ከኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን መካነ ኢየሱስ በአንዳንድ ወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ የተሰጠ መግለጫ፤
መስከረም 21-2017 ዓ/ም
በስመ አብ፤ በወልድ፤ በመንፈስ ቅዱስ ስም አንድ አምላክ፤ አሜን!
በጌታ የተወደዳችሁ በአገር ውስጥና ከአገር ውጭ የምትገኙ የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን መካነ ኢየሱስ ምዕመናን፤ በያላችሁበት ሁሉ የእግዚአብሔር ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ፡፡
የዚህ መግለጫ ዓላማ ካለፉት ጥቂት ወራት ወዲህ የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን መካነ ኢየሱስ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻን ከሚባርኩና ግብረ ሰዶማዊያንን ለመንፈሳዊ አገልግሎት ከሚጠሩና ከሚያሰማሩ አብያተ ክርስቲያናት ጋር የአጋርነት ስምምነት ፈርማለች ወይም ልትፈርም ነው፤ በሚል እየተሰራጨ ያለው ወሬ ትክክለኛ አለመሆኑን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ምዕመናንና አገልጋዮች ለማስገንዘብ ነው፡፡
እንደሚታወሰው የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን መካነ ኢየሱስ በ19ኛው ዓብይ ጉባኤ ከሲዊድን ቤተ ክርስቲያንና በሰሜን አሜሪካ ከምትገኘው ወንጌላዊት ሉተራን ቤተ ክርስቲያን ጋር የነበራትን የአጋርነት ግንኙነት እንዲቋረጥ ወስኖ ነበር፡፡
ይህን ጉዳይ አስመልክቶ ምክክር የተጀመረው በ1998 ዓ.ም. በይርጋለም ከተማ በተካሄደው 2ኛው የቤተ ክርስቲያኒቱ ካውንስል ስብሰባ ቢሆንም፤ ሥነ መለኮታዊ አቋም ተይዞ ውሳኔ መስጠት የተጀመረው በግምቢ ከተማ በተካሄደው 6ኛው ካውንስል ስብሰባ ነበር፡፡ በዚህ ካውንስል ቤተ ክርስቲያኒቱ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻን መባረክንና ግብረሰዶማዊያንን ወደ ቅስና አገልግሎት መጥራትን በጽኑ በመቃወም፤ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻን ከሚፈጽሙና ግብረሰዶማዊያንን ወደ ቅስና ለመጥራት ውሳኔ ካደረጉት ጋር ያላትን ግንኙነት ለማቋረጥ የምትገደድ መሆኗን ይፋ አድርጋለች።
ይሁን እንጂ ቤተ ክርስቲያኒቱ ከእነዚህ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ከነበራት ታሪካዊ ግንኙነት የተነሳ፤ ይህንን ውሳኔአቸውን በማጤን እንዲመለሱና ምላሻቸውን በአንድ ዓመት ውስጥ እንዲያሳውቁ ጥሪ ብታደርግም የአብያተ ክርስቲያናቱ ምላሽ አዎንታዊ አልነበረም። ይኸው ጉዳይ ለ7ኛው ካውንስል ሪፖርት ተደርጎ ቀደም ሲል የተወሰነው ውሳኔ ተፈጻሚነት እንዲያገኝ አቅጣጫ ተቀመጠ፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ 8ኛው ካውንስል ከላይ ስማቸው የተጠቀሰውን ብቻ ሳይሆን፤ ተመሳሳይ አቋም የያዙትን አብያተ ክርስቲያናት ጭምር ታሳቢ ያደረገ የትድግና ሚሲዮናዊነት (Rescue Mission) አገልግሎት እንዲታቀድና ለዚህም የአፈጻጸም መመሪያ እንዲዘጋጅ ወሰነ፡፡ በየካውንስሉ ስብሰባዎች የተላለፉት ውሳኔዎች የዓብይ ጉባዔውን ይሁንታ ማግኘት ስለነበረባቸው፤ 19ኛው የቤተ ክርስቲያኒቱ ዓብይ ጉባዔ በ6ኛው፣ በ7ኛው እና በ8ኛው ካውንስል ስብሰባዎች የተላለፉትን ውሳኔዎች ተቀብሎ በማጽደቅ ቤተ ክርስቲያኒቱ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻ ከተቀበሉትና ግብረሰዶማዊያንን ከሚያቀስሱ አብያተ ክርስቲያናት ጋር የነበራት የአጋርነት ግንኙነት እንዲቋረጥ ወሰነ፡፡
