Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

@nolawiiher


ዘየአምን ለአማኑኤል በስሙ ፣ ኅቱም በማኅተመ ደሙ ፣ ውኩል በጸሎተ ማርያም እሙ ፣ ወለቅዱሳን ተላዌ ሃይማኖቶሙ ። ይህ ቻናል የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ትምህርቶች የሚተላለፉበት ነወ ።
#ለሃሳብ ለአስተያየት 👉 @Nolawiher1
Facebook :- https://www.facebook.com/estifanos.dejene.94

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

22 Oct, 16:31


ከአበው ሕይወት

አንድ መነኩሴ ለሌላው መነኩሴ እንዲህ ብሎ ጠየቀው "የምጸልየው ጸሎት የቃሉ ኃይል አይታወቀኝምና ምን እጠቀማለሁ?" አለው። ያ መነኩሴም ሲመልስለት "የቃሉ ኃይል ለአንተ የማይታወቅህ ቢሆንም ሰይጣናት የቃሉን ኃይል ያውቃሉና ይደነግጣሉ ፤ ስለዚህ ነገር ትንሽ ትንሽ እያልክ በመጸለይ ወደ እግዚአብሔር አጋዥነት እስከምትደርስ ድረስ እና ከልብህ መደንደን እንድትለመልም ፣ ከዘወትር ድካምም እንድትድን ጸሎትን አታቋርጥ" አለው።

አባ አጋቶንን "የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማግኘት የትኛው ሥራ ይሻላል? በጌታችን ፊትስ በዝቶ ጥቅም የሚሰጠው ማንኛው ሥራ ነው?" ብለው ጠየቁት። እርሱም "የዋህ ልብ እና በመፍራት በመንቀጥቀጥ የሚቀርብ ንጹሕ ጸሎት ነው" አላቸው።

ኹል ጊዜ ልቡ ንጹሕ የሆነለት ሰው እግዚአብሔርን ያየዋል ፤ ኹል ጊዜ ወደ እግዚአብሔር የሚመለስ ሰው አጋንንትን ያባርራቸዋል። ፍላጎቱን የሚንቅ ሰው በልቡ ውስጥ ጌታን ያያል። ንጽሕናን የሚወድ ሰው በመንግሥተ ሰማይ የኹሉ አባት ጌታን ያያል።

መጽሐፈ ገነት ዘውእቱ ዜና አበው ፤ 2ኛ ዕትም 2010 ዓ.ም

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

19 Oct, 17:00


''ንጽሕናዋን ቅድስናዋን በወደደ ጊዜ በጽርሐ አርያም እናት ትሆነው ዘንድ ወደ ሰማይ አላወጣትም፣ እርሱ ራሱ ወልድ ወርዶ በጸራቢው በዮሴፍ ቤት አደረ እንጂ፣ በዚያ ትወልደው ዘንድ በኪሩቤል ሠረገላ አላስቀመጣትም ስሟ ናዝሬት በምትባል ሀገር በገሊላ ሳለች በማኅፀኗ አደረ እንጂ፣ ዳግመኛም በቤተልሔም በበረት ተኛ፣ ላምና አህያ በትንፋሻቸው አሟሟቁት በክንድ ታቀፈ፣ በሰሎሜም እጅ ተዳሰሰ፣ ከድንግል እናቱ ጡቶች ወተትን አመነጨ፣ የእናቱን ጡት ለመጥባት አፉን ከፈተ" (ገድለ አቡነ ገብረመንፈሥ ቅዱስ)

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

13 Oct, 06:24


ከውድቀት ያነሳኸኝ የሕይወት በሬ ፣ ኮሞት የሰወርከኝ መድኅኔ ክርስቶስ ሆይ አመሰግንሃለሁ ።  በእኔ ተስፋ የማትቆርጥ አንተ ብቻ ነህና አመሰግንሃለሁ  ። ሁሉ ሲሰለቸኝ አንተ ብቻ ቻልከኝ አከብርሃለሁ  ። ጌታ ሆይ እንደ አምስቱ ቤተ ሳይዳ በሮች ወዳጅ ፣ ተስፋ ፣ አስታዋሽ ፣ የሚደግፈኝ ፣ አፍቃሪ አልነበረኝም ። አንተ ግን ወደ እኔ በመምጣት ወዳጄ ፤ ልትድን ትወዳለህን በማለትህ ተስፋዬ ፤ በማዳንህ አስታዋሼ ፤ አልጋህን ተሸክመህ ሂድ በማለትህ አይዞህ ባዬ ፤ ደግመህ ኃጢአት አትስራ በማለትህ አፍቃሪዬ ሆንክ ልቤ ያመሰግንሃል  ። ልዑል ሆይ ዛሬም ጉብዝናዬ ለዓለም ድካሜ ወደ አንተ ሆኗል ። ስለማትታዘበኝ ወደ አንተ መጣው ። የ አለማወቄን መሥፈርት ማወቅ አድርጌ ፣ እውነት ባልወለደው ስሜት ተነድቼ ፣ ዓለማቢስነቴን እንደ መሰልጠን ቆጥሬ የጎደልኩበት ሕይወት ብዙ ፤ ያጠውትም በረከት ስፍር ቁጥር ያለውም ። ጌታ ሆይ እኔ የአሁን ሰው ነኝ ትኩሱ ፍቅርህ ይቀስቅሰኝ ። የዕድሜዬን ብዛት ላንተ እሰጥህ ዘንድ ክንድህ ይዘርጋልኝ ። ዘመኔን አንተ ባየህልኝ ዓይን እንድትመራው እማጸንሃለሁ ። ታሪክን የሚለውጥ መቻልህ ከጸባዖትህ ይፍሰስልኝ ። በማላፍርበት ደግነትህ ለዘለዓለሙ አሜን !

