ዮሐንስ ጌታቸው

@phronema


ርቱዕ ሐልዮ
ጥያቄና አስተያየት ካልዎት ይስጡ!
@tmhrte_tsdk_bot

ዮሐንስ ጌታቸው

22 Oct, 04:28


#የዛሬ_ገጠመኝ#

ትንትና ማታ አዳማ አቡነ አረጋዊ ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ኖሮኝ ከአዲስ አበባ ወደ አዳማ ሄድኹኝና እንዳቀርብበት በተሰጠኝ ርእሰ ጉዳይ በጣም በአጭሩ አቀረብኹኝ። አስቀድመው እዚያው እንዳድር አመቻችተውልኝ ስለ ነበር፤ አድሬ ካደርኹበት ቦታ ሌሊት 11፡30 ተነሥቼ ተዘገጃጀኹና ወጣኹኝ። ካደርኹበት ወደ አዲስ አበባ ለመመለስ የአዲስ አበባ ሚኒ ባሶች ወዳሉበት መናኸሪያ መሄድ ነበረብኝ። ስለዚህም ኹለት ሰው የያዘ ባለ ባጃጅ ታክሲ እየፈለግኹ መሄዴን ገምቶ መናኸሪያ ነህ አለኝ፤ አዎን አልኹኝ። አቆመልኝ አንደኛው ተሳፋሪ ከባጃጁ ወጥቶ በቅርብ ስለምወርድ ብሎ ከመሐል አስገባኝ። መሐል መግባት ባልወድም እሺ ይኹን ብዬ ገባኹኝ።

ጉዞ ወደ መናኸሪያ ተጀመረ። እየሄድን ነው! ትንሽ ሄድ እንዳልን ልወርድን ነው ያለው ሰውዬ 50 ብር አውጥቶ ለባለ ባጃጁ ይሰጠዋል። ባለ ባጃጁም ዘርዝር አልያዝኹም፥ ዝርዝር ብር ያለው ይኖር ይኾን ይለናል እኔንና አንደኛውን ባጃጁን እየነዳ። እኔም ወደ ቲሴ እጄን ከትሁና በይውህና ኾኜ 40 ብር አለኝ፥ መልሱ ስንት ነው? ልስጠውን? አለኹኝ። በዚያን ጊዜ 10 ብር ብቻ ስጠኝ ይበቃል አለኝ። ሰጠኹት። በዚህ ሂደት በቅርብ ወራጅ ነኝ ያለኝ ሰውዬ በእጁ ቦርሳ ይዟል፥ ኪሩን እንደሚፈታትሽ ኾኖ የኔን ስልክ በጣም በእርጋት ከኪሴ ያወጣል። እኔም የኾነ ስሜት ይሰማኛል! የሻሼ አራዳ ነኝና😂 ስቀልድ ነው ገጠሬ ነኝ! ስልኬን ከኪሴ መውጣቷ ገብቶኛል።

ባለ ባጃጁም ወዳት መናኸሪያ ነህ? ወደ አሰላ ወይስ ወደ አዲስ አበባ ሲለኝ፥ ወደ አዲስ አበባ አልኹት ላካስ ወደ ሌላ መስመር እየወሰደኝ ኖሯል! አትነግረኝምን? እዚህ ውረድና ወደዚያ ሄደህ ሌላ ባጃጅ ያዝ ብሎ የሰጠኝን 10 ብር እንዳዛኝ ኾኖ ይሰጠኛል። እኔም ተቀብዬ ልወርድ ስል ኪሴን ቼክ አደረግኹኛ🙄 ስልኳን አጅሬው ከኪሴ አውጥቷታልና፥ ወንበሩም ላይ ቁጭ ብላለች፥ ቶሎ በፍጥነት ብድግ አድርጌያት ወረድኹላቸው! በአራዶች አራዳ ኾንኹባቸው። እየመረራቸው የሄዱ ይመስለኛል። እንዳወጣኸው ወደ ኪስህ አትከተውም ነበርን? ምን አንቀራዘዘህ? የጠዋት አየራችንን አከሰርኸው? ከኪሴ አውጪው ደግሞ ወይኔ! ምን ዓይነት መርዝ ነው😂 እያለኝ ይኾናል።

ስልኬን ቢወስዷት ስልክ ይገዛል በውስጡ ያስቀመጥዃቸው ዶክመንቶች ግን እጅጉን የሚጠቅሙኝ ናቸው። በዚያ ኀዘን ይሰማኝ ነበር። በዚህ አጋጣሚ ስልኮች ግን ሳያዝኑብኝ አይቀርም። በእጄ ብዙ ዓመት የመበርከት አጋጣሚ አግኝተዋልና። ከ5 ዓመት በታች የቆየ ስልክ ትዝ አይለኝም። አኹን የያዝኹት ግን ገና ኹለት ዓመቱ ነበር😁

ይህ ገጣኝ ምን አመለከተኝ መሰላችሁ፥ ንቍ ካልኾንን ሰይጣን እኛ በምንፈልገው መንገድ ወደ እኛ መጥቶ ወደ ምንሄድበትም የሚሄድ መስሎ የሚያጠቃን መኾኑን ነው። ብዙዎቻችንን በኃጢአት ጣዕም አስምጦ የሚያስቀረን እኛ በምንወደውና በምንመርጠው መንገድ መጥቶ ነው። በእርሱ ቍጥጥር ውስጥ ያስገባን ሲመስለው እንኳን በጥንቃቄና በንቃት የምንጓዝ ከኾነ በእግዚአብሔር ቸርነት ወጥመዱን መስበር እንችላለን። ተስፋ መቍረጥ፣ ትክዝ ብሎ መጨነቅ ወደ ጉዳት የሚያደርሰን እንጂ የሚጠቅመን አይደለም። ዐይነ ልቡናችን የሚሰረቀው ባልተገባ ጭንቀት ውስጥ ገብተን ስንዋኝ ነው። ምንም እንኳን አጋንንት እኛን ለመጣልና ወደ ኀዘን ውስጥ ለማስገባት ቢጥሩ፣ የምንወደውንም ነገር በር አድርገው ቢቀርቡን በጥንቃቄና በንቃት የምንኖር ከኾነ አንወድቅም። እግዚአብሔር አምላካችን አጋንንት ከሚያሴሩብን ክፉ ሴራ ይጠብቀን።

ሌላኛው መልእክት። ምንም እንኳን አዳማ በተደጋጋሚ በጉባኤ ምክንያት ብሄድም ብዙም አላቃትም። እነዚህ ሰዎች የበለጠ እናጥቃው ቢሉ የፈለጉበት ወስደው የፈለጉትን ሊያደርጉብኝ ይችሉ ነበር። ያሳደገኝ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ግን በአምላክ ቸርነት በዕለተ ቀኑ ከዚያ ጠበቀኝ። ይህ ማለት እኛ በማናስበው መንገድ ለጥቃት ራሳችንን አጋልጠን ብንሰጥ እንኳን እግዚአብሔር የሚጠብቀን መኾኑን ነው። አላወቅን ይኾናል እንጂ እግዚአብሔር ብዙ ጊዜ ከክፉ ሴራ ጠላትን እንኳን በእኛ ላይ እንዳይሠለጥኑ ሕሊናቸውን የሚከለክል ቸር አምላክ መኾኑን ልብ እንበል። ክፉ ነገር ከደረሰብን በኋላ ብቻ የሚያድነን ሳይኾን እንዳይደርስብንም አስቀድሞ የሚያድነን አምላክ ኹሌም እናመስግነው። በእምነትና በንጽሕና ኾነንም እርሱ የሚፈልገውን እናድርግ።

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

20 Oct, 18:54


++++++#ጠባቧ_መንገድ#++++++

"በተጨባጭ እውነታ ሰፊውንና ልቅ የኾነውን መንገድ ይዘን ሳለ ጠባቡንና የቀጠነውን መንገድ እየተከተልን እንደ ኾነ በማሰብ እንዳንታለል በራሳችን ላይ ቅርብ ትኲረት እናድርግ። ቀጥሎ የሰፈረው ነገር ጠባብ መንገድ ማለት ምን እንደ ኾነ ያሳይሃል፦ ሆድን ማጎስቆል (ስስትን መግደል)፣ ትጋሃ ሌሊት (ሌሊቱን ሙሉ መቆም)፣ ጥቂት ውኃ መጠጣት፣ ቍራሽ ዳብ መብላት (ከፊለ ኅብስት)፣ በተዋርዶ ድርቅ መንጻት፣ መናቅ፣ ፌዝን መቀበል፣ መሰደብ፣ የገዛ ፈቃድን ቆርጦ መጣል፣ በሚያስቆጣ ነገር መታገሥ፣ ባለ ማጉረምረም ንቀትን መታገሥ፣ ስድቦችን ቸል ማለት፣ ያልተገባ ጠባይን ጸንቶ መታገሥ፤ ሲታሙ አለመቆጣት፣ ሲዋረዱ አለመቆጣት፣ ሲነቀፉ ትሑት መኾን ነው። የገለጽናቸውን ጎዳናዎች የሚከተሉ ብፁዓን ናቸው፣ መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና። ማቴ 5፡3-13።" እንዲል ዮሐንስ ዘሰዋስው። (ሳሙኤል ፍቃዱ (ተርጓሚ)፣ ምዕራግና ድርሳን፣ 2011 ዓ.ም፣ ገጽ 102)።

በዚህ አባት ጽሑፍ ውስጥ አንደኛ ራሳችንን መመርመር እንዳለብን ተገልጿል። ልቅ በኾነው ሰፊ መንገድ በተባለው የዓለማዊነት መንገድ ላይ መኾን አለመኾናችንን በትኩረት እንድናስተውል ምክረ ሐሳብ ቀርቧል። ኹል ጊዜም ቢኾን ትክክለኛ ወደ ኾነው መንገድ ለመግባት አስቀድሞ የቆምንበትን መንገድ እና በዚያ መንገድ እንድንጓዝ ያደረገንን ውስጣዊ ፍላጎት መረዳት ያስፈልጋል። ምን ያህልስ ጊዜ ልቅ በኾነው የኃጢአት መንገድ ተጉዘን ይኾን? ምን ያህልስ የዚያ መንገድ ጣዕም በውስጣችን ቀርቶ ይኾን? እንዴትስ ከዚያ መንገድ መውጣት እንችላለን። እያልን በእርጋታ ለራሳችን ጥያቄ እያቀረብን ራሳችንን እንመርምር።

ኹለተኛው መሠረታዊ ነገር ጠባብ መንገድ ማለት ምን ማለት እንደ ኾነ የተገለጸበት ነው። ጥቂት መመገብን ከመለማመድ ጀምሮ ማንኛውንም ክፉ የተባሉ ነገሮችን የሚያደርጉብንን መታገሥ ተገቢ መኾኑን ያስረዳል። መንገዱን ጠባብ ያሰኘውም፥ የተገለጹትን ነገሮች ለመተግበር እጅግ የሚከብዱ ስለ ኾነ ነው። ጽድቁንና መንግሥቱን እያሰብን የምንኖር ከኾነ ግን ከባድ ሊኾኑ አይችሉም። ጠባቡ መንገድ ጣዕመ መንግሥተ እግዚአብሔርን እያሰቡ ኃጢአትን መጥላትን ማዕከል ያደረገ ነውና። የሚንቁንን፣ የሚሰድቡንን፣ የሚያሙንን መታገሥ ለብዙዎቻችን አስቸጋሪ ነው። በእውነትም የሚጠሉንን ላለመጥላት እየታገልንን ኹሌ ራሳችንን ትዕግሥትን ብናለማምድ እግዚአብሔር ይረዳናል። ትዕግሥት በእኛ ጥረት ብቻ ሳይኾን ከእግዚአብሔርም ጸጋ ኾኖ የሚሰጥም ነገር ነውና። እኛ ከልባችን ክፉን በትዕግሥት ስንቀበል እግዚአብሔር ጽናቱን ይሰጠናል። የጠባቡ መንገድ መድረሻው መንግሥተ እግዚአብሔር መኾኑን በሕሊናችን ውስጥ አስቀምጠን፥ መንግሥቱን እያሰብን እንኑር። አንድ ሯጭ ትኲረቱን በሙሉ የሚያደርገው ቀድመውት ያሉ ተወዳዳሪዎች ላይ እንደ ኾነ ኹሉ እኛም ትኲረታችንን ወደ መንግሥተ እግዚአብሔር አቅጣጫ ካደረግን በእኛ ላይ የሚደረጉ ክፉ ነገሮችን ኹሉ ሳናያቸው ማለፍ እንችላለን።

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

18 Oct, 17:19


ቤቱን በዓለት ላይ የሠራ ልባም ሰው!

ሙሉ ቪዲዮውን ሊንኩን በመጫን ዩትዩብ ላይ ማግኘት ትችላላችሁ ።
👇👇👇👇👇👇👇👇👇👇
https://youtu.be/HudBRUiCdCQ?si=Vc32xgpVI7KGwxwp

@MasyasTube

ዮሐንስ ጌታቸው

14 Oct, 14:52


+++++++#በበጎነት_መጽናት#+++++++++

ማር ወግሪስ እንዲህ ይላል፦ "ዳግመኛም ስማኝ ልንገርህ! ለዘለዓለም ላንተ ይብስብሃልና ባደርክበት ኹሉ ቃልህን አትለውጥ። በሰዎች መካከል ጥልን አትዝራ፤ አነዋወርህ ኹሉ በሰላም ይኹን፤ ወደ ልቡናህም ቍጣን አታስገባ፤ ወንድምህ የበደለህን ከቶ አታስብ። የቍጡ ሰው ድካሙ ኹሉ በዐይን ጥቅሻ በከንፈር ንክሻ ፈጥኖ ያልፋልና። ቂምን በልቡናው የሚያኖር ሰው የሰይጣን ደቀ መዝሙሩ ነው፤ የዘለዓለም ሕይወትንም አያያትም። ማንንም ማንን አትማ፤ ከማንም ጋር አትከራከር፤ የባልጀራህን ንብረት አትመኝ የሌላውንም አትቀማ።

ሐሜተኛ ሰው የእግዚአብሔር ጠላቱ ነው። በጠላትህ ውድቀትና ሞት ደስ አይበልህ፤ ባዘኑት ላይ አትሣለቅ፤ ለዕውሩ መሰናክል አታኑርበት። ስትጸልይ ለመቀመጥ አትቸኩል፤ ለጸሎት ጽሙድ ኾነህ በቆምክበት ቦታ ኹሉ አትነቃነቅ፤ በመካነ ጸሎትህ ላይ አዘውትረህ ቆመህ ተገኝ። ለለመነህ ኹሉ ስጥ፤ ከሌለህ ደግሞ እግዚአብሔር ይስጥህ ካለው ያድርስህ ብለህ በለዘበ ቃል ተናገር። የምትሠራውን ሥራ ኹሉ ፊት አይተህ አድልተህ አትሥራ። የደረሰብህን ኹሉ እግዚአብሔርን አመስግነህ ተቀበል። ይህንን ያደረግህ እንደ ኾነ በእግዚአብሔር ትእዛዛትና ሕግጋት አንተ በእውነት ፍጹም ነህ። እኔስ በእውነት የእግዚአብሔርን ጥበብ አደንቃለሁ።" እንዲል። (ገብረ ኪዳን ግርማ (አባ፣ የአራቱ ጉባኤያት የምስክር መምህር)፣ መጽሐፈ ወግሪስ፣ 2013 ዓ.ም፣ ገጽ 51)።

