስፋ የቆረጥኩ ሲመስላት አንገቴ ስር ሳመቺኝ አለሁልህ ያለቺኝ መሰለኝ ።

የሆነ ቀን ሁለት ሰዓት አርፍጄባት ስመጣ ፊቷ ፍም መስሎ ቆየኝ "አሁን መጣው አሁን መጣው" እያልክ እንዲ አታድርግ እንደዚህ አይነት መጠበቅ አልወድም አለቺኝ ። ከዛን ቀን ጀምሮ እንደዛ ማድረግ አቆምኩ

የሆነ ቀን ቀንቼ ጨቀጨኳት ፎከርኩ አብራራሁ በትህትና አስረዳቺኝ ቀጥላ ሁለተኛ እንዲ የሚያናድድህ ጉዳይ ውስጥ አልገባም አለቺኝ እውነቷን ነው አልደገመቺውም

የሆነ ቀን ትወጂኛለሽ ወይ አልኳት እስከ ሰማይ ድረስ ብዙ ነው የምወድህ አለች ። የሆነ ቀን ትወደኛለህ ወይ አለቺኝ ሊያውም እንደሞኝ ሊያውም ምንም ክፋት አይቶ እንደማያቅ
ሊያውም ምንም ምርጫ እንደሌለው ሰው አይነት ነው የምወድሽ አልኳት ።

ለካ ኑሮን ከሚያሳምሩት ግምባር ቀደሙ መዋደድ ነው ። እርስበርሳቹ ተዋደዱ እንዲል ቃሉ ።
ሃዬ
© Adhanom Mitiku

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

25 Sep, 04:39


የምወደው ልጅ ነበር ። እርጋታው ህልሙ መልኩ ሁኔታውን
እወደዋለሁ ስህተቱን ድክመቱን ሳይቀር ነበር የምታገሰው ።

ብጥር ...ብጥር... ከኔ ጋ ማቆየት አልቻልኩም ።

ጊዜ ሄደ ...

እኔም ሄድኩኝ

ሌላ መስመር ሌላ ኑሮ ሌላ ጠዓም አየሁኝ እሱ
ዘግይቶ ወደ ምፈልገው መንገድ መጣ

ዳር ዳር አለ እንዳልገባኝ ሆንኩኝ እብረን እንድንሆን ጠየቀኝ ..ዋጋሽ ገብቶኛል ወድጄሻለሁ አለኝ ።

አልታበይኩም አልጎረርኩም ሰነፍ ነው ቀድሞ ደርሶ ባረፈደ የሚያሾፈው ። ብስለት የሚለካው የሆነልን ሲመስለን በያዝነው አቋም እና ሁኔታ ነው ።

በትህትና አልችልም አልኩት ።

Timing is every thing ፀሎቴ ውስጥ ህልሜ ውስጥ ቅዠቴ ውስጥ ማሳካት የምፈለገው ውስጥ እምይዘው አቋም ውስጥ እሱ ነበር ። ጊዜ ሁኔታ አጋጣሚ ተደራረበ እና አንዱም ውስጥ ጠፋ !!

ምንም ስላላዋጣ ግዜ ልቤ ውስጥ የተወለደውን ፍቅር አደብዝዞት ነበር ። ልቤ ውስጥ የተከማቸውን ፍቅር ስላልወደደው ፍቅሬን ፊት ነስቼው በግዜ ብዛት ተነነ ።

ብቻ መወደድ ከብዶኝ ስለነበር ሳስታውሰው እረፍት አይሰማኝም ነበር ። እረፍት የሌለው ፍቅር ምኑን ፍቅር ነው ??

ናፍቆኝ ጓጉቼ ሳገኘው አይኑ ለኔ ስሜት አልባ እንደሆነ ስለሚነግረኝ ናፍቆቴ ወደ ድብርት ይቀየራል ።

የሚለኝን ያደረገውን የሆነውን ሁኔታውን ትርጉም አየሰጠው ስቀምር የማድር እንደነበርኩ እኔን ካልሆነ አይገባውም !!

ዛሬ ሁኔታሽ አንቺነትሽ ሁሉ ትርጉም ሰጠኝ አብረን እንሁን አለኝ ። ዘግይቶ ነበር Timing is every thing

እንደማይሆን እያወኩ ፍላጎት እንዳለኝ ምልክት ሰጥቼ አልበድለውም !!

