ነገረ ወንጌላውያን

@negere_evangelical


በወንጌላውያን አማኞች ዘንድ የሚፃፉ ፅሁፎች፣ ዘገባዎችና ዜናዎች ይቀርባሉ! ትምህርቶች፣ መረጃዎችና ምካቴ እምነቶች በዚህ ቻናል ይስተናገዳሉ! በተለያዮ ሶሻል ሚዲያዎች የሚገኙ ፀሐፊያን የሚፅፉቸው ፅሁፎችን እናጋራለን።

ነገረ ወንጌላውያን

21 Jan, 00:21


ተሐድሶውና ማርቲን ሉተር

በቤተ ክርስቲያን የተሐድሶ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ የነበረው ጀርመናዊው ማርቲን ሉተር (Nov.10, 1483 - Feb.18, 1546)፣ "ጻድቅ በእምነት ይኖራል" (ሮሜ 1፡17) የሚለውን ቃል መሠረት በማድረግ፣ በወቅቱ የነበረውን የሮም ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ በተለይም በድነት፣ በአማኝና በቤተ ክርስቲያን ማንነት ዙሪያ ፊት ለፊት በመቃወም የጀመረው ታላቅ የተሐድሶ ንቅናቄ በቅርቡ አምስት መቶ ዓመት አልፎታል። ይህን ታሪካዊ ቀን ለማስታወስ በዓለም ዙሪያ፣ በተለይም በትውልድ ሀገሩ በጀርመን ዝግጅት ተደረጎ ነበር። ሉተር የወቅቷን የሮም ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያንን ስሁት አስተምህሮና ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በቀጥታ የሚጋጭ ተልኳዊ የራስ-ግንዛቤ የተቃወመበት 95 ጭብጥ ሀሳብ የያዘ ጽሑፍ "thesis" በቪተንበርግ ከተማ ቤተ ክርስቲያን (Wittenberg Castle Church) በር ላይ የለጠፈው ጥቅምት 31፣ 1517 ነበር። ይህቺ ቀን፣ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ አዲስ ምዕራፍ ከፍታለች፤ የታሪክም መገንጠያ ሆና ትታሰባለች።

ሉተር ማንም ሊደፍረው የማይችለውን የሮማ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስትያንን የተሳሳተ መሠረት፣ በነፍሱ በመወራርድ አናውጧል። April 18, 1521 በንጉሥ ቻርልስ አምስተኛ (የስፔንና የሮማ ካቶሊካዊ ግዛት ንጉሥ) በተሰየመው የቤተ ክህነት ፍርድ ቤት፣ አስተምህሮውን እንዲሽር (recant) በተጠየቀ ጊዜ፡- በታሪክ "እነሆ እዚህ ቆሜለሁ" (Here I stand) በመባል በሚታወሰው የሙግት ንግግሩ እንዲህ ብሎ ነበር፦

"የተከበሩትን ፓፓ ጨምሮ፣ ማንም ግለሰብ ቅዱሳት መጻሕፍትን በማስረጃነት በመጥቀስ ስህተቴን ካሳየኝ፣ ጽሁፌን በአደባባይ አቃጥላለሁ። ሆኖም ኅሊናዬ የቅዱሳት መጻሕፍት እውነት እስረኛ ሆኗል፤ ስለዚህ ከበራልኝ የእውነት ብርሃን ፈቀቅ ለማለት ኅሊናዬ አይፈቅድም፤ አያዋጣኝምም!"

May 8, 1521፣ ፍርድ ቤቱ "ኑፋቄ" በማለት ከቤተ ክርስቲያን አባልነት በሞት ፍርድ አገደው። ሥራዎቹም ታገዱ፤ ማንበብም ሆነ ማሰራጨት ሕገ ወጥ ድርጊት መሆኑ ታወጀ። ይሁን እንጂ፣ ሉተር እስከሞተበት ጊዜ ድረስ በታማኝት፣ በሞት ጥላ ውስጥ እያለፈ አገልግሏል።

ሉተር በብዙ መከራ ውስጥም እያለፈ፣ ውሎው ከእግዚአብሔር ቃል ጋር፣ ልቡም በመንግሥቱ ንጹህ የወንጌል ሥራ ላይ ያተኮረ ነበር። ትጉህ፣ የማይለጉም፣ ለጠራው እግዚአብሔርና ለበራለት እውነት ታማኝ ነበር። በዓመት ሁለት ጊዜ መጽሐፍ ቅዱስን ከጥግ እስከ ጥግ ያነብ ነበር። በሙሉ ጊዜ ፕሮፌሰርነት እያገለገለ፣ መጽሐፍ ቅዱስን በጀርመንኛ ተርጉሞ፣ ለገዛ ሕዝቡ የማይጠፋ ርስት አድርጎ አውርሷል። የእግዚአብሔርን ቃል እንደ ሕይወቱ እስትንፋስ አድርጎ ነበር የሚይስበው። የዘወትር የውስጥ ጩኸቱም;፟ "ዓይኖቼን ክፈት፥ ከሕግህም ተኣምራትህን አያለሁ።" (መዝ 119፡18) የሚል ነበር። እንዲህም ብሎ ጽፏል፦ "መጽሐፍ ቅዱስ ዛፍ፣ በውስጡም የተጻፉት ቃላት ቅርንጫፎች ቢሆኑ፣ እያንዳንዱን ቅርንጫፍ ደጋግሜ ወጥቼ ወርጄበታለሁ።" (What Luther Says: An Anthology, Vol. 1, p. 83)። ይኽም ለቃሉ የነበርው ረሃብ ያሳየናል። ከርስቶስን ያማከለ ታላቅ የቃሉም ሰባኪ ነበር። ከ1510-1546 ሦስት ሺህ ጊዜ ያህል ሰብኳል። ያም ማለት በአንድ ቀን ተኩል፣ አንድ የወንጌል ስብከት ማለት ነው። ምንም እንኳን፣ የቀድሞ አባቶችን ሥራዎች ጠንቅቆ ቢያጠናም፣ የስብከቱ ዋና ምንጭ ቅዱስ ቃሉ ነበር። የጸሎት ሰው ነበር - ከልቡ! ከከንቱ ኀይማኖተኝነት የመነጫ ሙት ልምምድ ሳይሆን፣ በመንፈስ ቅዱስ ኀይል የተደገፈና ሕያውነት የተሞላ ጸሎት ነበር። የተሃድሶውም ጩኸት መሠርቱ፣ የእግዚብሔር ቃልና የመንፈስ ቅዱስ ሙላት ነበር። የእኛስ የስብከታች መካከለኛ ምን ይሆን?

መዝሙር 46 ብዙ አጽናንቶታል። ልጅ ሞቶበታል፤ ከስሜት መርበሽ ጋር ታግሏል። እድሜውን በሙሉ በሞት ዐዋጅ ጥላ ውስጥ ነበር የኖረው። ማንም ሰው ቢያገኘው፣ እንዲገድለው ሕጋዊ ፈቃድ የሰጠው የቻርልስ አምስተኛ የሞት ዐዋጅ እንዲህ ይል ነበር፡-"ሥጋዬ፣ ነፍሴ፣ ደሜ፣ በመንግሥቴ ግዛት ያለ አስተዳደርና ዜጋ ሁሉ ሉተርን ከምድር ገጽ እንዲያጠፋው አዝዣለሁ" (Heiko A. Oberman, Luther: Man Between God and the Devil, 29.)። በኩላሊት ህመምና የራስ ምታት (ማይግሬን)፤ በሆድ ድርቀት፤ በጆሮ ቁስልና የትኩሳት ንዳድ ይሰቃይ ነበር። በአጋንት መንፈስ ነው የሚመራው፤ ሀሰተኛ ነብይም ተብሏል። August 2, 1527 የጻፈው ማስታወሻ እንዲህ ይላል፦

"ከሳምንት በላይ በሞትና በሲዖል ጥላ ውስጥ ተመላልሻለሁ። በክርስቶስ ላይ ያለኘ መታመን እስኪፈተን ድረስ መላው አካሌና መጋጣጠሚያዎቼ ሁሉ ታመዋል። የመከራ ጎርፍና ማዕበል ተባብረው፣ እምነትን የሚፈትን ድቅድቅ የቀን ጨለማ ውስጥ ከተውኛል። ተስፋ መቁረጥ ልቤን አድክሞታል። ይሁን እንጂ በቅዱሳን ምልጃ ተርፈኩኝ፤ እግዚአብሔርም በምህረቱ አሰበኝ፤ ከመከራዬም አሳረፈኝ። " (Man Between God and the Devil, 323.)

እናም ከዳዊት ጋር፦ "አምላካችን መጠጊያችንና ኀይላችን፣ በሚደርስብን መከራ ሁሉ የቅርብ ረዳታችን ነው። ስለዚህ ምድር ብትነዋወጥ እንኳ፣ ተራሮችም ወደ ባሕር ጥልቅ ቢሰምጡ አንፈራም። ውሆች ቢያስገመግሙ፣ ዐረፋ ቢደፍቁም፣ ተራሮችም ከውሆቹ ሙላት የተነሣ ቢንቀጠቀጡም አንደናገጥም።" (መዝ 46:1-3) በማለት ዘምሮ፣ በጸጋው ለትውልድ የሚተርፍ ሥራ ሠርቶ አለፈ።
ጌታ ተሃድሶውን ይስደድልን፣ ዘመንን መረዳት እንደአባቶች ይለግሰን! አሜን!
(በዶ/ር Girma Bekele )

#ተሐድሶው
#ማርቲን_ሉተር

ነገረ ወንጌላውያን

21 Jan, 00:16


“ተሓድሶና ቃሉ”

በአውሮፓ በ፲፮ኛው ክፍለ ዘመን የተጀመረው ተሓድሶ፥ ቤተ ክርስቲያንን ከአደገኛ የሞት እንቅልፍ አባንኗታል ። አዳሽነት ባህሪው የኾነው አሐዱ-ሥሉስ አምላክ በደካማ ሰዎች በኩል ቤተ ክርስቲያኑን ጎብኝቷታል ። ክስተቱ ቁልፍ ነገረ መለኮታዊ ዕሳቤዎች የተነቀነቁበት ብቻ አልነበረም ። የአገሮቹን ማኅበረ-ኢኮኖሚያዊ ገጽታ ላይ ጭምር ትልቅ ለውጥ ያመጣ ነበር ። የቤተ ክርስቲያን ተሓድሶ ያልነበረውን አላመጣም ፤ ዐዲስ ነገር አልጀመረም ። መሰረቱ ላይ የተከመረውን አቧራ አራገፈ እንጂ! ድንግዝግዝ ጭጋግ ላይ ብርሃን ፈነጠቀ እንጂ!

