ኦርቶዶክስ ሃይማኖታችን

@haymanotachn


✞የኦርቶዶክስ ቻናል✞
> የየዕለቱ ስንክሳር
>ኦርቶዶክሳዊ ጥያቄዎች ከነመልሱ
> በቅርብ የጀመረው አስተማሪ ታሪኮች
> መንፈሳዊ ዝማሬዎች
> የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ
> መንፈሳዊ ፊልሞች
> መንፈሳዊ ትምህርቶችና
የተለያዩ ፁፎች
#ሁሉም_በየእለቱ

ኦርቶዶክስ ሃይማኖታችን

23 Oct, 20:42


✞ አምላከ ቅዱሳን ለእነርሱ ካደለው ፍቅራቸው ለእኛም አይንሳን:: በረከታቸውንም ያብዛልን::

🕊

[  † ጥቅምት ፲፬ [ 14 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  ]

፩. አቡነ ዘሚካኤል [አረጋዊ]
፪. ቅዱስ ፊልዾስ ሐዋርያ [ከ፸፪ [72] ቱ አርድእት]
፫. ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ መርዓዊ
፬. ቅዱስ ሙሴ መርዓዊ
፭. ቅድስት እድና [የአረጋዊ እናት]
፮. አባ ማትያስ [የአረጋዊ ረድዕ]

[   †  ወርሃዊ በዓል  ]

፩. አባ ዮሐንስ ጻድቅ
፪. እናታችን ቅድስት ነሣሒት

" ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ይወስዳል:: ጻድቅን በጻድቅስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ይወስዳል:: ማንም ከእነዚህ ከታናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ውሃ ብቻ በደቀ መዝሙር ስም የሚያጠጣ እውነት እላቹሃለሁ ዋጋው አይጠፋበትም::" [ማቴ.፲፥፵፩] (10:41)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖

ኦርቶዶክስ ሃይማኖታችን

23 Oct, 20:42


🕊

✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞

✞ ጥቅምት ፲፬ [ 14 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ✞

† 🕊  አቡነ አረጋዊ ዘደብረ ዳሞ  🕊 †

✞ በሃገራችን ስም አጠራራቸው ከከበረ አባቶች አንዱ እኒህ ጻድቅ ናቸው:: ጻድቁ የተወለዱት በ፭ [5]ኛው መቶ ክ/ዘመን አጋማሽ ኣካባቢ ሲሆን ወላጆቻቸው ንጉሥ ይስሐቅና ቅድስት እድና ይባላሉ:: የተለወለዱበት አካባቢም ሮም ነው::

ስማቸው ብዙ ዓይነት ነው:: ወላጆቻቸው ዘሚካኤል ሲሏቸው በበርሃ ገብረ አምላክ ተብለዋል:: በኢትዮዽያ ደግሞ አረጋዊ ይባላሉ:: አቡነ አረጋዊ ምንም የንጉሥ ልጅ ቢሆኑም በልጅነታቸው መጻሕፍትን ተምረው ነበርና ጠፍተው ገዳም ገቡ::

በዚያም በገዳመ ዳውናስ [ግብጽ] የታላቁ ቅዱስ ዻኩሚስ ደቀ መዝሙር ሆነው ከነ አባ ቴዎድሮስ ጋር ሥርዓተ መነኮሳትን ተምረዋል:: ከመነኮሱ ከዓመታት በኋላም ወደ ሃገራቸው ሮም ተመልሰው በማስተማር ፯ [7] ያህል የቤተ መንግስት ሰዎችን ወደ ምናኔ ማርከዋል::

"የት ልሒድ" ብለው ሲያስቡም ቅዱስ መልአክ በክንፉ ጭኖ ወስዶ ኢትዮዽያን አሳያቸው:: ተመልሰውም ለ፰ [8] ባልንጀሮቻቸው "ሃገርስ ባሳየሁዋችሁ! ሐዋርያ ሳያስተምራት በሕጉ በሥርዓቱ ጸንታ የምትኖር" ብለው ከ፰ [8]ቱ ጋር ወደ ኢትዮዽያ መጡ::

በዚህ ጊዜም እናታቸው ቅድስት እድናና ደቀ መዝሙራቸው አባ ማትያስ አብረው ነበሩ:: ወደ ሃገራችን የመጡ በ፬፻፸ [470]ዎቹ አካባቢ ሲሆን አልዓሜዳ በክብር ተቀብሏቸዋል:: በቤተ ቀጢን [አክሱም] ተቀምጠውም መጻሕፍትን እየተረጐሙ: ወንጌልን እየሰበኩ ቆይተዋል::

ለሥራ በተለያዩ ጊዜም አቡነ አረጋዊ በዓት ፍለጋ ብዙ ደክመዋል:: በመጨረሻ ግን ደብረ ዳሞን [ደብረ ሃሌ ሉያን] አይተው ወደዷት:: የሚወጡበት ቢያጡም ጅራቱ ፷ [60] ክንድ የሚያህል ዘንዶ ተሸክሞ ከላይ አድርሷቸዋል::