የሕይወት መርሐችን ከላይ በተገለጸው መሠረት ቢኾን በበጎ መጽናት እንችላለን። ክፉ ነገር በሕሊናች ውስጥ በመጣ ጊዜ ወዲያው አስወግደን ብናስወጣው እና ሕሊናችን ውስጥ የእግዚአብሔርን ቃል ኹል ጊዜ ብናስቀምጥ፥ በዚያም ቃል ብንመሰጥበት ሕይወታችን የተስተካከለ ይኾናል። ድንገት ስሜታዊ ኾነን ወደ ክፉ ልንሳብ ስንል ራሳችንን የምንቆጣጠርበት የእግዚአብሔር ቃል ውስጣችን ሊኖር ይገባል። በእርግጥም የሕይወት መርሐችንን በቃለ እግዚአብሔር እያደረግን ስንሄድ ስሜታችን በራሱ በቃለ እግዚአብሔር እየተገራ ይሄዳል። ውስጣችንም በቃለ እግዚአብሔር መመራትን እንደ ግዴታ መቀበል ይጀምራል። እንዲህ ሲኾን ብንጣላ ወዲያው ይቅር እንባባላለን፥ ቢበድሉን እንታገሳለን፥ ቢሰድቡን ስድብ የሚገባን ኃጥእ እንደ ኾን አድርገን እንቀበላለን፣ ቢንቁንም የክፉ ሥራችን ውጤት መኾኑን አምነን ያለተቃውሞ እንቀበላለን። እንዲህ በበጎ እየጸናን ስንሄድ የሚረብሸን ነገር በእኛ ላይ ኃይሉን እያጣ ይሄዳል፤ ሕይወታችንም በፍጹም ሰላምና ዕረፍት ይመላል።

እንግዲህ ምክንያታዊ ነኝ ብለን ከምናስበው አጸፋዊ መልስ ኹሉ እየራቅን እንሄዳለን። እንዲህ ያደረግኹት እንዲህ ስላደረገችኝ/ገኝ ነው እያሉ ከመናገር ኹሉ ነጻ እንወጣለን። በሕይወታችን የሚገጥሙንን ችግር የምንላቸውን ነገሮች ኹሉ የመጋፈጥና የማሸነፍ ብርታታችን ታላቅ ይኾናል። የብዙ ዓመታት ሕማም ቢኾን፣ ወይም የገንዘብ እጦት ችግር ቢኾን፣ ወይም ከሰዎች ዘንድ ፍቅር አጣኹኝ ብሎ የማሰብ ፈተናም ቢኾን እንሻገረዋለን። መጀመሪያ መስተካከል ያለበት አስተሳሰብ እና ነገሮችን የምንረዳበት መንገድ ነው። ሲቀጥልም የመኖር ትርጒሙና ዓላማው ግልጽ ኾኖ ሊገባን ያስፈልጋል። ይህ በትክክል ሲገባን ያን መፈጸም ዋና ዓላማችን እየኾነ ይመጣል። ስለዚህ ሰይጣን ሊጥለንና ጥቅም አልባ ሊያደርገን የሚፈጽምብን ጥቃት ኹሉ ይከሽፋል። በበጎነት ጽናታችንም ድል ይነሣል። ስለዚህ ስንኖር ለምንድን ነው የምኖረው? እንዴትስ እንድኖር ነው ፈጣሪ የሚፈልገው? ፈጣሪስ እንደሚፈልገው መኖር ያልቻልኩት ለምንድን ነው? ለመኾኑ በበጎነት ጸንቼ እንዳልኖር የሚከለክለኝ ምንድን ነው? የሚሉ ጥያቄዎችን ለራሴ እየጠየኩ ሕይወቴን እያስተካከልኹኝ ልኖር ይገባኛል። በምን መመሪያ እንዳንል ከላይ ማር ወግሪስ ያስቀመጠልን ድንቅ የሕይወት መመሪያ አለልን።

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

10 Oct, 19:44


https://youtu.be/ISLQf-zUAeQ?si=bkgwuu7OEpkuriy6

ዮሐንስ ጌታቸው

08 Oct, 05:59


+++++++#የሰይጣን_ወጥመድ#+++++++

አባ ኔቅጣስ ስለ ኹለት ወንድሞች የሚከተለውን ተናግረዋል። አንድ ጊዜ ኹለት መነኮሳት በአንድነት ለመኖር ወሰኑ። አንደኛው በልቡ "ወንድሜ የሚፈልገውን ኹሉ አደርግለታለሁኝ" ሲል ቃል ገባ። ሌላኛውም "የወንድሜን ፈቃድ እፈጽምለታለሁ" ሲል በልቡ ወሰነ። በዚህ ውሳኔያቸው ለብዙ ዘመናት በለጋሥነት ኖሩ። በዚህ ፍቅራቸው የቀና ሰይጣን ሊለያያቸው ተነሣ። በበኣታቸው በር ላይ ቆመና ለአንደኛው ርግብ ለሌላኛው ቍራ መስሎ ታያቸው። በዚህ ጊዜ አንደኛው መነኩሴ "ርግቧን አየሃት?" ሲለው ሌላኛው ደግሞ "ርግብ አይደለችም ቍራ ናት" ሲል መለሰ። "ርግብ ናት"፣ "ቍራ ነው" ክርክር ጀመሩ። ክርክሩ ወደ ጭቅጭቅ፣ ጭቅጭቁ ወደ ድብድብ አመራና ደም በደም እስኪ ኾኑ ድረስ ተደባደቡ። በመጨረሻም ተለያዩ። ከሦስት ቀናት በኋላ ወደ ልባቸው ተመልሰው ኹለቱም ተፀፀቱ። ይቅርታም ተጠያየቁ። ኹለቱም በተለያየ መልክ አንድ ዓይነት ነገር ማየታቸውንና ልዩነታቸው የመጣው ከነገሩ ሳይኾን ከዲያብሎስ መኾኑን ተረዱ። እስከ ዕለተ ሞታቸውም ድረስ አብረው ያለ ፀብ ኖሩ። (ዳንኤል ክብረት (ዲ/ን፣ አርተር)፣ በበረሓው ጉያ ውስጥ፣ ሦስተኛ ዕትም 2004 ዓ.ም፣ ገጽ 57-58)።

ብዙ ጊዜ መንፈሳዊ ሕይወታችን ምስቅልቅል የሚልብን በእንዲህ ዓይነት ስውር የሰይጣን ወጥመድ ነው። አንድን ነገር በእርጋታ ከመመርመር ይልቅ ያየነውን ብቻ መሠረት አድርገን ወደ ተሳሳተ ውሳኔ የምንገባም እና የእግዚአብሔርን መግቦት የምንጠራጠር ብዙ ሰዎች አለን። ከሌሎች ጋር በፍቅር ለመኖር የወሰነውን ውሳኔ ድንገት በአንዲት ተራ ምክንያት የምናፈርስ መኾኑን እናስተውል። የገመጠንን ነገር በልቡናችን ከገባነው ቃል ኪዳን ጋር እያስተያየን በትዕግሥት ልንጸናና ረጋ ልንል ሲገባን በጥድፊና ተቃራኒ መልስ እየመለስን ወደ ጥልና ፀብ የምንገባ ልንጠነቀቅ ይገባናል። የልቡናችንን ዐይን ስሜታዊነታችንን አንጫነው፤ እኔ የማየው ብቻም ነው ትክክል ብለንም የሌሎችን ሐሳብ አንግፋ። ለሕይወታችን ሊጠቅም የሚችለውን ወዳጅ እኔ እንደ ማየው አላየም ብለን አንግፋው። በጎ አንድነት እንዳይኖር የሚሻ ጠላት ልዩነትን ኾነ ብሎ እየፈጠረብንም እንደ ኾነ ልብ እንበል። የሚሻለን ኹሌም ቢኾን ራስን ዝቅ አድርጎ ለሕይወት ከሚጠቅመን ወዳጃችን ጋር በአንድነት መኖር ነው። እግዚአብሔር ዓይነ ልቡናችንን ያብራልን።

በሌላ በኩል ደግሞ አንድ ነገር በተለያየ መንገድ ለተለያዩ ሰዎች በማሳየት ሰይጣን ምን ያህል ፀብና ጥልን የሚፈጥር ክፉ ጠላት መኾኑን ልብ ማለት እንችላለን። ክፉው ጠላት ሰይጣን እኛን ለመጣል ያን ያህል የሚዋጋ ከኾን እኛስ እርሱን ለመግጠም ምን ያህል ሠልጥነን ይኾን? ይህን ኹላችንም ለየራሳችን እንጠይቅ። በክርስትና ሕይወት በጣም የዛልን፣ በእምነታችን ላይ ጥርጣሬ የመጣብን፣ በሃይማኖታዊ ጉዳይ ለዘብተኛ ወደ መኾን እየሄድን ያለን በሙሉ ለአንድ አፍታ ቆም ብለን እናስብ። ጠላት ምን ያህል የጥፋት ጉድጉድ እየቆፈረልን እንደ ኾነም ልብ በማለት ንቁ ተዋጋጊ እንኹን። ሊዋጋው እና ሊያጠፋው በብዙ ኃይል ታጥቆ የሚመጣን ጠላት እያየ ባዶ እጁን ቍጭ ብሎ የሚጠብቅ ተዋጋ ይኖራልን? ቢኖሩ እንኳን ለማሸነፍ ያሰበ ሳይኾን አስቀድሞ በስንፍናው ምክንያት የተሸነፈ ጠላትም ሲመጣ እጁን ሰጥቶ ባርያ ሊኾንለት ያቀደ ብቻ ነው ሊኾን የሚችለው። ወይም ሕይወቱን የጠላና ለበለጠ ሥቃይና መከራ ራሱን በፈቃዱ አሳልፎ ለመስጠት የፈቀደ ሞኝና ሰነፍ ነው ሊኾን የሚችለው። ይህ ደግሞ በራስ ላይ ራስን ጠላት እንደ ማድረግ ነው። ስለዚህ በጥንቃቄ እንኑር።

ሰይጣን በተለያየ መልክ እየተገለጠ ወደ ልዩነትና ፀብ የሚወስድ መኾኑን ልብ ከማለት ጋር እኔ የማየው ብቻ ነው ትክክል ከማለት በፊት ጸሎት ማድረግ ወደ እግዚአብሔር መጮህ ያስፈልጋል። ብዙ ጊዜ ልዩነት እየመሰሉን የምንጣላባቸው ነገሮች ልክ እንዲሁ ናቸው። ወደ ልዩነት፣ ፀብና ክርክር፣ አለፍ ሲልም ወደ ጭቅጭቅ እና ድብድብ ድረስ የሚያደርሰን ለነገሮች ያለን የተቃረነ አረዳድ ነው። ኹላችንም ማንኛውንም ነገር በጸሎትና እግዚአብሔርን በመጠየቅ ብናደርገው እጅጉን ጠቃሚ ነው። ተቃራኒ የሚመስለን ወደ ፀብ ሊያመራን የሚችል ነገር ኹሉ የጠላታችን የዲያብሎስ ወጥመድ መኾኑን ኹሌም ልብ እንበል። የእኔ ብቻ ትክክል ነው፣ ያንተ ትክክል አይደለም እያሉ የሌሎችን ሐሳብም ኾነ ንግግር ለማድመጥ ፈቃደኛ አለመኾን ወደ ጭቅጭቅና ከዚያም አልፎ ደም እስከ ማፋሰስ ድብድብ የሚያደርስ መኾኑን ልብ ይሏል። እንዲህ ዓይነት የልዩነትና የፀብ ፈተና በገዳም እንኳን የማይቀር መኾኑን ኹል ልብ እንበል። ስለዚህ አንዱ እሳት ሲኾን ሌላው ውኃ፣ አንዱ ቍጡ ሲኾን ሌላው በራድ፣ አንዱ ቸኳይ ሲኾን ሌላኛው ረጋ ያለ ትዕግሥተኛ መኾን አለበት። ዕለት ቀንና ሌሊት እንደሚኖረው ሕይወትም ብርሃንና ጨለማ ይኖረዋል። ጨለማ ብቻ ቢኾን ወይም ብርሃን ብቻ ቢኾን አኹን ባለን አኗኗር ጥሩ አይኾንም ነበር። እንቅልፍም ንቃትም ያስፈልጋሉና። አንዱ ሲተኛ አንዱ ካላነቃ፣ አንዱ ሲስት ሌላኛው ካላቀና እንዴትስ ሕይወት ሥምረት ሊኖራት ይችላል?

ኹለቱ መነኮሳት ለጊዜው ባይረዱትም ዃላ ወደየልቡናቸው ሲመለሱ ያጣላቸው ሰይጣን እንደ ኾነ ተረድተው፡ ይቅር ተባብለው፡ አንዴ አለያይቷቸው ደም ያፋሰሳቸውን ጠላት እስከ ሞታቸው ድረስ ተዋግተው ድል አድርገውት እነርሱ በፍቅር በአንድነት ምድራዊ ሕይወታቸውን አጠናቀዋል። እንግዲያውስ እኛም እንደነርሱ ወደየ ልቡናችን ተመልሰን የተጣላን ይቅር ብንባባልና ወደ ልዩነት እና ፀብ የመራን ሰይጣን መኾኑን ተረድተን በፍቅርና ክርስቲያናዊ በኾነ አንድነት ብንኖር አሸናፊ መኾናችን በዚያ ይታወቃል። እግዚአብሔር ለኹላችንም ንጹሕ ልቡና አድሎ በፍቅር በአንድነት የምንኖርበትን ኃይል ይስጠን፤ አሸነፍኩ ተሸነፍኩ ከሚያስብል ክፉ እልህና ግራ መጋባት ይሰውረን፤ በእርሱ ቃል ልቡናችን ተሸንፎ ራሳችንን ከኹሉ የምናንስ አድርገን ለመቍጠርም ያብቃን አሜን።

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

02 Oct, 05:19


የቱ ይበልጣል?

