ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

@tonetore


ኢትዮጵያ በጥንት ግብጻውያን ቋንቋ ቶኔቶር፣ጵንጥ፣የኩሽ ሀገረ እየተባለች ትጠራለች።ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር ማለት ነው።በሌሎች ሀገሮች ስነ ጽሑፍ ኢትዮጵያና አቢሲኒያ በማለት ተገልጻለች።በቻናሉ መንፈሳዊ ትምህርቶች ወደ እናንተ ይደርሳሉ። እግዚአብሔር አምላካችን ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያን ከነጣቂው ተኩላ ይጠብቅልን።ድንግል ሆይ የአስራት ሀገርሽን ኢትዮጵያን ጠብቂያት።
ለሌሎችም ያጋሩ 👉 @tonetore

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

22 Jun, 19:26


ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር pinned «ሥርዓተ ማኅሌት ዘበዓለ ጰራቅሊጦስ በቅድሚያ ፲፭ቱን ነቢያት ይደገማል። ይ.ካ አቡነ ዘበሰማያት። አያይዞ ሰላም ለኪ በዜማ ይባላል። መሪና ተመሪ ተሰመይኪ ፍቅርተ እየተቀባበሉ ይበሉ። በኅብረት ወበእንተዝ ይበሉ። ተመሪ ለብቻው ታቦትን ይበል። ከመቅደስ እስከ በትረ አሮን ይታደላል። ለኪ ይደሉን መሪ ለብቻው በዜማ ይበል። ወበእንተዝን በኅበረት ይዘመማል። ቀጥሎ ተፈሥሒ ማርያም ለአዳም ፋሲካሁ…»

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

22 Jun, 19:25


ሥርዓተ ማኅሌት ዘበዓለ ጰራቅሊጦስ

በቅድሚያ ፲፭ቱን ነቢያት ይደገማል።
ይ.ካ አቡነ ዘበሰማያት።
አያይዞ ሰላም ለኪ በዜማ ይባላል።
መሪና ተመሪ ተሰመይኪ ፍቅርተ እየተቀባበሉ ይበሉ።
በኅብረት ወበእንተዝ ይበሉ።
ተመሪ ለብቻው ታቦትን ይበል።
ከመቅደስ እስከ በትረ አሮን ይታደላል።
ለኪ ይደሉን መሪ ለብቻው በዜማ ይበል።
ወበእንተዝን በኅበረት ይዘመማል።
ቀጥሎ ተፈሥሒ ማርያም ለአዳም ፋሲካሁ ይባላል።
መልክአ ሥዕል ይከተላል።
ከተአምር ቀጥሎ ምስባክ ይባላል።

ምስባክ

ወተንሥአ እግዚአብሔር ከመ ዘንቃሕ እምንዋም፤
ወከመ ኃያል ወኅዳገ ወይን፤
ወቀተለ ፀሮ በድኅሬሁ። (መዝ. ፸፯ : ፷፭)

ከምስባክ ቀጥሎ ሦስት ወንጌል  ማቴዎስን ማርቆስንና ሉቃስ ይነበባል። ዮሐንስን ለቅዳሴ ይቆያል

አርያም

ሃሌ ሉያ ለአብ፤ ሃሌ ሉያ ለወልድ፤ ሃሌ ሉያ ወለመንፈስ ቅዱስ፤
ቀዳሚ ዜማ ግበሩ በዓለ በትፍሥሕት፤
እስከ አቅርንቲሁ ለምሥዋዕ፤
ዛቲ ፋሲካ ቀዳሚት ሕግ።
ይህንን በመሪ በኩል ይዘመማል፣ በአንሽ በኩል ያለምራት ሁለተኛው አርያም ይዘመማል

አርያም

ሃሌ ሉያ ለአብ፤ ሃሌ ሉያ ለወልድ፤ ሃሌ ሃሌ ሉያ ወለመንፈስ ቅዱስ፤ ይገብሩ በዓለ ሰማያት፤
ይገብሩ በዓለ ደመናት፤
ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ፤
ተሐጺባ በደመ ክርስቶስ።

ምልጣን

ዮም ፍሥሐ ኮነ በሰንበተ ክርስቲያን፤
እስመ ተንሥአ ክርስቶስ እሙታን፤
ቀደሳ ወአክበራ እምኲሎን መዋዕል አልዓላ፤
አማን፤ ተንሥአ እምነ ሙታን።

አመላለስ

"አማን በአማን"/፪/ ተንሥአ
"አማን በአማን"/፪//፩/
ተንሥአ እምነ ሙታን/፬/

ወረብ

ዮም ፍሥሐ ኮነ ሰንበተ ክርስቲያን
እስመ ተንሥአ ክርስቶስ እሙታን/፪/
"ቀደሳ ወአክበራ"/፪/ ወአልዓላ እምኲሎን መዋዕል/፪/

የምልጣኑን ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ እስመ ለዓለም

እስመ ለዓለም

ትንሣኤከ ለእለ አመነ፤
ብርሃነከ ፈኑ ዲቤነ።

አመላለስ ትንሣኤከ ለእለ አመነ/፪/
ፈኑ ዲቤነ ብርሃነከ ፈኑ ዲቤነ/፪/
አያይዘህ የኪዳን ሰላም (ይእቲ ማርያም)

በዚያ ኪዳን ይቀጥላል...
ከኪዳን ቀጥሎ መዝሙር

መዝሙር

ሃሌ ሉያ ይትፌሣሕ ሰማይ ወትትኃሠይ ምድር፤
ወይንፍሑ ቀርነ መሠረታተ ሕምዝ፤
ወይበውኡ አድባር ወአውግር፤
ወኲሉ ዕፀወ ገዳም፤
ወዮምሰ ዓባይ ፍሥሃ በሰማያት፤
ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ፤
ተሐጺባ በደመ ክርስቶስ።

