መንፈሳዊ ጉባኤ

@menfesawi_gubae


ወዳጄ ሆይ፥ ሁለንተናሽ ውብ ነው፥ነውርም የለብሽም።
መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን 4 : 7

@Menfesawi_Gubae

ጥያቄ ካላችሁ ከታች ባለው አድራሻ መጠየቅ ትችላላችሁ።

@HenokAsrat3

መንፈሳዊ ጉባኤ

22 Oct, 01:33


“ምን ፍሬ አፈራን?”  በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

ልጆቼ! እስኪ ፍቀዱልኝና ዛሬ አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁ፡፡ ብዙውን ጊዜ ቤተ ክርስቲያን ትመላለሳላችሁ፡፡ መልካም ነው፡፡ ግን ምን ለውጥ አመጣችሁ? ምን ፍሬ አፈራችሁ? ታገለግላላችሁን? ከአገልግሎታችሁ ምን ረብሕ አገኛችሁ?

ጥቅምን ካገኛችሁ በእውነት ምልልሳችሁ የጥበበኛ ምልልስ ነበር ማለት ነው፡፡ ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ ወንጌላውያን እንዲህ እያስተማሩን ሳለ የማንለወጥ ከሆነ ግን የእስከ አሁን ምልልሳችን የአይሁድ ምልልስ ነበር ማለት ነው፡፡ አይሁዳውያን ሕገ ኦሪትን የተሰጠቻቸው ኃጢአታቸውን በእርሷ መስታወትነት አይተው ንስሐ እንዲገቡባት ነበር፡፡ እነርሱ ግን የንስሐ ፍሬ ሳያፈሩባት እንዲሁ ይመኩባት ነበር፡፡ ስለሆነም ለሕይወት የተሰጠቻቸው ሕግ ሞት ሆና አገኟት፡፡ እኛም እንዲህ ለኵነኔ ያይደለ ለጽድቅ የተሰጠችን ወንጌል ፍሬ የማናፈራበት ከሆነ ከአይሁዳውያን የባሰ ቅጣት ትፈርድብናለች፡፡

እስኪ ምሳሌ መስዬ ላስረዳችሁ፡፡ አንድ የሚታገል ሰው (wrestler) በየጊዜው ተጋጣሚውን እንደምን ማሸነፍ እንዳለበት ልምምድ የሚያደርግ ከሆነ ክህሎቱ ይዳብራል፡፡ ተጋጣሚውም በቀላሉ ማሸነፍ ይቻሏል፡፡ በየጊዜው ራሱን የሚያሻሽል (Update) የሚያደርግ ሐኪም ጐበዝ አዋቂና ሕመምተኞችን በአግባቡ የሚረዳ ይሆናል፡፡ በየቀኑ ቃሉ የሚነገረን እኛስ ምን ለውጥ አመጣን? ምን ፍሬ አፈራን?

እየተናገርኩ ያለሁት ለአንድ ዓመት ብቻ በቤተ ክርስቲያን የቆዩትን ምእመናን አይደለም፡፡ እየተናገርኩ ያለሁት ከልጅነታችን አንሥተን በቤቱ ለምንመላለስ እንጂ፡፡ ይህን ያህል ዘመን በቤቱ እየተመላለስን ፍሬ ካላፈራን ቤተ ክርስቲያን ደርሰን ብንመጣ ምን ጥቅም አለው? አባቶቻችን አብያተ ክርስቲያናት ያነጹልን ለምንድነው? ዝም ብለን እንድንሰባሰብ ነውን? እንደዚህማ በገበያ ቦታም መሰባሰብ አንችላለን፡፡ አበው አብያተ ክርስቲያናትን ያነጹለን ቃሉን እንድንማርበት፣ በተማርነው ቃልም የንስሐ ፍሬ እንድናፈራበት፣ ሥጋ ወደሙን እንድንቀበልበተ፣ እርስ በእርሳችን እንድንተራረምበት እንጂ ለሌላ ዓላማ አይደለም፡፡
ታዲያ ምን ፍሬ አፈራን?