የቤተ ክርስቲያን ተሓድሶ በቀላል ቋንቋ እውነተኛውን የወንጌል ብርሃንና እርሱን የሚመጥን ኑሮ መልሶ መቀዳጀት ማለት ነው ። ወደ ቀደመው ርቱዕ መንገድ መመለስ ነው ።
እግዚአብሔር በደካማ ሰው በኩል የቤተ ክርስቲያኑን የፊት መጨማደድ በቃሉ ሂጶብ የሚያጸዳበት፥ በጸጋው ዘይት ዝገቷን የሚያራግፍበት ሂደትም ነው ። ምክንያቱም በጎሎጎታ የተመረቀው የሰማያዊው መንግሥት አብዮት ጥልቀቱና ኅይሉ መታወቅ ስላለበት ። የመስቀሉ ሥራ ሁሌም ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች ሞኝነት እንደሆነ መቀጠል አለበት ። ሰው በራሱ ሞራላዊ ጥረትና የአዕምሮ ልህቀት አምላክን ማወቅና ከኅጢአት በሽታው መገላገል እንደማይችል ሊገባው ያስፈልጋል ። ባጠቃላይ የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ !

ተሓድሶው ሲጀመር እጅግ አወዛጋቢ ነበር ። በክርስትና ስም በተደላደለው የሰው ሥርዐትና ወግ ላይ የተወረወረ ቦንብ ነው ። ፍንዳታው ከሩቅ ተሰምቶ በየቦታው ሲብላሉ የነበሩ ተመሳሳይ ጩኸቶች እንዲሰሙ አስችሏል ። እስከዛሬም ድረስ ‹ቤተ ክርስቲያን መታደስ አለባት› የሚለው የተሓድሶ ጩኸት ለአንዳንዶች ጆሮ የማይስማማ እንግዳ ድምጽ ነው ። ጥቂቶችን ያስቆጣል ፤ በሌሎች ዘንድ ግርታንና ፌዝ ይፈጥራል ። አወዛጋቢነቱ በከፊል የሚመነጨው ሰው ጒረኛና ጥቅመኛ ስለሆነ ነው ። ትህትናንና ዝቅ ማለትን ፣ በየትኛውም ጉዳይ 'አስተዋፆ የለህም ወይም አትችልም' መባልን አይፈልግም ። ተሓድሶ ደግሞ የሰውን ጥበብና ችሎታ አሳንሶ የእግዚአብሔርን ጥበብ [መሲሑን] የማላቅ ፕሮጀክት ነው ።

በተሓድሶ ነገረ-መለኮት ውስጥ የሰው ትምክህት ቅንጣት ቦታ የለውም ። ተሓድሶን መናፈቅ ማለትም ይኼንን “መራራ”
እውነት ዐውቆና ፈቅዶ መቀበል ማለት ነው ። ሰው ድነቱን — ወይም ስለ እግዚአብሔር ያለውን ልከኛ እውቀትና ምልልስ — በራሱ ማስተዋል ፣ በመልካም ሥነ ምግባር ወይም በኅይማኖት ድርጅት አባልነት ማግኘት አይችልም ። ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚመሰክሩት የሰማዩ መንግሥት ጉዳይ ከሀ እስከ ፐ ከእግዚአብሔርና ለእግዚአብሔር ነው ። ማንም በመልካም ሥራው እንዳይመካ!

ማዳን የእግዚአብሔር ነው ስንል ምን ማለታችን ነው? እግዜሩ የሰውን ድነትና ዋስትና በተመለከተ ኪዳን የገባውም የፈጸመውም ብቻውን ነው እያልን ። ይኼም ዘላቂና አስተማማኝ አምላካዊ ኪዳን ነው ። በብሉይ ኪዳን ለአብርሃም የተገባለት የተስፋ ቃል የተፈጸመው በዐዲሱ ኪዳን በመሲሑ ደም ነው ። ከኅጢአት በሽታ መዳን ፣ በትንሣኤው ኅይል መጽደቅ ፣ ዐዲስ ፍጥረት መኾን ፣ መላ-ዐለሙን በሚያድስበት ድንቅ አሠራሩ ከርሱ ጋር አብሮ ሠራተኛነት ፣ በዐዲሱ ሰማይና ምድር ከንጉሡ ጋር በትንሣኤ አካል መክበር ... ተጀምሮ እስከሚያልቅ በእግዚአብሔር ጸጋ ላይ ብቻ ከተመሠረተ - ክብሩም ምስጋናውም ለእርሱ ብቻ ይገባል ። “የሚመካ በእግዚአብሔር ይመካ” እንዲል ቃሉ!

ይኼን እውነት ሓዳሲያኑ ከየትም አላገኙትም ። ልዩ ፍጥረት አልሰበከላቸውም ፤ ልዩ መገለጥም አልመጣላቸውም ። በእጃቸው የነበረውን ቅዱሳት መጻሕፍትን አክብረው ሲገልጡትና ሲያጠኑ - እውነቱ በራላቸው ። ለአስተምህሮም ሆነ ለምልልስ ቃሉን ቀዳሚ ባለስልጣን አድርገው ሲሾሙ - ለእግራቸው መብራት ለመንገዳቸው ብርሃን ሆነላቸው ። ከቆየ የቤተ ክርስቲያን ልማድም ሆነ የሰው ወግ ቃሉን ሲያስበልጡ — የጸጋው ጉልበትና የሰው ድሽቀት ታያቸው ።
“ቅዱሳት መጻሕፍት ብቻ” ብለው ሲጸኑ — ሁሉም ጉዳይ ቦታ ቦታውን ያዘላቸው ።

በOctober 31, 1517 ፣ 95ቱን አንቀፆች በቪተንበርግ ካቴድራል ማስታወቂያ ሰሌዳ በመለጠፍ የተሓድሶን እሳት በመለኮስ ፈር ቀዳጅ የሆነው ጀርመናዊው ማርቲን ሉተር፥ ስለተቀጣጠለው እንቅስቃሴ ሲናገር “I did nothing; the Word did everything. - እኔ ምንም አላደረኩም፤ ሁሉን ያደረገው ቃሉ (የእግዚአብሔር) ነው!” እንዳለው ነው!

ክብር ለአዳሹ ያሕዌ ይሁን!

#ተሓድሶው_ሲታወስ
#ቅዱሳት_መጻሕፍት_ብቻ

በፍጹማን ግርማ

ነገረ ወንጌላውያን

21 Jan, 00:10


ዓመታዊ የስትራውስ-ኬዳሞ ሌክቸርስ በኢቫንጀሊካል ቲዮሎጂካል ኮሌጅ (ETC) ከጥቅምት 6 - 8፤ ከ 11፡00 - 1፡15 ሰዓት ይከናወናል። ማርክ ኤል ስትራውስ (ዶ/ር) የዘንድሮው ሌክቸር ተናጋሪ ናቸው። ይህንን ዝግጅት እንድትታደሙ ተጋብዛችኋል!

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 23:45


"የቆማችሁበትን ወንጌል ላሳስባችሁ እወድዳለሁ።" (1ቆሮ. 15፥1)

የቤተ ክርስቲያንም ሐዋሪያዊ ተልእኮ የሚመነጨው፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰበከው የእግዚአብሔር መንግሥት ወንጌል ነው። በእርሱ ቤዛዊ የመስቀል ሞት የእግዚአብሔር መንግሥት ተገልጧል። (ማር. 1፥15፤ ሮሚ 1፥2-5)። ከዚህ ዘላለማዊ እውነት ውጪ ቤተ ክርስቲያን የራሷ የሆነ ማንነትና ተልእኮ የላትም። ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ኹሉን ዐቃፊ፣ ክፍት፣ ገደብ የለሽና የዘፈቀደ እንቅስቅሴ አይደለም። ጅማሬውም፤ ፍጻሜውም ክርስቶስ ነው።

ኾኖም ክርስትና ዐውዳዊ ነው። ቃል ሥጋ ሆነ! በርግጥ አምላክ እንደ እኛ ኾነ። የሰውን ኹለተና፣ በሥጋ ብቻ ሳይሆን በጊዜ፣ በቦታ፣ በቋንቋና በባህል ተካፍሏል። ባህል የለሽ (culture-less) ክርስትና የለም። ባህል ስንል፣ የማኅበራዊ ስብስባችን የጋራ ፋይዳ ነው። ይህም ርእዮተ ዓለምን፣ እምነትን፣ ልማድን፣ ሥነ ምግባርን፣ ቋንቋን፣ ትውፊትን፣ ሙዚቃንና አጠቃላይ ማኅበራዊ መስተጋብሮችን ያካትታል።

ወንጌልን ሰው ኹሉ በቋንቋውና በባህሉ ዐውድ ሊሰማው ይገባል። ወንጌል ዘላለማዊ ነው፤ አይቀየርም። ዐውድ ግን በጊዜና በቦታ የተለያየ ነው። እውነተኛ ዐውዳዊነት የወንጌልን መልክእት ሳይቀይጥ፣ ሳይቀንስና ሳይጨምር የማስተላለፍ ዐደራ ነው። በእውነተኛ አግባብነቱ፣ ርቱእ ነገር መለኮታዊ ዐውዳዊነት በአዲስ ኪዳኗ የመጀመሪያ ቤተ ክርስቲያንና በእኛ መካከል ያለውን የቋንቋና የባህል ርቀት የሚገናኝ ድልድይ ነው።