" አልችልም" አልኩት

ቁርጣችንን አልነግር እያሉ እንደሚበድሉን መሆን አልፈለኩም ተፈላጊ የመሆኔን እርሃብ ለማስታገስ ወለም ዘለም እያልኩ አልበድለውም

በትህትና " አልችልም ሌላ የህወት መንገድ ላይ ነኝ " አልኩት ። እየመከርኩ አልተመፃደኩም ። መልካሙን ሁሉ እንዲገጥመው ግን በልቤ ተመኝቼለታለሁ ።

ትክክለኛ ነገር ትክክለኛ የሚያደርገው timing ነው !
timing is every thing እንዲሉ አበው!!
© Adhanom Mitiku

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

24 Sep, 14:08


ቤተዘመድ ጋር አብረን ስንሄድ ግን እንደ መልካም ሚስት- እናት እና አባቱ እንደሚፈልጓት አይነት- እሆንና ምግብ አቀርበለታለሁ፡፡ እናቱ ልጃቸው እንዲህች አይነት ድንቅ ሚስት አግብቶና በትዳሩ ተደላድሎ ስለሚኖር ኩራት ኩራት ይላቸዋል፡፡
የማያደንቀን ሰው የለም፡፡ ‹‹ድንቅ ጥንዶች›› ይሉናል አንዳንዶቹ፡፡ እውነታው ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡
አናወራም፡፡
አንጣላም- ለጠብ የሚሆን ጉልበት እንኳን አልነበረንም፡፡
ውድቅት ላይ ቤት ቢመጣ ግድ አይሰጠኝም፡፡
ውጪ ያስቀመጣት ሴት ብትኖር እንኳን ደንታ የለኝም፡፡
ያስቀመጣት ካለችውም የወንድ ቅርፊት እንጅ ደህና ወንድ እንዳላገኘች ስለማውቅ አይቆረቁረኝም፡፡ የወንድ ልጣጭ ነው ያገኘችው፡፡ የወንድ ጭራ፡፡

የባለቤቷን ጉድለቶች አንድ በአንድ የምትቆጥር፣ ኩንታል ስህተቶቹን ተሸክማ የምትኖር፣ የወንድነት ጥላ የራቀው እርቃን እና ደካማ ባሏን አብጠርጥራ የምታውቅ ሚስት ሆኛለሁ፡፡
እርግጥ ነው- እኔም ደካማ ጎን አለኝ- ምን ጥያቄ አለው? እዚህና እዚያ ምላሴን ያዳልጠኝ ይሆናል፡፡ ነገረኛ ብጤም ሳልሆን አልቀርም፡፡ እሱም ከአንዴም ሁለት ሶስቴ ጨቅጫቃ መሆኔን ነግሮኛል፡፡

እንዲህ ስለመሆኑ እና እንዲህ እንዲሆን ምክንያት ስለሆኑት ነገሮች የማወቅ አንዳችም ፍላጎት ግን የለኝም፡፡

አንዴ የሆነ አውሮፓ ያለ ኤርፖርት ውስጥ ሆኜ በጉዞ የተዳከሙ እና ጥውልግ- ትክት ያሉ ሰዎች- አይኖቻቸውን ባዶ አየር ላይ ተክለው-- ዝም ብሎ በራሱ የሚሄደው ተንቀሳቃሽ ደረጃ ላይ በደመነፍስ ሲሳፈሩና በድንዛዜ ሲሄዱ ሳይ ‹‹ትዳሬ ልክ እንደዚህ ነው››› ስል ትዝ ይለኛል፡፡

በቅርቡ የሆነ ደረሰኝ ኪሱ ውስጥ አግኝቼ ነበር፡፡ ከጓደኞቹ ጋር ሲዝናና አምሽቶ የከፈለበት ነው፡፡ ለአንድ ጠርሙስ ውስኪ እና ለሚበላ ነገር ሰባት ሺህ አምስት መቶ ብር ከፍሏል፡፡ በአንድ ምሽት ሰባት ሺህ አምስት መቶ ብር! ያውም በአዘቦት ቀን፡፡
ደረሰኙን ሳይ ልቤ በጩቤ የተወጋ መሰለኝ፡፡ የልጆቹን ትምህርት ቤት ክፍያ አልከፍልም የሚል ግን ለመጠጥ ይሄን ያህል ብር የሚያወጣ ወንድ ሆኗል፡፡
ስለ ልጆቹ ጉብዝና ለወላጆቹ፣ ለዘመድ አዝማድ የሚጎርር ግን ተማሩ አልተማሩ ግን የማይሰጠው ሰው ሆኗል፡፡ ያውም ከእኔ በስንት እጥፍ የሚበልጥ ደሞዝ እየበላ፡፡