አንድ እውነተኛ ክርስቲያን ለሦስት ሠራተኞች በቤቱ ውስጥ የቀን ሥራ ሰጣቸው። ሠራተኞቹ ሥራቸውን በጨረሱ ጊዜ ይሸልማቸው ዘንድ ጠራቸው። ታዲያስ ከፊታቸው ሦስት የወርቅ ሳንቲምና ሦስት መንፈሳዊ መጻሕፍትን አስቀምጦ፥ የወርቅ ሳንቲሙን ወይም መጽሐፉን እንዲመርጡ ነገራቸው።

ሁለቱ ሠራተኞች ወዲያውኑ "በበጋ እንጨት እንገዛበታለን" እያሉ የወርቅ ሳንቲሞችን ወሰዱ። ሦስተኛው ሠራተኛ ከፊቱ ያለውን መጽሐፍ አንሥቶ "ዐይነ ሥውር እናት አለችኝ ምሽት ምሽት ላይ ከዚህ መጽሐፍ የኾነ ነገር አነብላታለሁ" እያለ ወሰደ።

ሃይማኖተኛው ክርስቲያንም ፈገግ አለበትና እባክህ የመጽሐፉን የመጀመሪያውን ገጽ ከፍተህ ምን እንደ ተጻፈበት አንበብ አለው። ወዲያውኑ ሠራተኛው መጽሐፉን ሲከፍት፥ ባየው ነገር ተደነቀ ሦስት የወርቅ ሳንቲም በመጀመሪያው ገጽ ላይ ተጣብቆ ነበርና።

ከዚያን እውነተኛው ክርስቲያን ሦስቱን ሠራተኞች እንዲህ አላቸው "ስሙ፤ ምድራዊ ቁሶች መልካሞች ናቸው። ነገር ግን ዘለዓለማዊ ቁሶች የበለጠ መልካሞች ናቸው። ዘለዓለማዊ ነገር የሚፈልግ ሁሉ ምድራዊውን ነገርንም እንደማያጣ ዕወቁ። ክርስቶስ እንዲህ ብሏልና " እናንተስ አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፤ ሌላው ሁሉ ይጨመርላችኋል።" ማቴ ፮፡፴፫። (Orthodox parables and short history)

ይህ ታሪክ አሁን ያለነውን አብዛኛዎቻችንን የሚመለከት ይመስለኛል። ብዙዎቻችን የምንሠራው ምድራዊ ነገር ለማግኘት ብቻ ብለን ነው። ሌላው ቀርቶ ድርጊታችን ዓለማዊ ኾኖ እንኳን የሚያጸድቅ ሽልማት ሲቀርብልን አንፈልግም እንላለን። ምርጫችን በተራ ኃላፊ ነገር ላይ ብቻ የተመሠረተ ነውና። እሳትና ውኃ ቀርቦልን ምረጡ ስንባል ልቡናችን የሚከጅለው እሳት የተባለውን ዓለማዊ ሥራ ለመሥራት ብቻ ነው። ጾምና ምግብ በምርጫ ቀርቦልን ጾምን ትተን ምግብን ብቻ በመምረጥ ሆዳም የኾን ጥቂት አይደለንም። መጽሐፍ ቅዱስና ተራ የዚህ ዓለም ልብ ወለድ ቀርቦልን ወዲያው የምንመርጠው ልብወለዱን ነው። ይህ እንግዲህ በምን ያህል ርቀት የክርስትናን ጉዳይ ሳንረዳ እንደቀረንና ሕይወታችንም እውነተኛ የሕይወትን ትርጒም ትታ ፍሬ አልባ እንደ ኾነችብን አመልካች ነው።

ከክርስትና መከራ እና ከዓለማዊ ደስና የቱ ይሻላችኋል ተብሎ ምርጫ ቢቀርብልን የሁላችንም ምርጫ ደስታን ማግኘት ነው። ምክንያቱም በመከራ ውስጥ የሚገኘውን የማይመረመር ደስታ አናውቀውምና። ሕይወትና ሞት ቀርቦልን የምንመርጠው ሞትን ነው። ይህም ማለት የሞትን ሥራ በጣም እንወደዋለን የሕይወትን ሥራ ግን ፈጽሞ እንጠላለን። ፖለቲከኛው በፖለቲካው፣ ነጋዴው በንግዱ፣ ሠራተኛው በሥራው የሚመርጠው የቱን ነው? ፍትሐዊነት የጎደለውን የሞትን ሥራ አይደለምን?

ከፍቅረ እግዚአብሔርና ከፍቅረ ዓለም በእኛ ዘንድ የቱ ይበልጣል? በዕለት ተዕለት የሕይወት መርሐችን ውስጥ ፍቅረ ዓለም እጅጉን ሠልጥኖብናል። ዓለማዊ ፊልሙ ውስጥ ያለው ፍትወት፣ በመጠጥ ውስጥ ያለው ስካር፣ በዘፈን ውስጥ ያለው ጭፈራ፣ መቀባባቱ፣ አለባበስን አጋንኖ የተለየ ለመምሰል መሞከሩ፣ ታምራላችሁ መባሉ በጣም የሚጣፍጥ ይመስለናል፤ ኾኖም ፍቅረ እግዚአብሔርን ምን ያህል ጣፋጭ እንደ ኾነ ለመረዳት ትንሽ እንኳን ጥረት አናደርግም። በእርግጥ ለመቅመስ ብንጥር ያ ሁሉ ነገር የማይጠቅም መኾኑን እንረዳ ነበር! ስለዚህ የቀረቡልንን ምርጫዎች በእርጋታ እንመርምር፡ የበለጠውን ትተን ወደሚያንሰው አንጓዝ። በጽድቅ ውስጥ እኛ ይበቃናል የምንለው ሳይኾን እግዚአብሔር ያስፈልጋችኋል የሚለውን ሦስት የወርቅ ሳንቲም ሳያስቀምጥልን መቼም አይቀርም። ሌላው ቀርቶ እኛ በምንመርጠው ዓለማዊነት ውስጥ ከምናገኘው አንድ ሳንቲም የሚበልጥ ወደ እግዚአብሔር ስንሄድ ለምድራዊ ኑሯችን ስንኳን ሦስት እጥፍ ይሰጠን ነበር።

ክርስቶስ በመስቀል ላይ የከፈለልንን የፍቅር መሥዋዕትነት ከማስታወስ ይልቅ የዚህ ዓለም ኃላፊ ታሪኮችን ብቻ በማስታወስ አእምሯችንን ያደካከምን ስንቶች ነን? ከወንጌል ይልቅ የፊልም አክተር በሕልማችን የሚመጣብን፣ ከመዝሙር ይልቅ ዘፈን ከአፋችን የሚፈስ፣ ከመንፈሳዊ ጥበብ ይልቅ ዓለማዊ ድንቍርና የሚስማማን፣ ከትሕትና ይልቅ ትዕቢት የሚያንቀን ስንቶች ነን? እንግዲህ የወርቁን ወርቅ መጽሐፍ ቅዱስን ትተን በምድራዊ ወርቅ የተመሰሉትን ዓለማውያት መጻሕፍትን ብቻ በማንበብ የተጠመድን ክርስቲያኖች የቆምንበትን እንመርምር። ለዴማስ በምርጫ ቅዱስ ጳውሎስ እና ተሰሎንቄ ቀርበውለት ነበር፥ ዴማስ ግን የተወደደውን ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስን ትቶ ተሰሎንቄን መረጠ። ተሰሎንቄ ውጫዊ መልኳ የዴማስን ልብ ማረከው። እንግዲህ እኛም እንዲሁ ነው እያደረግን ያለነው። በሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የተመሰለች ወንጌልን ትተን ኀላፊ የኾነች የዚህ ዓለም ጣዕምን ወደናልና። ለጊዜው ምርጫችን ልክ ይመስለናል፥ ኾኖም የእግዚአብሔር ቃል የተጻፈበትን ቅዱስ መጽሐፍ ትተናል። የችግሮቻችን ኹሉ ምንጭ አመራረጣችን ላይ ነው ያለው። ምርጫችን ካልተስተካከለ ሕይወታችን ጨለማ ውስጥ ይኾናል።

ወደ ትዳር ሕይወት የሚጓዙ አካላትም፡ ሊያገቡት ያሰቡትን አካል ከእምነታቸው አስበልጠው ይመርጣሉ። እምነቱ ርቱዕ ወይም ቀና ኦርቶዶክሳዊ አለመኾኑን እያወቁ፡ እምነቱን ትተው እርሱን ይመርጣሉ። ለዚህም የተሳሳተ ምርጫቸው የየራሳቸውን የመከላከያ ምክንያት ያዘጋጃሉ። ምርጫቸው ልክ እንዳልኾነ እንዲነገራቸው ፈጽሞ አይፈልጉም። ስለዚህ እነዚህ አካላት ስለ ሃይማኖታቸው በፍጹም ልልነት ውስጥ ኾነው ሳለ ጠንካሮች እንደ ኾኑ አድርገው ለማሳየት ይፈልጋሉ። ነገሮችን ኹሉ በራሳቸው ስሜትና ግለ ምልከታ እንዲታይ ይፈልጋሉ እንጂ እንደ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንዲታይ አይፈልጉም። ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ወደ እነርሱ እንዲወርድ ይፈልጋሉ እንጂ እነርሱ ወደ ሥርዓቱ መሄድ አይፈልጉም። ይህ በእጅጉ ያስገርማል። ኦርቶዶክሳዊት ሃይማኖታችን ወርቅ ያለበትን መጽሐፍ ቅዱስን ትምስላለች። ከላዩ ሲታይ ወርቆቹ አይታዩም፥ ስለዚህም ዓለማውያን ብዙም አይመርጡትም። ኾኖም ግን ውስጡ ለሥጋ ሕይወታችን የሚያስፈልጉ ወርቆችም አሉት። ስለዚህ ዕይታችንን እናጥራ፡ እውነተኛውን የክርስትና ሕይወት ምርጫ እንረዳ። ከእኛ ስሜትና መረዳት ይልቅ እግዚአብሔርን ከልብ ለመስማት እንዘጋጅ፤ የየዕለት የሕይወት ምርጫችንን በፈቃደ እግዚአብሔር መሠረት ላይ እናቁመው። እግዚአብሔር የሚወደውን ፈቃድ ትተን ለምድራዊ ሕይወት ምቾት ብቻ ስንል የተቅበዘበዝንበት ጊዜ ይበቃል። የእውነት የእግዚአብሔርን ፈቃድ ማድረግ እንጀምር። እግዚአብሔር በቸርነቱ ዐይነ ልቡናችንን ወደ እውነተኛ ምርጫ ይምራልን።


እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ምልጃ ይርዳን አሜን!

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

30 Sep, 19:10


++++++#ኦርቶዶክሳዊ_ኑሮ#++++

"ሁል ጊዜም በተወሰነ ሰዓት የመንቃት ልምድ ይኑርህ። ምክንያተኝነትን ከአንተ አስወግድ። ከሰባት ሰዓት በላይ የእንቅልፍ ጊዜ አይኑርህ። ከእንቅልፍህም በነቃህ ጊዜ የተሰቀለውን ጌታችንን በመስቀል ላይ እንዳለ አድርገህ አስብ። ራስህን በብርድልስ ሙቀት አታታል። ከመኝታህ አፈፍ ብለህ ተነሣ። ለጸሎት ስትዘጋጅ ወገብህ የታጠቀ መብራትህ የበራ ይኹን። የጸሎት ልብስህን ልበስ። ይህ ጊዜ የዝግጅት ጊዜ ነው። በሠራዊት ጌታ በልዑል እግዚአብሔር ፊት ልትቆም መኾንህን አስብ። ሁል ጊዜም አእምሮህ የአባትህን የአዳምን የእናትህን የሔዋንን ውድቀት ያስታውስ። አምላክህን የሚያስብ በጎ ሕሊና እንዲኖርህ አባትህ አዳም ተጠልፎ በወደቀበት የሥጋ ሐሳብ፣ የሥጋ ኃጢአት ተጠልፈህ እንዳትወድቅ ፈጣሪህን ለምነው። በፊቱ የምትቆምበትን ጸጋ ብርታት እንዲሰጥህ ለምነው።

... በሕመምህ ጊዜ መጀመሪያ በእግዚአብሔር ታመን፥ አዘውትረህ የጌታ ሥቃይ ይታሰብህ። ሥቃይህንና ሕመምህን ያሥታግስልህ ዘንድ የምታውቀውን ጸሎት ያለማቋረጥ ጸልይ። በሕይወት ዘመንህ ሰላማዊና የተረጋጋ ሕይወት እንዲኖርህ ከፈለግህ ሕይወትህን ሊታመን ለሚችለውና አደራውን ለመጠበቅ ለሚቻለው ለእግዚአብሔር አስረክብ። ራስህን ለእግዚአብሔር አሳልፈህ መስጠት ካልቻልክ ፍጹም የኾነ መረጋጋትን አገኛለሁ ብለህ እንዳታስብ። ፍቅር የሚገባውን አምላክህን ውደደውና በፍቅር ኑር። (ታደለ ፈንታው (ዲ/ን)፣ መክሊት፣ 2004 ዓ.ም፣ ገጽ 90-99)።

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

26 Sep, 07:11


++++#ለሚፈሩህ_ምልክትን_ሰጠሃቸው#+++

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

+==+++++==+==+++++=++=++
መዝ 60፥4 ላይ ልበ አምላክ ዳዊት “ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው" በማለት የተናገረው በምሥጢር ክርስቶስ የሚሰጠንን የሐዲስ ኪዳን ልዩ ምልክት ሲያመላክት ነው። እግዚአብሔር የሚሰጠንን ልዩ ምልክት ገንዘብ ለማድረግ አስቀድመን ሊኖረን የሚገባው “ፈሪሐ እግዚአብሔር" ነው። ፈሪሐ እግዚአብሔር ወደ ጽድቅ መግቢያ በር ስለ ኾነ ልዩ ምልክትን ከእግዚአብሔር ለማግኘት የግድ የፈሪሐ እግዚአብሔርን ልብስ ውስጣችንን ማልበስ አለብን። ያ ልዩ ምልክት ቅዱስ መስቀሉ ነውና! መስቀል ዓለምን በሙሉ አምላካችን ክርስቶስ ወደ ራሱ የሳበበት የሰላም ዓርማ ነው። ይህ ምልክት ክርስቶሳውያን የመኾናችን ዋና መለያ ነው።

=++=+=+=+==+=++=++=+=+=+
እግዚአብሔርን የማንፈራ በፊቱ ቆመን የምንተቻች፣ እርስ በእርሳችን የምንናናቅ እንዴት ምልክቱን ልናገኝ እንችላለን? በፈሪሐ እግዚአብሔር ውስጥ እስካልኖርን ድረስ ምልክቱን ማግኘት አንችልም። ለሚሳለቁበት፣ መቅደሱን የሳቅና የስላቅ ስፍራ ለማስመሰል ለሚጥሩ፣ ትሕትና ለሌላቸው፣ ቅዱሳን መላእክት በመንቀጥቀጥ የሚያመልኩትን አምላክ በመቅደሱ ተገኝተው የሚተኙበት ሰዎች ምልክቱን አያገኙትም። “ለሚፈሩት" ሲል ለሚያመልኩት ማለት ነው። እናመልክሃለን ብለው በተግባር ግን ፈጽሞ የራቁ ሳይኾን በእውነት የሚያምኑበት ናቸው ልዩ ምልክትን የሚያገኙት። ወደዚህ ምልክት ውስጥ በፍቅር እስካልገባን ድረስ ፍቅርንና ሰላምን ገንዘብ ማድረግ አንችልም። በተግባራዊ ሕይወታችን ውስጥ የቀበርነውን መስቀል በንጹሐን መምህራን በኩል ቆሻሻውን አስነሥተን መስቀሉን እስካላወጣነው ድረስ መስቀል የሕይወት ምልክት ነው ብለን የምንፈክር እንጂ በእርግጥም መኾኑን በሕይወት መግለጥ ያቃተን ግብዞች መኾናችንን እናረጋግጣለን።
++=++==++==+++==++=++++=

