ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

@ethbiblica


ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

22 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

እግዚአብሔር ሕዝቡን ከግብጽ ምድር ካወጣ በኋላ በምድረ በዳ ኪዳኑን በቃሉ አጸናላቸው—በዐሥርቱ ትእዛዛት። ይህን ተቀብሎ ለሕዝቡ ያደረሰው ሙሴ ነበር፤ "ሙሴ እህል ሳይበላ፣ ውሃም ሳይጠጣ ከእግዚአብሔር ጋር አርባ ቀንና አርባ ሌሊት በዚያ ነበር፤ በጽላቶቹ ላይ የቃል ኪዳኑን ቃሎች፣ ዐሥርቱ ትእዛዛትን ጻፈ" (ዘፀ 34፥28)። እግዚአብሔር ለአብርሃም እንደ ገባው ኪዳን ሕዝቡን በታላቅ ክንድ ካስወጣ በኋላ፣ ለኪዳኑ ፍጻሜ የሚጠበቅባቸውን በሕጉ በኩል ገለጠላቸው። ጌታ ኢየሱስ እንዳረጋገጠልንም፣ እነዚህ ትእዛዛት እግዚአብሔርንና ባልነጀራን በመውደድ የሚፈጸሙ ናቸው—ማቴ 22፥40። በ 40 ቀን ቆይታ ይዞ የወረደው ኪዳን፣ በቆይታ—በሕይወት ዘመን—የሚጸና ነው። እግዚአብሔር ፍጹምና የማይለወጥ ስለሆነ ኪዳኑን አያፈርስም፤ በኪዳኑ በመጽናት በርሱ የሚታገዙም እንዲሁ በፍቅር ኪዳኑ ውስጥ ይጸናሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

22 Oct, 04:01


የዕለቱ ቃል

"ሙሴ እህል ሳይበላ፣ ውሃም ሳይጠጣ ከእግዚአብሔር ጋር አርባ ቀንና አርባ ሌሊት በዚያ ነበር፤ በጽላቶቹ ላይ የቃል ኪዳኑን ቃሎች፣ ዐሥርቱ ትእዛዛትን ጻፈ።"

(ዘፀ 34፥28 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

21 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ኪዳን የኀብረት ውል፣ የአንድነት ማኀተምም ነው። በመጽሐፍ የኪዳን ጀማሪ እግዚአብሔር እንደ ሆነ ተገልጧል። ውሃ ዓለምን ካጠፋ በኋላ እግዚአብሔር ታዞ በመርከብ ትውልድን ላስቀረው ኖህ እንዲህ አለው፤ "በእኔና በእናንተ መካከል፣ ከእናንተም ጋር ካሉ ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ጋር፣ ከሚመጣውም ትውልድ ሁሉ ጋር የማደርገው የኪዳኑ ምልክት ይህ ነው፤ ቀስተ ደመናዬን በደመና ላይ አደርጋለሁ፤ ይህም በእኔና በምድር መካከል ለገባሁት ኪዳን ምልክት ይሆናል" (ዘፍ 9፥12-13)። ይህ ምልክት አሁን በምድር እንደ ተጠለፈና ለሌላ ጥፋት እንደዋለ አይደለም፤ በደመና መካከል አሁንም ጻድቁንና መሓሪውን አምላክ ይገልጣል። ጌታ ለኪዳኑ ቁርጠኛ ስለሆነ ምልክቱን አልሻረም። ተለዋዋጭ ያልሆነ አምላክ ሁልጊዜ ታማኝ ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

21 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"እግዚአብሔርም እንዲህ አለ፤ 'በእኔና በእናንተ መካከል፣ ከእናንተም ጋር ካሉ ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ጋር፣ ከሚመጣውም ትውልድ ሁሉ ጋር የማደርገው የኪዳኑ ምልክት ይህ ነው፤ ቀስተ ደመናዬን በደመና ላይ አደርጋለሁ፤ ይህም በእኔና በምድር መካከል ለገባሁት ኪዳን ምልክት ይሆናል።'"

