አንድ መነኩሴ ለሌላው መነኩሴ እንዲህ ብሎ ጠየቀው "የምጸልየው ጸሎት የቃሉ ኃይል አይታወቀኝምና ምን እጠቀማለሁ?" አለው። ያ መነኩሴም ሲመልስለት "የቃሉ ኃይል ለአንተ የማይታወቅህ ቢሆንም ሰይጣናት የቃሉን ኃይል ያውቃሉና ይደነግጣሉ ፤ ስለዚህ ነገር ትንሽ ትንሽ እያልክ በመጸለይ ወደ እግዚአብሔር አጋዥነት እስከምትደርስ ድረስ እና ከልብህ መደንደን እንድትለመልም ፣ ከዘወትር ድካምም እንድትድን ጸሎትን አታቋርጥ" አለው።
አባ አጋቶንን "የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማግኘት የትኛው ሥራ ይሻላል? በጌታችን ፊትስ በዝቶ ጥቅም የሚሰጠው ማንኛው ሥራ ነው?" ብለው ጠየቁት። እርሱም "የዋህ ልብ እና በመፍራት በመንቀጥቀጥ የሚቀርብ ንጹሕ ጸሎት ነው" አላቸው።
ኹል ጊዜ ልቡ ንጹሕ የሆነለት ሰው እግዚአብሔርን ያየዋል ፤ ኹል ጊዜ ወደ እግዚአብሔር የሚመለስ ሰው አጋንንትን ያባርራቸዋል። ፍላጎቱን የሚንቅ ሰው በልቡ ውስጥ ጌታን ያያል። ንጽሕናን የሚወድ ሰው በመንግሥተ ሰማይ የኹሉ አባት ጌታን ያያል።
መጽሐፈ ገነት ዘውእቱ ዜና አበው ፤ 2ኛ ዕትም 2010 ዓ.ም