አመላለስ

ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ/፪/
ተሐጺባ በደመ ክርስቶስ/፬/

ሰላም

ፍጹመ ንጉሠ ኮነንዎ አይሁድ፤
ተካፈሉ አልባሲሁ ሐራ ሰገራት፤
ወኮርዕዎ ርእሶ በኅለት፤
ረገዝዎ ገቦሁ በኲናት፤
ትንሣኤሁ ገብረ በሰንበት፤
ሰላመ ይጸጉ ለነገሥት ለአሕዛብ ወለበሐውርት።

መልካም በዓል
👉 @tonetore

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

16 Mar, 13:03


ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር pinned «በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!! የተወደዳችሁ እና የተከበራችሁ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች! በእግዚአብሔር ፍጹም ሰላም እንደምን ሰነበታችሁ? እኔ በቅዱሳኑ ጸሎት እና ቅድስና የባሕርይ ገንዘቡ በሆነው በእግዚአብሔር ቸርነት ይኸው ዛሬን ደርሻለሁ። ዛሬ መድረስ ከሱቅ የሚገዛ የሸቀጥ ዕቃ አይደለም። ዛሬ መድረስ ከመንግሥት መሥሪያ ቤት በስጦታ መጠቅለያ ላስቲክ ታሽጎ የሚሰጥ…»

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

16 Mar, 13:03


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

የተወደዳችሁ እና የተከበራችሁ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች!

በእግዚአብሔር ፍጹም ሰላም እንደምን ሰነበታችሁ?

እኔ በቅዱሳኑ ጸሎት እና ቅድስና የባሕርይ ገንዘቡ በሆነው በእግዚአብሔር ቸርነት ይኸው ዛሬን ደርሻለሁ።

ዛሬ መድረስ ከሱቅ የሚገዛ የሸቀጥ ዕቃ አይደለም።

ዛሬ መድረስ ከመንግሥት መሥሪያ ቤት በስጦታ መጠቅለያ ላስቲክ ታሽጎ የሚሰጥ የስጦታ ዕቃም አይደለም።

ዛሬ መድረስ ከቤተሰብ በውርስ የሚገኝ የውርስ ገንዘብም አይደለም።

ዛሬ መድረስ ከእግዚአብሔር ብቻ የምናገኘው ልዩ ስጦታ ነው።

ስለዚህ አይታለፉም በተባሉ በሞት በተከበቡ ዘመናት ውስጥ አልፈን በሕይወት ዛሬ የመድረሳችን ምሥጢር የእግዚአብሔር የቸርነቱ ምልክት ማሳያ ነው።

በአባታዊ ፍቅሩ እየወደደን፤
በቸርነቱ ብዛት እየጠብቀን ዛሬን ያደረሰን እግዚአብሔር ምስጋና ለስሙ ይሁን!

አሜን!!!

እንግዲህ ይህንን ያህል በእግዚአብሔር በቸርነቱ ብዛት ተጠብቀን ዛሬ ከደረስን ዛሬ ያደረሰንን እግዚአብሔርን እያመሰገንን ለነገው ሕይወታችን ስንቅ የሚሆነውን የእግዚአብሔርን ቅዱስ ቃል ደግሞ አሁን ለጥቂት ደቂቃ በጋራ እንማማራለን።

የትምህርታችን ርዕስ፦
“ለርኵሰት ሳይሆን እግዚአብሔር በቅድስና ጠርቶናል።”
የሚል ነው።
1ተሰ.4፥7

እንደሚታወቀው የዐቢይ ጾም ፪ተኛው ሳምንት "ቅድስት" ይባላል።

የስሙ ስያሜ የቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ ከሆነው ከቅዱስ ያሬድ የተገኘ ነው።

በዚህ ወቅት ቤተ ክርስቲያን
በሥርዓተ አምልኮዋ፤
በሥርዓተ ቅዳሴዋ፤
በመዝሙሯና
በስብከቷ ሁሉ ስለ ቅድስና በሰፊው ታስተምራለች።

በቅዳሴ ላይ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች፦
፩ኛ=በገባሬ ሠናይ ዲያቆን 1ተሰ.4፥1-13
፪ኛ=በንፍቅ ዲያቆን 1ጴጥ.1፥13-ፍ.ም.
፫ኛ=በንፍቅ ካህን
ሐዋ.10፥7-30

ምስባክ፦
"እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ
አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ
ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ።"
የሚል ሲሆን ትርጉሙም፦
"እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ።
ምስጋናና ውበት በፊቱ፥
ቅዱስነትና ግርማ በመቅደሱ ውስጥ ናቸው።"
ማለት ነው።
መዝ..95(96)፥5

በምሥጢራዊ ትርጉም ሲፈታ ደግሞ፦
"እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ"
እግዚአብሔር ምን ሠራ ትለኝ እንደ ሆነ እግዚአብሔርስ እርሱ እግዚአብሔር ስለሆነ ሰባቱን ሰማያት ሠራ።

"አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ"
እምነትና መልካም ምግባር ያለውን ሰው ይወድዳል።

"ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ"
ቅዱስ ቅዱስ ተብሎ መመስገንም የባሕሪይ ገንዘቡ ነው።
የሚል ትርጉም አለው።

በዚህ እለት የሚነበበው የወንጌል ክፍልም
ማቴ.6፥16-25 ሲሆን፦

በዛሬው እለት የሚቀደሰው ቅዳሴ ደግሞ ካሉት 14 ቅዳሴያት መካከል "ቅዳሴ ኤጲፋንዮስ" ነው።

አሁን መጀመሪያ ወደ አነሣነው ርዕሰ ጉዳይ ስንመለስ፤

የትምህርታችን ርዕስ፦
“ለርኵሰት ሳይሆን እግዚአብሔር በቅድስና ጠርቶናል።”
የሚል ነው።
1ተሰ.4፥7

እዚህ ላይ ስለ ቅድስና ስናነሣ፤
"ቅድስና" የእግዚአብሔር የባሕሪይ ገንዘቡ ነው።
"አንተ ብቻ ቅዱስ ነህ" ተብሎ የሚዘመርለት እንደ እርሱ ያለ ቅዱስ የትም የለምና።
ራእ.15፥3-4