(ዘፍ 9፥12-13 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

20 Oct, 07:00


መልእክተ ሰንበት

የሰው ጸሎትና የእግዚአብሔር ፈቃድ ሲስማሙ ውጤቱ ትልቅ የሆናል፤ "በእግዚአብሔር ፊት ለመቅረብ ያለን ድፍረት ይህ ነው፤ ማንኛውንም ነገር እንደ ፈቃዱ ብንለምን እርሱ ይሰማናል። የምንለምነውን ሁሉ እንደሚሰማን ካወቅን፣ የለመንነውንም ነገር እንደ ተቀበልን እናውቃለን" (1ዮሐ 5፥14-15)። ፈቃዱን ለማወቅ እርሱን ማወቅ ያስፈልጋል፤ እርሱም በቃሉ ይታወቃል። ፈቃዱ ያረፈበት ቃሉም ለምንቀርብበትና ለምንጠይቅበት እምነት መሠረት ነው። የእግዚአብሔር ፈቃድና ማመን የጸሎት መሠረታውያን ከሆኑ፣ ጸሎት በቃሉ ይሠራል፤ ያድጋል፤ ቀላል መንፈሳዊ ተግባርም ይሆናል። በቃሉ ውስጥ የተጠቀሱት ከ600 በላይ ጸሎቶችም ብዙ ትምህርት ይሆናሉ።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

"አትጨነቁ" የሚለው ቃል ለተናጋሪ የሚቀለውን ያህል ለሰሚ ቀላል አይደለም። ያለንበት ጊዜ፣ ሁኔታውና ዙሪያ ገባው ሁሉ አሳሳቢ ነው፤ አስጨናቂም ጭምር። ይሁንና ግን ከእግዚአብሔር ትከሻ የሚተልቅ፣ ከእጁም የሚርቅ ምንም ነገር የለም። ቃሉም እንዲህ ይለናል፤ "በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ፣ ከምስጋናም ጋር ልመናችሁን በእግዚአብሔር ፊት አቅርቡ እንጂ ስለ ማንኛውም ነገር አትጨነቁ" (ፊል 4፥6)። የእግዚአብሔር ፊት ጸሎት የተከፈተበት ቦታ ሁሉ ይገኛል። እርሱ ይሰማን ዘንድ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ቀርቦናል፤ ያጽናናንና ያበረታን ዘንድ፣ ይረዳንና ያጸናንም ዘንድ ትኩረቱ ሁልጊዜ በእኛ ላይ ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

18 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ፣ ከምስጋናም ጋር ልመናችሁን በእግዚአብሔር ፊት አቅርቡ እንጂ ስለ ማንኛውም ነገር አትጨነቁ።"

(ፊል 4፥6 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ወደ እግዚአብሔር ቤት ለሚመጡ ሁሉ እግዚአብሔርን ከመስማትና ሐሳብንና ሸክምን ለርሱ ከማሰማት የበለጠ ነገር የለም፣ ቤቱ የጸሎት ቤት ነውና። ጌታ ወደ መቅደሱ በክብር በገባ ጊዜ በድምቀቱና ሆታው፣ በዝማሬውና በስግደቱ የሚገባውና የጎደለው ነገር እንዲሸፈን አልፈቀደም። ይልቁንም ለዋጮችን ገሠጸ፤ ገባታንም ገለበጠ። በጊዜው የነበሩ ሰዎች 'ስሜታዊ ሆነ' ብለው አስበው ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ድርጊቱ የእግዚአብሔር ቃል ላይ የተመሠረተ፣ ስሜቱም "የቤትህ ቅናት ይበላኛል" እንደ ተባለ ቃሉ ላይ ያረፈ ነበር። እርሱም መቅደሱን እያጸዳ የጠቀሰው ቃሉን ነው፤ "‘ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል’ ተብሎ ተጽፏል፤ እናንተ ግን፣ የዘራፊዎች ዋሻ አደረጋችሁት አላቸው" (ማቴ 21፥13)። "የጸሎት ቤት!" ዛሬም ብዙ ስሙ የሚጠራባቸው 'ቤቶች' አሉ። ስንቶቹ ግን ትኩረታቸው ራሱ እግዚአብሔር፣ ፍለጋቸውም (በጸሎት) እርሱ ይሆን? ሕዝቡን መስማት የሚወድድ፣ ለሕዝቡም የሚጠነቀቅና የሚመልስ አምላክ ይህ እንዲስተጓጎል ወይም እንዲሸፈን አይፈልግም። እርሱን ከማነጋገር፣ እርሱንም ከመስማት በላይ ሰዎች እርስ በርሳቸው የሚነጋገሩበት የትኛውም ሃይማኖታዊ መሰብሰብ ዋነኛ ነገር አጉድሏል።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