ክርስቶስ በደሙ የዋጀንና የእግዚአብሔር መንግሥትና ካህናት ያደረገን “ከነገድ ሁሉ፣ ከቋንቋ ሁሉ፣ ከወገን ሁሉ፣ ከሕዝብ ሁሉ” ነው። የእርሱ ቤዛዊ የመስቀል ሥራ በኀጢአት የተለወሰውን የሰውን ኹለንተና ዋጅቷል። ይህም ባህላችንን ያካተተ ነው ስለዚህ የክርስቶስ ብቸኛ ቤዛዊ ሥራ ዋጅቶናል ስንል፣ ከኀጢአትና ባዕድ አምልኮ ጋር ትሥሥር ካለው ከየትኛው ባህል ጭምር ማለታችን ነው። ክርስቶስ በእነዚህ ፋይዳዎች ላይ ደባል ሆኖ አይደለም ያዳነን! ይልቁንም፣ የእርሱ ሕዝብ ያደረገን እነዚህን ማንነቶች ኹሉ በማደስ ለክብሩ እንድንኖርለት በማድረግ ነው። በአንድ ጊዜ ለክርስቶስም ከወንጌል ጋር ተቃርኖ ላለውም ባህልና ማኅበራዊ ዕሳቤ መኖር አንችልም!

ቅይጥነት በብዙ መልኩ የዘመናችን ወንጌላዊ ክርስትና ተጋዳሮት ነው። ለዚህ ዐቢይ ምክንያት የመጸሐፍ ቅዱስን የመጨረሻ ባለሥልጣንነትና የክርስቶስን ማዕከላዊነት ጠርዝ ላይ ያቆመ ልዝብ ዐውዳዊነት ነው። በርግጥ በመንፈሳዊ ሕይወታችንና ልምምዳችን እስተንፋሰ እግዚአብሔር የኾነውን ቅዱስ ቃል የመጨረሻ በያኝ፣ እንዲሁም በአስተርዕዩተ እግዚአብሔር (በእግዚአብሔር መገለጥ) ክርስቶስ እኩያ የሌለው፣ ብቸኛ፣ ፍጹም፣ ወሳኝና፣ የመጨረሻ አዳኝ አድርገን ከተቀበልን፣ ከወንጌል እውነት ጋር ከሚጣረሱ ፋይዳዎች ጋር ቀጥታ የሆነ የማይታረቅ ግጭት አለን። መርሳት የሌለብን የትኛውም ባህል በኀጢአት የተለወሰ ነው። ሰው ድኅነት ሲያገኝ ዕይታውና ዕሴቱ ኹሉ ሥር ነቀል በኾነ መልኩ ይቀየራል። በየትኛው ትውልድና ዐውድ መካከል ያለች የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ተልእኳዊ ተአማኒነትና ቅቡልነት የሚመዘነው በዚሁ ዘላለማዊና ጳውሎስ “የልጁ ወንጌል” በማለት ስለሚመስክርለት የእግዚአብሔር መንግሥት የምሥራች ነው።

የወንጌላውያን እምነት ሚሲዮናዊ ማዕከል የነበረው የምዕራቡ ዓለም፣ አሁን የደረሰበት የድኅረ ክርስትና የአመራር፣ መንፈሳዊና ሥነ ምግባራዊ ቀውሶች ዘገምተኛ የቍልቍሎሽ መንገድ ጅማሬ፣ የቅዱሳት መጻፍሕፍት እውነትቶች ዐዐውዱ ተቀባይነት እንዲኖራቸው ሲበርዝና፣ ክርስቶስንና ሥራውን ጠርዝ ላይ ባሰቀመጠ ጊዜ ነበር። ቢያንስ በስኮትላንድ የዛሬ መቶ ዐሥራ ሁለት ዓመት የነበረውን ወርቃማ ዓለም ዐቀፋዊ የወንጌል አጀንዳ መነሻ ካዳረግን (The 1910 World Missionary Conference, Edinburgh, 14-23 June 1910)፣ የእኛን የወቅቱን ኹሉን ዐቃፊ የአስተምህሮና አመራር ቀውስ ስመለከት በፈጣን ሩጫ የገባንበት ይመስለኛል።

የስብከተ ወንግጌል ተኣማኒነትና የጽድቅ ተጽእኖ ዐቅም መሠረቱ ያረፈው፣ ለእግዚአብሔር ቃል የመጨረሻና የበላይ ባለሥልጣንነት ባለን መሠጠትና ታማኝ ባለ ዐደራነት ላይ ነው። አማኙ ማኅበረ ሰብ፣ ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የተጠራ፣ የተመረጠ ትውልድ፣ የንጉሥ ካህናት፣ ቅዱስ ሕዝብ፣ ለርስቱ የተለየ ወገን ከሆነ (1ጴጥ 2፥9)፣ ይህን መሠረታዊ እምነት ከሚያፋልስ የትኛውም ንጽረተ ዓለም፣ ባህል፣ አስተምህሮ፣ ሃይማኖትና ርዕዮተ ዓለም ጋር የማይታረቅ ልይነት አለው።

በዚህ አግባብነት የአገራችን የተልያዩ በዓላት ባህል ብቻ ሳይኹኑ መፈሳዊ ገጽታም አላቸው። በየትኛውም መልኩ (ቢያንስ እንደ ወንጌላውያን አማኞች) ልባችን ላይ የበራውን የወንጌል እውነት ካላደበዘዝን በስተቀር፣ ኹሉቱ እውነቶች መለያያት አንችልም። ይኸው እውነት በኦሮሞው ኢሬቻ፣ በሲዳማው ፍቼ ጨምበላላ፣ በወላይታው ጊፋታ፣ በሀዲያው ያሆዴ እንዲሁም በሌሎች ባህላዊ በዓላት ላይ ባሉት ዕይታዎች ኹሉ ላይ አግባብነት አለው። ከሰብአዊ መብት አንጻር፣ ሌላውን በዐመፅ እስካላሰገደደ ድረስ፣ ማንኛውም ግለ ሰብ ወይም ሕዝብ ያሻውን ባህል የማክበር ነጻ ፈቃድና መብት አለው። ኾኖም ኹለት የአተያይ ተፋልሶዎች አሉ። አንደኛው፣ ባህላዊ በዓላት ፈጽሞውኑ ሃይማኖታዊ ገጽታ የላቸውም የሚለው ሙግት ነው። ኹለተኛው ደግሞ፣ እነዚህ ባህላዊ በዓላት ከወንጌል እውነት ጋር ምንም ዐይነት ተቃርኖ የላቸውም የሚለውና ኹሉን አስደሳችነት የተጠናወተው ልዝብ ክርስቲያናዊ ፋይዳ ነው።

እነዚህ አመለካከቶች ናቸው የምዕራቡን ዓለም ክርስትና ሕይወት ለነሳው ብዝኀተ ሃይማኖተኝነት (religious pluralism) እንዲሁም ሸንጋይ አካታችነት (dishonest inclusivism) አሳልፎ የሰጡት። ብዝኀተ ሃይማኖተኝነት፣ የክርስትናንን መሠረታዊ ዕሴቶች በማደብዘዝና በሃይማኖቶቸ መካከል ያለውን ልዩነት አንጻራዊ በማድረግ፣ ሁሉንም “የአንድ እውነት” የተለያዩ ገጽታዎች በማድረግ ይሟገታል። የእኛንም መድረክ መቦርቦር ጀምሯል። የኹለቱም ዕይታዎች ችግር ክርስትና ከባህልና ከሌሎች ሃይማኖቶች ጋር ሊኖረው የሚገባውን ጤናማና ሚዛናዊ የኾነ መጽሐፍ ቅዱሳዊና ነገረ መለኮታዊ አቋም ማለዘቡ ነው።

በኢማኑኤል ካንት የፍልስፍና ተጽዕኖ ሥር የወደቀው እና የወንጌል እምነቱን በለዘብተኛ ነገረ መለኮት አስተምህሮ (liberal theology) የተካው፣ ኬምብሪጅን ጨምሮ በተለያዩ ከፍተኛ ተቋማት በማስተማሩ በስፋት የሚታወቀው ጆን ሂክ፣ “ሁሉም ሃይማኖቶች የአንዱ መለኮታዊ እውነት ልዮ ልዩ የሆኑ አቻ መልኮች ናቸው” በማለት የዘራው ክፉ ዘር፣ የምዕራቡን ዓለም የወንጌል እምነት ለመሸርሽር ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል። (An Interpretation of Religion: Human Response to the Transcendent, Basingstoke: Macmillan, 1989, 301)]። ሂክ፣ “በሃይማኖቱ ዓለም ውስጥ፣ ክርስቶስ ወደ አንዱ አምላክ ከሚያመላክቱ የመገለጥ ከዋክብት መካከል አንዱ ኮከብ እንጂ፣ በራሱ ብቸኛና ፍጹም ብርሃን አይደለም” በማለት ከሞገተ በኋላ፣ ክርስቶስን መካከለኛና ብቸኛ አዳኝ አድርጐ መስበክ፣ “ሃይማኖታዊ ኢምፔሪያሊዝም ነው” በማለት ደምድሟል (Philosophy of Religion [Englewood: Prentice – Hall, 1983] 107ff)።

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 23:45


የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል አሁን ለደረሰበት የራስ ውድቀት ትልቅ አስተዋጽኦ ያደረገው፣ የወንጌልን ንጽሕና ያጠለሸ ልቅ ኢኪዩሚዝም (ecumenism) እንደ ሆነ ታሪክ ያስገነዝበናል። የካውንስሉ ሁሉን ዐቃፊነት (ሃይማኖት፣ ባህልና ፓለቲካ) መርሕ መሠረት ያደረገው፣ “ዶክትሪን ይለያያል ፍቅር አንድ ያደርጋል” የሚለው ተቃርኗዊ አመለካከት ነው። የዚህ ዐይነቱ ኢኪዩሚዝም መንፈስ ምድራችን ላይ እያኮበከበ መሆኑን ልብ ልንል ይገባል። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማግሥት የዓለም አብያተ ክርስቲያናንት ካውንስል በአምስተርዳም ሲመሠረት፣ አሁን የደረሰበት መንፈሳዊ ቀውስ ላይ እደረሳለሁ ብሎ አልነበረም።

ወንድሞችና እኅቶች፣ የወንጌል እውነት ሲቀየጥ የማንነተ ቀውስ ይገጥመናል፤ መንፈስ ቅዱስም ይሸሸናል። ልብ እንበል! ይህን የምለው ከብዙ አክብሮትና ትሕትና ጋር ነው። የክርስቶስ ወንጌል ከደባል ጋር የማያኖረውና ሊፋቅ የማይችል ድንበር አለው። የክርስትና መልእክት ዋጋ ያስከፍላል! በባህልና ሙዚቃ ሰበብ ለትውልዱ ምን ይሆን እያስተላለፍን ያለነው?