እንደ ወጡም "ሃሌ ሉያ ለአብ: ሃሌ ሉያ ለወልድ: ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ" ብለው ቢያመሰግኑ ከሰማይ ሕብስት ወርዶላቸው ተመግበዋል:: በዚህም ቦታዋ "ደብረ ሃሌ ሉያ" ተብላለች:: ጻድቁ ቦታውን ከገደሙ በኋላ ከተለያየ ቦታ መጥተው ፮ [6]ሺ ያህል ሰዎች በእጃቸው መንኩሰዋል::

ምናኔን በማስፋፋታቸውና ሥርዓቱን በማስተማራቸውም "አቡሆሙ ለመነኮሳት ዘኢትዮዽያ-የኢትዮዽያ መነኮሳት አባት" ይባላሉ:: አቡነ አረጋዊ በሕይወታቸው ከተጋድሎ ባሻገር በወንጌል አገልግሎትና መጻሕፍትን በማዘጋጀትም ደክመዋል::

ቅዱስ ያሬድና አፄ ገብረ መስቀልም ወዳጆቻቸው ነበሩ:: በተራራው ግርጌ ያለችውን ኪዳነ ምሐረትን ለሴቶች ሲገድሟት ቀዳሚዋ መነኮስ እናታቸው ንግስት እድና ሁናለች::

ጻድቁ ንጹሕ ሕይወታቸውን ፈጽመው በተወለዱ በ፺፱ [99] ዓመታቸው በዚህ ቀን በገዳሙ በስተምሥራቅ አካባቢ ተሰውረው ብሔረ ሕያዋን ገብተዋል:: ጌታም ፲፭ [15] ትውልድን የሚያስምር የምሕረት ቃል ኪዳን ሰጥቷቸዋል::


† 🕊  ቅዱስ ፊልዾስ ሐዋርያ  🕊 †

✞ በዘመነ ሐዋርያት በዚህ ስም የሚጠሩ አባቶች ፪ [2] ነበሩ:: አንደኛው ከ፲፪ [12]ቱ ሐዋርያት ሲቆጠር ዛሬ የምናከብረው ደግሞ ከ፸፪ [72]ቱ አርድእት ይቆጠራል:: ቅዱስ ፊልዾስ ያደገው የኖረውም በቂሣርያ አካባቢ ሲሆን ባለ ትዳር የልጆች አባት ነው::

ጌታ ሲጠራው እንኩዋ ፬ [4] ደናግል ሴቶች ልጆች ነበሩት:: ከጌታ ሕማማት በፊት ተልኮ አስተምሯል:: ከበዓለ ሃምሳ በኋላም ፯ [7]ቱ ዲያቆናት ሲመረጡ አንዱ እርሱ ነበር:: [ሐዋ.፮] (6) በቅዱስ እስጢፋኖስ መሪነትም ፰ [8] ሺውን ማሕበር አገልግሏል::

ቅዱስ እስጢፋኖስ ተገድሎ ፰ [8]ሺው ማሕበር ሲበተንም ቅዱስ ፊልዾስ ፬ [4]ቱን ልጆቹን አስከትሎ ወደ ሰማርያ ወርዷል:: በዚያም መሠሪ ስምዖንን ጨምሮ የሃገሪቱን ሰዎች አሳምኖ አጥምቁዋል::

መቼም ቢሆን እኛ ኢትዮዽያውያን የማንዘነጋው ግን ጃንደረባውን ባኮስን ማጥመቁን እና ለሃገራችን የወንጌልን ብርሃን መላኩን ነው:: ጃንደረባው ቅዱስ ባኮስ ከጉዞ መልስ ትንቢተ ኢሳይያስን [ኢሳ.፶፫] (53) ሲያነብ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ቀርቦ ምሥጢረ ሥጋዌን አስረድቶታል::

ሠረገላውም ቁሞለት ቅዱስ ባኮስን አጥምቆት ተነጥቆ ሔዷል:: [ሐዋ.፰፥፳፮] (8:26) ቅዱስ ፊልዾስ በቀሪ ዘመኑ ከተባረኩ ፬ [4] ደናግል ልጆቹ ጋር ሲሰብክ ኑሮ በዚህች ቀን ዐርፏል::

†  🕊  ሙሽራው ቅዱስ ሙሴ  🕊  †

✞ የዚህ ቅዱስ ወጣት ታሪክ ደስ የሚልም: የሚገርምም ነው:: በሮም ከተማ በምጽዋት: በጾምና በጸሎት ከተቃኙ ሃብታሞች [መስፍንያኖስና አግልያስ] ተወልዶ: በሥርዓቱ አድጐ: መጻሕፍትን ተምሮ በተክሊል አጋቡት::

በሠርጉ ማግስት ሙሽሪትን ቢያያት በጣም ታምራለች:: "ይህ ሁሉ ውበትና ምቾት ከንቱ አይደለምን!" ብሎ በሌሊት ጠፍቶ: ነዳያንን መስሎ ከሮም ሃገረ ሮሆ [ሶርያ አካባቢ] ሔደ::