17 Oct, 04:01


የዕለቱ ቃል

"‘ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል’ ተብሎ ተጽፏል፤ እናንተ ግን፣ የዘራፊዎች ዋሻ አደረጋችሁት አላቸው።"

(ማቴ 21፥13 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

16 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ዮናስ ለመታዘዝም ሆነ ወደ አምላኩ ለመጮኽ ወደ ምድር መጨረሻ መውረድ ነበረበት። በዓሣው ከተዋጠ በኋላ የአምላኩን ሉዓላዊነት፣ የፈቃዱንም ጉልበት ተረዳ። ቢርቅም እንኳን ልመናን አቀረበ፤ “ነፍሴ በዛለች ጊዜ፣ እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተን ዐሰብሁ፤ ጸሎቴም ወደ አንተ፣ ወደ ቅዱስ መቅደስህ ዐረገች" (2፥7)። ሰው እንጂ እግዚአብሔር አይርቅም፤ ከየትም ሆኖ ይሰማል። ነፍስ "በዛለች ጊዜ" ፍቱን መድኀኒቷም ጸሎት ነው። ደጋፊዋም ሩቅ አይደለም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

16 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

“ነፍሴ በዛለች ጊዜ፣ እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተን ዐሰብሁ፤ ጸሎቴም ወደ አንተ፣ ወደ ቅዱስ መቅደስህ ዐረገች።"

(ዮና 2፥7 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

15 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ጸሎት አይቋረጥም። ይህ ሲባል ግን ተግዳሮት አይገጥመውም ወይም አያታግልም ማለት አይደለም። አንድን ሰው ብቻ ለማጥቃት አንድ ትልቅ አገር ሕግ አወጣ፤ ጸሎት ለ30 ቀናት ይቋረጥ ተባለ። "ዳንኤልም ዐዋጁ እንደ ወጣ ባወቀ ጊዜ ወደ ቤቱ ሄደ፤ መስኮቶቹ በኢየሩሳሌም አንጻር ተከፍተው ባሉበት በሰገነቱ ቀድሞ ያደርግ እንደ ነበረው በቀን ሦስት ጊዜ ተንበርክኮ ጸለየ፤ አምላኩንም አመሰገነ" (ዳን 6፥10)። ለርሱ ጸሎት ብቻ ሳይሆን ምስጋናም አይቋረጥም። በገሃድ (በግልጽ) አምላኩን ማነጋገሩን ቀጠለ። እግዚአብሔር ከአዋጁ፣ ከዛቻውና ከአንበሳው በላይ እንደ ሆነ ለማመን አልተቸገረም። ስለዚህም የዘወትር መንፈሳዊ ተግባሩን ቀጠለ። የሚያምነውንና የሚወደውን አምላክ ሳያነጋግርስ እንዴተ ቀናት የቆጠራሉ!

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

15 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ዳንኤልም ዐዋጁ እንደ ወጣ ባወቀ ጊዜ ወደ ቤቱ ሄደ፤ መስኮቶቹ በኢየሩሳሌም አንጻር ተከፍተው ባሉበት በሰገነቱ ቀድሞ ያደርግ እንደ ነበረው በቀን ሦስት ጊዜ ተንበርክኮ ጸለየ፤ አምላኩንም አመሰገነ።"