“አቤቱ፥ በአማልክት መካከል እንደ አንተ ያለ ማን ነው?
በምስጋና የተፈራህ፥
ድንቅንም የምታደርግ፥
በቅድስና የከበረ እንዳንተ ያለ ማን ነው?” ተብሎ እንደ ተጻፈ።
ዘጸ.15፥11

የቅዱሳኑ "ቅድስና" ከእግዚአብሔር በስጦታ ይሰጣቸዋል።

እግዚአብሔር ግን በባሕሪዩ ለዘላለም ቅዱስ ነው።

በመሆኑም ሰማያውያን መላእክት፦
“ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፤
ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች"
እያሉ ያለማቋረጥ ቀን እና ሌሊት ያመሰግኑታል።
ኢሳ.6፥3

ስለዚህ፦
“እተካከለው ዘንድ በማን መሰላችሁኝ? ይላል ቅዱሱ።”
ኢሳ.40፥25

እንግዲያውስ ኑ!
እኛም ከቅድስት ሐና ጋር፦
እንደ እግዚአብሔር ያለ ቅዱስ የለም፥
እንደ አምላካችንም ያለ ጻድቅ የለም፤
እያልን እንዘምርለት!
1ሳሙ.2፥2

ስለ እግዚአብሔር የባሕሪይ ቅድስና ከመጽሐፍ ቅዱስ ብዙውን መመልከት እንችላለን።
ኢሳ.57፥15
ሕዝ.36፥20-21
ሉቃ.1፥50
ኢሳ.6፥3
ራእ.4፥8

እንግዲህ ይህ በባሕሪዩ ቅዱስ የሆነው እግዚአብሔር፦

"እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝና፤ ሰውነታችሁን ቀድሱ፥
ቅዱሳንም ሁኑ፥
እኔ ቅዱስ ነኝና፤
በምድርም ላይ በሚሳብ ተንቀሳቃሽ ሁሉ ሰውነታችሁን አታርክሱ።
እኔ አምላካችሁ እሆን ዘንድ ከግብፅ ምድር ያወጣኋችሁ እግዚአብሔር ነኝ፤ እንግዲህ እኔ ቅዱስ ነኝና እናንተ ቅዱሳን ሁኑ!" ይለናል።
ዘሌ.11፥44-45

እርሱ አባታችን ነው፤
እኛም ልጆቹ ነን፤
ስለዚህ ልጆች በአባታቸው ሊወጡ ስለሚገባ አባታችን እግዚአብሔር እርሱ በባሕሪዩ ቅዱስ እንደ ሆነ እኛም ደግሞ በኑሮአችን ቅዱሳን ልንሆን ይገባል።

ምክንያቱም መጠራታችንም በቅድስና ለቅድስና ነው እና።
1ተሰ.4፥7

ስለዚህ በቅድስና መኖር ያልቻለ ሰው ከተጠራለት ዓላማ ውጪ ሆኖአል ማለት ነው።

በቅድስና መኖር ሲባል ግን ምን ማለት ነው???

እንደ ዘካርያስና እንደ ኤልሣቤጥ የእግዚአብሔርን ትዕዛዝና ሕግጋት
እየፈጸሙ በእግዚአብሔር ፊት ጽድቅን ጠብቆ መኖር።
ሉቃ.1፥6

በተረገመ ትውልድ ውስጥ እንኳ እንደ ኖኅ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቅ ሆኖ መገኘት።
ዘፍ.7፥1

ከአፍ ወደ ውጭ የሚወጣው ክፉ ንግግር ሰውን ያረክሳልና ክፉ ከመናገር መቆጠብ።
ማቴ.15፥18
ኤፌ.4፥29
1ሳሙ.2፥3

ከሕሊና ውስጥ ክፉ አሳብን ማስወገድ።

በልብ ውስጥም ቂምን አለመቋጠር።

በጠቅላላው በቅድስና መኖር ማለት የራስን ምኞት ትቶ እንደ እግዚአብሔር ሐሳብና ፈቃድ መኖር ማለት ነው።

ርኩሰት ግን የሥጋ ሥራ ነው።
እርሱም፦
👉ዝሙት፥
👉ርኵሰት፥
👉መዳራት፥
👉ጣዖትን ማምለክ፥
👉ምዋርት፥
👉ጥል፥
👉ክርክር፥
👉ቅንዓት፥
👉ቁጣ፥
👉አድመኛነት፥
👉መለያየት፥
👉መናፍቅነት፥
👉ምቀኝነት፥
👉መግደል፥
👉ስካር፥
👉ዘፋኝነት፥ ይህንም የሚመስል ነው። እንደዚህ ያሉትን የርኩሰት ሥራ የሚሠሩ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም ተበሎ በግልጥ ተጽፎልናል።
ገላትያ 5፥19-21

ኑ!
ቅዱስ እግዚአብሔር በቅድስና እንድንኖር ጠርቶናልና ሀጢአትን ሁሉ ትተን በቅድስና ጎዳና ላይ እንመላለስ!

ለቅድስና ተጠርታችሁ አትርከሱ!

ለዝማሬ ተጠርታችሁ ዘፋኞች አትሁኑ!

ለፍቅር ተጠርታችሁ በጥላቻ አትመላለሱ!

ለዕርቅ ተጠርታችሁ ቂመኞች አትሁኑ!

ለሕይወት ተጠርታችሁ ለሞት እጅ አትስጡ!

በብርሃ ተጠርታችሁ ወደ ጨለማ አትሂዱ!

ለክብር ተጠርታችሁ ለውርደት አትሁኑ!