ዲያቆን እስጢፋኖስ ደጀኔ
ጥቅምት 3 ቀን 2017 ዓ.ም

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

29 Sep, 07:35


በአንተ ማረፍ ማን ይሰጠኛል? ልቦናዬ ይጥለቀለቅ ዘንድ ፥ ክፋቴን እረሳ ዘንድ ፥ አንተን ብቸኛው ሀብቴን አቅፍ ዘንድ! ወደ እኔ መግባትህን ማን ይሰጠኛል? አንተ ለእኔ ምንድነህ? እንድናገር በርኅራኄህ አንደበቴን ዳስሰው ፥ እንዳፈቅርህ ግድ የምትለኝ ፥ ምላሽ ባልሰጥ ቁጣህ የሚነደውና ከለላ የሚያሳጣኝ ፥ እኔ ለአንተ ምንድነኝ? አንተን አለማፍቀር ራሱ ጉስቁልና አይደለምን? ኦ! አቤቱ ጌታዬ አምላኬ ፥ በርኅሩኅነትህ መልስልኝ ፥ አንተ ለእኔ ማን ነህ? እሰማህ ዘንድ ተናገረኝ ፥ እነሆ በፊትህ የልቦናዬ ጆሮዎች ተከፍተዋልና፥ አቤቱ ጌታዬ ክፈትና ለነፍሴ "እኔ ነኝ መድኃኒትሽ" በላት ይህን ድምፅ በሩጫ ተከትዬ በመጨረሻም አንተን ልይዝህ እፈልጋለሁ፤ ሰምቼህ ወደ አንተ ልሩጥ ፥ በአንተም ላይ ራሴን ልጣል ፥ እባክህ ፊትህን ከእኔ አትሰውር፤ ላለመሞት ልሙት ብቻ ፊትህን ልይ።"

ሊቁ አውግስጢኖስ

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

27 Sep, 05:28


መስቀል በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ/347-404/ እንደ ተሰበከው

እንኳን ለ2017 ዓ.ም የመስቀል በዓል በሰላምና በጤና አደረሳችሁ !

የጌታ መስቀል ለጆሮ ደስ የማይልና የሚያሳዝን ነው ። ነገር ግን ደስታንና ሐሤትን ይዟል ። መስቀል ለአይሁዳውያን ፈተና ፣ ለአሕዛብ እብደት ነው ። ለእኛ ለአማኞች ግን ድኅነታችንን ያስታውሰናል ። አንድ ሰው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለ መስቀል ሲያነብ ሌላኛው የመስቀሉን መከራ ይታወሰዋል ። አማኞች መስቀሉ ላይ ሳይሆን ሰቃዮቹ ላይ ይበሳጫሉ፣ የሚያሳዝን ኀዘንና ልቅሶን ያወጣሉ ። መስቀሉ የቤተ ክርስቲያን ድኅነት ፣ መስቀሉ በእርሱ ተስፋ ለሚያደርጉ ሽልማት ነው ። መስቀል ከተያዝንበት ከሰይጣን ቊራኝነት ነጻ አውጥቶናል ። የተቀበልነው የመጀመሪያው በረከትም መስቀል ነው ። መስቀል የእግዚአብሔር ጠላቶች ከእግዚአብሔር ጋር የታረቁበት ፣ ኃጥአን ለክርስቶስ ቃል የገቡበት ነው ። በመስቀሉ ከጠላትነት ነጻ ወጣን ፣ በመስቀሉም የእግዚአብሔር ወዳጆች ሆንን ። መስቀሉ ከዲያብሎስ ሥልጣን ነጻ አወጣን ፣ ከሞትና ከጥፋትም አዳነን ። መስቀሉ ከሚጠፋው ነገር አላቅቆ ለሕያውነት የተገባ ሕይወትን ሰጥቶ የሰውን ባሕርይ ወደ መልአካዊነት ቀየረ ።