(ዳን 6፥10 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Oct, 11:00


የዕለቱ ሐሳብ

ሰሎሞን የመጀመሪያውንና ትልቁን ቤተ መቅደስ ሠርቶ በጨረሰ ጊዜ ጸሎት አቀረበ። ጸሎቱ ሥራ የጨረሰ ሰው ጸሎት ነው—ጸሎት ሥራ ለመጀመር ብቻ ሳይሆን ከጨረሱም በኋላ ለምረቃም ይደረጋል። የ1 ነገሥት 8ቱ ጸሎትም የምረቃ ጸሎት ነው። በቃሉ ተጽፎ ከቀረልን መካከል ረጅሙ የሆነው ይህ ጸሎት፣ አንድ ጊዜ ብቻ የሚሰማ ሳይሆን ዘወትር የሚሰማ ሆኖ የቀረበ ነበር፤ "...ይህች በእግዚአብሔር ፊት ያቀረብኋት የራሴ ልመና በቀንና በሌሊት ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር ፊት ትቅረብ" (ቍ. 59)። እግዚአብሔር በሰማይ የሚቀበላቸው እንዲህ ዐይነት ጸሎቶች ፈቃዱ ያረፈባቸው ስለሆኑ፣ በጽሞና ሲታሰቡ የሚሰሙ ናቸው። ኪዳን ያረፋባቸው ስለሆኑ ውጤታቸው ታላቅ ነው። በጸሎት መካከል ጽኑ ጸሎት ማቅረብ እግዚአብሔርን፣ ፈቃዱንና ለዘመኑ የሚሆነውን ዕቅዱንም መረዳት ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

14 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"...ይህች በእግዚአብሔር ፊት ያቀረብኋት የራሴ ልመና በቀንና በሌሊት ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር ፊት ትቅረብ።"

(1ነገ 8፥59 አመት)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

13 Oct, 07:01


መልእክተ ሰንበት

መጻሕፍት ሁሉ ስለ ጌታ ይናገራሉ። የመጨረሻው መጽሐፍ--ዮሐንስ ራእይ--ደግሞ በተለየ ትኩረት የመጨረሻውን ዘመን መጀመሪያና መጨረሻ ከሆነው ጌታ አንጻር ይተርከሰል። እርሱም በመጀመሪያው ምዕራፍ ላይም እንዲህ ተጽፏል፤ “ያለውና የነበረው፣ የሚመጣውም፣ ሁሉን ቻይ ጌታ አምላክ፣ 'አልፋና ዖሜጋ እኔ ነኝ' ይላል" (ራእ 1፥8)። ለሙሴ ራሱን ከገለጠበት ጊዜ ጀምሮ ያለና የሚኖር መሆኑ ተደጋግሞ ተገልጧል። ዘመን-አላፊ ብቻ ሳይሆንም ሁሉን ቻይ ነው። ይህ አምላካዊ ባሕርይው ትናንት፣ ዛሬ፣ ለዘላለምም አብሮት አለ። ጊዜና ለውጥ በርሱ ላይ አይነበቡም፤ እርሱ ግን ሁሉን ያነብባል፣ ይቆጣጠራልም።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

11 Oct, 11:01


የዕለቱ ሐሳብ

ጊዜና ሁኔታ የጌታ አገልጋዮች ናቸው፤ አንሰው ወይም በዝተው አስቸግረው አያውቁም። የእግዚአብሔር ጕብኝትም በነርሱ 'ሙላት' እና 'ጉድለት' አይወሰንም። መልአኩ ገብርኤል ወደ ማርያም መጥቶ፣ "የልዑል ኀይል ይጸልልሻል" ብሎ ከተናገራት በኋላ፣ ስለ ዘመዷ ኤልሳቤጥ "በስተርጅና" መጸነስ አሳሰባት። እግዚአብሔር ዮሐንስ በዕድሜ ባለጠጋዋ ኤልሳቤጥ፣ ክርስቶስ ጌታ ደግሞ በወጣቷ ማርያም እንዲጸነሱ አደረገ፤ የመጀመሪያው ታምራዊ፣ የሁለተኛው መለኮታዊ፣ "ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና" (ሉቃ 1፥37)። ይህም እውነት ዛሬም፣ ለዘላለምም ያው ነው።

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

11 Oct, 04:00


የዕለቱ ቃል

"ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና።"

(ሉቃ 1፥37 አመት)