ደግሞም ይህንን ምክር የሚጥል ሰውን የጣለ አይደለም፥
መንፈስ ቅዱስን በእናንተ እንዲኖር የሰጠውን እግዚአብሔርን ነው እንጂ።
1ኛ ተሰ.4፥8

ስለዚህ "እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለ ተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ።”
1ጴጥ.1፥15-16
╭✥✥✥✥✥✥✥✥✥╮
✥┈┈••●◉✞◉●••┈••✥
. አባ ኒቆዲሞስ (ጳጳስ)
. 07/07/2016 ዓ.ም
. ከሕይወት ተራራ ላይ
✥┈┈••●◉✞◉●••┈┈✥
╰✥✥✥✥✥✥✥✥✥╯

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

24 Feb, 16:56


የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የጾመ ነነዌ መልዕክት
++++++++++++++++++++++++++++++++++
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
'ተንሥእ ወሑር ኅበ ነነዌ ሀገር ዐባይ - ተነሥተህ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ"
ዮና ፩;፪
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ወኤጲስ ቆጶሳት፤
መንፈሳዊ ተልእኮ ተቀብላችሁ በየተሰጣችሁ ጸጋ በተለያየ ስፍራ ሆናችሁ የምታገለግለ‐ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤
በመንፈስ ቅዱስ ልደት የከበራችሁ ምእመናን ወምእመናት ልጆቻችን በሙሉ፤ ዘመንን በዘመን እየተካ፣ መዓቱን በምሕረት እየመለሰ የሚያኖረን እግዚአብሔር እንኳን ለ2016 ዓ.ም ጾመ ነነዌ አደረሰን አደረሳችሁ ለማለት እንወዳለን፡፡

በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበሩት የሰው ልጆች በኃጢአት በወደቁ ጊዜ እግዚአብሔር አምላክ የሁሉ አባት በመሆኑ ተወልዶ ብልጫ የለም" እንዲሉ ከእስራኤል ውጭ ወዳለችው ነነዌ ነቢዩ ዮናስንና ነቢዩ ናሆምን ልኳል። በበደል ውስጥ ሆነው ቢጾሙም ሆነ ቢጸልዩ ጸሎቱ ድል የሚነሣ መሥዋዕቱም የሚያስምር አይሆንምና፡ ንስሐም ለድሀና አቅም ለሌለው የሚሰበክ ሳይሆን ከሊቅ እስከ ደቂቅ ያደፈ ሁሉ የሚጠራበት የሕይወት መስታወት ነውና የሕይወት ትንሣኤ በሆነው ንስሐ ነነዌን ለማንሣት ዮናስ ወደ ንጉሡና ወደ ሠራዊቱ የንስሐ ሰባኪ ሁኖ ተልኳል።

ነነዌ ከተማዋ አድጎ፡ ልማቷ ቢሰለጥንም እግዚአብሔር ግን የተመለከታት ፈርሳና ተበላሽታ ነበር፡፡ በፈረሰ ልብ የሚገነቡ ከተሞች የቀን ጉዳይ እንጂ ፍርስራሽ መሆናቸው አይቀሬ ስለሆነ ዛሬ ነነዌ ከታሪክ መዝገብ ላይ ብትሰፍርም በዓይን ግን የምትታይ አይደለችም። ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የነነዌን ጾም ያወጀችው ዓመት ሙሉ የተጣላ በነዚህ ሦስት ቀናት እንዲታረቅ፣ ሲካሰስ የሚኖር ሕዝብም ወደፈጣሪው በንስሐ እንዲመለስ ነው።

እግዚአብሔር አምላክ ነቢዩን ወደ ነነዌ ሲልከው፡- “ተነሥተህ ሂድ" ማለቱ በበደል የሳተን በሩቅ ሆኖ መተቸት መንፈሳዊ ተልእኮ ባለመሆኑ ተነሥተን ብንሄድ፣ መንገድ አጋምሰን ወገኖቻችንን ብንፈልግ ሁሉንም ለንስሐ ማብቃት እንደምንችል ሲያስተምረን ነው፡፡ ለመነሣት ስንፍናንና ፍርሃትን ድል መንሣት ያስፈልጋል። ለይቅርታ ስንነሣ ትዕቢትን እናሸንፋለን። ፉክክርን እናርቃለን። ለጋራ ሀገራችን የጋራ መፍትሔ፡ ለጋራ ቤተ ክርስቲያናችን የጋራ መድኃኒትን እናገኛለን።

በሌላ በኩል አምላካችን እግዚአብሔር በደለኛይቱን ከተማ ታላቂቱ ከተማ በማለት ሲጠራት ሕዝቡንም ግራና ቀኙን የማያውቅ በማለት ራርቷል። እግዚአብሔር አምላክ አክባሪ፤ አዛኝ፡ በደለኛውንም በክብር እንጂ በውርደት የማይጠራ አምላክ ነው። እኛም ይህንን የነነዌን ጾም ስንጾም በአንድ በኩል እንጀራን የተራቡ፣ በሌላ በኩል ሰላም የተራቡ ወገኖች ስለአሉን ወደ እነዚህ ወገኖች የንስሐን ስብከት፣ የማጽናናትን መልእክት ይዘን መሄድ አለብን። በተጨማሪም ከቀዬአቸው የተፈናቀሉትን፡ በረሃብ፣ በመታረዝ፣ በጦርነት ውስጥ የሚገኙ ወገኖቻችንን የመከራ ማቅ በሕሊናችን ተሸክመን ስለጸሙ የተውነው የዕለት ቊርሳችንን ለእነርሱ ሞትን ማባረሪያ እንዲሆን ልንፈቅድ ያስፈልጋል።

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን!