የመስቀሉ ኃይል ምንኛ ታላቅ ነው ! በእርሱስ ለሰው ልጆች የሆነው ለውጥ ምን ያህል ታላቅ ነው ! ከጥልቅ ጨለማ ማለቂያ ወደሌለው ብርሃን ፣ ከሞት ወደ ዘላለማዊ ሕይወት መለሰን ፣ ከመጥፋት ወደ ሕያውነት መራን ። በመስቀሉ ያልተደረገልን ምን መልካም ነገር አለ ? በመስቀሉ በኩል ጽድቅን ቅድስናን ተረዳን የመለኮትንም ባሕርይ ተማርን ። በመስቀሉ በኩል ስለ እግዚአብሔር እውነቱን ተረዳን ። በመስቀሉ በኩል ከእርሱ ርቀን የነበርነው ከክርስቶስ ጋር አንድ ሆንን ፣ ለመንፈስ ቅዱስ ጸጋም የተገባን ሆንን ። በመስቀሉ በኩል የፍቅርን ኃይል ተማርን ፣ ለሌሎችም ነፍሳችንን አሳልፈን ለመስጠት ቆረጥን ። በመስቀሉ በኩል ተነቃቅተናል ። የምናደርገው ሁሉም ጊዜአዊ አይደለም ፣ የሚመጣውን በረከት እንሻለን ። የማይታየውንም እንደሚታይ አድርግን እንቀበላለን ። መስቀሉ ይሰበካል ፣ በእግዚአብሔር ላይ ያለ እምነት ይገለጣል ። የእርሱም እውነት በዓለም ሙሉ ይስፋፋል ። መስቀሉ ይሰበካል ፣ በትንሣኤ ላይ ያለው እምነት ፣ የሰማዩ መንግሥትና ሕይወትም ያለ አንዳች ጥርጣሬ ይነገራል ። ከመስቀል በላይ እጅግ የተወደደ ፣ ነፍስን አብልጦ የሚያድን ምን አለ ? መስቀሉ ርኩሳን መናፍስት ላይ የሆነ ድል ፣ ጠላትን የምንቃወምበት መሣሪያ ጌታም የእባቡን (ራስ የቀጠቀጠበት) ሰይፍ ነው ። መስቀል የአብ ፈቃድ ፣ የአንድያ ልጁ ክብር ፣ የመንፈስ ቅዱስ ደስታ ፣ የመላእክት ጌጥ ፣ የቤተ ክርስቲያን መጠበቂያ ፣ የቅዱስ ጳውሎስ ምስጋና ፣ የቅዱሳን ከለላ ፣ የዓለምም ብርሃን ነው ።

ዛሬ መስቀሉ ምንም ያህል የሚፈለግና በተገቢ ሁኔታ የሚወደድ ቢሆንም ፣ በጥንት ዘመን እጅግ አስፈሪና አሳፋሪ ምልክት ነበር ። አሁን ግን መስቀል ለንጉሥ ዘውድ የተመረጥ ማጌጫ ዓለም ላይ እጅግ ውዱ ምልክት ነው ። የመስቀሉ ምልክት አሁን ጌታና ባርያ ፣ ሚስትና ባል ፣ ኮረዳና ባለ ትዳር ፣ ባርያና ነጻ በሆናችሁት በእናንተ ዘንድ ይገኛል ። (ክርስቲያኖች) በሁሉም ቦታ ይህን የመስቀል ምልክት በተከበረው የሰውነት ክፍልና በግንባራቸው ልክ እንደ ተሳለ ዓምድ ተሸክመው ይዞራሉ ። በተቀደሰው ማዕድ ላይ ፣ በካህኑ ልብስ ላይና በምሥጢራዊውም እራት ከጌታ ሥጋ ጋር አብሮ ይደምቃል ። በሁሉም ቦታ ከፍ ብሎ ወደ ላይ ተሰቅሎ ታዩታላችሁ ፡- በቤት ፣ በገበያ ቦታ ፣ በበረሃ ፣ በመንገድ ፣ በተራራና በኮረብታ ፣ በባሕር ፣ በመርከብ ፣ በደሴት ፣ በሣጥን ፣ በልብስ ፣ በጦር መሣሪያ ፣ በአዳራሽ ፣ በብርና በወርቅ ዕቃ ፣ በሥዕላት ፣ በታመሙ እንስሳት አካል ላይ ፣ ርኩስ መንፈስ ባደረባቸው ሰዎች አካል ላይ ፣ በጦርነት ፣ በዓለም ፣ በከሰዓት ፣ በምሽት ፣ በበዓላት ፣ በመናንያን በአት ከፍ ብሎ ተሰቅሎ ታዩታላችሁ ። ማንም ሰው አያፍርም ፣ መስቀልም የሚያሳፍር ሞት ምልክት ነው በሚለው አሳብም አይናደድም ። በተቃራኒው ሁላችንም አክሊል ፣ ወርቅና ውድ ከሆነ ድንጋይ በላይ ለራሳችን እንደ ማጌጫ አድርገን እናከብረዋለን ። አንሽሽ ፣ አንፍራ ፤ ነገር ግን አቻ እንደሌለው ሀብት እንሳመው ፣ እናክብረውም ።

መልካም በዓል !