እርግጥ ነው እንዳሻው እንዲሆን ፈቅጄለታለሁ፡፡ የውሸት እንዲኖር ተባብሬዋለሁ፡፡ ጥሩ አባት እና መልካም ባል ነኝ ብሎ የሚያምንበትን የቁጩ አለም ገንብቶ የውሸት እንዲኖር ይሁንታዬን ሰጥቼዋለሁ፡፡
እዋሽለታለሁ፡፡ ከዚህ ሁሉ ነገር የሚስጠላው ነገር ግን የእሱ ውሸታምነት እኔንም የውሸት የምኖር ውሸታም ማድረጉ ነው፡፡ ሁለመናዬ ውሸት የሆነ ሰው አድርጎኛል፡፡

ምናልባት ጠርጥራችሁ ከሆነ ከሌላ ሰው ጋር መውጣት አልጀመርኩም፡፡ ሰው ጠፍቶ አይይለም፡፡ መግቢያ መውጫ ያሳጡ ብዙ ወትዋቾች አሉኝ፡፡
ግን በህግ ባለትዳር ነኝ፣ ትዳር ያለኝ ላጤ ብሆንም፡፡ ከባለቤቴ ጋር ‹‹ትዳር›› የሚባል ለትርፍ የተቋቋመ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር የምንመራ ሁለት ሰዎች ብንሆንም፡፡

እንደሚስት በምንም ነገር እንዲያግዘኝ መጠየቅ ካቆምኩ ቆየሁ፡፡
እንደ ቤቱ ራስ፣ እንደ አባዋራ እሱን መከተል ከተውኩ ቆየሁ- መምራት አቁሟላ!

ግርማ ሞገሱ ጠፍቶ አይኔ ላይ ከኮሰሰ፣ ለእሱ ያለኝ ክብር ብን ብሎ ከጠፋ ሰነባበተ፡፡
በፊት በፊት ያማልለኝ የነበረ ያ ወንዳወንድነቱ….ለምሳሌ ጠዋት ጠዋት ከወገቡ በላይ ራቁቱን ሆኖ ጥርሱን ሲፍቅ ሳየው የሚሰማኝ ሞቅታ በፀፀት ተተክቷል፡፡

እስከ መቼ ነው እንደዚህ የምኖረው ግን?
እኔስ እስኪያንገሸግሸኝ፣ እስኪያቅተኝ ድረስ እዚህ ያጋደለ፣ ጣራው የሚያፈስ ጎጆ ውስጥ መኖር እችላለሁ፡፡
ከሁሉ የሚያንገበግበኝ ግን ልጆቼ የአባታቸውን ሁኔታ መረዳት መጀመራቸው ነው፡፡
አባታቸው ለቤተሰቡ ጥላ ከለላ የሚሆን ጠንካራ አባወራ አለመሆኑን ማየት መጀመራቸው ነው፡፡በተለይ ለወንድ ልጆቼ አብዝቼ እጨነቃለሁ፡፡ የአባወራ ምሳሌ አድርገው ለሚስሉት ምስኪን ልጆቼ፡፡
የወንድነት አርአያ አድርገው የሚቆጥሩት - እሱን በሆንኩ የሚሉት ሰው ይሄ በመሆኑ፣ ልጆቼ አውላላ ሜዳ ላይ ስለቀሩብኝ አዝናለሁ፡፡

ስለ ልጆቼ እጣ ፈንታ የምጨነቀው እኔ ብቻ፣ ለቤተሰቤ የምወጋው እኔ ብቻ መሆኔ ልቤን በሃዘን ያደማዋል፡፡ ውስጤን ይሰረስረዋል፡፡ ያበግነኛል፡፡
ከዚህ ግራ የገባው ሁኔታ እንዴት ማምለጥ እንዳለብኝ አላውቀም፡፡
ምክንያቱም….የቤቴን ወጪ መሸፈን እችል ይሆናል፣ ከልጆቼ ጋር ማውራት እና መጫወት እችል ይሆናል፣ የቤት ሥራቸውን አብሬያቸው መስራት፣ ሲጎብዙ ማበረታታት፣ እንደ እናት ስለ እነሱ መፀለይ አያቅተኝ ይሆናል፡፡ ግን እንዴት መልካም አባወራ መሆን እንዳለባቸው ላሳያቸው፣ አርአያ ሆኜ ልመራቸው አልችልም፡፡ ያንን ሊያደርግ የሚችለው አባወራው ብቻ ነው፡፡ የእኔ አባ ወራ ተብዬ ደግሞ ሃላፊነቱን አሽቀንጥሮ ጥሎ፣ ወንድነቱን እንደ አሮጌ ካፖርት አውልቆ ወንበር ላይ ማንጠልጠልን መርጧል፡፡
-----አበቃ------