ይህንን የነነዌ ጾም ልንቀበል ዋዜማ ላይ ባለንበት በዚህ ጊዜ በቤተክርስቲያናችን ጥንታዊ ከሆኑት ገዳማት አንዱ በሆነው በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም የሚገኙ፣ ዓለሙን ትተው በፈቃዳቸው ረሀብተኛ እና ጥማተኛ ሆነው ሀገርን በጸሎት የሚጠብቁ መነኮሳት ጫካው መኖሪያችሁ፣ ዳዋው ልብሳችሁ፤ ቅጠሉ ምግባችሁ መሆን አይችልም ተብለው የሰማዕትነትን ጽዋ ተጎንጭተዋል፡፡ እነርሱ በሥጋ እየሞቱ እኛም በየቀኑ ሟቾችን እየቆጠርን በኀዘን ለመኖር የተፈረደብን ሆነናል፡፡
ይህ ለእነርሱ ክብር ቢሆንም ለቤተክርስቲያን ግን ታላቅ ደወል ያሰማ ክስተት ነውና ውሉደ ክህነት ቤተክርስቲያናችሁን የምትጠብቁበት፣ የመከራውን ማዕበል ለማለፍ በመንፈሳዊ ፍቅር አንድነትን ማጽናት የሚያስፈልግበት ጊዜ መሆኑን እናሳስባለን፡፡

በመጨረሻም ታላቅ ሀገር ይዘን፣ ምድሩ ሳይጠበን አመል እያጋፋን ነውና ጸማችን፣ ጸሎታችን ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶ ለሀገር ደኅንነት፡ ለሕዝብ ድኅነት እንዲያመጣልን፡

እግዚአብሔር ይቅር ብሎን ዘመኑን በምሕረት ያሻግረን ዘንድ በታላቅ ንስሐ፣ በጸሎትና በአስተብቍዖት ወደ እግዚአብሔር እንድንቀርብ አባታዊ መልእክታችንን በመሐሪው አምላክ ስም እናስተላልፋለን።

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ || ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!! አሜን።

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

አዲስ አበባ፡ ኢትዮጵያ
የካቲት 16 ቀን 2016 ዓ.ም

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

24 Feb, 06:58


"ቃለ እግዚአብሔር እምድንግል አስተርአየ ፤ ኤልሳቤጥ ኮነት ዓባየ ፤ እስመ ወለደት ነቢየ።" ቅዱስ ያሬድ

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መታሰቢያዋን ለሚያደርግ ስሟን ለሚጠራ በስሟ ለድኆችና ለችግረኞች ቀዝቃዛ ውኃ ለሚሰጥ የክብር ባለቤት ከሆነ ከተወደደ ልጅዋ ከጌታችንና ከመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምሕረት ቃል ኪዳንን የተቀበለችበት በዓል ነው።

ዳግመኛም በዚህች ዕለት የመጥምቁ ዮሐንስ እናት የከበረች ኤልሳቤጥ ዐረፈች።

የእመቤታችን ጣዕሟን ፍቅሯን ያሳድርብን፤ የቅድስት ኤልሳቤጥ በረከት ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይኑር። አሜን

እንኳን አደረሰን አደረሳችሁ

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይባርክ !
ብጹዕ አቡነ ሄኖክ
👉 @tonetore

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

23 Feb, 08:29


ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር pinned «ቅዱስ አቡነ ሰላማ የማያውቁት "የሰላማ መንበር" [በመ/ር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል] #ክፍል_1 ፩) መግቢያ እና ትርጉም የቤተ ክርስቲያን መንበር ሐዋርያዊ ነው። ሐዋርያዊ መንበር ጌታችን አስተምሮ ከሾማቸው ከዐሥራ ሥያሜ የወጣ አይደለም፣ ሥልጣነ ክህነት የሚተላለፍበት፣ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ትምህርተ ሃይማኖት እና ቀኖና ምንጩ ወይም ሥሩ የሚነገርበት የሐዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን አማናዊና ሐዋርያዊ…»

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

23 Feb, 08:18


ሕንዳዊው ብፁዕ ዶ/ር ር ግ ሪርየስ የጻፉትን መሠረት አድርገው ብፁዕ ዖር ዘካርያስ ሰር ኤፍሬም እንዳት፤ መንበርን ከምድር እስከሰማይ ስቶርያት የሰጣቸው ጌታችን ነው - ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፡፡ እውነት እላችኃለሁ እናንተስ የተከተላችሁኝ በዳግመኛ ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በሚቀመጥበት ጊዜ እናንተ ደግሞ በአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገድ ልትፈርዱ በአሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ። ማቴ ፲፱፥፳፰ የሚገርማችሁ መንበርን ለሐዋርያት ሲሰጥ ለይሁዳም ሰጥቶት ነበር፤ ነገር ግን ይሁዳ ሥልጣኑን ስለናቃት፤ መጠራቱን ለምድራዊ ሥራና ቁሳዊ ፍላጎት ስለሸጠ፣ ጌታውን ክዶ ለሰዎች ፍላጎት ስለተንበረከከ መንበሩ ለሌላ ተሰጠች ብሏል፡፡ በርግጥም የይሁዳ ከሐዋርያዊ ጥሪው እና ከተሰጠው መንበር ተዋረደ ለሰማያዊ ሥልጣን ተጠርቶ ምድራዊ፤ ለመንፈሳዊ ክብር ተጠርቶ ቁሳዊ ስለሆነ በምትኩ ማትያስ ተመረጠ፡፡ እሱ ጎደለ እንጅ መንበረ ሐዋርያት አልጎደለም፡፡