ሐዋርያው ጳውሎስም፣ በክርስቶስ ልጁ ለነበረው ወጣቱ ጢሞቲዎስ ዐደራ ሲለው (1ጢሞ 6፥20)፣ በእጁ ያለውን ወንጌል፣ እግዚአብሔር ለእኔ በዐደራ ከሰጠኝ የክብር ወንጌል (1 ጢሞ 1፥11)፣ በማለት፣ ወንጌል ተጀምሮ እስከሚያልቅ ድረስ ለቤተ ክርስቲያን በዐደራ የተሰጠ የእግዚአብሔር መልእክት መሆኑን በጥብቅ በማሳሰብ ነበር።

“ጳውሎስ፣ የክርስቶስ ኢየሱስ ባሪያ፣ ሐዋርያ ሊሆን የተጠራና ለእግዚአብሔር ወንጌል የተለየ፤ ስለዚህ ወንጌል በነቢያቱ በኩል በቅዱሳት መጻሕፍት አስቀድሞ ተስፋ ተሰጠ። ወንጌሉም ስለ ልጁ፣ በሥጋ ከዳዊት ዘር ስለ ሆነ፣ በቅድስና መንፈስ ደግሞ ከሙታን በመነሣቱ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑ በኀይል ስለ ተገለጠው ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። በእርሱ በኩል ስለ ስሙ ከአሕዛብ ሁሉ መካከል ሰዎችን በእምነት አማካይነት ወደሚገኘው መታዘዝ ለመጥራት ጸጋንና ሐዋርያነትን ተቀበልን።” (ሮሜ 1፥1-5)

በመቀጠልም፣ በሕይወቱ ማብቂያ ዋዜማ ላይ ጳውሎስ በአራት ምስክሮች ፊት መጋቢ ጢሞቴዎስን ስለ ወንጌል ባለ ዐደራነት በጥብቅ ያሳስበዋል፦

🎚በእግዚአብሔር ፊት
🎚እንዲሁም በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ ባለው በክርስቶስ ኢየሱስ ፊት
🎚መገለጡንና
🎚መንግሥቱን

በማሰብ ይህን ዐደራ እልሃለሁ፦ ቃሉን ስበክ!

ጌታ ሆይ፤ የአንተን ወንጌል ዐደራ ጠባቂ፣ ታማኝ አስተላላፊም አድርገን። አሜን!

ግርማ በቀለ (ዶ/ር)

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 23:35


መጋቢ ሰሎሞን ጥላሁን

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 23:33


ተሐድሶ ፈልገን፣ አሮጌ አቍማዳም ይዘን አይኾንም። ታዲያ ከዚህ ወዴት እንሂድ?

ከቤተ ክርስቲያን ልጀምር። ኾኖም በፈራጅነት መንፈስ ሳይኾን፣ በእግዚአብሔር ምሕረትና ጸጋ እንደ ተደገፈና እውነተኛ ተሐድሶን እንደሚናፍቅ አገልጋይ የቀረበ ተማጽኖ ነው።

“ሰዎች ቢውድቁ፣ እንደ ገና ከወደቁበት አይነሡምን? ሰው ተሳስቶ ወደ ኋላ ቢሄድ፣ ከስሕተቱ አይመለስምን? ታዲያ፣ ይህ ሕዝብ ለምን ፊቱን አዙሮ ወደ ኋላ ይሄዳል? ለምንስ ኢየሩሳሌም ዘወትር ወደ ኋላ ትመለሳለች? ተንኰልን የሙጥኝ ብለው ይዘዋል፤ ሊመለሱም ፈቃደኛ አይደሉም።” (ኤር. 8፥3-5)

እግዚአብሔር የይሁዳን ልበ ደንዳናነትና ያንኑ ያከሰራትን የጥፋት ጐዳና በተደጋጋሚ ለመሄድ መወሰኗን የገለጠበት መንገድ፣ እንደ አገር የእስከ አሁኑን አካሄዳችንን የሚያሳይ ይመስለኛል። ይሁዳ ያለፈው የእሥራኤል ታሪክ ያለመማሯ ብቻ ሳይሆን፣ እጅግ በከፋ መልኩ በመድገሟም አዝኗል። “ከከሓዲዋ ይሁዳ ይልቅ ከዳተኛዪቱ እስራኤል ጻድቅ ሆና ተገኘች።” (ኤር. 3፥11)። ልክ እንደ እስራኤል፣ የአመራር፣ የመንፈሳዊ፣ የፍትሕና የሞራል ቀውስ፣ ይሁዳንም ለራስ ጥፋት አሳልፎ ሰጥቷታል።

ጌታችንን ከጠቀሰው የአቍማዳ ምሳሌ እንደምንረዳው፣ የፈሪሳዊነት መንገድና ተሐድሶ ምንጊዜም ዕርቅ አይኖራቸውም። ከእግዚአብሔር ቃል የበላይ ባለሥልጣንነት ርቀን፣ ባለፈው ዓመት ይኼድንበትን ያንኑ መንገድ በመድገም ተሐድሶን ተስፋ ማድርግ የራስ ግጭት ነው። የዘመኑ ክርስትና መልክ ላለፉት 30 ዓመታት የዘራነው ነው። መስቀሉን በመሸክምና ለራስ ፈቃድ በመሞት ለወንጌል እውነት የሚኖር ደቀ መዝሙር አፈርተናል ማለት በብዙ መልኩ አይቻለም። ለዚህም በወንጌላዊው አማኝ ማኅብረ ሰብ መካከል ያለው የአስተምህሮ፣ የአመራር፣ የሥነ ምግባርና የሞራል ቀውስ ገላጭ ነው። ቅቡለንትና ተዓማኒንት በማጣት እጅግ ተጐድተናል። በንግዱ ዓለም ያለው “ደንበኛን በየትኛው መልኩ” የማፍራትና የመያዝ ዕሳቤ ገዝቶናል። እውነትና መስበክ፣ መገሠጽና ተጠያቂነት ያለው የደቀ መዝሙርነት ሕይወት ማስረጽ ተጀግርናል። በቍጥር ላይ እንጂ በጥራት ትኵረት አጥተናል። አባላትን ማጣት እንፈልግምና!

የምዕራቡ ዓለም ክርስትና አሁን ለደረሰበት የራስ ውድቀት ትልቅ አስተዋጽዖ ያደረገው የራስ-ግንዛቤ ዝግመታዊ ዝመት፣ የወንጌልን ንጽሕና ያጠለሹ ልቅ/ልዝብ ኢኪዩሚኒዝም እንዲሁም ሃይማኖታዊ ሸማችነት (religious consumerism) እንደሆኑ ታሪክ ያስገነዝበናል። ሃይማኖታዊ ሸማችነት ሰብእ ተኮር ነው። የ “ሰው” (የሸማቹ) ሃይማኖታዊ የገበያ ፍላጐት ገዢው ፋይዳ ነው። በዚህ ሃይማኖታዊ የንግድ ለውውጥ ጌታ ከአጥር ውጭ ነው። በዚህ ላይ ኹሉን ዐቃፊነት (ሃይማኖት፣ ባህልና ፓለቲካ) መርሖ መሠረት ያደረገው “ዶክትሪን ይለያያል ፍቅር አንድ ያደርጋል” የሚለው የአንድነት ፍለጋ፣ የሰሜኑንን ክርስትና መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማንነት አሳጥቶታል። ዓለምና ቤተ ክርስቲያን ተወዳጅተዋል። ይኽም ጌታ "በኖራችሁበት በግብፅ እነርሱ እንደሚያደርጉት አታድርጉ፤ እኔ በማስገባችሁ በከነዓን እንደሚያደርጉትም አታድርጉ፤ ልማዳቸውንም አትከተሉ።" (ዘሌዋውያን 18፥3)፤ እንዲሁም "ነገር ግን የጠራችሁ እርሱ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተም በኑሯችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ፤ ምክንያቱም 'እኔ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ' ተብሎ ተጽፏል።" (1 ጴጥሮስ 1፥1516)። በማለት ለኪዳኑ ህዝብ ከሰጠው ማንነት ጋር በተቃርኖ የቆመ ድብልቅነት ነው። ዓለምን መስለንም ተሐድሶም ፈልገንን እንዴት ይኾናል?