by Hiwot Emshaw

@AlexAbreham

Alex Abreham በነገራችን - ላይ

24 Sep, 14:08


ሴት እና ትዳር- ‹‹እርቃን››- ክፍል ሁለት

-------------------
ትዳራችን ይነፍስበት የጀመረው እዚህ ግባ በማይባሉ ጥቃቅን ነገሮች መነሻነት ነበር፡፡

አለ አይደል…ጠዋት ከእንቅልፋችን ስንነቃ እንዴት አደርሽ ማለት ሲተው…(ባሎች፣ እባካችሁ..ሁሌም ሚስቶቻችሁን እንዴት አደርሽ ብላችሁ ጠይቁ….በክር ከተሰራች አሻንጉሊት ጋር አይደለም እኮ ተኝታችሁ ያደራችሁት! አንድ ቀን እንዴት አደርሽ ብላችሁ መጠየቅ ስትረሱ ነገም አታስታውሱም…ከዚያ ይለምድባችሁና ልክ አዳሪ ትምህርት ቤት እንደሚኖር ተማሪ ብድግ ብላችሁ ካልጋ መውጣት ትጀምራላችሁ፡፡ )

እና እንዳልኳችሁ ጠዋት መነሳትና ሰላም ሳይለኝ ወደ ሽንት ቤት መሄድ ጀመረ፡፡
ሁልጊዜ እንዴት አደርህ የምለው እኔ ሆንኩ፡፡ ከዚያ እኔ ብቻ እንዴት አደርህ ማለቱ ታከተኝ፡፡ እየቆየ ሲሄድ ጠዋት ጠዋት እኔን ማየት እንኳን እንዳቆመ ማስተዋል ጀመርኩ፡፡

ልብስ እየለባበስን ስናወራ እንኳን ጭራሽ አያየኝም፡፡ ለማየት የማስቀይም አይደለሁም፤ ሁሌም ራሴን በመስታወት ስለምመለከት ይሄንን አውቃለሁ፡፡ እና ታዲያ ምን ሆኖ ነው የማያየኝ? እኔ ደግሞ ሰው ካላየኝ ኖርኩ አልኖርኩ ግድ እንደሌለው ነው የሚሰማኝ፡፡ ካላየኸኝ የለሁም ማለት ነው…ድምጽ ብቻ ያላት መንፈስ ሆንኩ ማለት ነው…(.ወንዶች፣ እባካችሁ ሚስቶቻቸሁን እዩ፡፡ )

ጠዋት ጠዋት ሰላም ማደሬን ባይጠይቀኝም፣ ባያየኝም ግን ትዳራችን ጥሩ የሚባል ነበር፡፡ ቤቱን ማስተዳደር ላይ አልሰነፈም፡፡ ለልጆቹ መጫወቻ እና ልብስ ይገዛል፡፡ አንዳንዴም አብሯቸው ይጫወታል፡፡

ከዚያ ሕይወት በማይታሰብ ፍጥነት መክነፍ ጀመረች፡፡ ልጆቻችን ትምህርት ቤት ሲገቡ የትምህርት ቤት ክፍያ ራስ ምታት እና ለነገ ጥሪት የመቋጠር ጭንቀት ይወጥረን ጀመር፡፡ ባለቤቴ ትልልቆቹን ወጪዎች ሲችል እኔ ደግሞ ጥቃቅን የቤት ቀዳዳዎችን እየደፈንሁ ኑሮ ቀጠለ፡፡

ከዚያ ሳይታወቀን ሁለታችንም በየራሳችን ዛቢያ የምንሽከረከር፣ በማይገናኙ መንገዶቻችን አለእረፍት የምንሮጥ እና የምንባዝን ሰዎች ሆንን፡፡