በዚያም በፍጹም ምናኔ: በ፯ [7] ቀን አንዲት ማዕድ እየበላ: በረንዳ ላይ እየተኛና እየለመነ ለዓመታት ኖረ:: ሁሌም ቀን የለመነውን ማታ ለነዳያን አካፍሎ እርሱ ሲጸልይ ያድር ነበር:: በአካባቢው ክብሩ ሲገለጽበትም የሐዋርያውን የቅዱስ ዻውሎስን በረከት ፍለጋ ወደ ጠርሴስ ሔደ::

ነገር ግን ጥቅል ነፋስ መርከቧን ገፍቶ ሮም አደረሳት:: ቅዱስ ሙሴም "የአምላክ ፈቃድ ነው" ብሎ በወላጆቹ ደጅ ተኝቶ ለ፲፪ [12] ዓመታት ተጋደለ:: ወላጆቹ ፈልገው ስላጡት በበራቸው የወደቀው ነዳይ እርሱ ይሆናል ብለው አልጠረጠሩም::

ከብዙ ተጋድሎም በኋላም ዜና ሕይወቱን ጽፎ በዚህች ቀን: በዕለተ እሑድ ዐርፏል:: ጌታችንም "መታሰቢያህን ያደረገውን ሁሉ ካልተጠራጠረ እምረዋለሁ" ብሎታል::

በዚያም ሕዝቡ: ካህናቱና ሊቀ ዻዻሳቱን ጌታ አዟቸው አግኝተውታል:: ወላጆቹ ማንነቱን በለዩ ጊዜም ታላቅ ለቅሶን አልቅሰዋል:: ሥጋውም ብዙ ተአምራትን አድርጉዋል::


† 🕊 ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ መርዓዊ  🕊 †

✞ ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ በሃገራቸው ልሳን 'አብደል መሲሕ' ይባላል:: ለቅዱስ ሙሴና ለሌሎችም ሙሽርነትን ትቶ መመነንን ያስተማረ እርሱ ነው:: አባቱ ታላቁ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ሲሆን እናቱ መርኬዛ ትባላለች:: የጻድቃን ትውልድ የተባረከ ነውና [መዝ.፻፲፩፥፩] (111:1) ታላቁ አቡነ ኪሮስ አጐቱ ናቸው::

ስለዚህ ቅዱስ ምን እነግራቹሃለሁ! ሙሉ ታሪኩ ከቅዱስ ሙሴ ጋር ተመሳሳይ ነውና:: ልዩነቱ ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ በገዛ ፍቃዱ አካሉ በመቁሰሉ ምክንያት ሰዎች ሊለዩት አልቻሉም ነበር::

በአርማንያ: በእመቤታችን ቤተ ክርስቲያን ደጅ ለ፲፭ [15] ዓመታት ሲጋደል ወደ ወላጆቹ ሃገር ቁስጥንጥንያ ተመልሶ ለ፲፭ [15] ዓመታት ተፈትኗል:: ምንም የንጉሥ ልጅ ቢሆንም የአባቱ ባሮች በጥፊ ይመቱት: ጽሕሙን [ጺሙን] ይነጩት: ቆሻሻ ይደፉበት: ሽንታቸውንም ይሸኑበት ነበር::

ለእርሱ ወዳጆቹ ውሾች ነበሩ:: በአባቱ ደጅ ለ፲፭ [15] ዓመታት መከራን ከተቀበለ በኋላ "ጌታ ሆይ! የአባቴ አገልጋዮች በእኔ ላይ ያደረጉትን ሁሉ በደል አድርገለህ አትቁጠርባቸው" አለ:: በዚህች ቀን ሲያርፍም ጌታችን ፯ [7]ቱን ሊቃነ መላእክት ከነ ሠራዊታቸው አስከትሎ ወርዶ በክብር አሳርጐታል:: አጠቃላይ የገድል ዓመታቱም ፴ [30] ናቸው::

ኦርቶዶክስ ሃይማኖታችን

23 Oct, 17:16


                           †                           

  [   🕊 እ መ አ ም ላ ክ 🕊    ]  

🌼▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬🌼


❝ አጽምዕ ሰማይ ዘእነግረከ ወስምዒ ምድር እምዜና ስደታ ንስቲተ ለእመ መለኮት ክቡር ዘልበ ይከፍል ወኅሊና ያንቀለቅል ሶበ ይትነገር ሕማማ ለድንግል፡፡ አመ ወፅአት በፍርሃት እምሀገረ ዳዊት ዘይሁዳ በብሥራተ መልአክ እንግዳ ኢረከበት ማየ በፍኖት ዘታሰትዮ ለወልዳ። ❞

🕊

[ ሰማይ የምነግርኽን ስማ ፤ ምድርም በሚነገር ጊዜ ልብን የሚከፍልና ኅሊናንም የሚያነዋውጥ የድንግልን መከራ በሚነገር ጊዜ ከክቡር መለኮት እናት ከስደቷ ዜና ጥቂት ስሚ፡፡ በእንግዳ መልአክ ብሥራት የይሁዳ ክፍል ከምትኾን ከዳዊት ከተማ ከይሁዳ በፍርሀት በወጣች ጊዜ ለልጇ የምታጠጣው ውሃ በመንገድ አላገኘችም፡፡ ]

[ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ]


†                       †                      †
💖                    🕊                   💖

ኦርቶዶክስ ሃይማኖታችን

23 Oct, 15:43


                          †                          

💖  [    የትሕርምት ሕይወት !    ]  💖

🕊                       💖                      🕊


[       “ አገልግሎትን በተመለከተ ! "       ]

[ ሥራን አስመልክቶ የሰጠው ትምህርት ! ]

--------------

❝ ወደጄ ሆይ ! በምትሠራው ሥራ ምክንያት አትዘን፡፡

በምትሠራው ሥራ ላይ በፍጹም ስኬታማ ልሆን አልቻልኩም፡፡ እኔ ስንፍናን የተሞላሁ ፣ የደነዘዝሁ ነኝና በፍጹም ይህን ተግባር ልፈጸም አልችልም፡፡ እጆቼ ያለ ፍሬ ከሥራው ብዛት የተነሣ ዝለዋል፡፡ ሥራውን ለመሥራት አሁን አቅሙ የለኝም ስለዚህ ወደመጣሁበት እመለሳለሁ ... የሚል ሐሳብ በአእምሮህ ውስጥ ከቶ አይመላለስ::

እንደ አንድ አማኝ በእግዚአብሔር ታመን ፥ እንዲህ ባለ ነገርም ተስፋ አትቁርጥ፡፡ ነገር ግን ወደ መንግሥቱና ወደ እርሱ ደስታ ስለጠራህ ስለ ጌታችን ስለ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብለህ መከራውን ሁሉ ታግሠህ ኑር፡፡ እንዲህ ተብሎ እንደተጻፈ ፦ “እውነት እላችኋለሁ ፥ የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ ፥ ይህን ተራራ ከዚህ ወደዚያ እለፍ ብትሉት ያልፋል ፤ የሚሳናችሁም ነገር የለም፡፡” [ማቴ.፲፯፥፳]

ስለዚህ ተወዳጆች ! ሆይ እምነት ይኑረን ፤ እኛ ተስፋ ያደረግናቸው ከቶ ሊያድኑን የማይችሉ ሰዎችን ሳይሆን እግዚአብሔርን ነው፡፡ እንዲህ ተብሎ እንደተጻፈ ፦ “በእግዚአብሔር የታመኑ እንደማይታወክ ለዘላለም እንደሚኖር እንደ ጽዮን ተራራ ናቸው::” [መዝ.፻፳፬፥፩] የኃያላን ጌታ ሆይ በአንተ ተስፋ የሚያደርጉ ብፁዓን ናቸው፡፡ ❞

[  ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ  ]


🕊                       💖                   🕊

ኦርቶዶክስ ሃይማኖታችን

23 Oct, 13:12


                          †                          

[    🕊    ገ ድ ለ   ቅ ዱ ሳ ን   🕊     ]

▬▬▬▬▬▬   †    ▬▬▬▬▬▬

[  የአባታችን የቅዱስ መቃርዮስ የተጋድሎ ሕይወቱና ትምህርቱ  ]

[                ክፍል  ሃያ ስድስት                 ]

💛

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

[  እግዚአብሔር የአባ መቃርዮስን ጩኸት እንደ መለሰለት  ]

                         🕊                         

❝ በአንድ ወቅት ታላቁ አባ መቃርዮስ ከአስቄጥስ ወደ ግብፅ እየሄደ ሳለ ትንሽ ቅርጫቶች ተሸክሞ ነበር፡፡ እርሱም በደከመው ጊዜ ቁጭ አለ፡፡ ዓይኖቹን ወደ ሰማይ አቅንቶ ፦ " ጌታ ሆይ ፣ ምን ያህል እንደ ደከመኝና እንደዛልኩ የምታይ አንተ ነህ " አለ፡፡ ይህን ካለ በኋላ ወዲያውኑ ራሱን ከቅርጫቶቹ ጋር በዓባይ ወንዝ ዳር ላይ ደርሶ አገኘው፡፡

የቅዱስ መቃርዮስ ደቀ መዝሙር የነበረው አባ በብኑዳ እንዲህ አለ ፦ " አንድ ቀን ቅዱስ መቃርዮስ ቆሞ ሲጸልይ ሳለ እግዚአብሔር እንዲህ ሲል ተናገረው ፦ ' መቃራ ሆይ ፣ እገሌ በምትባል ሀገር ያለማቋረጥ በትጋት የሚያገለግለኝንና የሚያመሰግነኝን አንድ ገበሬ ምሰል፡፡ ' ይህን በሰማ ጊዜ ከመጀመሪያዎቹ አርድእት አንዱ የሆንኩትን እኔን በብኑዳን ፦ ' ተነሥና ምርኩዝህን ይዘህ ከእኛ ጋር እገሌ ወደምትባል ሀገር እንሂድ ' አለኝ፡፡ ወደዚያ ሄደን ከወንዙ ሐይቅ ዳር ደረስን ፣ የሚያሻግረን በፈለግን ጊዜ አላገኘንም ነበርና ስፋቱን እየተመለከትን ሁላችንም ዝም ብለን በዚያ ተቀምጠን ነበር፡፡ ቅዱስ መቃርዮስ ግን በተመሥጦ ሆኖ ራእይን እያየ ነበር፡፡