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

22 Sep, 07:07


መዝሙር 51

¹ አቤቱ፥ እንደ ቸርነትህ መጠን ማረኝ፤ እንደ ምሕረትህም ብዛት መተላለፌን ደምስስ ።
² ከበደሌ ፈጽሞ እጠበኝ፥ ከኃጢአቴም አንጻኝ ፤
³ እኔ መተላለፌን አውቃለሁና፥ ኃጢአቴም ሁልጊዜ በፊቴ ነውና ።
⁴ አንተን ብቻ በደልሁ፥ በፊትህም ክፋትን አደረግሁ፥ በነገርህም ትጸድቅ ዘንድ በፍርድህም ንጹሕ ትሆን ዘንድ ።
⁵ እነሆ፥ በዓመፃ ተፀነስሁ፥ እናቴም በኃጢአት ወለደችኝ ።
⁶ እነሆ፥ እውነትን ወደድህ፤ የማይታይ ስውር ጥበብን አስታወቅኸኝ ።
⁷ በሂሶጵ እርጨኝ፥ እነጻማለሁ፤ እጠበኝ፥ ከበረዶም ይልቅ ነጭ እሆናለሁ ።
⁸ ሐሤትንና ደስታን አሰማኝ፥ የሰበርሃቸውም አጥንቶቼ ደስ ይላቸዋል ።
⁹ ከኃጢአቴ ፊትህን መልስ፥ በደሌንም ሁሉ ደምስስልኝ ።
¹⁰ አቤቱ፥ ንጹሕ ልብን ፍጠርልኝ፥ የቀናውንም መንፈስ በውስጤ አድስ ።
¹¹ ከፊትህ አትጣለኝ ፥ ቅዱስ መንፈስህንም ከእኔ ላይ አትውሰድብኝ ።
¹² የማዳንህን ደስታ ስጠኝ ፥ በእሽታ መንፈስም ደግፈኝ ።

አሜን !

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

19 Sep, 17:57


ስለ አዲሱ የቻናላችን ሎጎ አጭር ማብራሪያ!

ጌታችን መልካም እረኛ (ኖላዊ ኄር ነው) ጌታችን ራሱን እኔ ነኝ ብሎ ከገለጠባቸው እኔነት አንዱ ኖላዊ ኄር እኔ ነኝ የሚል ነው ዮሐ 10:11 እርሱ የማይተኛ ትጉህ እረኛ ነው። ሎጎው በሁለት የክብ መስመሮች ጎልቶ መታየቱ የቅድስት ቤተክርስትያንን ህብረት ፣ አንድነት ፣ ኩላዊነት ለመግጽ ነው ።በክቦቹ መሃከል ላይ የወይን ፍሬ፣የቅዱስ መስቀል፣የቅዱስ ጽዋ ምስል መቀመጡ ቤተክርስትያን የምትሰጠንን ሰማህያዊ ምግብ ክቡር ደሙና ቅዱስ ስጋውን አግልቶ ለማሳየት ሲሆን ወይኑ ከመስቀል እና ከጽዋ ጋር  መቀመጡ የጌታችን ደመና ሥጋ መልኮቱን ያገኘነው በመስቀል ላይ በመዋሉ ይህን አርነት ለማውሳት ተጠቅመነዋል፤ በሎጎው መሃል ላይ የእረኛ ዱላ፣ቅዱስ መስቀል፣ የበግ ምሰል እንዲሁም የመጽሐፍ ምስል ይታያል። የእረኛው ዱላ ከመስቀልና ከበግ ምስል ጋር  ተጣምሮ መቀመጡ እረኛችን /ኖላዊ/ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እኛ በጎቹን በፍቅሩ ዱላ እየከለለ፣ በመስቀሉ ኅይል እየጠበቀ ለዛሬ መድረሳችንን ያሳያል ።ከበጉ ስር የሚታየው ምስል የቤተክርስትያን ውበት የሆነው መጽሐፍ ቅዱስ ሲሆን መጽሐፉ ላይ የተጠቀሱት ወ እና ቅ ፊደል ወልድ ቅዱስ የሚል ትርጉም ሲኖረው ይህም ወልድ የቤተክርስትያን  መሰረት፣ጌጧ፣ስብከቷ መሆኑን ለመግለጽ ነው ።የቻናላችን ስም በክብ ምስል ተጽፎ መቀመጡ ቤተክርስትያን ጉልላት አርነት በማድረግ ነው። ለሰራዎቻችሁ ሎጎ ማሰራት የምትፈልጉ በ0949478257 ልታናግሩን ትችላላችሁ ! 

ስብሐት ለአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ለዓለም ወለዓለም አሜን !

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

18 Sep, 04:08


ሳትደክም ሁሉን ትሽከማለህ፣ ሳታጎድል ለሁሉ ትመግባለህ፣ ዝም ሳትል ለሁሉ ታስባለህ ፣

ሳትጎድል ለሁሉ ትሰጣለህ ፣ ሳትነጥፍ ለሁሉ ታረካለህ፣ ሳትዘነጋ ሁሉን ታስባለህ፣

ሳትተኛ ሁሉን ትጠብቃለለህ፣ ቸል ሳትል ሁሉን ትሰማለህ ፣ ሳትቀበል ለሁሉ ትተዋለህ።

ባዕድ የማይሰጠው ክቡር፣የማያዙት ፈጣሪ፣ የማይሾሙት ንጉሥ፣ የማይነቅፉት ጌታ፣ የማያበድሩት አምላክ፣ የማይሰጡት ባለ ጸጋ ሆይ እናመሰግንሃለን !