እሱ ቤት ከሚኖርበት ጊዜ ስራ ላይ የሚያሳልፈው ጊዜ እየበዛ፣ ቤት ሲመጣም በድካም ብትንትን ብሎ እና ልጆቹን እንኳን ማናገር እንዳይችል ሆኖ፣ ለመኝታ ብቻ ሆነ፡፡
እሁድ እሁድ ቤት ይሆናል ግን ከቅዳሜ የዞረ የመጠጥ ድምሩን ስለሚያወራራድ እንዳለ አይቆጠርም፡፡ ሁሌም በስራ ደክሞ ስለሚገባ ልጆቼን ብስክሌት መንዳት እንኳን ያስተማርኳቸው እኔ ነኝ፡፡ ለነገሩ ጭራሽም ለማድረግ አልሞከረ፡፡

እያደር እሱ ሊያከናውናቸው የሚገቡ ስራዎችን ፣ ሊወጣቸው የሚገቡ ሃላፊነቶችን እኔ ማድረግና መወጣት ጀመርኩ፡፡ የቧንቧ ሰራተኛ ፈልጎ ማግኘት…የልጆቹን ትምህርት ቤት መምረጥ፡፡

ልጆቻችን እያደጉ ሲሄዱ አብሯቸው ማሳለፍ ያለበትን ጊዜ ሳያሳልፍ እድሜያቸው እንዳያልፍና እንዳይቆጨው ብዬ ጊዜ እንዲሰጣቸው የምችለውን ሁሉ ጣርኩ፡፡ እስቲ መናፈሻ ወይ መጫወቻ ቦታ ውሰዳቸው…ብስክሌት አብረሃቸው ጋልብ….አዋራቸው፣ ወንዶቹን ደግሞ እንዴት አይነት ወንድ…እንዴት አይነት አባት መሆን እንዳለባቸው አሳያቸው ስል ወተወትኩት፡፡

እሱ ግን ሁሌም ጊዜውን የሚሻማ ነገር አያጣም፡፡ ሁሌም ከዚህ የሚበልጥበት ነገር አይጠፋም፡፡

ከዚያ የቤተሰቡ ራስ እኔ ሆንኩ፣ ውሳኔ አሳላፊዋ ሆኜ አረፍኩ፡፡ ከጊዜ በኋላ የትምህርት ቤት ክፍያ በጊዜ መክፈል አቆመ፡፡ ጭራሽ ትምህርት ቤቱ ደውሎ ክፍያ ይጠይቀኝ ጀመር፡፡ ያን ጊዜ የዚያኛውን ሴሚስተር ራሴ እከፍልና የሚቀጥለውን እንዲከፍል ባየው ባየው እሱ እቴ!

---
አባቴ ለእናቴ ምን አይነት ባል እንደነበር አላውቀም፡- ምናልባት እንደ ባል ያጎደለባት ነገር ይኖር ይሆን አላውቅም፡፡፡ ለእኔ ግን ምን አይነት አባት እንደነበር ጠንቅቄ አውቃለሁ፡፡ ሃላፊነቱን የሚያውቅና በአግባቡ የሚወጣ አባት ነበር፡፡ በዚያ ላይ ኩሩ ነበር- የእኔ አባት፡፡

አንዴ አስታውሳለሁ- አስር ወይ አስራ አንድ አመቴ እያለ- ቅዳሜ ቀን ነው…. ጠዋት ቁርስ እየበላን በልጅነት አእምሮዬ ያኔ- ምክንያቱ አልገባኝም ግን የሆኑ የባንክ ሰራተኞች ወደ ቤታችን መጡ፡፡ አባዬ እኔና እማዬን ካለንበት ትቶን ሊያናግራቸው ይሄዳል፡፡

በሳሎኑ መጋረጃ ውስጥ ውጭ ቆሞ ሲያዋራቸው አያለሁ፡፡ ከአጥራችን ውጪ የቆመው የጭነት መኪና የቤት እቃችንን በሙሉ ለቃቅሞ ለመሄድ የጓጓ ይመስላል፡፡ እማዬ ከተቀመጠችበት ሳትነሳ፣ አንዴ እንኳን ሳትንቀሳቀስ፣ ተነስታ ወደ አባዬ ሳትሄድ እዛው ቁጭ ብላለች፡፡
የእሷ ተረጋግቶ መቀመጥ እኔንም ሲያረጋጋኝ አስታውሳለሁ፡፡ እሷ እንደዛ ረጋ ብላ ቁጭ ካለች ውጪ እየሆነ ያለው (መጥፎ ነገር ይመስላል) ምንም ነገር ቢሆን አባዬ መላ እንደማያጣለት እና ወደ ቁርሱ እንደሚመለስ ነገረኝ፡፡
እናም ልክ እንዳሰብኩት ሆነ፡፡ አባዬ ያንን ቀን ልክ ሌሎች ቀኖችን እንደሚያሳልፈን በብልሃት አሳለፈን፡፡
ከዚያ በኋላ ስለ ወንድነት ያለኝ ግምት አባቴን ተደግፎ የተሳለ ሆነ፡፡ ወንድ ልጅ፣አባወራ ሲሆን ቤተሰቡ የሚገጥመውን ችግርን ወጥቶ እንደ ወንድ መጋፈጥ እንዳለበት፣ ከዚያም በኩራትና በልበ ሙሉነት መቆም እንዳለበት ከአባዬ ተማርኩ፡፡
.