እኔም አባታችን ፣ እግዚአብሔር ጸሎትህን እንደሚሰማ አውቃለሁና ይረዳን ዘንድ ጸልይ አልኩት፡፡ ያን ጊዜም እየማለደ ጸለየ፡፡ ወዲያውኑ ታላቅ አዞ ከባሕሩ ወጣ ፤ ቅዱሱም ' እግዚአብሔር ከወደደና አዝዞህ ከሆነ አሻግረን ' አለው፡፡ ያ አዞም ተሸከመንና ወደ ማዶ አሻገረን፡፡ ቅዱስ መቃርዮስም ያንን አዞ ' እግዚአብሔር ዋጋህን እስከሚሰጥህ ድረስ ወደ ውኃው ግባ ' አለው፡፡ እርሱም እራሱን ወደ ውኃው አጠለቀ፡፡

ወደ ሀገሩ በወጣንና ወደዚያ በደረስን ጊዜ በሀገረ ገዢው እርሻ ላይ ተሰማርተው የሚሠሩ ብዙ ገበሬዎችን አገኘን፡፡ አረጋዊው መቃራም እነዚያን ገበሬዎች እያንዳንዳቸውን እየተመለከተ በበሩ አንጻር ተቀመጠ፡፡ እግዚአብሔር ስለ እርሱ ያመለከተው ያ ገበሬ በመጣ ጊዜ በዙሪያው ከብባው ያለችውን ጸጋ እግዚአብሔር ተመለከተ ፣ በትዕግሥት የተከደነ መሆኑንም አየ፡፡ ሰላምታ ሰጥቶ የተቀደሰች መሳምን ሳመው፡፡ ከዚያም እርሱን ይዞ ለብቻው ገለል አደረገውና ፦ 'እግዚአብሔርን የምታገለግልበት ሥርዓተ ተልእኮህ ምንድን ነው ? ' አለው፡፡ ያ ገበሬም ፦ ' እኔ በዚህ ዓለም ለቀሲስ [ ለካህን ] እላላካለሁ ፣ ጌታዬ ሰማያዊ ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስም ዋጋዬን ይሰጠኛል፡፡ ስለዚህም ይህን ያህል ዘመን ሁሉ ዘወትር አገለግላለሁ ፣ እኔም ልቤ የቀና ነው ' አለው፡፡

መቃርዮስም ፦ ' ይህን ሃሳብ ከየት አገኘኸው?' አለው፡፡ እርሱም ፦ " ሠራተኞቹን አምጧቸውና ደመወዛቸውን ስጧቸው " ካለው ከጌታ ቃል ነው ' አለው፡፡ ቅዱስ መቃርዮስም ይህን ነገር ከእርሱ በሰማ ጊዜ ሳመውና መከረው ፣ በላዩም ላይ ማሕየዊ በሆነ በትዕምርተ መስቀል ባረከው፡፡ ከዚያም ሲመለስ ነፍሱን ፦ ' መቃራ ሆይ ወዮልህ ፣ የዚህን ዓለማዊ ወንድም ያህል እንኳን አእምሮ የለህም ፣ ብታውቅበትና በምግባርህ እግዚአብሔርን ብታገለግል እርሱ ዋጋህን ይሰጥሃል' እያለ በመንገድ ላይ ሁሉ ታላቅ ለቅሶን ያለቅስ ነበር፡፡ "

" ወደ ወንዙ በደረስን ጊዜ የሚያሻግረን ስላጣን አባት መቃርዮስ በዚያ ጸለየ፡፡ እኛንም ፦ ' ልጆቼ ሆይ እግዚአብሔር እስኪረዳን ድረስ ተቀመጡ ' አለን፡፡ እኔም በዚያ ትንሽ ተኛሁና በነቃሁ ጊዜ እኔና እርሱን በበኣታችን በር ፊት ቆመን አገኘሁት፡፡ እኔም 'ይህ ነገር እንዴት ሆነ? አልኩት፡፡ እርሱም ፦ 'ልጄ ሆይ ነቢዩ እንባቆምን ከይሁዳ ምድር ወስዶ  ባቢሎን ከነቢዩ ዳንኤል ዘንድ እንደ ዓይን ጥቅሻ አድርሶ እንደ ገና ወደ ቦታው የመለሰው እርሱ ነውና እግዚአብሔርን አመስግን ፤ እኛንም ከዚህ ያደረሰን እርሱ ነው' አለው፡፡ ❞

የአባታችን የቅዱስ መቃርዮስ ምልጃና ጸሎቱ አይለየን፡፡

ይቆየን !