ቅዳሴ ዮሐንስን ወልደ ነጐድጓድ

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

18 Sep, 03:55


Channel photo updated

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

11 Sep, 12:47


እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ማቴዎስ 2017 ዓ.ም በሰላምና በጤና አሸጋገራችሁ !

ጠርቼህ የማላፍር ፣ ሰመተህ የማትሸሸኝ ፣ ደግፈህ የምታቆመኝ ፣ ከልለህ የምታሻግረኝ ፣ አቅፈህ አለው የምትልኝ ፣ የዘመኔ ውበቱ ፣ የኑሮዬ በረከቱ ፣ የዕድሜዬ ሀሴቱ ፣ የልቤ ወዳጁ መድኃኒት ክርስቶስ ሆይ አመሰግንሃለሁ ። በትላንትናው የማትለካኝ በዛሬው የምትቀበለኝ የልቤ መድኃኒቷ ሆይ አመሰግንሃለሁ ። የደስታዬ ምንጯ ነህ ፣ የመኖሬ ምክኒያቷ ነህ ክብር ይድረስህ ። እኔ ሳልለወጥ አዲስ ነገር የምሻ አሰልቺ ልጅህ ነኝ እኔን ለቻሉኝ ክንዶችህ ምስጋና ይገባል ። አረ አንተስ ተመስገን ። ጌታዬ መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ሁሌ አሮጌው ልቤ አዲስ ነገር ይሻላል ።  ምኞቴ ትርጉሙ ሀሳቤ ማረፊያው አዲሱ ፍቅርህ ነው ። ልቤ የተገዛላቸው ብዙ ምኞቶች አሉ ። ለአንዱ ለአንት መገዛት አቅቶኛልና እባክህ አዲሱ ፍቅርህ ልቤን ያስጊጥልኝ ። ብዙ ሆኜ ለአንተ አልሆንኩምና አዲሱ ፍቅርህ አንዲሰራኝ እለምንሃለሁ ። በዚህ አዲስ ዘመን አንተ ለእኔ የሆነክውን የምረዳበትን ልብ አድለኝ ። ለአንተ አለመታዘዝ ጎድቶኛል ፣ አንተን እምቢ ማለት በከንቱ ሰፍራ አውሎኛል ። አዲሱ ዘመን የንስሐ ይሁንልኝ ፣ አዲሱ ፍቅርህ አዲስ ሰው ያድርገኝ ፣ ከትናንት ጥፋት የተማረ ፣ በዛሬ ፍቅርህ የተማረከ ፣ በተስፋው ቃልህ ያጌጠ ሕይወትን ከጸባዖት አፍስስልኝ ። ትናንትን ያሳለፍከኝ ለዛሬ ተማኝ ነህ ፣ የነጌም ስንቄ ነህ በዚህኛውም ዘመን ዋሴ አንተነህ ነህና አመሰግንሃለሁ ! ለአምላክነትህ የምሰግድበትን ፣ ለአባትነትህ የምታዘዝትን ልብ አድለኝ ። በማላፍርበት ደግነትህ ለዘለዓለሙ አሜን !

ዲያቆን እስጢፋኖስ ደጀኔ
መስከረም 1ቀን 2017 ዓ.ም

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

27 Aug, 05:32


አበው ስለ እመቤታችን እንዲህ አሉ !

"አምላክ ከንጉሥ ሔሮድስ ሴት ልጅ ቢወለድ ኖሮ አልጋ ወራሽ በሆነና ባልተሰደደ ነበር። እርሱ ግን የድሆች ልጅ የሆነችውን ድንግል መረጠ" አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ

"ታላቁ ተራራ ሆይ ታናሽዋ ብላቴና የተሸከመችህ ራስህን በሚቻላት መጠን አድርገህላት ነው ፣ ታላቁ እሳት ሆይ ታናሽዋ ብላቴና ተሸክማህ ያልተቃጠለችው ኃይልን ትችል ዘንድ አጽንተሃት ነው " ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ

"ይህ ዓለም የእግዚአብሔርን ልጅ በቀጥታ ከእግዚአብሔር አብ እጅ ለመቀበል የተገባ ሆኖ ስላልተገኘ ፣ ዓለም ከእርስዋ ይቀበል ዘንድ አንድያ ልጁን ለድንግል ማርያም እናት ትሆነው ዘንድ ሠጣት" ቅዱስ አውግስጢኖስ

"ሔሮድስ የማይያዘውን ይይዝ ዘንድ ተነሣ ፣ ዓውሎ ነፋስንም በቤቱ አስገብቶ ሊዘጋ ታገለ" አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ

"ጌታ ሆይ እናትህን ማን ብለን እንጥራት? እናት ብቻ እንዳንላት ድንግል ሆና አገኘናት ፣ ድንግል እንዳንላት ልጅ ታቅፋ አየናት። ጌታ ሆይ እናትህን ለመጥራት እንዲህ የሚያስቸግር ከሆነ አንተን ከቶ ምን ብለን እንጠራሃለን??" ቅዱስ ኤፍሬም

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

22 Aug, 15:53


ድንግል ሆይ !