መንፈሳዊ ጉባኤ

21 Sep, 16:57


https://vm.tiktok.com/ZMhFWjew7/ This post is shared via TikTok Lite. Download TikTok Lite to enjoy more posts: https://www.tiktok.com/tiktoklite

መንፈሳዊ ጉባኤ

20 Sep, 23:54


#ወንድሞቼ_ሆይ ወደ ቤተ ክርስቲያን ውድ ስጦታዎችን ይዛችሁ ስትመጡ አያለሁ፡፡ መልካም አድርጋችኋል፡፡ ነገር ግን ስትመለሱ ደግሞ መበለቶችን፣ ደሀ አደጎችንና ሕጻናትን ስትበድሉ አያችኋለሁ፡፡ ታድያ ይህን ሁሉ እያደረጋችሁ በወርቅ የተንቆጠቆጠ ምሥዋዕና ጽዋዕ ብታቅረቡ ምን ይጠቅማችኋል? ለምንስ መሥዋዕቱን ማክበር ስትፈልጉ አስቀድማችሁ ልባችሁን መባ አድርጋችሁ አታቀርቡም? ልባችሁ በጭቃ ተጨማልቆ ምሥዋዑ እንኳን ወርቅ ፕላቲንየምስ ቢሆን ምን ይረባችኋል? ምንስ ይጠቅማችኋል?

#ተወዳጆች_ሆይ!
አመጣጣችን በወርቅ የተለበጠ መሠዊያ ለማቅረብ ሳይሆን ይኸን ከልብ በመነጨ ለማቅረብ ይሁን፡፡ ከልባችን የምናቀርበው ነገር ሁሉ ከወርቅ የበለጠ መባ ነው፡፡

#ልብ_በሉ!
ቤተ ክርስቲያን የወርቅ ወይም የነሐስ ማቅለጫ ቦታ አይደለችም፤ ለቅድስና የተጠሩ ሁሉ እና የመላእክት ኅብረት እንጂ፡፡ስለዚህ ከስጦታችሁ በፊት ልባችሁን ይዛችሁ ኑ፡፡ እግዚአብሔር እኮ ሥጦታችንን የሚቀበለው ደሀ ሆኖ ሳይሆን ስለ ነፍሳችን ብሎ ነው፡፡

#ክርስቶስን_ማክበር_ትወዳላችሁን?
እንግዲያስ ዕራቆቱን ስታዩት ችላ አትበሉት፡፡ እናንተ ወደ ቤተ መቅደስ ስትመጡ እጅግ ውድ በሆኑ ልብሶች አጊጣችሁ ስትመጡ እርሱ በብርድና በመራቆት ሊሞት ነውና ብያንስ ትንሽ እንኳን እዘኑለት፡፡ ቤተ መቅደስ ረግጣችሁ ቤተ መቅደስ አትምጡ፡፡ በቃሉ “ይህ ሥጋዬ ነው” ያለው ጌታ በተመሳሳይ ቃሉ “ተርቤ ስታዩኝ አላበላችሁኝም፤ ከሁሉ ከሚያንሱት ከእነዚህ ለአንዱ ስላላደረጋችሁት ለእኔ ደግሞ አላደረጋችሁትም” ብሏልና።

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ

መንፈሳዊ ጉባኤ

20 Sep, 23:49


ፈረስ የሚጋልብ ሰው ልጓሙን በአግባቡ ካልያዘው በቀር ፈረሱም ጋላቢውም ይጎዳሉ፡፡ አንድ እባብ የነደፈው ሰው ባለመድኃኒቶችን አግኝቶ መርዙ ወደ ሰውነቱ ኹሉ እንዳይሰራጭ ካላደረገ በቀር ወደ ሞት ሊደርስ ይችላል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ አንድ ትንሽ ቁስል በጊዜው ጊዜ ካልታከሙት በቀር ሰፍቶና ተስፋፍቶ ትልቅ ቁስል ወደ መኾን ያድጋል፡፡

በእኛ በክርስቲያኖች ዘንድም እንደዚህ ነው፡፡ የኃጢአት ቁስል የሚሰፋው ችላ ሲባል ነው፡፡ ገና ትንሽ ነው በሚባልበት ደረጃ ካላራቅነው በቀር ነገ ከነገ ወዲያ ትልቅ ቁስለ ነፍስ ይኾናል፡፡