ምልክት (Banner) የሚያመለክተው አምላካችን ክርስቶስ ዓለምን ለማዳን አንድ ጊዜ የገባበት መቅደስ የተባለውን ቅዱስ መስቀልን ነው። መስቀል ለክርስትናችን መለያ ምልክት ነው። ክርስትናን ከመስቀል ነጥሎ ለማየት መሞከር ማለት ቤተክርስቲያንን ከክርስቶስ ነጥሎ ለማየት እንደ መፈለግ ነው። መስቀል የቤተክርስቲያን ሙሽራ ክርስቶስ ቅድስት ቤተክርስቲያንን በደሙ ሲያጭ ፥መታጨቷን ለመግለጽ ያኖረላት ምልክት ነው። ቤተ ክርስቲያን ጉዞዋ በሙሉ ወደ ድኅነት የሚመራ ነው። በምድር ላይ በምእመናን ልብ ውስጥ መስቀል እየሳለች ሰማያዊቷን መንግሥት ታጓጓናለች።
=+=+=+=+=+=+=+=+=+=+=+=+

መስቀልን በአንገታችን ላይ ማድረጋችን የክርስቶስ ሙሽሪቶች መኾናችን ይታወቅ ዘንድ ነው። አንዲት ሴት ከታጨች በኋላ ሌላ ወንድ መፈለግ የለባትም፤ ሌላም ወንድ እንዲፈልጋት የሚያደርግ ሥራ መሥራት የለባትም። ቤተክርስቲያን መስቀሉን ከክርስቶስ በምልክትነት ከተቀበለች በኋላ ሌላ ነገር አትፈልግም። መስቀል የሕይወቷ ዓርማ አድርጋ ስትታወቅበት ትኖራለች እንጂ። መስቀል በምድር ያለችው ቤተ ክርስቲያን የሚደርስባትን መከራ የሚያመለክት ነው። መከራ ደግሞ የክርስትና ሕይወት መልክ ነው። ብዙዎቻችን የዚህ መሠረታዊ ሐሳብ ተቃራኒ የኾነ ሕይወት ነው ያለን። ከክርስቶስ መከራ ይልቅ የዘፋኞች ዘፈን ልባችንን የማረከብን፤ ከክርስቶስ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ይልቅ የዚህ ዓለም ተራ መብልና መጠጥ የሚያረካን ከክርስትናው እውነተኛ መንገድ እጅግ የራቅን ነን። ስለዚህ ምልክቱን ስንተው አጋንንትም መጥተው አደሩብንና ከሙሽራው ፈቃድ ለዩን።

+=+=+=+=+=+=+=+=+=+=+=++
ምልክት የተባለው በቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳርያ “የክርስቶስ ደም" ነው ይላል። በእርግጥ ይህን ደም ምልክት አድርገን የምንኖር ከኾነ ጠላት ድል ያደርገን ዘንድ አይችልም። መስቀል ደግሞ በዚህ ትርጒም የምልክት ምልክት ነው። የክርስቶስ ደም የፈሰሰበት የሕይወት ዕፀ ነውና። በመስቀል ላይ የተቆረሰውን የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋ የፈሰሰውን ክቡር ደም እናይበታለን። መስቀሉን ስንስም የምንስመው ዕፅነቱን ብቻ አይደለም ይልቅስ በዚያ ላይ ከሞት የሚያድነን ንጹሕ የክርስቶስን ደም ነው። ስለዚህ በመስቀል ዐይንነት ክርስቶስን እናየዋለን። በምልክቱ በኩል ምልክቱን የሰጠንን አምላክ ደሙን ሲያፈስልን ተመልክተን ፍቅሩን እናደንቃለን።

=+=+=++=++++==+===+==+++

“ለሚፈሩት ምልክትን ሰጠሃቸው" የተባለውን ብዙ ሊቃውንት የእስራኤላውያን በኲር በግብጽ ምድር የተረፈበትን የፋሲካውን በግ ደም ነው ይላሉ። ያ ምንም የማያውቀው በግ ደሙ በቤቱ ጉበን ላይ በመቀባቱ ምክንያት የእስራኤል በኩራት ከዳኑ ሕያው በግ ክርስቶስ ቤት አድርጎ በቀራኒዮ በገባበት መስቀል ላይ ባፈሰሰው የሚናገር ደም'ማ እንዴት የበለጠ ድኅነት ይገኝ ይኾን? በኩራችን ክርስቶስን ከልባችን ውስጥ ለማጥፋት የሚተጉትን ክፉ አስተሳሰቦች በሙሉ እንዋጋቸው። ኹል ጊዜም ነገረ መስቀሉን ምልክት አድርገን የአጋንንትን ሐሳብ እናርቅ፤ በእግዚአብሔር ቃልም መሠረት ሳንሠቀቅ መከራ መስቀሉን ለመሸከም እንትጋ። የእውነት መኖር ከጀመርን ሕይወታችን በራሱ የመስቀል ሕይወት ይኾናል፤ ብዙ ግራ የተጋቡ ሰዎችንም የመሰቀል ሕይወትን ጣዕም አቅምሰን ከስሕተታቸው መመለስ እንችላለን። በመኾኑም ምልክታችንን ከጥልቅ ውስጣችን ሕያው አጥር አበጅተን መጠበቅ አለብን።

“እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ አደረሳችሁ"

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

21 Sep, 20:21


ዲያቆን ዮሐንስ ጌታቸው || (አቤል እና ቃኤል) ወንድምህ አቤል ወዴት ነው?
https://youtube.com/watch?v=uDULKeHpZ_o&si=Kwq35tIClKd8fj7A

ዮሐንስ ጌታቸው

21 Sep, 04:10


++++++++#ግብዝነት#+++++++++

ግብዝ ሰው (አስመሳይ ሰው) በድብቅ እግዚአብሔር የለም ብሎ የሚያምን ነው፤ እግዚአብሔር አለ ብሎ የሚያምን ቢኾን ኖሮ፣ እርሱን ፊት ለፊት ለማታለል ባልደፈረ ነበር። REFERENCE A Puritan Golden Treasury, compiled by I.D.E. Thomas, by permission of Banner of Truth, Carlisle, PA. 2000, p. 151። በሕይወታችን አስመሳይነትን ለብሰን የምንኖር ከኾነ አኗኗራችን ድራማ ይኾንብናል። የሚኾነውና እንዲኾን የምንፈልገው እርስ በእርሱ ይምታታብናል። መልካም መባል እጅግ የምንፈልግና በሰዎች ዘንድም እንደዛ እንድንባል የሚያደርጉ ነገሮችን በማስመሰል የምንተውን፡ ከእውነተኛ የመልካምነት ሕይወት ግን ፈጽሞ ራቅ ያልን ጥቂት ሰዎች አይደለንም።

ግብዝነት ተግባራዊ የኾነ የመጠራጠር ሕይወት ነው። እግዚአብሔርን በአንደበታችን ላንክደው እንችላለን፣ በሕይወታችን ውስጥ ሰዎች እርሱን የምናመልክ አድርገው እንዲያስቡ አድርገን ልንተውን እንችላለን፡ በድብቅ ወይም በስውር በውስጣችን ያለው ግን ድፍረትና ትዕቢት፡ ራስን ማክበር ስለ ኾነ እግዚአብሔር ከሚፈቅደው ውጪ ኾነን እንገኛለን። የዚህ ኹሉ መነሻው ከእውነት መንገድ መውጣትና እውነትን በተግባራዊ የሕይወት ክፍላችን ውስጥ መግፋታችን ነው። ለዚህም ነው ሕይወታችን ከጥፍጥና ይልቅ ምሬት እንዲስማማው ያደረግነው።

መልካም የኾነው እርሱ በአርአያውና በአምሳሉ ፈጠረን እኛ ግን በፈቃዳችን ጥመት ምክንያት ሌላ አርአያን ተላበስን። ውስጣችንን በዚህ ዓለም ፍቅር አሰከርናት፥ የእግዚአብሔር የኾነውን በጎ ነገር ከተግባራዊ ሕይወታችን አራቅነው፥ ራሳችን ላይ በክፉ ዝንባሌያችን ምክንያት የዝሙትን እሳት አነደድን። ራሳችንም ባነደድነው የዝሙት እሳት ተቃጠልን፣ ረከስን፣ ቆሸሽንም፤ ኾኖም በሰዎች ዘንድ ንጹሕ አድርገን ራሳችንን በማሳየት ጻድቅ ተሰኘን፥ ይህ በእጅጉ አስገራሚ ነው።

ግብዝነታችን ከማደጉ የተነሣም፥ ግብዝ መኾናችንም ተረሳን፥ ውስጣችን በከንቱ ውዳሴ፥ በዚህ ዓለም ክብር ገነነች። ሰዎችን ከሰዎች አበላለጥን፥ ፍትሐዊነትን ከአእምሮችን በግብዝነታችን ብሩሽ አጠብናት፥ ፍትሕ ርትዕ የምትመስል ሌላ አዲስ ነገር አበጃጀን። ስለዚህም የማንሰማ፥ የማናስተውል፥ አፍቅሮተ ሰብእ የሌለን፥ በራስ ወዳድነት ጽናት የታጠርን፥ ከእግዚአብሔር ይልቅ ለዓለም የተመቸን፥ በውስጣችን ፈጽሞ የረከስን፥ ወደ እውነተኛ ሕይወት የመመለስ ፍላጎትና ወኔያችን የሞተብን ስንት ነን? እጅግ ብዙ! እግዚአብሔር በቸርነቱ ዓይነ ልቡናችንን ያብራል።

መፍትሔውም ወደ እውነት ለመመለስ ኹል ጊዜ ሳያቋርጡ መትጋት ነው። እውነት የምትሽሞደሞድ አይደለችም፥ በግል ስሜት የምትሠራም አይደለችም፥ ይልቅስ ከእግዚአብሔር ጋር ባለን አንድነት የምትረዳ ልዩ ሀብት ናት። ጌታ ራሱ "እኔ መንገድ እውነትና ሕይወት ነኝ" እንዳለ፥ እርሱ ባሳየን የአርአያነት ተግባራዊ የኾነ የእርስ በእርስ ፍቅር መንገድነት፥ እውነት የኾነውን የእርሱን ቃል አክብረን፥ ወደ ሕይወት መግባት አለብን። መንገዱን ካላገኘን እውነትን ሕይወትንም ማግኘት አንችልም። ስለዚህ ከግብዝነት ለመውጣት ስለ እውነት በእውነት መኖር መጀመር አለብን። በእውነተኛ የሕይወት ጎዳና ውስጥ እውነተኛ ፍቅር እና እውነተኛ ጣዕም ያለው ሕይወት አለና። ቆም ብለን አኗኗራችንን እንመርምር፥ የገፋናትን እውነት እንመልሳት፥ የጠላናትን አንድነት እንፈልጋት፥ ይህን ጊዜ የምናመልከው አምላክ ከግብዝነት እሳት ያድነናል። ይህ እሳካልኾነ ግብዝነታችንና ተመጻድቋችን ለማናስበው ትልቅ ችግር ይዳርገናል። ማስመሰላችንም ሕይወታችንን መራራና ርባና ቢስ ያደርግብናል፥ የሕይወት ብርሃንም ይነሣብናል። ይህን ኹሌም በማስተዋል ወደየ ልቡናችን እንመለስ!

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

19 Sep, 11:26


የማልገባ ልኾን እችላለሁ ብለን አርቀን አይተን እናለቅሳለን። ራሳችንን ስናይ ከማንም በእርግጠኝነት የምናንስ መኾናችን ይረዳናል። ዘፈን የሚዘፍኑ፣ የሚያመነዝሩ፣ የሚሰርቁና መሰል ድርጊቶችን የሚፈጽሙ ኹሉ ከእኛ የሚበልጡ እንደ ኾኑ ከልብ ይሰማናል። ፈያታዊ ዘየማን ከዚያ ኹሉ የሽፍትነት ሥራ በአንዴ ተላቆ የክርስቶስ የመስቀል ላይ ወዳጅ መኾኑን ኹሌም እናስተውላለንና!! ራስን በማየት መኖር ውስጥ ራስን ማካበድ፣ የተለየው ነኝ ብሎ ማሰብ፣ ራስን ማክበር፣ ራስን ከሌሎች ኹሉ ከፍ ከፍ አድርጎ መቍጠር፣ አይመጥነኝም፣ አትመጥነኝም እያሉ መዘማነን ኹሉ አይኖርም። ራሱን የሚያይ ሰው ኹሉን ንጹሕ አድርጎ ያያል። መጽሐፍ "ለንጹሕ ኹሉ ንጹሕ ነው" እንዲል። አመንዝራው፣ ሌባው፣ ጨካኙ፣ ሌላውም ኹሉ ከእርሱ የተሻሉ እንደ ኾኑ አድርጎ ይቈጥራልና።

++++++ ++++++++ ++++++++++

በቃ ዋናው መፍትሔ ራስን ማየት ነው። ራሳቸውን አይተው የወደቁ እነማን ናቸው? አጥርቶ በሚያይ በእግዚአብሔር ፊት ለፍርድ ከመቆማችን በፊት ኹል ጊዜ ራሳችን ራሳችንን እያየን በራሳችን ላይ እንፍረድ። እኔ ነኝ ዋናው ኃጢአተኛ ከልባችን እንበል። አባ ሙሴ ጸሊም ለታላቅ ክብር የበቁት ራሳን በማየት መሰላል ላይ ወጥተው ነው። በኃጢአተኛ ሰው ፍረድ ሲባሉ የራሳቸውን ኃጢአት ማሳያ በማዳበሪያ አፈር ተሸክመው፥ እርሱንም ቀድደው፥ ለራሳቸው ከልባቸው ይህ የእኔ ኃጢአት ነው፥ ማዳበሪያውን መልቶ ይፈሳል አሉ። እንግዲያውስ እንዴት በሌላው ይፍረዱ!! እርሳቸው ራሳቸውን አይተው ሌሎችንም ወደ ራሳቸው እንዲመለሱ አደረጓቸው። ማንኛውንም ችግር ለመፍታት ወደ ራሳችን መመለስ አለብን። ራስን በማየት ውስጥ ራስን ማወቅ አለ። ራስን በማወቅ ውስጥ በራስ ላይ መፍረድ አለ። በራስ መፍረድ ውስጥ ደግሞ ተአምኖተ ኃጢአት አለ። ኃጢአትን በማመን ውስጥ ደግሞ አንብዓ ንስሐ አለ። በአንብዓ ንስሐ ውስጥ የእውነት የኾነ ጸጸት አለ። በዚህ መንገድ ከኾነ ከዲያብሎስ ወጥመድ እንተርፋለን። ችግሩ፥ ራሳችንን ባለማየት ስለ ራሳችን የደነቆርን ኾነን ሳለ ሌላውን እናማለን፣ እንንቃለን፣ እንሰድባለን፣ እናንቋሽሻለን፣ እንጠላለን፣ በሌላው እንመቀኛለን፣ እንኲራራለን ... ብቻ ብዙ እናደርጋለን። ይህ በእውነቱ አሳዛኝ ደረጃ ላይ መድረሳችንን የሚያመለክት ነው። ስለዚህ ወደ ራሳችን እንድንመለስ አምላካችን ይርዳን አሜን!