በእውነት ተሐድሶን ከተጠማን፣ በእውነተኛነት ፍሬ በሚገለጥ ንስሓ ወደ እግዚአብሔር መመለስ ይኖርብናል። ይኽም ማለት የእግዚአብሔር ቃል እንደሚለው የውደቀታችን ጥልቀት መረዳት፣ መመለስና ወደ ቅዱስ ቃሉ መንገድ መመለስ ነው። “እንግዲህ ከየት እንደ ወደቅህ ዐስብ፤ ንስሓ ገብተህ ቀድሞ ታደርገው የነበረውን ነገር አድርግ” (ራእይ 2፥5) የእግዚአብሔር የምሕረት ደጆች አልተዘጉም። ፈሪሓ እግዚአብሔርን ከረገጥን፣ ምን ተስፋ አለን? ስለዚህ በግልና በጋራ የእግዚአብሔርን ምሕረት እንድናገኝ በእውነተኛ ንስሓ ወደ እግዚአብሔር እንመለስ።

ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ ናት፤ ያለ እርሱ ሕልውናም ኾነ መልእክት የላትም። በአጭሩ ቃሉ ይግዛን! ወደ ጽሎትም እንመለስ። እንደ ቃሉ ያልኾነ አስተምህሮ፣ አመራር፣ መንፈሳዊ ልምምድ ዅሉ ከመካከላችን ለማውጣት መወሰን አለብን። ያንኑ ከጌታ ቃል ውጪ የኾነ መንገድ እየኼድን ተሐድሶን ተስፋ ልናደርግ አንችልም። የተሐድሶ መንገዱ ይኸው ነው። ከዚህ ውጭ ዘመናችን እንዲሁ በናፋቂነት ያለቃል . . . ፈሪሳውያንና ክርስቶስ ተላለፈዋልና እግዚአብሔር ከዚህ ይጠብቀን!

አሜን!

በክፍል ኹለት ቤተ ክርስቲያንና ኅያላት ርእስ ጕዳይ እንገናኝ።

ግርማ በቀለ (ዶ/ር)

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 23:29


ንጹህ አንድነትና ግልጽ ልዩነት በክርስቶስ

1. ክርስቶስ አንድ አድራጊ ነው - ንጹሕ አንድነት

“ለተጠሩት ግን፥ አይሁድ ቢሆኑ የግሪክ ሰዎችም ቢሆኑ፥ የእግዚአብሔር ኃይልና የእግዚአብሔር ጥበብ የሆነው ክርስቶስ ነው።” (1ቆሮ. 1:24-25) በክፍሉ ዐውድ አይሁድ - ምልክት ፈላጊዎች ግሪክ - ጥበብ ፈላጊዎች ሁለቱም ያለ ልዩነት በክርስቶስ አምነው በጸጋው ሲድኑ የእግዚአብሔር ጥበብ የሆነው ክርስቶስ መገጣጠሚያ ድልድይ መገናኛ ማዕከል የአንድነት ምሰሶ ይሆና ቸዋል። ክርስቶስ አንድ አድራጊ ነው ይህም በመስቀሉ ሥራ ነው። ቃሉ ጥልን በመስቀሉ ገድሎ አሕዛብንና አይሁድን አዋህዶ አንድን አካል መፍጠሩን ነው የሚነግረን። “ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን በአንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋር ያስታርቅ ዘንድ ነው። … በእርሱ ሥራ ሁላችን በአንድ መንፈስ ወደ አብ መግባት አለንና። (ኤፌ. 2:16, 18) ባሪያ ቢሆን ጨዋ፣ ወንድ ቢሆን ሴት፣ ባለጠጋ ቢሆን ድሃ፣ የተማረ ቢሆን መሐይም፣ ባለሥልጣን ቢሆን ተራ ሰው፣ ክርስቶስን በማመን ወደ እግዚአብሔር ቤተሰብነት ወደ ክርስቶስ አካልነት መቀላቀል እንዲችል እግዚአብሔር በጸጋው አስችሎአል። ይህ አንድነት የመስቀሉ ሥራ በረከት ነው። ንጹህ አንድነት ነው። በክርስቶስ አንድ ነን።

ክርስቶስን ስንቀበል ሁላችን የተቀበልነው መንፈስ ቅዱስ አንድ ነው። ሐውስርያው ጳውሎስ ስለዚህ ሲናገር:- “አይሁድ ብንሆን የግሪክ ሰዎችም ብንሆን ባሪያዎችም ብንሆን ጨዋዎችም ብንሆን እኛ ሁላችን በአንድ መንፈስ አንድ አካል እንድንሆን ተጠምቀናልና። ሁላችንም አንዱን መንፈስ ጠጥተናል።” (1ቆሮ.12:13) ይላል። የአማኞች አንድነት መንፈሳዊ ነው የምንለው በክርስቶስ በመሆን ከተቀበልነው ከዚሁ መንፈስ የተነሳ ነው። ቤተ ክርስቲያን የመስቀሉን ቃል (የክርስቶስን ወንጌል) ያለ ማመንታት መስበክና በመስቀሉ ላይ በተሠራው የክርስቶስ ሥራ ሰዎችን ወደ አካሉ አንድነት መሳብ ጥሪዋና ተልዕኮዋ ነው። የማታለያ ወንጌል የክርስቶስን የመስቀሉን ሥራ የመንፈስንም አንድነት መሸፈን አይኖርበትም። “እኔ የዚያ ወገን ነኝ…፣ የሱ ተከታይ ነኝ…፣ ከዚያ ዘር ነኝ…፣ እኔ የእንትና አድናቂ ነኝ…፣ የሚባለው ልዩነት በክርስቶስ ላሉት ጨርሶ አይሠራም። የአንድነት ማዕከሉ ክርስቶስ ነው። የመስቀሉ ሥራ ነው። ይህ እምነት የ አንድነት ዋስትና ነው። ክርስቶስን ያለመስበክ የመስቀሉን ሥራ ዋጋ ቢስ ማድረግ የተቀበልነውንም መንፈስ ማቅለል ነው።

2. ክርስቶስ ልዩነት ፈጣሪ ነው - ግልጽ ልዩነት

“የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት፥ ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና።” (1ቆሮ. 1:18) ይላል። በዚሁ ክፍል የሚጠፉትና የሚድኑት በማለት ሁለት ክፍል አካላት ይታያሉ። በክርስቶስና በመስቀል ላይ ሥራው ምክንያት የሰው ዘር በግልጽ ለሁለት ተከፋፍሎአል። እግዚአብሔር ያዘጋጀውን የመዳንን መንገድ የሚቀበሉትና በሞኝነት ቆጥረው ችላ በማለት ልባቸው በአመጽ የሚደነድንባቸው በግልጽ ይለያያሉ። የልዩነቱን መስመር ማጥበብም ሆነ ማደብዘዝ አንችልም። በንስሓና በክርስቶስ በማመን ብቻ እንጂ ይህ የልዩነት መስመር በምንም በሌላ መንገድ ሊጠፋ አይችልም። ይልቁንስ የክርስቶስ ሥራ የመስቀሉ ቃል በግልጽነት በተሰበከ መጠን ይህ የልዩነት መስመር ይደምቃል። ልዩነቱ ግልጽ ይሆናል። የሚጠፉቱ ይህንን የመስቀሉን ቃል እንደ ሞኝነት ይቆጥሩታል። የሚድኑቱ በአንጻሩ በጎ ምላሽ ይሰጣሉ የእግዚአብሔር ኃይል ይሆንላቸዋል የመዳን በረከት ይሆንላቸዋል። በክርስቶስ ልዩነታችን ግልጽ ነው።

የሐዋርያው የመልዕክቱ ፍሬ ሃሳብ ከሰዎችና ከጥበብ ንግግራቸው ላይ ትኩረታቸውን አንስተው ወደ መስቀሉ መልዕክት እንዲመለሱ ነበር። ለዚህ ነው “እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን፤ ይህም ለአይሁድ ማሰናከያ ለአሕዛብም ሞኝነት ነው።” (1ቆሮ. 1:23) በማለት ዓይኖቻቸውን ከሰዎችና ከጥበብ ቃሎቻቸው ወደ ተሰቀለው ክርስቶስ የሚጋብዘው። በሚድኑትና በሚጠፉት መካከል ያለው ገደል ክርስቶስ በመስቀሉ ላይ ከሠራው ሥራ ውጭ በምንም ሊቀራረብ ስለማይችል ሰፊ ልዩነት ይፈጠራል። ብርሃን ከጨለማ ጋር ያለው ዓይነት ልዩነት፣ የጨውና አልጫ ዓይነት ልዩነት አለ። ዘመናዊውና ማኅበራዊው ወንጌል፣ ኢኮኖሚ ተኮር የሆነ ወንጌል፣ ስሜት ኮርኳሪው ወንጌል፣ የፈውስና የምቾት ወንጌል ይህንን በሚድኑትና በሚጠፉት መካከል ያለውን ልዩነት ደብዛዛ ያደርገዋል። የብልጽግና ወንጌል ክርስቶሳዊ ሳይሆን ቁስ ተኮር በመሆኑ ሁለቱን ወንጌል የለያቸውን ሰዎች ከሌሎች ጋር የማመሳሰል ዓላማ ያለው አጋንንታዊ ተልዕኮ ነው። የጠራ ሕይወትና የደመቀ ማንነት ያለው አማኝ በምን ሒሳብ ነው ድብልቅነት ግራጫ ማንነት የሚኖረው? ጨርሶ አይኖረውም። ልዩነቱ ደማቅ ነው።

የአንድነቱም የልዩነቱም መስካሪ ነኝ። “Preach Christ, and Christ, and Christ, and Christ, nothing else but Christ.“ Charles Spurgeon ትርጉሙም “ክርስቶስን ስበክ እና ክርስቶስን፥ እና ክርስቶስን ብቻ፥ ሌላ አይደለም ክርስቶስን ስበክ።”

ወርቅነህ ዳዊት

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 23:28


የማንነት ሕግ
ከተስፋዬ ሮበሌ
ክፍል ሁለት

እንኳን ለ2017 ዓ.ም አደረሳችሁ፡፡ ይህ በተከታታይ የማቀርበው ጽሑፍ ሁለተኛ ክፍል ነው፡፡ የጽሑፍ ዐላማ “የሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን” የሚባለውን ሐራጥቃዊ እንቅስቃሴ፣ ስለ አምላክ የሚያቀርበውን ትምህርት መገምገም ነው፡፡ በድጋሚ መልካም ዐዲስ ዓመት ይሁንላችሁ፡፡