ሐዋርያት ያስተማሩት ከጌታችን የተማሩትን ነው፤ የሐዋርያት ተከታዮች የሆኑ ጳጳሳት የሐዋርያትን ትምህርት ለመጠበቅ ሲሉ ሐዋርያት ባስተማሩባቸውና ሐዋርያት በመሠረቷቸው ቦታዎች መናብርትን መሠረቱ፤ መናብርቱ ግጭትና ጭቅጭቅ ለማስነሣት፣ በአንድ ቦታ ተወስኖ ለመቆየት የእኔ እኔ ለመባባል ወይም ልዩነት ለመፍጠር የተቋቋሙ ሳይሆን ትምህርተ ሐዋርያትን ለማስፋፋት እና ለመጠበቅ የተመሠረቱ ናቸው፡፡ መናብርቱ የተመሠረቱበት ዋና ምክንያት ለክፍፍል እና ለልዩነት፣ ወይም ለምድራዊ ዓላማ ሳይሆን ማንም እየተነሣ የራሱ መሠረት እንዳይፈጥር፣ አስተዳደራዊ ማእከላትን ለመፍጠር፤ የሥልጣነ ክህነትን ደረጃ ለመወሰን፣ አገልግሎትን ለማሳለጥ፣ ለወንጌልና ለትምህርተ ሐዋርያት መስፋፋት ሲሆን መናብርቱን ለማቋቋም እንደመሥፈርት የተወሰደው የዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት መቅድመ ትምህርት፤ መሥዋዕትነት፣ ተልእኮና ሥምሪት እንጂ ዘርን፣ ጎሣን፣ ፖለቲካዊ አቋምን መሠረት ያደረገ አይደለም፡፡ መናብርት ለአብያት ክርስቲያናት አንድነት፡' የተበታተነውን አንድ ለማድረግ ሥልታዊ መዋቅር ለመዘርጋት፣ ለወንጌል መስፋፋት እና ለቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ለትውፊት መጠበቅ አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ
ነው፡፡

እዚህ ላይ በትልቅ አጽንዖት ማየት የሚያስፈልገው የመናብርቱ ምሥረታ ከፖለቲካ ወይም ከመንግሥት መዋቅር ጋር ግንኙነት አልነበረውም፤ ክርስትና እንኳንስ በሮም መንግሥታት መዋቅር ልታቋቍም ይቅርና እንዲያውም በሮማውያን የምትሳደድ ነረች፡፡ የቤተ ክርስቲያን መዋቅር የራስዋን ሐዋርያዊ ተልእኮ መሠረት ያደረገ፣ ሁሉንም የዓለም ሕዝብ በቋንቋው፣ በባህሉ ሳትከፍል በአንድነት ለማዳረስ የተፈጸመ ነው፡፡ ነገር ግን የፖለቲካ መዋቅርን በተከተለችበት ጊዜ ሁሉ የገጠማት ችግር እና ስደት ነው።

፪) መንበር ያለ "ፓትርያርክ" እና ያለ "ሲኖዶስ"

#ይቀጥላል --->

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

23 Feb, 08:18


ቅዱስ አቡነ ሰላማ የማያውቁት "የሰላማ መንበር"

[በመ/ር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል]

#ክፍል_1

፩) መግቢያ እና ትርጉም

የቤተ ክርስቲያን መንበር ሐዋርያዊ ነው። ሐዋርያዊ መንበር ጌታችን አስተምሮ ከሾማቸው ከዐሥራ ሥያሜ የወጣ አይደለም፣ ሥልጣነ ክህነት የሚተላለፍበት፣ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ትምህርተ ሃይማኖት እና ቀኖና ምንጩ ወይም ሥሩ የሚነገርበት የሐዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን አማናዊና ሐዋርያዊ ታሪክ፣ ሃይማኖታዊና ቀኖናዊ ትውፊት የሚጀመርበት መነሻ ነው፡፡ መንበር ሥርወ ክህነት፣ ሥርወ ሃይማኖት፣ ሥርወ ቀኖና/ትውፊት ነው፡፡ በየትኛውም ዓለም ያሉ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት መንበራቸው ከሐዋርያት የሚወረስ ነው፡፡ የመንበራቸውም ሥያሜ በራሳቸው ያገኙት ወይም ራሳቸው እንደ ፈለጉት የለጠፉት ሳይሆን ኦርቶዶክሳዊ ትውፊትን፣ ታሪክን እና ቀኖናን መሠረት ያደረገ የሌሎች ቤተሰብ የሆኑ አብያተ ክርስቲያናትን መስማማት የሚጠይቅ፣ ዓለማዊ የሆኑ የፖለቲካ፣ የጎሣ፣ የኢኮኖሚ፣ የባህል ሙያዎችን መሠረት ያላደረገ ነው፡፡

በብሉይ ኪዳን ነቢዩ ሙሴ የሕገ ኦሪት መንበር ተሠይሞለታል! ስለዚህ ጌታችን (በማቴ.፳፫፥፪) “ጻፎችና ፈሪሳውያን በሙሴ መንበር ተቀምጠዋል” በማለት የኦሪት ሕግ መንበር የሙሴ መሆኑን ገልጧል፡፡ ምክንያቱም ነቢዩ ሙሴ የተጻፈ ሕግን የተቀበለ የመጀመሪያው ሰው ስለሆነ ነው፡፡ መምህራንም ሲናገሩ እስራኤል ኣብርሃምን በእምነት መሠረት፣ ሙሴን በሕግ መሠረት፣ አሮንን በሥርወ ክህነተ ኦሪት፣ ዳዊትን በሥርወ መንግሥት ይተረጕማል፡፡ እዚህ ላይ ልብ ማለት የሚገባው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ ከነገሥታትም ከካህናትም ትወለዳለች ሲባል የእርስዋ እናትና አባት በዘመናቸው ንጉሥና ካህን ናቸው ለማለት ሳይሆን ከሥርወ መንግሥት ከዳዊትና ከሥርወ ክህነት ዘኦሪት ከአሮን ሐረገ ትውልድ ስለምትገኝ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በመቅድመ ተአምረ ማርያም ላይ “ሥርወ ልደታ ለእግዝእትነ እምቤተ ዳዊት ንጉሥ መንገለ አቡሃ ወእም ቤተ አሮን ካህን መንገለ እማ” እንዲል፡፡