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

19 Sep, 11:26


+++++++#ወደ_ራስ_ማየት#++++++++

ወደ ራስ መመልከት የራስን ኃጢአት ወደ ማሰብ ያመጣል። ወደ ራስ መመልከት በውስጥ የሚንቦገቦገውን የዝሙት እሳት ለማብረድ ያግዛል። ወደ ላይ ለመውጣት ራስን ከመመርመር እንጀምር። ብዙ ችግሮች ችግር ኾነው እየቀጠሉ ያሉት ወደ ራሳችን ማየት ስላቆምን ነው። እኛ የሚመስለን እኛነታችንና እየኾን ያለው እኛነታችን ይለያያል። ወዳጆች ሆይ ወደ መልካም መንገድ መግባት ትፈልጋላችሁን? እንግዲያውስ ውስጣችሁን መርምሩ። ለራስህ ራስህን ሐኪም አድርገህ መርምር። ያልኾንከውን የኾንክ አይመስልህምን? ጥሩ ሰው እንደ ኾንክስ አይሰማህምን? ይህ ኹሉ ምንጩ ወደ ራስ ማየት ማቆምህ መኾኑን አስተውል! ራሱን የማያይ ሰው አዎንታዊነት አይኖረውም፤ በሰዎች ላይ ያየውን ነገር ቶሎ ብሎ ሌላ ትርጒም እየሰጠ በውስጡ ይሰቃያል፤ ወይም ከሌላው ይልቅ ራሱን የተሻለ እንደ ኾነ አድርጎ ያስባል።

ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ "ካህናትን በሚገባ አክብር። ለመዓርጋቸውም ክብር ስጥ፤ ሥራቸውን አትመርምር። በመዓርጉ ካህን መልአክ ነውና። በሥራው ግን ሰው ነው። በእግዚአብሔር ቸርነት ቄሱ በሰው ልጆችና በእግዚአብሔር መካከል ያለ አማላጅ ነው። የሰዎችን ስሕተት አትፈልግ። የወዳጅህን ኃጢአት አትግለጥ። የጎረቤትህን መጥፎ ጎን በንግግርህ አውጥተህ አትድገመው። በፍጥረት ላይ ፈራጅ አልኾንክምና። በምድር ላይ ገዥ አይደለህምና። ጽድቅን ካፈቀርክ ራስህን ገሥጽ። ለራስህ ኃጢአቶች ፈራጅ ለመተላለፍህ ብቻ ተነሳሒ ኹን። የሰዎችን መጥፎ ምግባር በተንኮል አትመርምር። ... በወዳጅህ ላይ ከተቆጣህ በእግዚአብሔር ላይ መቆጣትህ ነው። በልብህ ቍጣን ከተሸከምክ በጌታ ላይ መነሣትህ ነው። ድፍረትህም ከፍ ይላል። በክፉ ቅናት ከገሠጽክም ግሣጼው ኹሉ የክፋት ነው። በጎነት በውስጥ ከኖረ ምንም ጠላት በምድር ላይ አይኖርህም። እውነተኛ የሰላም ልጅ ከኾንክ በማንም ሰው ላይ ቍጣን አትቆሰቁስም። መቆጣትን የምታፈቅር ከኾነ በክፉው ነገር ተቆጣ ከዚያን ያንተ ኾኖ ታገኘዋለህ። የምትፈልገው ጦርነትን ለማወጅ ከኾነ ሰይጣን አማካሪ ኾኗል። ለመቆጣት ብትመኝ በአጋንንት ላይ ተቆጣ። በአርአያ ሥላሴ የተፈጠረውን ሰው የምትሳደብ ከኾነ የነፍሰ ገዳይ ቅጣት ይገባሃል። ሰውን ሙልጭ አድርጎ መሳደብ የእግዚአብሔርን አርአያ መሳደብ ነው" እንዲል። (Nicene and post Nicene Fathers second series V 13)።

++++++ ++++++++ ++++++++++

ለሀገራችን ጥፋትና ክፉ ሴራ ኹሉ መነሻው እኔ ነኝ፣ እኔ ስለ በደልኩና ከበደሌም መመለስ ስላልፈለግሁ ነው እንበል። ክርስቶስን ሩቅ ቦታ አንፈልገው እርሱ እዚሁ አጠገባችን ነው። በእርግጥም ራሳችንን ማየት ስንጀምር ድፍረታችን የት እንደ ደረሰ ይገባናል። በልምድ ደጋግመን እየፈጸምን ያለው ኃጢአት ኹሉ ተነቅሎ የሚወድቀው ራሳችንን ስናይ ነው። እልህኝነታችን ዋና ምንጩ ራሳችንን ማየት ማቆማችን ነው። በብዙ ደባ የተተበተብነው ከወደቅንበት የአስተሳሰቅ ውድቀት የተነሣ ነው። የአስተሳሰብ ውድቃታችን ዛሬም እንደ ትናንቱ ለምን የኾነ ይመስላችኋል? ራሳችንን ከጥልቅ ልቡናችን ስለማናይና ወደ ስንፍና ሕይወት ገብተን ከሚገጥመን ዝንጋዔ የተነሣ ነዋ! መልካም የኾነውን ወዲያው እንረሳለን፥ ምክንያቱም ራሳችንን አናይማ! የጉዳታችን ዋና ምንጭ ራስን አለማየት ነው።

++++ ++++ ++++++++ ++++++++

ማርያም ኃጥእት ለጽድቅ የበቃችው ራሷን ከማየት ጀምራ ነው። ራስን ማየት ወደ ንስሓ የሚያስገሰግስ ታላቅ መንገድ ነው። ማርያም ግብጻዊት በመስታወት ፊት ቆማ ውጫዊ መልኳን ታይ የነበረችው ወዲያው ወደ ራሷ ውስጣዊ ማንነት መለስ ብላ ስትመረምር እጅግ አስጠላታም ኾና አገኘችው። ራሷን ራሷ ጠላችው። የኃጢአቷ ክምር የነፍሷን መልክ አክስሎታልና። ስለዚህ ከዓይኖቿ የማይቋረጡ እንባዎች እንደ ምንጭ ይፈልቁ ጀመር። እንግዲህ የዚህ መነሻው ራስን ማየት ነው። ራስን ማየት ቅዱስ ጴጥሮስን ንስሓ እንዲገባው እንዳደረገው አስተውል። ታላቅ ሐዋርያ የኾነ እርሱ ራሱን ማየት ባቆመ ጊዜ አምላኩን አላውቀውም ብሎ ክዶት ነበርና። ወደ ራሱ ሲመለስ ግን የፈጸመውን በደል ተረድቶ የንስሐ እንባን አፈሰሰ። ምናልባት በሕይወታችን ውስጥ ክርስቶስን አላውቀውም ብለን ይኾን? በሕይወታችን ውስጥ የክርስቶስን ፈቃድ የማንፈጽምና የየግል ስሜታችንን ለማርካት ብቻ የምንኖር ከኾነ፡ በእርግጥም ክደነዋል ማለት ነው! ከሚመጣብን መከራ ለመትረፍ ብለን የዘለዓለማዊ ሕይወት ምንጭ የኾነውን ረስተን እየተቀመጣጠልና እያሽካካን የምንኖር ከኾነ ውጤቱ መራራ ነው የሚኾንብን! እንግዲህ ትክክል ያልኾነን ነገር መርጠን ትክክል የኾነውን ትተን የምንኖር ልብ እንበል! ምርጫችን የዘመናት ኀዘን ምክንያት ሊኾነን ይችላልና። ስለዚህ ወደ ራሳችን እያየን በፈሪሐ እግዚአብሔር ኾኖ ለመኖር እንወስን።

+++++ +++++++ +++++++++++++

ብዙ ማውራት ስለምንወድ ስለ ራሳችን ድክመት ማየት አቃተን። ከምንነቅፈው ሰው የበለጠ የሚያስነቅፍ ነገር እንዳለብን አልገባ ያለን ራሳችንን ሰለማናይ ነው። የቅዱሳን ሕይወት መነሻውም መድረሻው ራስን በማየት ላይ የተመሠረተ ነው። ራስን ማየት ራስን ወደ መናቅ፣ ራስን መናቅ ራስን ወደ መካድ፣ ራስን መካድ የክርስቶስን መስቀል ወደ መሸከም ልዕልና ያደርሰናል። የትሕትና ዋናው መግቢያው ራስን ማየት ነው። ጌታችን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ያደረጋቸው የአርአያነት ሥራዎች በሙሉ እኛን ለማንሣትና ራሳችንን እንድንመረምር ለማድረግ መኾኑን ልብ እንበል። ሰማዕታት ዓለምን ንቀው ደማቸው እስኪፈስ መታገሣቸው እኛን ለማገዝና ራሳችንን እንድናይ ለማስቻል ነው። መነኮሳት ስለ ክርስቶስ የሚመነኩሱት እኛ ቢያንስ ሥርዓት ይዘን የእነርሱን ታላቅነት በእኛ ታናሽነት አንጻር እንድናይ ለማበርታት ነው። ብርቱዎቹን ስናይ ወደ መቍረጥ እንወጣለን፤ ወይኔ! እኔ ደካማው ዓለም ላይ ተጣብቄ ያማረ የጣመ የምበላ ብለን በክርሰቶስ ፍቅር እንድንቃጠል መስታወት ኾነው ሊያሳዩን ነው። እኔ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ብዬ ትንሽዬ ነገር መተው ሲያቅተኝ ከኔ ወገን ያሉ ግን ኹሉን ትተው ተከተሉት፣ እኔ ልብሴ አላማረም ብዬ ስጨነቅ እውነተኞቹ መናኞች ግን ልብሳችን ክርስቶስ ነው ብለው ማረፊያቸው እርሱን አደረጉ። እንዲህ እያልን በጥልቀትና በተመስጦ ስንመረምር ምን ያህል የእውነት ሩቅ መኾናችንን መረዳት እንችላለን። ከዚያን ኹሌም ራሳችንን ያነስን እንደ ኾን ቈጥረን መኖር እንጀምራለን።

++++++ +++++++ ++++++++++++

ጌታችን ዝቅ ብሎ የሐዋርያትን እግር ሲያጥብ ይሁዳ ራሱን ማየት የማይፈልግ በመኾኑ ምክንያት ዝም ብሎ ታጠበ። ጌታ ዝቅ ያለው በይሁዳ ልብ ውስጥ ያለው የገንዘብን ፍቅር ዝቅ ለማድረግ ነበር፤ ይሁዳ ግን ግትር በመኾኑ ምክንያት በፈቃዱ ከሕይወት መንገድ ወጣ። በጌታችን እጅ የታጠቡ የይሁዳ እግሮች ወደ ጽድቅ ከመገሥገሥ ይልቅ በተቃራኒው የሚገሠግሡ ኾኑ። ጌታችን የይሁዳን እግር ሲያጥብ ይሁዳ የራሱን ልብ በፈቃዱ ስለ ዘጋው ሳይታጠብ ቀረ። ጌታችን ልቡናችንን የሚያጥብልን በእኛ ፈቃድ ላይ ተመሥርቶ ስለ ኾነ የይሁዳን ደንዳናነት ተረድቶ ዝም አለው። የምንቀባጥረው፣ ራሳችንን የምናዘማንነው በእርግጥም ራሳችንን ስለማናይ ነው። ራሳችንን ማየት ስንጀምር ባዶ መኾናችን ይገባናል። ኃጢአት የሚሠሩ ሰዎችን ስናይ ይህ ሰው ንስሓ ገብቶ ይመለሳል እኔ ግን ነገ ኃጢአት ሠርቼ ንስሓ

ዮሐንስ ጌታቸው

16 Sep, 10:26


) ይህ ጎርጎርዮስ የተባለ ሊቅ የሰናፍንጭን ቅንጣት በኢየሱስ ክርስቶስ መስሎ አስተምሯል። በአትክልት ስፍራ በመቀበሩ የሰናፍንጭ ቅንጣት ነው፤ በመነሣቱ ዛፍ ነው። በመሞቱ የሰናፍንጭ ቅንጣት ነው፤ ሞትን ድል አድርጎ በመነሣቱ የሰናፍንጭ ዛፍ ነው። በሥጋው ብቻ የሰናፍንጭ ዘር ነው፤ በግርማዊ ኃይሉ ግን የሰናፍንጭ ዛፍ ነው። በእኛ በመታየቱ የሰናፍንጭ ቅንጣት ነው፤ ነገር ግን ከሰው ልጆች ሁሉ ያማረ በመኾኑ የሰናፍንጭ ዛፍ ነው። የዚህ ዛፍ ቅርንጫፎች የተቀደሱ ስብከቶች ናቸው። ... በዚህ ዛፍ ላይ ባሉ ቅርጫፎች ላይ ርግቦች ያርፉበታል። ርግብ የተባሉት የንጹሐን ነፍሶች ናቸው፤ ከዚህ ምድር ሐሳብ ተለይተው በበጎ ምግባራት ክንፍ ከዚህ ዓለም ተጋድሎ በኋላ ወደላይ ይወጣሉ።" በማለት እጅግ ድንቅ ምሥጢር አስቀምጦልናል። የሰናፍንጭ ቅንጣት በተባለው የጌታችን ሞት አመካኝነት በኋላ ላይ የሰናፍንጭ ዛፍ የተባለውን ትንሣኤውን እንረዳለን። አይሁድ ክርስቶስ እንዲገደል ሲያደርጉ የሚነሣ አልመሠላቸውም፤ ምክንያቱም እንደ ሰናፍንጭ ቅንጣት ትንሽና ቀላል አድርገው አስበውታልና ነገር ግን እነርሱ ከናቁት ሞት ዛፍ የተባለው ትንሣኤ ይበቅላልና።

ይህም ብቻ ሳይኾን የክርስቶስ ሞቱና ትንሣኤው የእኛንም ሞትና ትንሣኤ አመልካች ነው። አባታችን አዳም ከነበረው ታላቅ ክብር ዕፀ በለስን በልቶ እንደ ሰናፍንጭ ቅንጣት ከፍጥረት ኹሉ አንሦ ሞትን ገንዘብ አደረገ። ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ አዳምን ያሳተው ለዘለዓለም ከእግዚአብሔር ለይቶ ለማስቀረት ነበር። የኾነው ኾኖ አምላካችን ክርስቶስ ግን በመርገመ ሥጋና ነፍስ ጎስቁሎ በርደተ መቃብር ላይ ርደተ ሲዖልን ገንዘብ አድርጎ የሚሰቃየውን አዳምን ያለበት መቃብር ድረስ ገብቶ እንደ ሰናፍንጭ ዛፍ ክብሩን በዓለም ትልቅ አደረገው። ሰናፍንጭ ክርስቶስን የሚክል ሲኾን ውጩ ቀይ መኾኑ መለኮትን የሚያሳይ ነው፤ ውስጡ ነጭ መኾኑ መለኮት የተዋሐዳት ሥጋ ፀአዳ ወይም ምንም ዓይነት የኃጢአት ትንታ የሌለበት ንጹሕ መኾኑን የሚያመለክት ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ቀዩ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ሲል የተቀበለውን የደም መከራ የሚያሳይ ሲኾን፤ ነጭ መኾኑ በእርሱ መከራ እኛ የምናገኘውን ክብር የሚያመላክት ነው። እንግዲህ በአጭሩ ሰናፍንጭን ስናስብ እነዚህን መልእክታት ማሰብ ብንችል መልካም ነው።