ተመልከቱ! ዛሬ ላለመቈጣት የሚታገል ሰው ነገ ሰዎችን የሚጎዳበት ዘዴን አይዘይድም፡፡ ሰዎችን የሚጎዳበት ዘዴ ካልዘየደም ብዙ ባልንጀሮች ይኖሩታል፡፡ ብዙ ባልንጀሮች ካሉት የሚጠላቸውም የሚጠሉትም ሰዎች አይኖሩም፡፡ ባልንጀራ እንጂ ጠላት የሌለው ሰውም የምግባር ኹሉ ፍጻሜ የኾነውን ፍቅር ገንዘብ ያደርጋል፡፡

ስለዚህ ተወዳጅ ሆይ! ወደዚህ ምግባር ታድግ ዘንድ ወደዚህ እንዳታድግ የሚያደርጉህን ጥቃቅን ኃጢአቶችን ከአንተ አርቅ፡፡ ሰፍቶ ተስፋፍቶ ነገ እንዳይቸግርህ ዛሬ በእንጭጩ እያለ ችላ አትበለው፡፡

ይሁዳ ገና የገንዘብ ፍቅር ደረጃ ላይ እያለ ራሱን ቢመረምርና ይህን ለማራቅ ቢጥር ኖሮ በኋላ ከተሰበሰበው ገንዘብ ወደ መስረቅ ባላደገ ነበር፡፡ ገና ከመጀመሪያው ደረጃ እያለ ችላ ባይል ኖሮ የኃጢአት ኹሉ ራስ የኾነው ኃጢአት ወደ መፈጸም ባልደረሰ ነበር፡፡

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንደዚህ ልናደርግ እንደሚገባን ሲያስተምረን ከዝሙት ብቻ እንድርቅ ሳይኾን የእርሱ ሥር የኾነውንና አይቶ መመኘትን ችላ ልንለው እንደማይገባን ነገረን (ማቴ.5፡28)፡፡ ኃጢአት ሥር ሰዳና ሰፍታ ከመቸገራችን በፊት በችግኝ ደረጃ ላይ እያለች ነቅለን መጣል ቀላል ነውና፡፡

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ

መንፈሳዊ ጉባኤ

10 Sep, 15:29


​​​​🌼 ልጄ ሆይ እንደ ዘመኑ አንተም ተለወጥ

ልጄ ሆይ....... ወጣትነት ፈትኖህ፤ለስጋህ አድልተህ፤ነፍስህን አቀጭጨኻት ከአለም የኖርክበትን ዓመትህን ጥለኸው በንሰሐ እንደ ዘመኑ አንተም ተለወጥ።

ልጄ ሆይ ..... በአዲስ አመት ለአምላክህ የሚገባህን ግብር ትፈፅም ዘንድ በፍቅሩ አፀድ እንድትገኝ ካለመታዘዘ ተለወጥ።

ልጄ ሆይ ....... በአፈር ከሚሸነፈው ስጋዊ ዘርህ ወጥተህ ሰማያዊነትን ከሚያለብስህ ከማይጠፋው ሰማያዊ ዘር ክብረት ታደርግ ዘንድ ሰውን ካለመውደድ ጥላቻ ተለወጥ።

ልጄ ሆይ ...... በምክንያቶች ተደልለህ አፅዋማትን ዘለህ፤ምስጋናን ነፍገህ፥አገልግሎትን ንቀህ ከአለም ጫጫታ ውስጥ የዘፈቀውን ማንነትህ እንዳያጠፋህ እንደ ዘመኑ አንተም ተለወጥ።

ልጄ ሆይ ...... ዲያቢሎስ በቃል እንዳያስትህ፤በማማለል እንዳይጠልፍህ የመንጋውን ጠባቂ ቃልን ስማ፤ የመታዘዝን በረከት ታገኝ ዘንድ ከትምህክትህ እንደ ዘመኑ አንተም ተለወጥ።