ክርስትና በራስዋ መሠረት ላይ የቆመች፣ የራስዋ ትውፊት ያላት በዓለማዊ ተለዋዋጭ የፖለቲካ እና የማኅበራዊ አስተሳሰብ ክስተቶች የማትወሰን፤ በዓለማዊ ወጀብ የማትናወጥ “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ አንተ አለት ነህ በአንተ ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ” ባለው መሠረት በሐዋርያዊ አለት (ኰኩሕ) ላይ የቆመች በመሆኗ ሥርዋም፣ ግንዷም ቅርንጫፎቿም፣ ፍሬዎቿም የራስዋ ናቸው፡፡ (ማቴ.፲፮፥፲፱) በመሆኑም የሐዋርያት መሠረተ እምነትና የትምህርት ሥምሪት የዓለምን መንገድ የተከተለ ሳይሆን የራስዋን ትውፊት፣ ዘዴና ሥልት የተከተለ ነው፡፡

ሥርወ ትውፊት ዘሐዋርያት የሆነው “ሐዋርያዊ መንበር" በአንድ ሀገር/ሀገራት ውስጥ ያለ ቤተ ክርስቲያን የሥልጣነ ክህነቱ ምንጭ፤ የእምነቱን መሠረት የትውፊቱን ዋልታ የሚያስረዳበት ቀኖናዊ፣ ታሪካዊ መነሻ ነው፡፡ ስለዚህም ቀደምት ኢትዮጵያውያን ማርቆስ አባታችን ሲሉ ኖረዋል። ምክንያቱም የኢትዮጵያ፡ የግብጽ፡ የሊቢያ፤ ... አብያተ ክርስቲያናት ሐዋርያዊ መንበራቸው ቅዱስ ማርቆስ ነው። ይህ በታሪክ፣ በቀኖና፣ በእምነትና በመላው ዓለም ባሉ ክርስቲያናዊ ትውፊቶች የተረጋገጠ ነው፡፡

ከሐዋርያት ያልተገኘ ሥርወ ክህነት የለም፤ ስለዚህ ሁሉም የሚጠሩት በሐዋርያት ስም ነው፡፡ የሮም መንበር የቅዱስ ጴጥሮስ፤ የኤፌሶን የቅዱስ ዮሐንስ፤ የአንጾኪያ የቅዱስ ጴጥሮስ ቀዳሚ መንበር፣ የእስክንድርያ የቅዱስ ማርቆስ ነው፡፡ (ፍትሕ መንፈሳዊ ፵፩)፤ የኢየሩሳሌም የቅዱስ ያዕቆብ፣ የአርመን የያዕቆብ፤ የታዴዎስና በርተሎሜዎስ፤ የሕንድ የቶማስ፤ እያለ ይቀጥላል፡፡ ይህ ትክክለኛ ታሪክ ሲሆን በቀኖናም የታወቀ ነው፡ ፡ ቅዱስ ጳውሎስ የሮምን፣ የገላትያን፤ የተሰሎንቄን... አብያተ ክርሰቲያናት መሥርቷል፤ ወይም አጽናንቷል፣ ግን በስሙ አልተጠሩም ምክንያቱም ቅዱስ ጳውሎስ ከጌታችን ዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ቁጥር አይደለም፡፡ ይሁን እንጂ ቅዱስ ጳውሎስ በስብከቱ በደብዳቤዎቹና በኋላም የአሕዛብና የአይሁድ ሊቃናትን ወደ ክርስትና በመመለሱ በእሱ ምክንያት የተመሠረቱት አብያተ ክርስቲያናት መሥራቻችን ቅዱስ ጳውሎስ ነው! የሐዋርያዊ ትውፊትና የመንበር ሥያሜ ግን በ፲፪ቱ ሐዋርያት ነው ይላሉ፤ ለዚህም እንደ ምሳሌ የግሪክ እና የቁስጥንጥንያ አብያተ ክርስቲያናትን ማየት ይቻላል።

አቴናን የሰበከው ቅዱስ ጳውሎስ ነው (የሐዋ ፲፯)፣ በቀዳሚ ስብከቱ የምኩራብ አለቃና የሽንጎውን ዋና ዳኛ ዲዮናስዎስን አሳምኗል፣ እጅግ ከፍተኛ ባለሥልጣን፣ ፈላስፋ፣ ዳኛ፣ እና የአርዮስ ፋጎስ መሪ የነበረው ዲዮናስዮስ እና ሀብታም የነበረችው ዲማሪስም ተጠመቁ፣ ዲዮናስዮስ የመጀመሪያው የአቴና ጳጳስ ሆነ፣ የአቴና መንበር ግን በዲዮናስዮስም ሆነ በሰባኪው ቅዱስ ጳውሎስ አልተጠራም፡፡ የአቴና መንበር ሐዋርያዊ መጠሪያ ቅዱስ እንድርያስ ነው።

ሁለተኛም የቊስጥንጥንያ ግዛት በነበሩት ተሰሎንቄ፤ ገላትያ መቄዶንያ፤ ኤፌሶን፤ ቆሮንቶስ በሙሉ ያስተማረው ስሙን በአሕዛብ ዘንድ የሚሸከም ንዋይ ኅሩይ የተባለ ቅዱስ ጳውሎስ ነው። መንበሩ የሚጠራው ግን በቅዱስ እንድርያስ ነው፡፡ ምክንያቱም ከቅዱስ ጳውሎስ በፊት ሐዋርያው ስላስተማረና ሐዋርያት ቀዳሚ ስለነበሩ ነው፡፡ ሐዋርያት ቀደምት ሌሎቹ ደኃርት ናቸው፤ ከቅዱስ ጳውሎስ በፊት ሐዋርያት ስላሉ የሐዋርያዊ መንበር ምንጭ ወይም ሥር ሊሆን አልቻለም! መንበር ምንጭ ነው፡፡ መንበር ሥር ነው! የትውፊትና የኦርቶዶክሳዊ ሐረገ ትውልድ መነሻና ጥንተ መሠረት ነው፡፡