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

16 Sep, 10:26


++++++##የሰናፍንጭ_ቅንጣት##++++++

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።


የሰናፍንጭ ነገር በወንጌል በተደጋጋሚ ተነግሯል። ማር 4፥31፣ ማቴ 13፥31፣ ሉቃ 13፥18። በአጭሩ ከሰናፍንጭ ቅንጣት የምንማረውን መልእክት እናያለን። ይህ የሰናፍንጭ ቅንጣት ጉዳይ በብዙ ሊቃውንት ዘንድ ትኩረት ያገኘ ጉዳይ ነው። እግዚአብሔር ለእኛ ስለሚራራልን እኛን ለማገዝ በብዙ ኅብረ አምሳል የገዘፈውን የሃይማኖት ምሥጢር ራሱ አምላካችን የሰውን ሥጋና ነፍስ ነሥቶ በተወለደ ጊዜ አስተምሮናል። ጴጥሮስ ክርስቶሎጎስ የተባለው ሊቅ የሰናፍንጭ ቅንጣትን አስመልክቶ ያስተማረውን ቀንጨብጨብ አድርገን እንመልከተው። የሰናፍንጭ ዘር ከኹሉም ወደሚልቅ ቁጥቋጦ ያድጋል። ... የሰናፍንጭ ቅንጣት የአማኞች ተስፋ ድምር ነውን? ... ይህቺ ከኹሉ የምታንሰው የእግዚአብሔር ፍጥረት ከጠቅላላው ሰፊ ዓለም ትበልጣለች። ... በእርግጥ የሰናፍንጭ ዘር የእግዚአብሔር መንግሥት ምሳሌ ናት። ... ልክ እንደ ሰናፍንጭ ቅንጣት በድንግል ማኅፀን ገነት ውስት ተተከለ፤ ወደ መስቀል ዛፍም አደገ፤ የዚህም ዛፍ ቅርንጫፉ በዓለም ኹሉ ይዘረጋል። ... ክርስቶስ ንጉሥ ነው፤ ምክንያቱም የሥልጣናት ኹሉ ምንጭ ነውና። ክርስቶስ መንግሥት ነው፤ የንግሥና ክብር በሙሉ በእርሱ ዘንድ ነውና። ... ክርስቶስ የሰናፍንጭ ዘር ነው፤ ምክንያቱም የመለኮትን አለመወሰን ከትንሽየው ሥጋና ደም ጋር አስማምቷልና። ከዚህ ተጨማሪ ምሳሌ ትሻላችሁን? ክርስቶስ ኹላችንንም በእርሱ ለማደስ ኹሉንም ኾኗል። " እያለ ያመሰጥራል። (Commentary by Peter Chrysologus Sermon 98: PL 52, 474-76) ።

በዚህ የሊቁ ትምህርት ውስጥ ብዙ ቁም ነገሮችን መማር እንችላለን። ከዚህ የሰናፍንጭ ቅንጣት ዕድገትን እንማራለን። አንድ ክርስቲያን ኹል ጊዜ በእምነቱም ኾነ በመንፈሳዊ ሕይወቱ ማደግ አለበት። ከማይታየው እምነት እስከሚታየው እምነት ከፍ ማለት አለበት። ከተራ ምእመንነት እስከ ደም ሰማእትነት ከፍ ማለት ያስፈልጋል። በኃጢአት ምክንያት እንደሰናፍንጭ ቅንጣት ያነሰው በጎነታችንን በንስሓና በተጋድሎ በማሳደግ መትጋት እንዳለብን መማር እንችላለን። ይህም ብቻ ሳይኾን የክርስቲያኖችን በአንድነት የመጸለይና የመትጋት ተስፋ ማየት እንችላለን። በአንድነት ስንጸልይ፣ ስንጾም ተስፋችን ከሰናፍንጭ ቅንጣትነት ወደ ዛፍነት ያድጋል። ስለዚህ ተስፋን ማጣት ድል እንዳያደርገን በአንድነት መትጋትና እግዚአብሔርን መለመን አለብን። ከዚህ ኹሉ በላይ በዚህች የሰናፍንጭ ቅንጣት የክርስቶስን በቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን መፀነስ እንማራለን። ሰማያዊው ንጉሥ እንደ ሰናፍንጭ ቅንጣት በድንግል ማሕፀን መፀነሱ እንደ ምን ይደንቅ ይኾን! የእርሱ ፅንሰት በማሕፀን እየተቆራኘ ፅንሶችን የሚያስጨንቀውን ሰይጣንን ቀጥቅጦ ለማጥፋት ነው።

የሰናፍንጭ ቅንጣት ትንሽ እንደ ኾነ የጌታን ከድንግል የመወለድ ነገር አምላክነቱን የሚክዱ አይሁድ አሣንሰው በማየት የፍጡር ልጅ ፍጡር አሉት። ይህቺ የሰናፍንጭ ቅንጣት የተባለችው የጌታን ፅንሰት የምታመለክት ቅንጣት ወደ ሰናፍንጭ ዛፍነት (ወደ መስቀለ ክርስቶስ) በማደግ ዓለምን በሙሉ ተሸከመች። የሰናፍንጭ ዛፍ የቅዱስ መስቀል ምሳሌ ነው። መስቀል ዓለምን ለማዳን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የገባበት መቅደስ ስለ ኾነች ሽፍታው ጥጦስ በቀኝ በኩል የተሰቀለው ወንበዴ በላዩአ ላይ ዐረፈባት። የክርስቶስ የማዳን ነገር ከፅንሰት የሰናፍንጭ ቅንጣትነት ተነሥቶ ወደ መስቀል የሞት ካሣነት አደገ። ብዙ ተጠራጣሪዎችም በዚህ የመስቀል ዛፍ አማካኝነት ወደ እውነት መንገድ እንደ ወፍ እየበረሩ መጥተው ዐረፉበት። ከሰናፍንጭ ቅንጣትነት ወደ ዛፍነት ማደግ ማለት የሰናፍንጭ ቅንጣት የተባለው ሰውነት በተዋሕዶ ምሥጢር ከአካላዊ ቃል ጋር አንድ በመኾን በሰናፍንጭ ዛፍነት መገለጥ ነው። በሌላ አገላለጽ ትንሿ የሰውነት አካልና ባሕርይ በተዋሕዶ አማካኝነት ትልቁን የመለኮትን ባሕርይና አካል ገንዘብ በማድረግ እጅግ መክበሯን መናገር ነው። ትስብእት የሰናፍንጭ ቅንጣት ናት፤ መለኮት የሰናፍንጭ ዛፍ ነው። የኹለቱ ተዋሕዶ ማለት የሰናፍንጭ ቅንጣት ቅንጣት መኾኗ እንዳለ ኾኖ ዛፍነትን ታስገኛለች። የሰናፍንጭን ዛፍ ቅንጣት ነው ማለት አይቻልም፤ ቅንጣቱም የለም ዛፉ ብቻ ነው ማለትም አይቻልም። አምላካችን እግዚአብሔር በቅንጣት የተመሰለውን የእኛን አካልና ባሕርይ በተዋሕዶ ከእርሱ የማይወሰን ማንነት ጋር አስማማው! ይህ በእውነቱ እጅግ አስደናቂ ምሥጢር ነው።
__ ___
ይህቺ የሰናፍንጭ ቅንጣት ሌላም ምሥጢር አላት፤ (commentary from the Navarre Bible) "ተካዩ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ የሚተክልበት ቦታ ዓለም ነው። የሰናፍንጭ ዘር የወንጌል ስብከትና የቤተክርስቲያን ምሳሌ ነው።" በማለት የሚያብራሩ አሉ። ከትንሽ የሰናፍንጭ ቅንጣትነት ወንጌልና ቅድስት ቤተክርስቲያን በዓለም ኹሉ ትሰፋለች። ዓለም በሙሉ የእውነትን ወንጌል ይሰበካል፤ የቅድስት ቤተክርስቲያንንም ክብር ያውቃል። በብዙዎች ዘንድ ቅድስት ቤተክርስቲያን እንደ ሰናፍንጭ ቅንጣት ትንሽ ተደርጋ ቦታ ሳይሰጣት ትኖር ይኾናል፤ የኋላ ኋላ ግን በዓለም ኹሉ ስትሰፋና ስትነገር፥ ዘሪዋ ኢየሱስ ክርስቶስም ኃይል ተአምራቱን ሲያደርግ አይተው ብዙ ሰዎች ወደ መዳን ይመጣሉ።
___ ___
የሰናፍንጭ ቅንጣትን ሊቁ አውግስጢኖስ ከክርስቲያን ሕይወት ጋር አገናኝቶ አስምሯል። (St. Augustine says, in the work already cited [Serm. 33 de Sanc. ])። የሰናፍንጭ ቅንጣት አንደኛ በእምነት የተመሉ ሰዎችን የሚያመለክት ነው፤ ለምሳሌ ቅዱሳን ሐዋርያትን የሚያሳይ ነው፤ ወይም መከራ የሚቀበሉ ክርስቲያኖችን ወይም ሰማዕታትን የሚያመለክት ነው በማለት ያስረዳል። በእርግጥም ሰማዕታት ስለ ክርስቶስ ፍቅር ሲሉ እንደ ሰናፍንጭ ቅንጣት የሚደቆሱና በእነርሱ መደቆስ ማለትም መታረድ፣ መገረፍ፣ መቃጠልና መሰቀል አጋንንታዊ ሐሳብ ያላቸውን አላውያን ነገሥታት ድል ያደርጋሉ። ሰናፍንጭ ውጯ ቀይ ውስጧ ግን ነጭ ነው። ሰማዕትነት ውጪው ቀይ ነው፤ ይህም ማለት ደምን እስከማፍሰስ ድረስ መከራና ሥቃይ የሚቀበሉበት ሕይወት ነው። ውስጡ ነጭ መኾኑ በሰማዕትነት ሕይወት የሚገኘው ክብር ምንም ዓይነት ጥቍረት የሌለበት እንደ በረዶ ነጭ ነው። በሌላ በኩል ውጩን ስናየው ጭንቅ በመኾኑ ምክንያት የመከራንና የሥቃይን ሕይወት እንዳንፈራና እንዳንሰቀቀ ውስጡን ነጭ በማድረግ ተስፋችን የለመለመ መኾኑን ያስገነዝበናል። ይህም ብቻ አይደለም በታላቁ ጸሎታችን ኹል ጊዜ "ወደ ፈተና አታግባኝ" በማለት የምንጸልየው፥ ሰማዕትነትን አታምጣብኝ ለማለት ሳይኾን በሚደርስብኝ መከራ በመሰቀቅ ወደ ክሕደት እንዳልገባ አድርገኝ ለማለት ነው።
___ ___
St. Gregory ( lib. 19 Moral. c. 11.

ዮሐንስ ጌታቸው

12 Sep, 11:53


የቅዱስ ዮሐንስ ምግቡ አንበጣ (Locust) ነው። አንበጣ የከንቱ ድካም ምሳሌ ነው። በሌላ በኩል ከአንበጣ መንጋ የሚሰማው ድምፅ እጅግ አስጠሊታም ነው። ስለዚህ አንበጣ መብላት ዋናው ምሥጢር በሚያስጠላና በሚከረፋ የኃጢአት ሥራ ውስጥ የሚኖሩትን ሰዎች በፍቅር ስቦ በደግነት አቅርቦ የሚጣፍጥ ምግብ አድርጎ መብላትን ነው። የማይበላ ሥራ ይሠሩ የነበሩ ኃጥአን በቅዱስ ዮሐንስ ስብከት በኩል የሚበላ ወደ መኾን መምጣታቸውን የሚያመልክት ነው። በሌላ በኩል የአሕዛብ ቤተክርስቲያን በክርስቶስ አምላክነት አምና በነቢያት አፍ እስክትሰበክ ድረስ ከበረች ማለት ነው። አዲስ ዓመት የሚከበረው ይህን በማድረግ ነው።

አንበጣ ከምድር ከፍ ብሎ በሰማይ ነው የሚበረው! ይህ መንፈሳዊ ተመስጦ ነው። ዮሐንስ የበላው ይህን የተመስጦ ምግብ ነው። ወደ ጥልቅ መንፈሳዊ ተመስጦ ውስጥ ገብቶ ምግቡን መልአካዊ ምስጋና አደረገው። እግዚአብሔርን ከጥልቅ ልቡ ውስጥ ሥሎት በተሰጠው የተመስጦ ጸጋ ክንፍ በሐሳቡ ወደ ሰማይ በረረ! አዲስ ዓመት የሐሳብ ወደ ሰማይ መብረሪያ እንጂ በምድር ላይ በሐሳብ ደረትነት እንደ መሳብ መንወዛወዝ አይደለም።

=====+++++=====+++======

ሶፍሮንየስ (Sophronius) የተባለ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስን “የሰውን ሥጋ የለበሰ መልአክ" ይለዋል። ይኸው ልቅ ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ምድረ በዳ የገባው የመላእክትን ኑሮ ለመኖር ነው ይላል። ይህ መንገድ ደግሞ ሰው ያለ መጠለያ ሊኖር የሚችል መኾኑን አመልካች ነው። አኹን እኛ የሠራነውን ዓይነት ቤት ሳይሠሩ በምድረ በዳ የሚኖሩ ቅዱሳን መኖራቸው መጠለያን እንደ ሕይወት ዋናና መሠረታዊ ዓላማ አድርገን ሐሳባችንን በምድራዊ መጠለያ እንዳንቀብረው ለማስገንዘብ ነው። አዲሱን ዓመት አዲስ የሚያደርገው የምንኖረው አኗኗር ነው። የዮሐንስን ዓመት በዮሐንሳዊ ሥራ ካላከበርነው እኛ ያለንበት ዐውደ ዓመት ሌላ ዐውደ ዓመት እንጂ የዮሐንስ አይደለም። ስለዚህ የእኛ ዓመት ዐውደ ዓመት የሚኾንልን የዮሐንስን ሥራ ለመሥራት ከጥልቅ ውስጣችን ስንሻ መኾኑን ተረድተን ዓመታችንን እውነተኛ እናድርገው።

መልካም ርእሰ ዓውደ ዓመት ቅዱስ ዮሐንስ ይኹንልን።

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

12 Sep, 11:53


###ርእሰ_ዐውደ_ዓመት_ዮሐንስ###

=======+++++=+========+=
አዲስ ዓመት የሚጀምረው ከቅዱስ ዮሐንስ የሰማዕትነት ዕለት ስለ ኾነ ከዓመቱ ጋር አብሮ አጥማቄ “ሥግው ቃል" ቅዱስ ዮሐንስ ይታሰብበታል። ቅዱስ ዮሐንስ የልደቱ ዕለት በደስታ ተጀምሮ በዕረፍቱም ዕለት በደስታ ይከበራል። በበረከት ጀምሮ በበረከት ተጋድሎውን ጨረሰ። የሰማዕታት የሰማዕትነት ዕለት ለዘለዓለማዊ ሕይወት የሚወለዱበት ዕለት ስለ ኾነ “የልደት ዕለት" ተብሎ በቅድስት ቤተክርስቲያን ይከበራል።