ለ. የበቂነትና የአስገዳጅነት ቅድመ ሁኔታ

ሰውን፣ “ሰው” እንድንል የሚያደርገን ወይም አንድ ነገር፣ “እርሱ ራሱ ነው” የምንለው፣ ምን ምን ቅድመ ሁኔታዎች ሲሟሉ ነው (መስፈርቱ ምንድን ነው)? በዚህ አንጻር ሁለት እጅግ ወሳኝ የሆኑ መስፈርቶች አሉ፡፡ አንደኛው፣ “የበቂነት ቅድመ ሁኔታ” (sufficient condion) የሚባለው ሲሆን ሌላው፣ “የወሳኝነት (አስገዳጅነት ወይም የአንጡራነት) ቅድመ” ሁኔታ (necessary condition) የሚባለው ነው፡፡ ጠቃሚ መስፈርቶች ስለሆኑ፣ ስለእነዚህ መስፈርቶች ጥቂት እንነጋገር[1]፡፡

የበቂነት ቅድመ ሁኔታ (sufficient condion) እንዲሁም የወሳኝነት (የአንጡራነት) ቅድመ ሁኔታ የሚባለውን እነሆ:— ለመኖር ዐየር ያስፈልገናል፡፡ ዐየር ካላገኘን እንሞታለን፡፡ ዐየር ለመኖር ወሳኝ (አስገዳጅ፣ አንጡራ) ቅድመ ሁኔታ (necessary condition) ነው፡፡ ነገር ግን ዐየር ስላገኘን ብቻ በሕይወት እንኖራለን ማለት አይደለም፡፡ ስለዚህ ዐየር በሕይወት ለመኖር ወሳኝ (አንጡራ) ቅድመ ሁኔታ ይሁን እንጂ፣ በቂ (ብቸኛ) ቅድመ ሁኔታ (sufficient condion) አይደለም፡፡ ለመኖር ዐየር እንደሚያስፈልገን ሁሉ፣ ምግብ ያስፈልገናል፤ ጤና ያስፈልገናል፤ ውሃ ያስፈልገናል፤ ምናልባትም መጠለያ ያስፈልገናል፡፡ እነዚህ ነገሮች ካልተሟሉ ዐየር ስላገኘን ብቻ በሕይወት አንኖርም፡፡ እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች (ዐየር፣ ውሃ፣ ጤና፣ መጠለያ) “በተናጠል ወሳኝ”፣ “በጥምረት በቂ” ቅድመ ሁኔታዎች ናቸው[2]፡፡ ስለዚህ በሕይወት ለመኖር ዐየር ወሳኝ (አንጡራ ወይም አንገብጋቢ) ቅድመ ሁኔታ ነው፡፡ በቂ (ብቸኛ) ቅድመ ሁኔታ ግን አይደለም፡፡

ቫይረሶችን ለማየት ማይክሮስኮፕ (microscope) ወሳኝ ቅድመ ሁኔታ ነው፡፡ ምክንያቱም የሰው ልጅ ዐይን በዚያ መጠን ደቃቅ የሆኑ ነገሮችን፣ ዐጒልቶ የሚያሳይ አጋዥ መሣሪያ ሳይኖር መመልከት አይችልም፡፡ ስለዚህ ማይክሮስኮፕ ቫይረሶችን ለማየት ወሳኝ ቅድመ ሁኔታ ይሁን እንጂ፣ በቂ ቅድመ ሁኔታ አይደለም፡፡ ሰው ማይክሮስኮፕ ስላለው ብቻ ቫይረሶችን ማየት አይችልም፡፡ ቫይረሶችን ለማየት፣ ወትሮውንም በትክክል የሚያይ ዐይን እንዲሁም የሚታይ ቫይረስ በአካባቢው ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ማይክሮስኮፕ ስላለ ብቻ፣ ቫይረስ ሊታይ አይችልም፡፡ ቫይረሶችን ለማየት ማይክሮስኮፕ ወሳኝ ቅድመ ሁኔታ ነው፤ ነገር ግን በቂ ቅድመ ሁኔታ አይደለም፡፡

አባት ለመሆን ወንድ መሆን ወሳኝ ቅድመ ሁኔታ ነው፡፡ ነገር ግን ወንድ መሆን ብቻ በቂ ቅድመ ሁኔታ አይደለም፡፡ ወንድ የሆነ ሁሉ አባት አይሆንምና፡፡ አባት ለመሆን ለዐቅመ አዳም መድረስ፣ ሚስት ማግባት (አውስቦ)፣ መካን አለመሆን…እንዲሁም ሌሎች ተጨማሪ ቅድመ ሁኔታዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ የሎተሪ ዕድለኛ ለመሆን፣ የሎተሪ ትኪት መቊረጥ ወሳኝ ቅድመ ሁኔታ ነው፤ ነገር ግን በቂ ቅድም ሁኔታ አይደለም፡፡ ምክንያቱም የሎተሪ ትኬት ስለቈረጡ ብቻ፣ የሎተሪ ዕጣ ዕድለኛ መሆን አይቻልም፡፡

አንድ አጥቢ እንስሳ ዐንገቱ ቢቈረጥ ይሞታል፡፡ ዐንገት መቊረጥ እንስሳን ለመግደል በቂ ቅድመ ሁኔታ ነው፡፡ ነገር ግን ሁል ጊዜ ዐንገት መቊረጥ ለመግደል ወሳኝ (አስገዳጅ፣ አንጡራ) ቅድመ ሁኔታ አይደለም፡፡ “ዐንገት ካልተቈረጠ ሞት የለም” ማለት አይቻልምና[3]፡፡ ይህ ደግሞ አንድ ነገር በቂ ነው ማለት፣ ወሳኝ ነው ማለት እንዳልሆነ አመልካች ነው፡፡

በአጠቃላይ በቂ ቅድመ ሁኔታ የምንለው:— (1) ጒዳዩ እውን እንዲሆን ዋስትና የሚሰጥ፣ (2) ጒዳዩ እውን ለመሆኑ ብቸኛ ቅድመ ሁኔታ ያልሆነ፣ (3) ጒዳዩ እውን እንዲሆን ከሚያስችሉ ቅድመ ሁኔታዎች መኻል አማራጭ ሆኖ የሚቀርብ ማለት ነው፡፡ “ዝናቡ ከዘነበ ሣሩ ይረጥባል” ማለት የዝናቡ መዝነብ ለሣሩ መርጠብ በቂ ቅድመ ሁኔታ ነው ማለት እንጂ፣ ብቸኛ ቅድመ ሁኔታ ነው ማለት አይደለም፡፡ ስለዚህም ከዝናቡ ውጪ፣ ሣሩን የሚያረጥቡ ሌሎች ምክንያቶች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ጤዛ ሊያረጥበው ይችላል፤ የሣሩ ባለቤት ሣሩን ውሃ ሊያጠጣው (በዚህ መንገድ ሣሩ ሊረጥብ) ይችላል፤ ለሣሩ መርጠብ ሌሎች ተጨማሪ ምክንያቶችም ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ወሳኝ (አስገዳጅ፣ አንጡራ) ቅድመ ሁኔታ የምንለው ግን፣ ጒዳዩ እውን እንዲሆን አስገዳጅ በሆነ ሁኔታ (የግድ መገኘት) ያለበት ግብዐት ወይም ቅድመ ሁኔታ ነው፡፡

ክፍል ሦስት ይቀጥላል…

የኅዳግ መዘክር
————————
[1] የበለጠ ማብራሪያ የሚፈልጉ ጸሓፊው፣ “ሥነ አመክንዮ የሙግት አደረጃጀት፣ አገማገምና አሰናዘር” በሚል ርእስ ያዘጋጀውን መጽሐፍ ወይም የሚከተለውን ጽሑፍ ይመለከቷል:— https://plato.stanford.edu/entries/necessary-sufficient/
[2] “individually necessary” and “jointly sufficient”
[3] የሥነ አመክንዮ ሊቃውንት፣ በቂ ቅድመ ሁኔታን ከመዘርዘር ወሳኝ (አንጡራ) ቅድመ ሁኔታን መዘርዘር ቀላል ነው ይላሉ፡፡ ይህን ምክር የምንሰማ ከሆነ፣ በቂ ቅድመ ሁኔታዎችን በምንዘረዝርበት ጊዜ፣ እኛ ያላየነው በቂ ቅድመ ሁኔታ ሊኖር ስለሚችል ነገሮችን አንገርብቦ (ክፍት) አድርጎ መተዉ ብልኅነት ነው፡፡

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 23:22


ማንነት ሕግ
ከተስፋዬ ሮበሌ
ክፍል አንድ

በተከታታይ የምለጥፈው ይህ ጽሑፍ በአገራችን፣ “የሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን” የሚባለው የሃይማኖት ድርጅት፣ በክርስቶስ ማንነት ላይ የሚያስተምረውን መስመር የሳተ ትምህርት ምክንዮአዊና መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት ይመረምራል፡፡ ለውይይት የቀረበ ጽሑፍ እንደ መሆኑ መጠን በጨዋነት መሟገት ወይም ዐሳብ መስጠት ይቻላል፡፡ ዕላፊ ቃል ለመሰንዘር የደፈረ፣ ለመባረር አይሰጋምና እናባርረዋለን፡፡ የሚሳደቡ ሰዎች ደግም የመሳደብ ዕድል እንያገኙ ይደረጋል፡፡