†                       †                         †
💖                    🕊                     💖

ኦርቶዶክስ ሃይማኖታችን

23 Oct, 10:53


🕊                        💖                       🕊   

[   🕊  የሥነ-ሥዕል ዐውደ ርእይ   🕊   ]

    ▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬

       [           በእንተ ሉቃስ          ]

- ከጥቅምት ፲፯ - ፳፬ [ 17 - 24 ]


የላፍቶ ፥ ፈለገ ብርሃን : ቅድስት ሥላሴ እና ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት የአቅሌሲያ ሕፃናት ሥነ-ሥዕል ክፍል

            [       ተጋብዛችኋል !       ]

[ ሳሪስ 58 ኪዳነ ምሕረት ጠበል 100 ሜትር ገባ ብሎ ]


🕊                        💖                       🕊

ኦርቶዶክስ ሃይማኖታችን

22 Oct, 21:22


በነዚህ ዓመታት ሁሉ ይህ አካሉ የተለወጠ ሕጻን ቅዱስ ዘካርያስ መሆኑን ያወቀ የለም:: እንዲህ የቆሰለውም አሲድነት ካለው የጉድጉዋድ ውሃ ውስጥ ሰጥሞ ለ፵ [40] ቀናት በመጸለዩ ነው::

በመጨረሻ ግን አባቱ በምልክት ለይቶት አለቀሰ:: "ልጄ! አንተ ለእኔ አባቴ ነህ" ብሎታል:: አበው መነኮሳትም ተሰብስበው እጅ ነስተውታል:: በ፯ [7] ዓመቱ የመነነው አባ ዘካርያስ በ፶፪ [52] ዓመቱ በዚህች ቀን ዐርፎ በክብር ተቀብሯል::

አምላከ አፈ ወርቅ ዮሐንስ የድንግል እመ ብርሃንን ፍቅሯንና ውዳሴዋን ይግለጽልን:: ከአባቶቻችን ክብርና በረከትንም ያሳትፈን::

[  † ጥቅምት ፲፫ [ 13 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት   ]

፩. ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ
፪. አባ ዘካርያስ ገዳማዊ
፫. አባ ማርዳሪ ጻድቅ
፬. ቅዱስ አብጥማዎስ ሰማዕት

[    †  ወርኀዊ በዓላት    ]

፩. እግዚአብሔር አብ
፪. ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላዕክት
፫. ፺፩ "99ኙ" ነገደ መላዕክት
፬. ቅዱስ አስከናፍር
፭. ፲፫ "13ቱ" ግኁሳን አባቶች
፮. ቅዱስ አርሳንዮስ ጠቢብ ገዳማዊ
፯. አቡነ ዘርዐ ቡሩክ

" እናንተ የምድር ጨው ናችሁ . . . እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ:: በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሠወር አይቻላትም:: መብራትንም አብርተው በዕንቅብ በታች አይደለም እንጂ በመቅረዙ ላይ ያናሩታል:: በቤት ላሉት ሁሉም ያበራል:: መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ::" [ማቴ.፭፥፲፫-፲፮] (5:13-16)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖

ኦርቶዶክስ ሃይማኖታችን

22 Oct, 21:22


 🕊

✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞

❖ ጥቅምት ፲፫ [ 13 ] ❖

[  ✞ እንኩዋን ለዓለም ሁሉ መምሕር "ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ" እና ለአባ "ዘካርያስ ገዳማዊ" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞  ]

†   🕊  ዮሐንስ አፈ ወርቅ  🕊   †

ለቤተ ክርስቲያን የብርሃን ምሰሶ ስለሆነላት ስለ ታላቁ ሐዋርያዊ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ምን እላለሁ? ምንስ እናገራለሁ? እንደ እኔ ያለ ኃጥእ: ለባሴ ሥጋና ገባሬ ንስሃ ስለሱ ሊናገር አይቻለውምና:: አባቶቻችን እንደ ነገሩን ስለ አፈ ወርቅ ለመናገር "አፈ ወርቅ" መሆን ያስፈልጋል:: እስኪ በቅዱሱ አባት ምልጃ ጥቂት ልሞክር::

ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ማን ነው?

ነገዱ ከሶርያ: የተወለደው በ፫፻፵፯ [347] ዓ/ም በእስክንድርያ ሲሆን አባቱ አስፋኒዶስ እናቱ ደግሞ አትናስያ ይባላሉ:: እነርሱ ደግ ቢሆኑ ይህንን እንቁ ልጅ እግዚአብሔር ሰጣቸው:: ዮሐንስ ለክርስቲያን እንደሚገባ በትምሕርትና በጥበብ አደገ:: ገና በሕጻንነቱ ወደ ግሪክ ሔዶ የዘመኑን ሳይንስ [ፍልስፍና] ከአፉ እስከ ገደፉ ተምሮ ተመልሷል::

ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅን ለየት ከሚያደርጉት ነገሮችም አንዱ ይሔው ነው:: በዘመናዊም ሆነ በመንፈሳዊ ትምሕርት ይህ ቀረህ የማይሉት ሊቅ የሆነው ገና በ፲፭ [15] ዓመቱ ነበር:: በ፪ [2] ወገን የተሳለ ሰይፍ በመሆኑ ስንኩዋን በሕይወተ ሥጋ እያለ ዛሬም ለንፉቃን ትልቅ የራስ ምታት ነው::

ቅዱሱ ገና በ፲፮ [16] ዓመቱ ሃብት: ንብረት: ውበት: ክብርና እውቀት የሞላለት ቢሆንም ያለውን ሁሉ ለነዳያን ሰጥቶ መጻሕፍትን ብቻ ሰብስቦ ከባልንጀራው ቅዱስ ባስልዮስ ጋር በርሃ ገባ:: ሰውነቱን በጾምና በጸሎት እየቀጣ በበርሃ ሲኖር ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስና ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ዼጥሮስ ወደ እርሱ መጡ:: ሊቀ ሐዋርያት የመንግስተ ሰማያትን መክፈቻ ስልጣን ቅዱስ ዮሐንስ ደግሞ ወንጌሉን ሰጥተው ተሰወሩት::

ከዚህች እለት በሁዋላ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ባሕረ ምስጢራት ሆነ:: ብሉይ ከሐዲስ: ከኦሪት ዘፍጥረት እስከ ራዕየ ዮሐንስ ድረስ በአንድምታ ትርጉዋሜ ተነተናቸው:: በተለይ ሐዲስ ኪዳንን እየመላለሰ አመሰጠረው:: ቅዱስ ሕሊናው ሳይታክት: ንጹሕ እጆቹ ሳይዝሉ የጻፋቸው ድርሳናት: መልዕክታትና ትርጉዋሜያት ቢቆጠሩ አሥር ሺህ ሞሉ:: በእውነት ለዚህ አንክሮ ይገባል! የሚገርመው ይህን ሁሉ ሲሰራ እድሜው ገና ለጋ: ማዕርጉም ዲቁና ነበር::

ከዚህ በሁዋላ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ቅስና ተሹሞ በስብከተ ወንጌል ብዙ ቦታዎችን አዳረሰ:: በቅድስናው ወደውታልና የቁስጥንጥንያ ፓትርያርክ አድርገው ሾሙት:: አፈ ወርቅ ሲናገርም ሆነ ሲያስተምር እንኩዋን የሚያወራ ኮሽ የሚል የለም:: ከጣዕመ ትምሕርቱ የተነሳ ሕዝቡ በተደሞ ይሰሙት ነበር:: ሲያስተምር ምድራዊው ሰው ይቅርና ልዑላኑ መላእክት ተሰብስበው ያደንቁት ነበር:: አንዴም እመቤታችን በሕዝብ መካከል "አፈ ወርቅ" ብላ ጠርታዋለች:: ለዛም ነው "አፈ ወርቅ" የሚባለው:: ቅዱሱ በሥልጣነ ቃሉ መልዐከ ሞትን ገስፆ ፲ [10] ዓመት አቁሞታል::

ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ለሰው ፊት አያደላም:: በርሱ ዘንድ ንጉሥና ደሃ ነዳይ እኩል ነው:: ለሞት ያበቃውም ይሔው ነበር:: ምክንያቱም የወቅቱ ንግስት አውዶክስያ ያንዲት ድሃ መበለትን መሬት ቀምታ "አልመልስም" በማለቷ መክሮ አወገዛት:: እርሷ ግን ከኃጥአንና መናፍቃን ጋር መክራ 2 ጊዜ አጋዘችው:: በተሰደደበት ሃገር ፍሬ አፍርቶ: አስተምሮና አሳምኖ በ፬፻፯ [407] ዓ/ም አርፏል:: ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን ሳይጠግቡት እንደናፈቁት በ፷ [60] ዓመቱ አጡት:: በወቅቱ ታላቅ ሐዘንና ለቅሶ ተደረገ::

ከዕረፍቱ አስቀድሞ አንድ ቀን የዘመኑ ደግ ንጉሥ
አርቃድዮስ ግብር አገባ:: [ግብዣ አዘጋጀ]

በዚያች ሌሊት ደግሞ ቅዱሱ ሊቅ ታጥቆ ሲጸልይ ሳለ: አባ ማርዳሪ የሚባል ጻድቅ ደግሞ ከሰማይ ፲፪ [12] ቱ ሊቃነ መላእክት [እነ ቅዱስ ሚካኤል] ከሰማይ በግርማ ሲወርዱ ተመለከተ::

ደንግጦ "ወዴት ናችሁ ጌቶቼ" ቢላቸው "ቁስጥንጥንያ: ወደ ዮሐንስ አፈ ወርቅ እንሔዳለን:: እርሱ እመቤታችንን እንደሚያመሰግናት ጌታ ነግሮናልና" አሉት:: "እባካችሁ እኔም የአፈ ወርቅ ምስጋናው እንገለጥልኝ መርቁኝ" አላቸው:: ሊቃነ መላእክቱም መርቀውት ጐዳናቸውን ቀጠሉ::