❝አንቺን የወለደ ማህጸን እንዴት ያለ ብሩክ ነው❞ አንቺን የታቀፉ ክንዶችስ እንዴት ያሉ ድንቅ ናቸው ! አስራ ሁለት ዓመት ወደ ቤተመቅደስ የተመላለሱ እግሮችሽስ እንዴት የከበሩ ናቸው ! የቅዱሱን መልአክ ብሥራት የሰሙ ጆሮዎችሸስ እንዴት ያሉ ንቁ ናቸው ! ❝የቃልን ሰው መሆን ያመነው ልብሽ እንዴት ያለ ንጹሕ ነወ ! ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ጌታን የተሸከመው ማሕፀንሽ እንዴት ያለ ግሩም ነው ! ይህን ታላቅ አምላክ የታቀፉ ክንዶችሽስ እንዴት ያሉ ጽኑ ናቸው ! ጌታዬን ያጠቡት ጡቶሽን እንዴት የለመለሙ ናቸው ! ድንግል ሆይ ክብርሽ ከፍ ያለ ነውና አከብርሻለሁ❞ ሰላሳ ሶስት ዓመት ከሶሶት ወር ከጌታ ጋር ያኖረሽን እምነት እኔ ልጅሽ ለአንድ ሰዓት እንኳ የለኝምና እጅግ ጎስቋላ ነኝ ። አስራ ሁለት ዓመት ከወንጌላዊው ዮሐንስ ቤት ያኖረሽን ልበ ሰፊነት እኔ ደካማው ልጅሽ ለአንድ ሰዓት እንኳ ከምወደው ጋር ለመሆን አልታደልኩምና እጅግ ደካማ ነኝ ! ቅድስት ሆይ የምልጃሽ በረከት የእግዚአብሔርን እገዛ ይላክልኝ ። ፍልሰትሽ መጪውን የምዕመናንን ትንሳኤ ጎልቶ ያሳያል ።  ዕርገትሽ መጪውን የምዕመናን ዕርገት በግልጥ ያስተምራል ። ከሚታስበው በላይ  ቅድስት ፣ ከሚነገረው በላይ ትሁት ፣ ከምሰማው በላይ ቡሩክት ፣ ከጻፉልሽም በላይ ንጽህት ፣ ከተረኩሽም በላይ ልዕልት ነሽና ልቤ ታመሰግንሻለች !

ዲያቆን እስጢፋኖስ ደጀኔ
ነሐሴ 16 ቀን 2016 ዓ.ም.

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

18 Aug, 09:33


ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን ክብረ መንግሥቱን ለገለጠበት ለበዓለ ደብረ ታቦር እንኳን አደረሳችሁ !

“ከስድስት ቀንም በኋላ ኢየሱስ ጴጥሮስንና ያዕቆብን ወንድሙንም ዮሐንስን”

ሌላኛው (ወንጌላዊ) “ከስምንት ቀን በኋላ”   ይላል ። ይህም ከማቴዎስ ጋር በደንብ ይስማማል እንጂ አይጋጭም ። ሉቃስ የተናገረበትንና ይዟቸው የወጣበትን ቀን ሲገልጽ ማቴዎስ ግን በመሐል ያሉትን ቀኖች ብቻ ይገልጻል። ነገር ግን ልብ በሉ እጸልይላችኋለሁም የማቴዎስን መልካምነት ተመልከቱ ፤ እርሱ ሳይመረጥ የተመረጡትን አልሸሸጋቸውም ። ዮሐንስም ብዙ ጊዜ በልበ ቀናነት የጴጥሮስን እንግዳ ምስጋናዎች በመመዝገብ እንዲህ ያደርጋል ። የእነኚህ ቅዱሳን ሰዎች አገልግሎት በሁሉም ቦታ ከቅንዓትና ከከንቱ ውዳሴ የጸዳ ነው ።

“ወደ ረጅም ተራራ ብቻቸውን አወጣቸው ። በፊታቸውም ተለወጠ ፥ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ ፥ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ ። እነሆም ፥ ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው ።” 

እነዚህን ብቻ ከእርሱ ጋር የወሰደው ስለ ምንድር ነው ? ምክንያቱም እነዚህ (ሦስቱ ሐዋርያት) ከሌሎቹ ስለሚበልጡ ነው ። ጴጥሮስ ብልጫውን (ጌታን) እጅግ በመውደድ ፣ ዮሐንስ ደግሞ በእርሱ (በጌታ) እጅግ አብልጦ በመወደድ አሳይተዋል ። ያዕቆብ ከወንድሙ (ከዮሐንስ) ጋር ጽዋውን መጠጣት እንችላለን ብሎ በመመለሱ  ፣ በመልሱ ብቻ ሳይሆን በሥራውም ነው ። ይህም ሌሎች ሥራዎችን በመሥራትና ያለውን በመፈጸም ነው ። እርሱ ቅን የነበረ ቢሆንም ለአይሁዳውያን ግን የሚያስጨንቅና የሚያሳዝን ነበር ። ሄሮድስ ራሱ ያዕቆብን በሰይፍ ያስገደለው አይሁዳውያንን ደስ ለማሰኘትና ታላቅ የሆነ ውለታ እንደ ዋለላቸው በማሰብ ነው ።