ከላይ የተጠቀሰው በ8ኛ ካውንስል የተወሰነው የትድግና ሚሲዮናዊነት አገልግሎትን አስመልክቶ ለተላለፈው ውሳኔ የአፈጻጸም መመሪያ ባለመዘጋጀቱ፤ 19ኛው የቤተ ክርስቲያኒቱ ካውንስል የ21ኛውን የቤተ ክርስቲያኒቱ ዓብይ ጉባኤ ውሳኔ መሠረት በማድረግ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሥነ መለኮታዊ አቋም በምንም መልኩ ሳይሸራረፍ ከእውነት የሳቱትን ለመመለስና በእምነት ያሉትን በደቀ መዝሙርነት ሕይወት ለማነቃቃትና ለማጽናት የሚያስችል ስልት ቀይሶ ለሥራ አስፈጻሚ ቦርድ እንዲያቀርብ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሚሲዮንና ቲኦሎጂ ቦርድ መራ፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱ ሚሲዮንና ቲኦሎጊ ቦርድም ሥራውን አጠናቅቆ ለሥራ አስፈጻሚ ቦርድ ሪፖርቱን አቅርቦ ማስተካከያዎች ታክለውበት እንዲዳብር ባዘዘው መሰረት፤ ይኸው ለቀጣይ ውሳኔ ሰጭ አካል የሚቀርብ ይሆናል፡፡ ይህም ማለት ሂደቱ ገና ያልተጠናቀቀና የመጨረሻ ውሳኔ ያልተሰጠበት እንደመሆኑ፤ የትድግና ሚሲዮናዊነት አገልግሎትን የሚያስጀምር እርምጃ እስካሁን አልተወሰደም፤ በዚህም አቅጣጫ የተደረገ አንዳች ስምምነት የለም፡፡
ስለሆነም ለምዕመናኖቻችና በየደረጃው ለሚገኙ አገልጋዮች የሚከተለውን መልዕክት አበክረን እናስተላልፋለን፡-
1. ቤተ ክርስቲያኒቱ ማናቸውንም ዓይነት ግብረሰዶማዊ ግንኙነት አጥብቃ ትቃወማለች፤ እንደዚሁም ግብረሰዶማዊነት በመጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ መሠረት ግልጽ የሆነ የድፍረት ኃጢአት እንደሆነ ስለምታምን ይህንን ኃጢአት ከሚፈጽሙ ጋር አትተባበርም፤
2. እግዚአብሔር በመጀመሪያ ጋብቻን በአንድ ተፈጥሮአዊ ወንድና በአንዲት ተፈጥሮአዊ ሴት መካከል ከመሠረተባቸው ምክንያቶች አንዱ የሆነውን የሰው ልጆች ትክክለኛ ወሲባዊ ግንኙነትንና የሥነ-ተዋልዶን ሥርዓት የሚያፋልስና በሙሽራው ክርስቶስና በሙሽራይቱ ቤተ ክርስቲያን መካከል ያለውን ምሳሌያዊ ግንኙነት የሚያፋልስ በመሆኑ ቤተ ክርስቲያኒቱ የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻን ትቃወማለች፡፡
3. ቤተ ክርስቲያኒቱ ግብረሰዶማውያንን ለቃሉና ለቅዱሳት ምስጢራት አገልግሎት መጥራትንም ሆነ ማቅሰስን አጥብቃ ትቃወማለች፤
4. ቤተ ክርስቲያኒቱ አሁንም ሆነ ለወደፊት የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻንና ግብረሰዶማውንን ማቅሰስን በተመለከተ የተወሰኑትን ውሳኔዎች በሙሉ እንደተጠበቁና የማይሻሻሉ መሆናቸውን ታረጋግጣለች፤
5. ቤተ ክርስቲያኒቱ ስማቸው ከተጠቀሰው ሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ስምምነት ፈርማለች በማለት የሚናፈሰው ወሬ ፈጽሞ ከእውነት የራቀ መሆኑን መሆኑን እንገልጻለን፤
6. በዚህ ትክክለኛ ያልሆነ መረጃ በማሰራጨት የቤተ ክርስቲያኒቱን ስም የሚያጎድፉና አንድነቷን ለማናጋት ከሚሰሩ ግለሰቦችም ሆነ ቡድኖች ፣ምዕመናኖቻችን እንዲጠነቀቁ እናሳስባለን።
7. በመጨረሻም በዚህ ጉዳይ ዙሪያ ጥያቄ የሚኖራቸው ምዕመናኖቻችን ካሉ በማንኛውም ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱ ማብራሪያ ለመስጠት ዝግጁ መሆኗን እናስታውቃለን፡፡
እግዚአብሔር ጸጋውንና ምህረቱን ያብዛልን።
የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን መካነ ኢየሱስ
መስከረም 21 ቀን 2017 ዓ/ም