እናትና ሚስት ሆኜ ቤቴን ማስተዳደር ምኞቴ ነበር፡፡ ባሏን የምትከተል፣ ታታሪና ጨዋ ሚስት መሆን ነበር ፍላጎቴ፡፡ ሚስት፡፡ ቀስ በቀስ ግን የአባወራውን ስራ መረከብ ጀመርኩ፡፡ ባል ሆንኩ፡፡ እሱ መወሰን ያለበትን ነገር መወሰን፡፡ የልጆቹን ትምህርት ቤት ክፍያ መክፈል፡፡

ያን ጊዜ በሌላ አይን እመለከተው ጀመር፡፡ በፊት የምመካበት እና የማደንቀው ወንድ መሆኑን አቆመ፡፡ አቅጣጫው ጠፍቶበት የሚማስን ሰው ሆኖ አገኘሁት፣ አቅጣጫው የጠፋበት ሰውን ደግሞ መከትል አልችልም፡፡

ከጊዜ በኋላ አንዳችን ለአንዳችን ጭራሹን ባእድ ሰዎች ሆነን አረፍነው፡፡
የባል እና ሚስት ወጋችን እንደ በርሃ ዝናብ በጭንቅ የሚመጣ እና በስንት ጊዜ የሚከሰት ነገር ሆነ፡፡
ከስንት አንዴ ሆኖልን ፍቅር ስንሰራ እንኳን ሃሳቤ ወደማልመው የእንጆሬ እርሻዬ እየሄደ ያስቸግረኛል፡፡
ስናወራ ከሌላ አለም እንደመጣ ሁሉ፣ ሁሉ ነገሩ እንግዳ ይሆንብኝ ጀመር፡፡ የማላውቀውን ቋንቋ እንደሚናገር እንግዳ ሰው፡፡

ይሄ ሁሉ የሆነው አሪፍ ሚስት መሆኔን ስላቆምኩ ይሆናል፡፡ እንደ በፊቱ አምሽቶ ሲመጣ እና እራት እየበላ የዚያን እለት ቢሮ ስለተፈጠሩ አስደናቂ ነገሮች ሲያወራኝ እያዳመጥኩ፣ ቁጭ ብዬ አላየውም፡፡

ይልቅ ለጥቂት ቀናት ፊልድ ሲሄድ ልቤ ጮቤ ይረግጣል፡፡፡
ያን ጊዜ ቤቱ ይሰፋኛል፣ ክፍሎቹ ወደ ጎን ልጥጥ ይላሉ… ያኔ.መተንፈስ እችላለሁ፡፡
ከፊልድ የሚመለስ ቀን ቀድሜው ገብቼ ደህና የሚበላ ነገር አዘጋጅቼ (ድሮ ቢሆን የምበላው ነገር እኔ ነበርኩ!) ለመጠበቅ አልቸኩልም፡፡ በፊት በፊት በየትኛው አውሮፕላን እንደሚመጣ፣ ትራንዚቱ የት እንደሆነ፣ ስንት ሰአት የት እንደሚደርስ አውቅ ነበር፡፡ አንዳንዴማ ኤርፖርት ሁሉ ሄጄ እቀበለው ነበር- ያውም ምን እንደሚናፍቀው ስለማውቅ ትኩስ ቡና በፔርሙስ ይዤ!
አሁንስ? አሁንማ ደስ የሚለኝ ሲሄድልኝ ነው፡፡ ምክንያቱም ቤት ውስጥ ሆኖ ልክ እንደ ወንዶቹ፣ ልክ እንደ ቤተሰብ አስተዳዳሪ፣ እንደ ደህና አባወራ ወዲህ ወዲያ ሲል ላየው ስለማልፈልግ ነው፡፡ በዚያ ላይ…የሚያገኘውን ገንዘብ የት እንደሚያደርገው ሳላውቅ ወይ ሳይነግረኝ…