ነገር ግን ለምንድር ነው ወዲያውኑ ወደ ተራራ ያላወጣቸው ? (ይህንንም ያደረገው) ሌሎቹን ደቀ መዛሙርት ከሰብአዊ ድካም ለመጠበቅ ነው ። ለዚህም ሲል ከእርሱ ጋር ወደ ተራራ የሚወጡትን ደቀ መዛሙርት ስም በግልጽ አልተናገረም ። ምክንያቱም (ስማቸውን ቢጠራ ኖሮ) የተቀሩት እርሱን ለመከተልና የክብሩን ነጸብራቅ ለመመልከት አብዝተው ስለሚፈልጉ እንደ ተረሱ ይሰማቸው ነበር ።

ለምን ታዲያ አስቀድሞ ተናገረ ?   አስቀድሞ በመናገሩ ታላቅ የሆነውን እውነት ለመያዝ ዝግጁ እንዲሆኑና በጊዜውም በነበረው ጥልቅ ስሜት ተሞልተው ፍጽም ንቁ በሆነ አእምሮአቸው እንዲገኙ ነው ።

ሙሴና ኤልያስን ለምንድር ነው ያመጣው ? ብዙ ምክንያቶችን ልናቀርብ እንችላለን ፦ የመጀመሪያው አንዳንዶች ኤልያስ ሌሎች ኤርምያስ አልያም ከታላላቆቹ ነቢያት አንዱ ነው ይሉ ነበርና የነቢያት አለቃ የሆነውን (ኤልያስን) በማምጣት በአገልጋይና በጌታ መካከል ያለውን ልዩነት እንዲመለከቱ አስቦ ነው ። በዚህም ጴጥሮስ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ነህ ለሚለው ምስክርነት የተሰጠው ምስጋና ትክክለኛነት ተገልጿል ።

ሆኖም ግን ከዚህ በተጨማሪ አንድ ሰው ሌላ ምክንያቶችንም መጥቀስ ይችላል፦ ሰዎች ክርስቶስ ሕግን ተላልፏል ፣ የራሱ ያልሆነውን የአብን ክብር ለራሱ አድርጓል ፣ የእግዚአብሔርንም ስም ያጠፋል ብለው ከሰውት ነበር ። እንዲህም አሉት፡- “ይህ ሰው ሰንበትን አያከብርምና ከእግዚአብሔር አይደለም”   በሌላም ስፍራ አይሁድ ይህንን ተናገሩ፡- “ስለ መልካም ሥራ አንወግርህም ፤ ስለ ስድብ ፤ አንተም ሰው ስትሆን ራስህን አምላክ ስለ ማድረግህ ነው እንጂ ብለው መለሱለት ።”   (ክርስቶስ ግን) እነዚህ ሁሉ ክሶች ከቅናት እንደ መጡ ፣ በአንዱም እንኳን ተጠያቂ እንዳልሆነ ፣ ጠባይና ተግባሩም ሕጉን እንዳልተቃረነ ፣ አልያም ራሱን ከአባቱ ጋር እኩል አድርጎ መጥራቱ የራሱ ያልሆነን ክብር ለራሱ መስጠት እንዳልሆነ ለማሳየት በዚህ ረገድ ምስክር የሚሆኑትን ጠራቸው ። የሕጉን መፍረስ ሙሴ ችላ አይልምና ፣ ለሚተላለፈው ፣ ሕጉን የተቀበለው ሙሴ ጠላት ክብር አይሰጥምና ሙሴን ጠራው ። ልክ እንደዚሁ ኤልያስም በበኩሉ ለእግዚአብሔር ክብር ቀናተኛ ነበር ። እርሱም የእግዚአብሔርን ጠላት ፣ በሐሰትም ራሱን እግዚአብሔር ብሎ የሚጠራ ራሱን ከአብ ጋር የሚያስተካክልን ሰው አያደምጥም አይታገሥም (ነበርና ኤልያስንም ጠራው)። ደብረ ታቦር ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንደ ሰበከው !

የጸባዖት ብርሀን በጓዳችን ይግባ !

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

11 Aug, 19:01


‹‹በአብ ዘንድ ልጅ .. በመንፈስ ዘንድ ቃል .. በድንግል ዘንድ ህፃን .. በነቢያት ዘንድ ነቢይ .. በሐዋርያት ዘንድ ሐዋርያ .. በሰማዕታትም ዘንድ አክሊል የሚሆን .. የማኅበር አለቃ እውነተኛ መምህር ይህ
ኢየሱስ ክርስቶስ ነው!››
[ኢየሱስ ክርስቶስ በመፅሐፈ ሰዓታት] አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

05 Aug, 05:57


የቅዱስ ባስልዮስ የምስጋና ጸሎት

“ለእኛ በጎ ነገርን ያደረገ ይቅር ባይ እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፤ ይቅር ባይ የጌታችን የአምላካችንና የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አባት ሰውሮናልና፣ ረድቶናልና፣ ጠብቆ አቅርቦናልና፣ ወደእርሱም ተቀብሎናልና፣ አጽንቶ ጠብቆናልና፣ እስከዚችም ሰዓት አድርሶናልና። አሁንም ክብርት በምትሆን በዚህች ዕለት በሕይወታችን ዘመን ሁሉ በፍጹም ሰላም ሁሉን የሚይዝ አምላካችን እግዚአብሔር ይጠብቀን ዘንድ እንለምነው። አምላካችን እግዚአብሔር ይቅር ባይ ስለሆነ።" አሜን !