ሀ. የቲሲየስ መርከብ

የጥንታውያን ግሪኮች አስተምህሮአቸውን የሚያዳምቁት፣ ነባቤ ቃላቸውን የሚያዋዙት፣ ታሪካቸውንና ተረታቸውን እያጣቀሱ ነበር፡፡ ስለ “ቲሲየስ መርከብ” (Ship of Theseus) መጀመሪያ የነገረን፣ ግሪካዊው የታሪክ ጸሓፊና ፈላስፋ ፕሉታርክ[1] ነው፡፡ አንድ ነገር ምንነት ወይም ማንነት (ቊሳዊ ወይም ኢቊሳዊ አካል) የሚተነተነው ከምን አንጻር ነው?[2] የሚለውን መሠረታዊ ጥያቄ በተመለከተ፣ ብዙ የፍልስፍና መጻሕፍት ይህን ታሪክ መንደርደሪያ አድርገው ይነሣሉ፡፡ እኔም ይህንኑ አግባብ ተከትዬ ስለ ቲሲየስ መርከብ እነሆ:—

የታሪክ ጸሓፊው ፕሉታርክ፣ “ቲሲየስ” የአቴና ንጉሥ እንደ ነበር፣ መርከቢቱም በግሪካውያን ሁሉ ዘንድ በስፋት እንደምትታወቅ ነግሮናል፡፡ እንደ ማንኛውም ቊስ አካል፣ በአገልግሎትና በዕድሜ ብዛት፣ መርከቧ የታነጸችበት እዕንጨት (ጣውላ) አንድ በአንድ ይወልቃል[3]፡፡ በሚረግፈው ዕንጨት ምትክ ሌላ ዐዲስ ዕንጨት እየተተካ፣ መርከቧ ረጅም ዓመታት አገልግሎት ሰጠች፡፡ በዚህ ሂደት አሮጌው ዕንጨት (ቅሬተ አካል) በቤተ መዘክር (በሙዚያም) እንዲቀመጥ ይደረግ ነበር፡፡ በቀኑ መጨረሻ መርከቢቱ የታነጸችበት መርከብ አንድ በአንድ ረግፎ፣ ሙሉ በሙሉ በተመሳሳይ ዕንጨት ይተካል፡፡

ለወሬ እንዲመቸን፣ መርከቧ የታነጸችው በአንድ ሺሕ የዕንጨት ዘንግ (ጣውላ) እንደ ሆነ እናስብ፤ እንዲሁም በወር እንድ የዕንጨት ዘንግ እየተነቀለ፣ በሌላ ተመሳሳይ እንጨት ይተካ ነበር እንገምት፡፡ በዚህ ስሌት ከሄድን በወር አንድ፣ በዓመት ዐሥራ ሁለት፣ በዐሥር ዓመት አንድ መቶ ሃያ እንዲሁም ሙሉ ለሙሉ ተነቅሎ ለማለቅ ወደ ሰማኒያ አራት ዓመት ይፈጃል፡፡ መርከቢቱ የመጀመሪያ ዕንጨት ተነቅሎ በሌላ ዐዲስ ዕንጨት ሲተካ መርከቢቱ፣ “እርሷ ነች ወይ?” ቢባል ብዙዎቻችን መልሳችን አዎንታዊ ሊሆን ይችላል፡፡ በዚህ ሁኔታ ሂደቱ ቀጥሎ፣ በአንድ በዓመት ውስጥ ዐሥራ ሁለት ዘንግ ቢለወጥ፣ እያቅማማንም ቢሆን መርከቢቱ፣ “ራሷ የቲሲየስ መርከብ ነች” እንል ይሆን?

“የቲሲየስ መርከብ በተወሰነ መጠን ተቀይራለች” ወይም ደግሞ፣ “ማንነቷን ሙሉ ለሙሉ አጥታለች” የምትባለው፣ ስንተኛው የዕንጨት ዘንግ ሲቀየር ነው? የሚለው ወሳኝ ጥያቄ ነው፡፡ የአንድ ሱሪ ሁለት ቊልፎች ረግፈው በሌላ ቊልፎች ቢተኩ፣ “ሱሪው ተቀይሯል” ላይባል ይችል ይሆናል፡፡ ቊልፎቹ ሁሉ ቢረግፉ እንዲሁም በብዙ ቦታ እየተቀደደ በተመሳሳይ ዕራፊ ጨርቅ ቢጣፍ፣ ሱሪው ተቀይሯል የሚባለው የሱሪው ምን የያህል አካል ሲቀየር ነው?

እንግሊዛዊው ፈላስፋ ቶማስ ሆብስ[4] የቲሲየስ መርከብን ታሪክ ይበልጥ በማዳመቅ እንዲህ ሲል ውይይቱን ያመጥቀዋል:— “በቤተ መዘክር የተሰበሰበው ቅሪተ አካል በመርከቧ ቅርጽ ተመልሶ ቢታነፅ፣ የቲሲየስ መርከብ የሚባለው በሥራ ላይ ያለው መርከብ ነው ወይስ፣ ተሰብስቦ በሙዚያም የተቀመጠውና ኋላ በዐዲስ መልክ የታነጸው መርከብ?”

ግዑዛን የሆኑ አካላት ብቻ ሳይሆኑ፣ ሕያዋን የሆንን እኛ ራሳችን፣ በጊዜ ሂደት ውስጥ ብዙ ነገራችን ተቀይሯል፡፡ ዕውቀታችን አድጓል፡፡ ተሞክሯችን ጐልብቶአል፡፡ እምነታችን፣ ፍላጎታችን፣ መሻተታችን፣ ትልማችን፣ ክብደታችን፣ የጠጒራችን መጠን (ወይም ቀለም) ተቀይሯል፡፡ ታዲያ የቀድሞ እኛነታችን፣ ከአሁኑ እኛነታችን አንጻር እንዴት ይተነተናል? በተክለ ሰውነትም ሆነ በዐስተሳሰብ ብዙ ተቀይረናልና፡፡ የሳይንስ ምሁራን የሰው ልጅ በየቀኑ በቢሊዮን የሚቈጠሩ ሴሎቹ በዐዲስ እንደሚቀየሩ ይገልጻሉ፡፡ በዝርዝር ጒዳዮች ላይ የተለያየ አስተያየት ቢኖራቸውም፣ የሰው ልጅ ከሰባት እስከ ዐሥር ዓመት ባለው ጊዜ ውስጥ ህዋሳቶቻችን (cells) ሙሉ በሙሉ በዐዲስ እንደሚለወጡ፣ ቢያንስ በአብዛኞቹ ዘንድ መግባባት አለ፡፡ በእውኑ የትላንቱ እኛ፣ ከዛሬው እኛ ጋር በምን አግባብ አንድ ሊሆን ይችላል?

ክፍል ሁለት ይቀጥላል…


[1] Plutarch (46 AD-119 AD)
[2] Metaphysics of Identity
[3] የጥንት መርከቦች ሞተር እንደሌላቸው ልብ ይሏል፡፡
[4] Thomas Hobbes (1588-1679)

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 23:07


አንደኛ ጴጥሮስ ከሚናገራቸው ዐበይት ርእሰ ጉዳዮች መካከል “ክርስቲያንና ኢ-ፍትሐዊ መከራ” ዋነኛው ነው። የጴጥሮስ ተደራሲያን ፈርጀ ብዙ የኾነ መከራ ይቀበሉ ነበር። ልዩ ልዩ ዐይነት ፈተና (1፥6)፤ ወርቅ በእሳት እንደሚነጥር፣ እንዲሁ አማኝን የሚያጠራ መከራ (1፥7)፤ የግፍ መከራ (2፥9)፤ ስለ ክርስቶስ ስም፣ መልካምና ጽድቅ በማድረግ የሚመጣ መከራ (3፥3-14)፤ ኀጢአትን በመታገል የሚከፈል ዋጋ (4፥1)።

የመከራቸው ምንጭም የተለያየ ነበር። ከይሁዲነት የተለወጡት፣ ክርስቶስን ጌታና መድኅን አድርገው በመቀበላቸውና ከአሕዛብ ክርስቲያኖች ጋር ኅብረት በማድረጋቸው ምክንያት ከአይሁድ የእምነት ተቋምና ማኅበረ ሰብ መገፋትና መገለል ይደርስባቸው ነበር። አሕዛብ የነበሩት ደግሞ፣ የቤተ ጣዖት አምልኮንና የዓለምን አኗኗር በመካድ ክርስትናን ስለተቀበሉ ከመጡበት ማኅብረ ሰብ ስደት ይመጣባቸው ነበር። እንዲሁም ሁለቱንም በጋራ፣ የኔሮ ጨካኝ መንግሥት ያሳድዳቸው ነበር።

ክርስትናና መከራ አይለያዩም። ይልቁንም ክርስትና በኀጢአት በተበከለውና በእግዚአብሔር ሉዓላዊ አገዛዝ ማዕቀፍ የተያዘው ሰይጣን በሚገዛበት ዓለም ውስጥ የሚኖር የሰልፍ ሕይወት ነው። መስቀሉን የተሸከሙ አማኞች ራሳቸውን ለጌታ ፈቃድ እያስገዙ፣ ከዓለምና ከሰይጣን የሚመጣባቸውን ውጊያ እየተጋፈጡ፣ የሚመጣውን የክርስቶስን መንግሥት በጽናትና በጽድቅ የሚጠባበቁ ለእግዚአብሔር የተለዩ ሕዝብ ናቸው። ይህንንም ሕይወት እንዲኖሩ የተጠሩት በደስታና በምስጋና እንጂ በማጉረምረም አይደለም። “ነገር ግን ክብሩ በሚገለጥበት ጊዜ ደስታችሁ ታላቅ እንዲሆን የክርስቶስ መከራ ተካፋዮች በመሆናችሁ ደስ ይበላችሁ።” (4:13)። ንጽረተ ዓለማቸው፣ አኗናራቸውና ዕሴታቸው ክርስቶሳዊ ነው።