መንበር በሰው ፍላጎት የሚሠየም ቢሆን ኖሮ አርመኖች ልክ እንደ አቡነ ሰላማ በ፫፻፩ ዓ/ም የአርመን ኦርቶዶክስን የመንግሥት ሃይማኖት ያደረጋት እና የመጀመሪያው የአርመን ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ከሣቴ ብርሃን ስም በሰየሙት ነበር፡፡ ኮፕቲኮች ዘመን አቆጣጠርን በቀየሩበት (ሐሳበ ሰማዕታትን) በተፍጻሚተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ወይም በታላላቆቹ ዓለም አቀፍ ቅዱሳን በቅ/አትናቴዎስ፣ ወይም በቅ/ቄርሎስ፣.. በሰየሙት ነበር፡፡ በሂደትም ሐዋርያዊ መንበር (Apostolic Throne) የሚለው ሥያሜ በፓትርያርክ ደረጃ የሚመራ መንበሩ ከጥንታውያን የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት አንዱ በሆነ ሐዋርያ ወይም ወንጌላዊ የተሠየመ ማለት ሆነ፡፡

በታሪክ የታወቁት መንበረ ፓትርያርክ ሁሉም ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ወይም ከወንጌላውያን በአንዱ ብቻ ተጠርተዋል፡፡ ስለ መንበረ ሐዋርያት ጥንታዊ ትርጉምና ትውፊት ከታሪክ ጸሐፊዎች ውስጥ ተርቱለስ (ተርቱሊያን) በ፪ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሲናገር “መንበረ ሐዋርያት ከሐዋርያት ጀምሮ የተከበሩ ናቸው፣ እነሱም ሐዋርያት (የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት) የመሠረቷቸው ሲሆኑ ሥልጣነ ክህነትን፣ እምነትን እና የዶግማ ትምህርትን አንዳቸው ከአንዳቸው በመውረስ የቆዩ ናቸው፡፡” (የተርቱለስ፡ መናፍቃንን ስለመቃወም የጻፈው መጽሐፍ፡ ሦስተኛ ምዕራፍ)

የቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ደቀ መዝሙር ቅዱስ ሄሬንዮስ በዚሁ በ፪ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደተናገረው “የሐዋርያት መንበር የሐዋርያት ትውፊት ምንጭ ነው፤ ሥር ነው፣ የሃይማኖት ቅብብል ማሳያ ነው፤ ንጹሕ የሆነ የክርስትናን ትምህርት በሚገባ ለማወቅ የሚፈልግ በእነዚህ መናብርት የተጠበቀውን ትውፊት ማወቅ ይበቃል በማለት መናብርቱ የሐዋርያትን ትምህርት እና ትውፊት ለመጠበቅ የተመሠረቱ መሆናቸውን ገልጧል፡ (የሄሬንዮስ መናፍቃንን ስለመቃወም የጻፈው መጽሐፍ፡ ምዕራፍ ሦስትና አራት)

ቶኔቶር ሀገረ እግዚአብሔር

22 Feb, 13:06


ሰሞኑን በማኅበራዊ ሚዲያ እየተዘዋወረ ስለሚገኘው  "መነኩሴ "ነኝ ባይ ግለስብ በሀገረ ስብከቱ የማይታወቅ መሆኑን ሀገረ ስብከቱ ገለጸ።
==================
የካቲት ፲፬ ቀን ፳፻ ፲ወ፮ዓ.ም
*******
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
******

የአርሲ ሀገረ ስብከት ሰሞኑን በማኅበራዊ ድረ ገጾች ራሱን "መነኩሴ"በማስመሰልና በአርሲ ሀገረ ስብከት አገልጋይ እንደሆነ በመግለጽ የሚንቀሳቀሰውን ግለሰብ የማያውቀውና ሐሰተኛ "መነኩሴ" መሆኑን ለጠቅላይ ቤተክህነት በጻፈው ደብዳቤ አስታወቀ።

ከየካቲት 12 ቀን 20916 ዓ.ም ጀምሮ በማኀበራዊ ሚዲያ እየተዘዋወረ የሚገኘው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ተችቶ የማስተቸት ድራማዊ ትዕይንት ላይ የቀረበው አስመሳይ " መነኩሴ "ግለሰብ በሀገረ ስብከታችን በተለይ በአሰላ ከተማ በቅዳሴ መምህርነት በስብከተ ወንጌል እንዳገለ በማስመሰል በሰጠው የሀሰት ምስክርነትን በተመለከተ እውነተኛ ምላሽ መስጠት ማስፈለጉን የጠቀሰው ሀገረ ስብከቱ"መንኩሴ "መሳዩ ግለሱብ  በሀገረ ስብከቱ በየተኛውም የከተማና የገጠር ገዳማትና አድባራት የማይታወቅና ምንም ዓይነት አገልግሎት ሲሰጥ ያልነበረ መሆኑን ገልጿል።

በተጨማሪ በሀገረ ስብከቱ የሚገኙት ሁሉንም አገልጋዮች የሚታወቁና የተመዘገቡ መሆኑን የጠቀሰው ሀገረ ስብከቱ ግለሰቡ በሀገረ ስብከቱ  ካሉት አገልጋች መካከል የማይታወቅና ያልተመዘገበ ከመሆኑም በላይ ሀገረ ስብከቱ በፍጹም የማያውቀው ቀሳጢ ነው በማለት ሐሰተኛ ማንነትን በመላበስ የቤተክርስቲያንን ስም ለማጠልሸተ የተሰማራ መሆኑን ገልጿል።

ስለሆነም የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ግለሰቡ የቤተ ክርስቲያናችንን ዓርማ ወይም አልባሳት በመልበስና የሀገረ ስብከታችንን መልካም ገጽታ በማጉደፉ ግለሰቡንና እዩ ጩፋ የተባለውን አጽራረ ቤተ ክርስቲያን በህግ እንዲጠይቅን ስንል በታላቅ አክብሮት እናሳስባለን፤በማለት ለጠቅላይ ጽሕፈት ቤቱ በጻፈው ደብዳቤ ጨምሮ ገልጿል።

@tonetore