=====++=+=+=+=========++
ቅዱስ ዮሐንስ ብዙ ልዩ ነገሮች ያሉት ልዩ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው። እስኪ ከስሙ እንጀምር “ዮሐንስ" ማለት የእግዚአብሔር መንግሥት (The Kingdom Of God) ማለት ነው። ይህ የስሙ ትርጒም “የእግዚአብሔር መንግሥት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ" የሚለውን ስብከቱን ያመለክታል። ለቅዱስ ዮሐንስ “ስሙ ስብከቱ! ስብከቱ ስሙ ነው።" በዚህ ዘመን እንዳለን ሰዎች ስሙን ተሸክሞት ብቻ ያለ ሳይኾን በተግባር እየኖረው የሚሰብከው ልዩ አገልጋይ ነው። አዲስ ዓመት አዲስ የሚኾነው ንስሓን በመጠማትና ከልብ በመሻት ስንጀምረው ወይም የመንግሥተ ሰማያትን ሥራ ብቻ ለመሥራት አቅደው ሲጀምሩ ነው።

==========+=====+++=====

ዮሐንስ ማለት እግዚአብሔር ደግ ነው (God is Gracious) ማለት ነው። ይህ ደግነት ከቂምና ከበቀል የራቀ በፍጹም ቸርነት ላይ የተመሠረተ ነው። በአዲስ ዓመት ውስጥ ገብቶ መኖር ማለት በደግነትና በርኅራኄ ውስጥ ገብቶ መኖር ማለት ነው። ለተራበ፣ ለተጠማ፣ ለታረዘ፣ ለታመመ የሚራራ ደግነትን የሚሠራ እርሱ በእርግጥም በአዲስ ዓመት ውስጥ ገብቷል። ይህ ደግነት ማስመሰልና መገበዝ የሌለበት ስለ ኾነ “ለራስ ራስን ደግ በማድረግ ይጀምራል።" ለራስ ደግ መኾን ማለት በንስሓ በር ራስን ወደ ደግነት ቤት (ወደ ምሥጢረ ቁርባን) ማቅረብ ነው።

====++++====++===++++===

የቅዱስ ዮሐንስ የስሙ ትርጒም የእግዚአብሔር ጸጋ (The Grace of God) ማለት ስለ ኾነ የማያልቅ ነው። ጸጋ እግዚአብሔር ተሰፍሮና ተለክቶ የማያልቅ እንደ ኾነ የቅዱስ ዮሐንስም የተጋድሎና የቅድስና ሕይወት ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደለም። በዚህ ዓለም ኃጢአት ውስጣችን የቆሸሸብንና ከጸጋ እግዚአብሔር የራቅን ሰዎች ወደ አዲሱ ዓመት የገባን አይምሰለን፤ አሮጌውን ይዘን አልለቅ ያልን አሳዛኞች እንጂ። ስለዚህ የርእሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ ስሙ እንኳን ሕሊናችንን ወደ እግዚአብሔር የሚመራ ነው። በኹሉም መስመር ጸያሔ ፍኖት ነው።

===+++===+++=====++===+=

ርእሰ ዓውደ ዓመት ዮሐንስ ሳይንስ በጣም ለሰው ሕይወት መሠረት ናቸው ያላቸውን ሦስት ነገሮች ምግብ፣ ልብስና መጠለያን የገለበጠና የሕይወት ዋናው መሠረት እግዚአብሔር መኾኑን የመሰከረ ነው። የሳይንቲስቶች ዓላማ ሰውን ከእግዚአብሔር መለየት ነው። የሕይወትን ዓላማ መሥመር መበጠስና በስስ ክር ያያያዘ አስመስሎ ማጥፋት ነው። የሕይወት ዋና ዓለማው እግዚአብሔርን ማግኘት ነው። እርሱን ስናገኝ ሌሎች ኹሉ ይጨመራሉና! እርሱን ከሕይወታችን መዝገብ አስወጥተን በዚህ ዓለም ላይ ብቻ ኑሮን ከመሠረትን የሕይወትን ዓላማ ረሳነው ማለት ነው።

መጽሐፍ "መንግሥቱንና ጽድቁን ፈልጉ ሌላው ይጨመርላችኋል።" ያለን ሕይወታችን መመሥረት ያለበት በዚህ ጽኑዕ መሠረት ላይ ስለ ኾነ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ ለዚህም መንገድ ጠራጊያችን ነው። ሳይንስ የሰውን ልጅ የመኖር ዓላማ መሬታዊ ብቻ አደረገው። የምትኖረው ለምግብ፣ ለመጠለያና ለልብስ ብቻ ነው በማለት ለዚህ ብቻ እንድንተጋና እንድንደክም አደረገን። በዘዴያዊ መንገድ ከኦርቶዶክሳዊው የመኖር ዓላማ ገፍትሮ በአሸዋ አስተሳሰብ ላይ ተከለን። ስኬትም እነዚህን ነገሮች ማግኘት ነው ብሎ ክርስቶስንና የእርሱ የኾኑ ቅዱሳንን አሳጣን። በዚህ አስተሳሰብ ከልጅነት ጀምሮ በእጅጉ አሰከረን። ስለዚህ ሰዎች እግዚአብሔርን ከመፈለግ ይልቅ እነዚህን ነገሮች ብቻ በጣም አትኩረው የሚፈልጉ ኾኑ። እንግዲህ አዲሱ ዓመት አዲስ ነው የሚባለው ይህን አስተሳሰብ ገልብጠን ክርስቶስን በማግኘት ጽኑዕ መሠረት ላይ ስንሠራው ነው። ጸያሔ ፍኖት ዮሐንስን አርአያ እናድርገው!! ከኋላው እንከተል። እንደ ዮሐንስ እግዚአብሔርን የሕይወታችን መሠረት ስናደርገው፡ እኛ ያስፈልጉናል የምንላቸውን ኹሉ እርሱ በቸርነቱ ይሰጠናል። እግዚአብሔር ኹሉን ማድረግ የሚችል ስለ ኾነ፥ እኛ ያስፈልጉናል በምንለውም በማንለው ሊያኖረን የሚችል መኾኑን ልብ እንበል። እንግዲህ ቅዱስ ዮሐንስ ወደ እግዚአብሔር ሐሳባችን የሚወስድል፥ በሰማይም ሕሊናችንን የሚተክል በጎ መንገድ መሪ ነው።

====+++====++++====+++====++

የዮሐንስ ልብሱ የግመል ጠጉር መኾኑን ስትሰሙ ምን ይታወሳችሁ ይኾን? “ባለ ጸጋ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ከሚገባ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፈሰ ይቀልላል" የሚለው አይታወሳችሁምን? ግመል የቤተ አሕዛብ ምሳሌ ነው፤ የመርፌ ቀዳዳ የርቱዕ ሃይማኖት ምሳሌ ነው። ስለዚህ የግመል ፀጒር መልበስ ማለት አሕዛብን በክርስቶስ አምላክነት አሳምኖ ወዳጅ ማድረግ ነው። አዲሱን ዓመት በመጠራጠር ሜዳ ላይ ሰይጣን የክሕደትን ኳስ የሚያስመታቸውን ወገኖቻችንን ወደ መዳን የምናመጣበት ሊኾን ይገባዋል። የግመል ፀጒር መልበሱ የኦሪት መጨረሻ የሐዲስ መግቢያ ላይ መነሣቱን የሚጠቁም መኾኑን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አመልክቷል። አዲሱ ዓመት በዚህ መሠረት ላይ መሠራት አለበት። ኦሪታዊ ሥራ አኹን የተሻረ ነው። ይኸውም መሥዋዕተ ኦሪትና ግዝረተ ኦሪት ቀርቷልና። በዚሁ አንጻር ለእኛ አኹን ኦሪታዊ ሥራ የሚኾነው ለድኅነት የማያበቃ ሥራ በአጠቃላይ ነው። ይህ ከሕይወታችን ተነቅሎ ወንጌል ክርስቶስ መምጣት አለበት። የድኅነትን ሥራ ወይም የእምነት ሥራ የሚባሉትን በጎ ምግባራትን መሥራት አለብን። አዲስ ዓመት በዚህ ነውና አዲስ የሚኾነው!!

====++++========+++++===

የግመል ፀጒር ደመ ነፍስ ስለ ሌለው የግመልን ፀጒር መልበስ ማለት ከዓለማዊ ሥራ መለየት፤ በፍጹም መንፈሳዊነት መኖር ማለት ነው። ጌጣችን የዚህ ዓለም ኃላፊ ነገር አይደለም። የግመል ፀጒር መልበስ ማለት ለውጫዊ ልብስ በመጨነቅ አለመኖር! የቅምጥልነትን ሕይወት መተው ማለት ነው። ልብስ የሕይወት መሠረት አይደለም፤ ሊኾንም አይችልም። ጉዟችን ክርስቶስን ወደ መልበስ መኾን አለበት እንጂ በምድራዊ ጌጥ ማጌጥ መኾን የለበትም። ሕይወታችን መርዛማ ወደ መኾን እየተሸጋገረብን ያለው አንዱ በውጫዊ ልብስ ራሳችንን ለማስደነቅ የምንጓጓ በመኾናችን ነው። ስለዚህ ቅዱስ ዮሐንስ ጭንቀታችን የእግዚአብሔር መንግሥት የሚያስገኝ የንስሓ ሥራ መኾን እንዳለበት የአዋጅ ድምፁን አሰማን! የግመል ፀጒር መልበስ ማለት የበጋችን ክርስቶስን ለድኅነተ ዓለም አለመሸለት የሚያመለክት ነው። ዮሐንስ ወደ አማናዊው በግ መሪ እንጂ እርሱ ራሱ በጉ አይደለምና። የክርስቲያን እውነተኛ ልብስ ክርስቶስ ገና ታርዶ ከጥንተ በደል አላደነንም የሚለውን ምሥጢር አመልካች ነው።

==++=+=+++++=====+++====

ዮሐንስ ጌታቸው

11 Sep, 07:33


አንችልም። እንቍጣጣሽን የሚያከብሩ ነገር ግን ከእንቍጣጣሽ ሐሳብ ራቅ ያልን ስንት ነን? እጅግ ብዙ።

=======+++=+++=+==+==+==

እንቍጣጣሽ “ዕንቍ ለጣትሽ" የሚለውን የሚያመለክት ከኾነ፤ ለጣት አንገታችን ዕንቍ መስቀል ሊኖረው ይገባል። ግን ይኽን “በአንገታችን" ያለውን ዕንቍ መስቀላችንን ጭልጥ አድርገን ረስተነው ጭፈራ ቤት ይዘነው እንገባለን፤ በስካር ሰውነታችንን ሸብረክ ስናደርገው ዕንቍ ያለበትን መስቀል ዝቅ ዝቅ እናደርገዋለን። ይህ ድርጊታችን ዕንቋችንን አስረስቶ ብዙ ዘመን ኃጢአት ስንሠራ ኖርን። በአዲሱ ዓመት ከወደቅንበት እንውጣ ዕንቋችንን እናንሣ! ውጤቱ መራራ የኾነ የጨለማ ሕይወት ይብቃን፤ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሕይወት መኖር አንድ ብለን እንጀምር። ምንም እንኳን ዓመቱ ቍጥሩ ቢጨምርም ከእግዚአብሔር ጋር ኾነን ካልኖርን ለእኛ ቍጥሩም ዓመቱም አሮጌ ነው። እውነተኛ ሕይወት እግዚአብሔር ስለ ኾነ፣ ከእርሱ ውጭ ኾነው የሚኖሩት ሕይወት ኹሉ ሕይወት አይባልም፤ የሚቆጠረውም እንዳለመኖር ነው። ሕይወት ማለት ከእግዚአብሔር ጋር መኖር ማለት ነው። እንግዲያውስ የ2017 ዓ.ም ዕቅድዎት ምን ይኾን? እንደ ቀድሞ ባለመኖር ውስጥ ኾኖ መኖር ነው ወይስ ከእግዚአብሔር ጋር መኖር? ይህን ኹላችሁም ለራሳችሁ መልሱ።

“አዲሱን ዕንቍጣጣሽን ዕንቍ አያሳጣን"

https://t.me/phronema

ዮሐንስ ጌታቸው

11 Sep, 07:33


#######ዕንቍ_ጣጣሽ#######

===++=====+++========+==
የ2017 ዕንቍጣጣሽ ልዩ የሚኾነው በዕንቍጣጣሹ ውስጥ በሚንቆጠቆጠው ሰው አማካኝነት ነው። በእርግጥም የእንቍጣጣሽ "ዕንቍነት" በያዡ አያያዝ ላይ የሚመሠረት መኾኑን መረዳት ለማናችንም አይከብደንም። በኃጢአት እና በበደል በጠቆረው በዚያው ማንነታችን ኾነን ከያዝነው፥ እንቍጣጣሽ ለእኛ ውበት አይደለም ማለት ነው። እንቍጣጣሽ ውበትን የሚገልጥ መኾኑን ከተረዳን ልቡናችንን ውብ እናደርጋት ዘንድ ግድ አለብን፥ ያ የማይኾን ከኾነ እንቍጣጣሽ ወዴት አለ? እንቍጣጣሽ “መንቆጥቆጥን" ወይም ማማርን፡ መዋብን የሚያመለክት ስለ ኾነ፤ ከጥልቅ ውስጣች በበጎ ምግባራት መንቆጥቆጥ አለብን። እንደ በረዶ የነጣውን የንጽሕናን ተግባር መልበስና የንጽሕናን ሥራ ማሳየት አለብን። ኹል ጊዜ ሕይወታችንን በኦርቶዶክሳዊው ሕይወት የተንቆጠቆጠ ለማድረግ እጅግ መትጋት አለብን። የእግዚአብሔር መንግሥት የሚወረሰው በብዙ መከራና ሥቃይ መኾኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉና። አዲሱ ዓመት በእኛ ኦርቶዶክሳዊ ሕይወት አዲስ ካልኾነ በቀር ምኑን ታደሰ!