በማግስቱ በቤተ መንግስት ውስጥ ሊቃውንቱ: መሳፍንቱ: ዻዻሳቱ: ሕዝቡ ሁሉ ተሰብስበው ከድግሱ በሉ:: ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ግን በመንበሩ ተቀምጦ ነበር እንጂ አልበላም:: ድግሱ ሲጠናቀቅ ንጉሡ አርቃድዮስ ሊቁን "ጥያቄ አለኝ" ብሎ በጉባኤ መካከል ጠየቀው::

"ምነው ወንጌላዊ ማቴዎስ 'ኢያዕመራ ዮሴፍ እስከ አመ ወለደት ወለደ ዘበኩራ-የበኩር ልጇን እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም' ማለቱ [ማቴ.፩፥፳፭] (1:25) ስለ ምን ነው?" ቢለው ቅዱሱ ተነስቶ: በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ይተረጉምለት ጀመር::

"ድንግል ማርያም ንጹሕ ብርሌን ትመስላለች:: ብርሌ የተለያየ ቀለም ያለው ፈሳሽ ቢያስገቡበት ቀለሙ አብሮ ይቀያየራል:: እመቤታችንም ጌታን ጸንሳለችና ሕብረ መለኮቱ ሲለዋወጥ መልኩዋ አብሮ ሲለዋወጥ እያየ ዮሴፍ ይደነግጥ ነበር::

'እርሷ ማን ናት? በማሕጸኗ ያለውስ ማን ነው?' እያለ ይጨነቅ ነበር:: ጌታን ከወለደች በሁዋላ ግን አንድ ሕብረ መልክ ሆናለችና:: አስቀድሞ ማን እንደ ነበረች አላወቀም::

አሁን ግን ልጇ አምላክ ዘበአማን: እርሷም ወላዲተ አምላክ መሆኗን አወቀ ማለት ነው" እያለ ሲተረጉም ሰምተው ሁሉም ሲያደንቁ በዚያ የነበረች ስዕለ አድኅኖ "አፈ ወርቅ! ልሳነ ወርቅ! አፈ በረከት!" ስትል ተናገረች::

ያን ጊዜ አርቃድዮስ የወርቅ ልሳን በሊቁና በስዕሏ ላይ አደረገ:: አፈ ወርቅ ግን ባጭር ታጥቆ "እሰግድ ለኪ! እሰግድ ለኪ! ወእዌድሰኪ . . ." ብሎ ዛሬ በተአምረ ማርያም የምናውቀውን ምስጋና ሰተት አድርጐ አደረሰላት:: ይህንን ምስጋናም ሊቃነ መላእክቱ ሰምተው እያደነቁ ወደ ሰማይ ወጥተዋል::

ቅዱሱ ሲጠራ እንዲሕ ነው :-

¤ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ
¤ አፈ በረከት
¤ አፈ መዐር [ማር]
¤ አፈ ሶከር [ስኩዋር]
¤ አፈ አፈው [ሽቱ]
¤ ልሳነ ወርቅ
¤ የዓለም ሁሉ መምሕር
¤ ርዕሰ ሊቃውንት
¤ ዓምደ ብርሃን [የብርሃን ምሰሶ]
¤ ሐዲስ ዳንኤል
¤ ሊቀ ዻዻሳት ዘበርትዕ [እውነተኛው]
¤ መምሕር ወመገስጽ ዘኢያደሉ ለገጽ
¤ ጥዑመ ቃል - - -


†  🕊  አባ ዘካርያስ ገዳማዊ  🕊  †

ይህ ታላቅ ጻድቅ ባለ ጥዑም ዜና ነው:: ወላጆቹ እሱንና አንዲት ሴትን ከወለዱ በሁዋላ አባቱ መንኖ ገዳም ገባ:: ከዘመናት በሁዋላ ረሃብ በሃገሩ ሲገባ እናቱ ወስዳ ለአባቱ ሰጠችው:: ይህን ጊዜ ዕድሜው ፯ [7] ዓመት ነበር::

በገዳም ከአባቱ ጋር ሲኖር ከመልኩ ማማር የተነሳ አባቶች መነኮሳት "ይህ ልጅ ይህን መልክ ይዞ እንዴት መናኝ መሆን ይችላል!" ሲሉ ሰማ:: በሌሊትም ተነስቶ በሕጻን አንደበቱ "ጌታየ! መልኬ ካንተ ፍቅር ከሚለየኝ መልኬን አጠፋዋለሁ" አለ:: ከገዳሙም ጠፋ::

አባትም በጣም አዘነ:: ከ፵ [40] ቀናት በሁዋላ ግን ሊያዩት የሚያሰቅቅ: አካሉ ሁሉ የቆሳሰለ አንድ ነዳይ ሕጻን መጥቶ ወደ ገዳሙ ተጠጋ:: ይህ ሕጻን በጾም: በጸሎትና በትሕትና ተጠምዶ ለ፵፭ [45] ዓመታት አገለገለ::