በቸር ዋሉ !

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

03 Aug, 18:27


ቀራንዮ በኢየሱስ ክርስቶስ ተቀደሰች ፤ ጎልጎታ አደፍ ጉድፍ በሌለባት በነጻች በሥጋው በድን ተቀደሰች።

በቀራንዮ የመከራው አልጋ ተተከለች ፤ ጎልጎታ ማሸለቢያው ሥፍራ ሆነች። ቀራንዮ የሠርጉ አፀድ ሆነች ፤ ጎልጎታም ድንኳኑ!

ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
[መጽሐፈ ምሥጢር ፤ ምእራፍ 15 ቁጥር

ጌታዬና አምላኬ መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ማረኝ!

ስብሐት ለእግዚአብሔር

Nolawi ኖላዊ ኄር ዘ-ኦርቶዶክስ

14 Jul, 08:18


አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ስለ ሥሉስ ቅዱስ እንዲህ አለ!

አብ የማይዳሰስ እሳት እንደሆነ ፤ ወልድም የማይያዝ እሳት ነው ፤ መንፈስ ቅዱስም በሃይማኖት ሙቀት ቤተክርስቲያንን የሚያሞቃት እሳት ነው። (ምእራፍ 1 ቁጥር 9 ፤ ገጽ 2)

አብ የማይጠልቅ ፀሐይ እንደሆነ ፤ ወልድም ዘወትር በቅዱሳን ላይ የሚያበራ ፀሐይ ነው ፤ ወልድ ዘወትር በቅዱሳን ላይ የሚያበራ ፀሐይ እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም ቤተክርስቲያንን የሚያስጌጣት ፀሐይ ነው። (ምእራፍ 2 ቁጥር 10 ፤ ገጽ 17)

በሦስትነት አንድ በአንድነትም ሦስት በሚሆን ፤ በባሕርይ አንድ በሚሆን ፤ በመለኮትም በሚተካከል በእግዚአብሔር ስም አንድ አምላክ እንጂ አማልክት አይባሉም። በመዋሐድ የተያያዙ በአንዲት ፈቃድም የሚተባበሩ በምስጋና መብረቅ የተጋረዱ በሚነድድ እሳትም የሚሸፈኑ ናቸው። አንዱ አንዱን ኹለተኛውም ከሦስተኛው አይቀድመውም የነፋሳት ሩጫን ያህል ፤ የዓይን ጥቅሻም ያህል ከሰዎች እና ከመላእክት ዘንድ በአንድነት የሚሰገድለት ለእርሱ ምስጋና ይገባል ፤ ጥንት ለሌለው ለፊተኛው ፤ ፍጻሜ ለሌለው ለኋለኛው ለዘለዓለሙ አሜን! (ምእራፍ 5 ቁጥር 1 ፤ ገጽ 51) ለማይበታተን ሦስትነታቸው ምስጋና ፤ ለማይጨመርበት አንድነታቸውም አኰቴት ፤ ለማይከፈል ሕልውናቸው ጌትነት ይገባል ፤ ለዘለዓለሙ አሜን አሜን!!! (ምእራፍ 3 ቁጥር 48 ፤ ገጽ 35) "የመንፈስ ቅዱስን ምግብ እንመገብ ፤ ይኸውም የእግዚአብሔር ቃል ነው ፤ ከሰይጣን አፍ በተጠራጣሪ ልብ ላይ የተዘራ የመከራ እንጀራን እንተወው ፤ ከነቢያት ከሐዋርያት አንደበት ለራሳችን ጥሩ ውኃን እንቅዳ ፤ ከዐመፃ መምህራን አንደበት የተቀዳውን የደፈረሰ ውኃ ግን እናፍስሰው።"

[ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ]
(መጽሐፈ ምሥጢር ምእራፍ 27 ቁጥር 60)

ምንጭ: መጽሐፈ ምሥጢር ግእዝና አማርኛ ፤ ትርጉም መምህር ኅሩይ ኤርምያስ ፤ አሳታሚ የቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫና የቅዱስ አባ በጸሎተ ሚካኤል አንድነት ገዳም ፤ 2011 ዕትም

የሥሉስ ቅዱስ አገልጋይ የቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ጸሎት ፣ ልመና ፣ ጸጋ እና በረከት አይለይን!!!

ስብሐት ለእግዚአብሔር

11,667

subscribers

423

photos

2

videos