=========+++======+====+

ብዙውን እድሜያችንን በእንቍጣጣሽ ሳይኾን የቆየነው በ " ዕንቍን አጣሽ" ሕይወት ነው። የሕይወት ዕንቍን ክርስቶስን ትተን “ዕንቍን አጣሽ" የተባለ ዲያብሎስን በማስደሰት ነው የኖርነው። ለዚህ ነው በእንቍ ጣጣሽ የዕንቍን አጣሽ ሥራ ስንሠራ የምንገኘው። ይህ በእጅጉ የሚያሳዝን ነው። በቀደመው ዓመትም ከእግዚአብሔር ይልቅ ዘፈንን በውስጣችን አንግሠን፡ በዲያብሎሳዊ ግብር ዓመቱን በርዘን የማያረጀውን አስረጅተናል። አኹንም እግዚአብሔር የሚሰጠንን አዲስ ዓመት ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጭ በኮንሰርት መርዘን ለመያዝ ተዘጋጅተናል። በእርግጥ ከእኛ በላይ የእኛ ጠላት ማን አለ? ራሳችን ከሰላም ውጭ ኾነን እግዚአብሔር ሰላም ካልሰጠን እያልን እንዘባበታለን! የሰላሙን ምንጭ ከልቡናችን ጥልቅ ገፍተን፥ የዓለምን ፍቅር በጥልቃችን አስገብተን በአዲሱም ዓመት አንድ ብለን ልንጨፍር፣ ልንዘፍን፣ ልንሰክር መዘጋጀታችን እጅጉን ያሳዝናል! በእንቍ ጣጣሽ “ዕንቋችን" ክርስቶስን በሕይወታችን ውስጥ መግለጥ አለብን። ዕንቍ የተባለን ጌታን ከሐዋርያት ጋር አግኝቶ ነገር ግን እንደ ፈሪሳውያን በግብዝነት ሕይወት ገፍቶ የማጣት “ጣ! ጣ!" ውስጥ እንዳንገባ ከቀደመው የበለጠ እንትጋ።

=====+++==++===========

እንቍጣጣሽ “እንቍጣጣሽ" የሚኾነው ዕንቍ ክርስቶስን የምናገኝበትን ሥራ ከግብዝነት ውጥተን ስንሠራ ነው። ዕንቋችን ክርስቶስን በዚህ ዓለም ርካሽ ፖለቲካ አማካኝነት “ጣጣ" አድርገው ከልባቸው ያጠፉ አሉ። በዚህ ዓለም ግሳንግስ ዘፈኑ፣ ተራ አስተሳሰብ፣ ራስ ወዳድነት፣ ዝሙትና መዳራት፣ ጥላቻና አረመኔያዊ ጭካኔ “ጣ! ጣ!" አድርገን ዕንቍ ወንጌልን ጥለን የምን እንቍ ጣጣሽን ማክበር ነው? ዕንቍጣጣሽ የሚከብረው በ"ዕንቍ" ወንጌል አማካኝነት መኾኑን ማን ባስታወሰን! ነፍሳችን የእግዚአብሔርን ቃል አጥታ በጽኑ ሕማም ውስጥ መኾኗን ገና አለመረዳታችን፡ ቃለ እግዚአብሔርን ካለመስማታችን በላይ ሌላ ጉዳት ነው። በበሽተኛ የሕይወት ምላሳችን ጥዕምት 2017 ዓ.ምን ልናመርራት ታጥቀናል። በጳጒሜን እንኳን እግዚአብሔር ዕድሜን የሚጨምርልን ወደ ልቡናችን እንድንመለስ ፈልጎ መኾኑን ዘንግተናል። የቀደመውን የጨለማ ሕይወት በብርሃን ወንጌል አማካኝነት አርቀን ወደ አዲስ አኗኗር እንዳንመጣ የቀደመው ልማዳዊ የኃጢአት ሕይወት አኹንም ገና እየጣመን ነው። አኹንም መልሳችን አንዴ ነው! ለበዓል ብቻ ነው! ዛሬ ዘና ፈካ ካላልኩ እስከ መቼ ልጨናነቅ! እያልን ለራሳችን ጥፋት ራሳችን የደከመ ምክንያት በማቅረብ እንስታለን።

==++=++++++==========++=
በእርግጥ እንቍጣጣሽ “ዕንቍን አመጣሽ" ከኾነ ከልባችን መዝገብ "ዕንቍ" መልካምነት መምጣት አለበት። ሕሊናችን በማስመሰልና በመገበዝ እሳት ተቃጥሎ አመድ አስተሳሰብ እንዳያመጣ መጠንቀቅ ይኖርብናል። ልባችንን “ልቤ ሆይ!" ዕንቍ ሰላምን አምጣልኝ እንጂ “ጣ! ጣ!" ጸብን አታምጣብኝ ከማለት እንጀምር። መልካምን በመምረጥ ካልጀመርን ዓመቱን የመልካምነት ቤት አድርገን መኖር አንችልም። ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ "መልካም የኾኑ ነገሮች ኹሉ ብንዘረዝር ከእርሱ የባሕርይ መልካምነት በጸጋ ያላገኘ ወይም ከእርሱ ያልተሰጠው መልካም ነገር በምድር ላይ የለም፤ ሊኖርም አይችልም። በቅዱሳት መጻሕፍት ተደጋግሞ እንደ ተገለጸው መልካሙ ኹሉ ከእርሱ የተገኘ ነው። መልካም ዘር የተባለው እርሱ ነው። መልካም መሬትም እርሱ የፈጠረው ነው። መልካም ፍሬን የሚያፈራው መልካም ዛፍም ኾነ ከልቡ መልካም ነገርን የሚያፈልቀው መልካሙ ሰው የእርሱ መልካምነት መገለጫዎች ናቸው። በአጠቃላይ 'እግዚአብሔርም ያደረገውን ኹሉ አየ፥ እነኾም እጅግ መልካም ነበረ" ዘፍ 1፥31 ተብሎ እንደተጻፈ ያለ እርሱ መልካም ነገር የለም፤ ሊኖርም አይችልም። ይህን የሚያውቁ ደግሞ ራሳቸውን መልካም መሬት አድርገው መልካሙን ዘር ተቀብለው መልካም ፍሬ ያፈራሉ። መልሰውም ከጎተራቸው መልካሙን ዘር አውጥተው እንደገና ይዘራሉ። በርግጥም መልካም ነገር አንድ ነው።" ይላል። (ግርማ ባቱ (መምህር)፣ የነገረ መለኮት መግቢያ፣ 2013 ዓ.ም፣ ገጽ 2-3)። ስለዚህ በመልካምነት ያልያዟት እንቍጣጣሽ ጣዕም አልባ ናት።

====+++=+++=+++=======+=

ይህ አዲስ ዓመት የቅድስት ቤተክርስቲያን “ዕንቍ ጣጣዋ" መኾን አለበት። ዕንቍ የተባሉ የምእመናንን መከራና ሥቃይ፣ ስደትና ረሃብ ጣጣዋ ሊኾን ይገባል። ፍትህ ርትዕ የተባለው ዕንቍዋ፥ ሰላሟን በሚሰብረው መንግሥታዊ አሠራር ሊመጣላት ባይችልም ወደ ዕንቍ ክርስቶስ ድምጿን ከፍ አድርጋ በማሰማት ርቱዕ ሰላምን ለልጆቿ ማፍሰስ አለባት። የቤተክርስቲያን ጣጣዋ (ፍላጎቷ) ዕንቍ (ሰላም፣ ፍቅር፣ አንድነት፣ የመሳሰሉትን) ላለማጣት መትጋት መኾን ነው ያለበት። የቤተ ክርስቲያን ሰላሟ ምን እንደ ኾነ በልጆቿ ልቡና ውስጥ መቅረጽ አለባት። ያኔ ዓመቱ በምእመናን ልቡና ሰላሟ የሚፈስባቸው አዲስ ዓመት ይኾናል። በእርግጥ ይህም የሚጀምረው ከእኛው ነው። የመጀመሪያዎቹ የእኛው ሰላም ባለቤቶች እኛው ነንና። እያንዳንዳችን ለእያንዳንዳችን ሰላምን ለማምጣት ከጣርን ሰላማችን አንድ ዓይነት ኾኖ ዓመታችን የጋራ ሰላማችን ምንጭ ሰላማዊ ይኾናል። እርስ በእርስ ስንጨካከንና ስንጠላላ፤ ከፈቃደ እግዚአብሔር ይልቅስ የየግል ስሜታችንን የሕይወታችን መርሕ ስናደርግ እውነተኛውን ሰላም ማግኘት ያቅተናል። ሰላሙን ስናጣና ተስፈኝነት ይጠፋናል፣ ጭንቀትና ፍርሓት ይጋርደናል። ይህ ደግሞ ሕይወታችንን ባልተገባ ክፉ ኀዘን ሰቅዞ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ እንድንኖር ያደርገናል። ይህ ከኾነ ዕንቍ ጣጣሽ ወዴት አለ?

====++====+++=====++====
እንቍጣጣሽን በዚህ ዓለም ተራ ማስክ (የዘረኝነት፣ የጥላቻ፣ የልዩነት፣ የረብሽና የመሳሰሉትን) ሸፍነን ጣጣ ውስጥ እንዳንገባ። ማስኩን የምንጠቀመው ኮሮናን ለመከላከል እንጂ ዕንቋችንን ለማራቅ መኾን የለበትም። ከልባችን የሚመነጨው የኃጢአት ጎርፍ በሰውነታችን ላይ ጎርፎ ጥርግርግ አድርጎ እንደ ወሰደን ማወቅ ሲያቅተን ቆሻሻው ሐሳባችን የሚወጣበትን አፍ “በማስክ" ሸፈነው። ኾኖም ግን አኹንም ያሸፈነንን ኮሮናን (ቆሻሻ ሐሳባችንን) ከፈት እያደረግን ማስወጣታችንን አላቆምንም። እንግዲህ በዚህ መንገድ ወደ እንቍጣጣሽ ውስጥ መግባት አንችልም። ወደ እንቍጣጣሽም መድረስ

ዮሐንስ ጌታቸው

10 Sep, 14:33


+++++++++#እስከ_መቼ#+++++++++

ኢትዮጵያውያን የቀደመውን የኢትዮጵያዊነት መልካም እሴት ትተን በማስመሰልና በከንቱ ሕይወት የምንቀጥለው እስከ መቼ ነው? ፖለቲከኞች በራሳቸው ልክ ሠርተው የሚያቀርቡልንን የሐሰት ትርክት እየሰማንና ሲያሻንም አንዳንዱን እውነት አድርገን እየወሰድን በተግባራዊ ሕይወታችን የጥላቻን ጎርፍ የምናጎርፈው እስከ መቼ ነው?

ፖለቲከኞች ውሸትን ልባቸው አድርገው ከውሽት ልቡናቸው ውስጥ የሚያፈሱትን የመንገድ ውኃ እየጠጣን፤ ከእነርሱ ባላነሰ መንገድ በፈጣሪያችን ላይ እየቀለድን የማስመሰልንም ሕይወት መሥዋዕት አድርገን የምናቀርበው እስከ መቼ ነው?

ፖለቲከኛው፣ ዘረኛው፣ ሐሰተኛው ነቢይ፣ ሌባውና አስመሳዩ እኛን የሚያታልለን በአግባቡ ስለማንመረምርና በውስጣቸው ደብቀው የያዙትን አጀንዳ ያልተረዳን መኾናችንን አውቀው ነው። ስለዚህ ድንቁርናችንን በር አድርገው ወደ ሕሊናችን ገብተው የሚያቃጥሉን እስከ መቼ ነው? እጃችንን ለጸሎት አንሥተን ልባችንን ኃጢአት ባለበት ቦታ የምናስቀምጠው እስከ መቼ ነው?

አንተ ልክ አይደለህም! አንቺም ልክ አይደለሽም እያልን አስተያየት የምንሰጠው ነገር ግን እግዚአብሔር ከሚፈቅደው እውነተኛ ሕይወት ውጭ በኃጢአት ጨለማ ውስጥ የምንኖረው እስከ መቼ ነው?

ክፉን በወቀስንበት ልክ በእግዚአብሔር ላይ የከፋውን የእኛን ሕይወት የማናስተካክለው እስከ መቼ ነው? እስከ መቼ ድረስ ልባችን ግትር ኾኖ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ባለመፈጸም ይጓዝ ዘንድ እንፈቅድ ይኾን?

መንግሥት ከሚያታልለን ይልቅ የማይታለለውን አምላክ እኛው ለማታለል የሄድንባቸው መንገዶች አይከፉም ይኾን? መንግሥት ለራሱ ድጋፍ ፈልጎ ያልኾነውን ኾነ የኾነውን አልኾነ እያለ የሐሰት ትርክቱን በሚዲያ ከሚያቀርበው ይልቅ በአርአያው የፈጠረንን አምላክ በሰውነት ሚዲያችን አላከብርህም ብለነው የምናቀርበው የኃጢአት ትርክቶች አይበልጡምን? እስከ መቼ እንዲህ እንኖራለን?

ክፉዎች ያቃጠሏቸው አብያተ ክርስቲያናትን አይተን ልክ አይደለም ብለን እንደ ምናወግዘው ኹሉ ዋናውን የእግዚአብሔር መቅደስ ሰውነታችንን በትዕቢት እሳት የምናቃጥለው እስከ መቼ ነው? እስከ መቼ ነው በኃጢአት ላይ ኃጢአት እየፈጸምን የምንኖረው? እስከ መቼ ነው እንወዳታለን የምንላትን ቤተክርስቲያን “ሰውነታችንን" በዘፈን፣ በጭፈራ፣ በስድብና በጥላቻ፣ በዝሙትና መዳራት በመሳሰሉት እሳቶች እያቃጠልን የምንኖረው?

የእኛን ቤተ ክርስቲያን ማቃጠል እስካላቆምን ድረስ የቤተክርስቲያን ቃጠሎ ቆመ! ማለት አንችልም። መቅደስ ሰውነታችንን ክርስቶስ የተባለው አማናዊው እጣን እንዲሸተትበት እስካላደረግን ድረስ ቤተ ክርስቲያን መሰደቧ አይቀርም። መጀመር ያለብን እኛው እኛን ከማስተካከል ነው። እኛ ከተስተካከልን ማንም ምንም አያደርገንም። ወደ ኦርቶዶክሳዊ አስተሳሰብና ሕይወት እንመለስ! በርቱዕ እምነት ርቱዕ የኾነ ኦርቶዶክሳዊ አነጋገር፣ አስተሳሰብና አተያይን አጽንተን መያዝ እንጀምር።

አዲሱ ዓመት የድንቁርና ጉዟችን ቆሞ! እግዚአብሔርን ከልባችን የምናገኝበትና ከእርሱ ጋር በደስታ የምንኖርበት ዘመን የሚኾነው እርሱን ለማግኘት ስንተጋ ነው። ማስመሰላችንን ከቀጠልን የሚያስመስሉብንም ይቀጥላሉ! እኛ ኹላችን ከማስመሰል ከወጣን ሊያስመስሉብን የሚያስቡ አካላት ማስመሰል አቅቷቸው ያቆሙታል። እኛ እነርሱን የምናሳየውን ነው እነርሱም እኛ ላይ የሚያደርጉት። ሁላችንም ፍቅርን ለማሳየት ከተነሣን ጥላቻን ይዞ የመጣውን መንገዱን መቀየር እንችላለን። የልዩነትና የዘረኝነት ሐሳብ ይዞ የሚመጣውን የአንድነትን ነገር በተደጋጋሚ ብናሳየው ከስሑት ሐሳቡ ይመለሳል። ስለዚህ አዲስ ዓመት ሲመጣ ያረጀንባቸውን የክፋት እሳቤዎች መተው እንዳለብን እንረዳ። የእግዚአብሔር ምሕረትና ይቅርታ እንዲጎበኘን በልባዊ ይቅርታ ዘመኑን እንጀምረው። በምንም ዓይነት ክፉ አስተሳሰብ ውስጥ ያለን ሰው ብናገኝ እግዚአብሔር በዚያ ሰው ላይ የሚያደርጋትን ምሕረት እናስብ። ይህንስ ለምን አያጠፋውም ወደሚል የሕሊና ፈተና ውስጥ ላለመግባት ከመጣር ጋር እውነቱን ወደ መረዳት አምጣው ብለን በፍቅር እንጸልይለት።

እግዚአብሔር አምላካችን ከልዩነትና 2016 ዓመተ ምሕረትን ካቆሸሸብን የዘረኝነት፣ የግድያ፣ የጭካኔ፣ የርኲሰት በሽታ በቸርነቱ ነጻ ያውጣን። አዲሱንም ዓመት በእርግጥም የምሕረት አድርገን እንድንኖረው ኃይሉን ያድለን። መልካም አዲስ ዓመት ይኹንላችሁ።

https://t.me/phronema