ስለዚህ፦

ክርስቶስን ጌታና መድኅን ላደረጕ አማኞች መከራን መቀበል እንግዳ አይደለም።
የክርስቶስ እውነተኛ ተከታይ የመሆናቸው አንዱ የመገለጫ ፍሬ ስለ ስሙ የሚቀበሉት መከራ ነው።
ስለ ክርስቶስ ስም መሰደብና የጽቅድን መንገድ በመሄድ የሚመጣ መከራን መቀበል ክብር ነው፤ “የክብር መንፈስ የሆነው የእግዚአብሔር መንፈስ በእናንተ ላይ ስለሚያርፍ ብፁዓን ናችሁ።” (4፥14)። ኀጢአትን፣ ባዕድ አምልኮን፣ ሥጋንና ዓለም በመካድ ክርስቶስን ለማክበር በሚደረግ መሰጠት የሚመጣ መከራ የክብር ማዕረግ ነው።
በሥነ-ምግባር ብልሹነትና አስመሳይነት መከራን መቀበል ከክብር መጉደል ነው። “ከእናንተ ማንም መከራን የሚቀበል ቢኖር፣ ነፍሰ ገዳይ ወይም ሌባ ወይም ወንጀለኛ ወይም በሰው ነገር ጣልቃ ገቢ ሆኖ መከራን አይቀበል፤” (4፥15)።

ጴጥሮስ በኖረበት ማኅበራዊ ዐውድ፣ “ክርስቲያን” መሆን በወቅቱ ከነበረው ማኅበራዊ፣ ሃይማኖታዊና ፓለቲካዊ ዕሴት ጋር የሚያጋጭ ነበር። ለክርስቶስ መድኅንነትና ጌትነት ራሱን አሳልፎ የሰጠ አማኝ፣ ከኢየሩሳሌም (በጴጥሮስ ዐውድ ፈሪሳዊነት) እንዲሁም ከሮም (የወቅቱ የፓለቲካ ማዕከልና ክብር) ፋይዳዎች ጋር በማይታረቅ መልኩ ተለያይቷል። አማኖች የክርስቶስን ፈለግ በመከተል ሥር-ነቀል ለኾነ የጽድቅ ኑሮ ተጠርተዋል። ስለዚህ የእርሱ በመሆናቸውም ሊያፍሩ አይገባም፤ ይልቁንም ሊደሰቱ እንጂ! “ክርስቲያን በመሆኑ መከራ ቢደርስበት ግን ስለዚህ ስም እግዚአብሔርን ያመስግን እንጂ አይፈር። (4፥16) መከራቸውንም ሆነ አጠቃላይ የዚህ ዓለም ሕይወታቸውን መምራት ያለባቸው በእግዚአብሔር ዙፋን ሥር እንደሚቆሙ በማሰብ ሊሆን እንደሚገባው በአጽንዖት ያሳስባቸዋል።

ለእኛም እንዲሁ ነው! ክርስቶስን መመስልና መከራ አይነጣጠሉም፤ በአንድ ጊዜ ክርስቶስንና ዓለምን ማስደስት አንችልም። አዲስ መንግሥት፣ አዲስ አገዛዝና አዲስ ማንነት ተቀብለናል። ሌሎች የማንነት መገለጫዎቻችን በሙሉ አንጻራዊ ሆነዋል። ገዢው ማነንት በክርስቶስ የተገኘው አዲሱ "ሰውነት" ሆኗልና! ኑሮአችን በቀዳሚነት እግዚአብሔርን ተለመልካችና አድማጭ ያደረገ በመሆኑ፣ ድርጊታችን ብቻ ሳይሆን፣ የልባችን መነሣሣትና የውስጥ ግፊት ክርስቶስን በመፍራት ሊሆን ይገባዋል። ክርስትና በጥንቃቄ ለእግዚአብሔር ክብር የሚኖር ኑሮ ነው። "ማንም በእርሱ እኖራለሁ የሚል፣ ኢየሱስ እንደ ተመላለሰ ሊመላለስ ይገባዋል።" (1 (ዮሐንስ 2 ፥6)

እግዚአብሔር ጻድቅ ፈራጅ ነው። በኢፍትሐዊነት ላይ የሚፈርድበት የራሱ ጊዜ አለው፤ ግፉአን ስለ ፍትሕ የሚያሰሙት ጩኽት በከንቱ አያልፍም። በተለይም በጽድቅ መንገድ እየሄዱ ስለ ክርስቶስ ወንጌል ዋጋ የሚከፍሉ የሚያሰሙት! እስከዚያ እንዴት እንኑር?

“ስለዚህ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ መከራ የሚቀበሉ ሁሉ ነፍሳቸውን ለታመነ ፈጣሪ ዐደራ ሰጥተው መልካም ማድረጋቸውን ይቀጥሉ።” (1 ጴጥሮስ 4 ፥19)። ለራስ በለመሟገት ኾለተናን - ማለትም የሕይወትን ኹነቶችን በሙሉ፣ መልስ የሌላቸውን ጥያቄዎች፣ የሰዎችን ክፋት፣ ኢፍ-ትሐዊነትን፣ መገፋትን - ለእግዚአብሔር ሉዓላዊነት አሳልፎ በመስጠት መልካም ማድረግን መቀጠል። እግዚአብሔር ጻድቅ ፈራጅ ነውና! ስፐርጀን እንዳለው "የምንታመነው በዙፋኑ ላይ ሉዓላዊ ኾኖ ለዘላለም የተቀመጠውን እግዚአብሔር ነው።"

ግርማ በቀለ (ዶ/ር)

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 23:06


የምትችሉ ከሆነ እንድትታደሙ ተጋብዛችኋል!

ነገረ ወንጌላውያን

20 Jan, 22:54


[መስቀሉ የእምነታችን ጅማሬና ፍጻሜ የተሸመነበት ሰማያዊ ጥበብ ነው።]

°°°°
እምነታችን የጀመረው ከእናታችን ማህፀን የተወለድን ቀን አይደለም ፤ እምነታችን የጀመረው ከመስቀሉ ስር በፈሰሰው ክቡር የልጁ ደም ላይ ባለ መታመናቸንና መደገፋቸን ላይ ነው። ይህ በእግዚአብሔር ምህረትና ይቅርታ እምነታችን ያረፈበት መነሻ ነውና መዳረሻ አለው ።
ይህም መዳረሻ ከእምነታችን ጀምሮ በህይወታችን በተከወኑ ትሩፋቶች ላይ የሚቀር ሳይሆን እዛው መስቀሉ ላይ የተመረኮዘ ነው። እምነታችን የተጀመረበት የመስቀሉ ቦታ የምንጨርስበት መዳረሻችንም ነው ። የእምነታችን መጀመሪያና መጨረሻ በመስቀሉ ማለትም ስለ ኃጢአታችን በፈሰሰው ክቡር የኢየሱሰሰ ደም ላይና ራሱን ምትክ ባደረገበት የቤዝሆት ጎዳና ላይ ያረፈ ነው።
°
ለዛም ነው ለራሳችንና በዚህ ክቡር ደም ለተዋጁ “ ... እኛ ደግሞ ሸክምን ሁሉ ቶሎም የሚከበንን ኃጢአት አስወግደን፥ የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፥ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ... ።”[ዕብ 12፥1-2] በሚል ህያው ቃል የምንተናነጸው ። አዎ በመስቀሉ ላይ የተሰራውን የድህነት ሥራ በማመን የጀመርነው መንገድ መጨረሻ አለው ፥ ያም መጨረሻ ለመዳን መስቀሉን እንዳየነው እስክንጨርስም ድረስ ትኩር ብለን እያየን መንገዳችንን በትዕግስት እንድንሮጥ የሚያዝ ነው።
°
ስለዚህም በእምነት የጀመርነው መንገድ የክብር ፍጻሜን የሚያገኘው ፥ በመስቀሉ ስራ ለኛ የሆነልንን በማሰብና በዛም ሀሴት እያደረጉ ባለመቀጠል ሳይሆን ፤ መስቀሉን ዘወትር እየተመለከትን ፈለጉን በተወበት አካሄድ ሩጫችንን በትዕግስት በመሮጥ ነው። ቻርልስ ሰፐርጀን በአንድ ስብከቱ ላይ ይህንኑ ሃሳብ ሲያደረጅ " የእምነትህን ራሰና ፈጻሚውን ኢየሱስን እንጂ እምነትህን አትመልከት ። ምክንያቱም ጸሎትህን ፣ ቃለ እግዚአብሔርን ስታካፍል ያለ እይታህን ፣ መልካም ተግባርህን ፣ ወይም ትጋትህን በማየት ደስታን አታገኝም። ለነፍስህ እረፍት የሚሰጣት አንተ ያለህ ሳይሆን ኢየሱስ ላንተ የሆነው ነው።" ብሏል ።
°
ሩጫችንን በትዕግስት የምንሮጠው አንድም እንዳንዘገይ ሁለትም ተሰነካክለን እንዳንቀር ነው። መስቀሉን ስናይ ፈለጉን በተወልን መንገድ ላይ ነንና በነፍሳችን ዝለን እንዳንደክም ፣ ጽናቱም ጽናታችን እየሆነ ያግዘናል ፣ በመልካም እጁም እየደገፈና እየሸላለመ ይመራናል። አዎ መስቀሉ የዳንንበት ብቻ ሳይሆን እስከፍጻሜም የምንጠብቅበት መመካታችን ፤ ደግሞም ስለዘላለሙ ህይወት እርግጠኛ የሆንንበት መተማመኛችን ነው።
°
እናማ አይናችንን ዛሬም በመስቀሉ ላይ በማድረግ ፥ ሞቱንና መከራውን ስናስብ የክብር ፍጻሜያችን ህያው ተስፋ ፥ ያለድንግዝግዝ ወገግ ብሎ ይታየናል። ደግሞም ጎዳናውን በማሰብና በመመልከት እንጽና ፤ ያኔ የማጽናናቱ ደመና በመስቀሉ ስራ ለተጠለልን ለኛ [ ለጥገኞቹ ] የየዕለት ጠል በመሆን ያረሰርሰናል።ምክንያቱም መስቀሉ የእምነታችን ጅማሬና ፍጻሜ የተሸመነበት ሰማያዊ ጥበብ ነውና ነው።

____
image "Swann Galleries Inc."

ዳዊት ታዬ