ልጄ ሆይ .....ቀናት ሳይሆን መንፈስህ ይለወጥ፤ፀሐይ ሳትሆን የህይወት ጀንበርህ ይለወጥ።

ልጄ ሆይ ......ዕለታት አይሰልጥኑብህ፤ ዘመናት  እስከ ሞትህ ጥግ ድረስ እስኪገፉህ ሳትጠብቅ አንተም እንደ ዘመንህ ተለወጥ

ልጄ ሆይ .....የእግዚአብሔር ፍቅር ለተከፈተ ልብ ቸር ነው ። ርህራሄው ጥልቅ ነው ። በአምሳሉ ፈጥሮሃል እና እንዳትጠፋ አንድያ ልጁን ለሞት አሳልፎ እስከመስጠት የደረስ ጥልቅ ፍቅር አሳይቷል ። ስለዚህ ከዘመንህ ቀድመህ ተለወጥ።

ልጄ ሆይ ...አዛኝቷን ተለማመን፤መላአኩን ተማለደው ፤ቀደምት ቅዱሳን አባቶችህን ጥራ፤ ፃድቃንን ዘክር እንጅ ላለመለወጥ ተማምለው ቀናት ብቻ ከሚለወጥባቸው ሰልፈኞች ተርታ አትገኝ ።

በንስሐ ወደ በረቱ የምንመለስበት ዘመን ይሁንልን! አሜን

🌻 መልካም አዲስ አመት ይሁንልን
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
━━━━━━━━━━━━━━━━━━
🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏
       

መንፈሳዊ ጉባኤ

06 Sep, 02:15


የስሙንም ትርጉም ስንመለከት ‹‹ሩፋ›› ማለት ሐኪም ማለት ነው፡፡ ኤል ማለት እግዚአብሔር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ሩፋኤል ማለት የእግዚአብሔር ሐኪም ማለትነው፡፡ ሌላው መልአከ ሰላም ወጥዒና ወይም የሰላም እና የጤና መልአክ ይባላል፡፡

የሰው ልጆችን ከተያዙበት ከተለያዩ በሽታውች በጸሎቱ፣ በአማልጅነቱ እንዲፈውስ ስልጣን እና ጸጋ የተሰጠው ታላቅ መልአክ ነው፡፡
ሩፋኤል ማለት የእግዚአብሔር ሐኪም ማለት መሆኑን ነብየ

እግዚአብሔር ቅዱስ ሄኖክ በመጽሐፈ ሄኖክ ምዕራፍ 10 ቁጥር 13 ላይ ‹‹በበሽታ ሁሉ ላይ፣ በሰው ልጆችም ቁስል ላይ፤ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው›› እንዲሁም እዛው መጽሐፈ ሄኖክ ምዕራፍ 6 ቁጥር 3 ላይ

‹‹በሰው ቁስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መልእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው››  በማለት እግዚአብሔር ለቅዱስ ሩፋኤል በሰውነታችን ላይ የወጣውን፤ ቁስል እና ደዌ፤ ይፈውስ ዘንድ ስልጣን እንደሰጠው፣ ሐኪም እንዳደረገው ነግሮናል፡፡

እንዲሁም ፈታሄ ማሕፀን ይባላል፡፡ እንኳን በምጥ የተያዙትን ሴቶች፣ እናቶች፤ ቀርቶ እንስሳት እንኳን ምጥ ሲፀናባቸው፣ ስሙን ከጠሩት ይፈታቸዋል፡፡ ይህ መልአክ በተለይ ለሴቶች እጅጉን ረዳታቸው ነው፡፡ ከፀነሱበት ጊዜ አንስቶ እስኪወልዱ አይለያቸውም፡፡

በተለይ በእርግዝናቸው ጊዜ ስሙን እየጠሩ፣ መልኩን እየጸለዩ፣ ጸበሉን እየጠጡ እየተዳበሱ፣ ከተማጸኑት ጭንቀታቸውን ያቀላል፣ በሰላም ያዋልዳቸዋል፡፡

ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይሁንና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ፤ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታችንን ስለ ቅዱስ ሩፋኤል እንዲያሳውቃቸው፣ ክብሩን እንዲገልጽላቸው ጠየቁት፡፡ ጌታም ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ገብርኤል እና ቅዱስ ሩፋኤልን እንደሚመጡ አዘዛቸው፡፡ እነሱም መጡ፡፡

ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል ስለ ራሳቸው ከተናገሩ በኃላ ጌታም ቅዱስ ሩፋኤልን ‹‹ክብርህን ንገራው›› አለው፡፡ ቅዱስ ሩፋኤልም ለጌታ ሰግዶ ለሐዋርያት ብዙ ምስጢር ነገራቸው፡፡

በተለይም ስሙን ለሚጠሩ፣ መታሰብያውን ለሚያደርጉ፣ በጸሎቱ ለሚማጸኑ፣ እንደማይለያቸው፣ እንደሚረዳቸው፣ ክብር እንደሚያሰጣቸው ለሐዋርያት ነግሯቸው ወደ ሰማያት አርጓል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያትም በወቅቱ ወንጌልን ሲያስተምሩ፣ ስለ ቅዱስ ሩፋኤል ክብር እና በእሱ የሚገኘውን መልአካዊ እርዳታ፣ ለምዕመናኑ በደንብ አስተምረዋል፡፡

ቅዱስ ሩፋኤል ልቦናን ደስ የሚያሰኝ፤ ባለ መድኃኒት ፈዋሽ፤ የጸሎት መዝገብ መክፈቻ የተሰጠው፤ በዙፋን ላይ በክብር የሚቀመጡ መላእክት መሪ፤ የሰውንም ይሁን እንስሳን ማሕፀን የሚፈታ፤ አዋላጅ፣ ምጥን የሚያቀል፣ ታላቅ መልአክ ነውና እንጠቀምበት፡፡

ስለዚህ የቅዱስ ሩፋኤል ቀን የዘነበውን ዝናብ በዕቃ ቀድታችሁ አስቀምጡ፡፡ ያንንም ጸበል ቤታችሁን፣ ደጃችሁን፣ እንዲሁም የሥራ ቦታችሁን እርጩበት፣ እየቆጠባችሁ እህል ስታቦኩ አብኩበት ጠጡት ተጠመቁበት፡፡ ብዙ በረከት እና ፈውስ ታገኙበታላችሁ፡፡

እህል እና ገንዘብ የሚሰልብባችሁን የሰላቢ መንፈስ ያርቅላችኃል፡፡
ውጭ ሀገር ያላችው እህት ወንድሞቼ ጸበል መጠመቅ ስለማይመቻችሁ፤ ውኃ አቅርባችሁ፣ ያስለመዳችሁትን ጸሎት ውሃው ላይ ጸልያችሁ ‹‹አምላከ ቅዱስ ሩፋኤል›› ባርክልኝ ብላችሁ ቤት ውስጥ ተጠመቁ ጠጡት፡፡

ጳግሜን መጠመቅ ከጥንት አባቶቻችን ጀምሮ የነበረ እና በየአመቱ ጳግሜን መጠመቅ የሚናፈቅ ጊዜ ስለሆነ ተጠቀሙበት፡፡ በዚሁ አጋጣሚ እኛም እንጦጦ ማርያም ጳግሜን የጸበል አገልግሎት ስለምንሰጥ መጥታችሁ መጠመቅ ትችላላችሁ፡፡

#ጳግሜ_ሦስት_ርኅወተ_ሰማይ_ነው_ሰባቱ_ሰማያትይከፈታሉ_ጸሎታችን_በሙሉ_ያርጋል፡፡

ጳግሜ ሦስት ርህወተ ሰማይ ይባላል፡፡ ርኅወተ ሰማይ ማለት የሰማይ መከፈት ማለት ነው፡፡ ይህም የሰማይ መስኮቶች ወይም ደጆች የሚከፈቱበት እለት ነው፡፡ ርኅወተ ሰማይ ወይም የሰማይ መከፈት ሲባል፤ በሰማይ መከፈት እና መዘጋት ኖሮበት ሳይሆን፤

ቅዱሳን መላእክት የሰውን ልጆች ጸሎት፣ ልመና፣ ያለ ከልካይ፤ ወደ እግዚብሔር የሚያሳርጉበት ቀን ስለሆነ ነው፡፡ እንዲሁም ሊቀ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል የዓመቱን የጸሎት መዝገበ የሚከፍትበት ቀን ስለሆነ ነው ርኅወተ ሰማይ የተባለው፡፡

በእርግጥ በንስሐ ሆኖ ለሚጸልይ ሰው ለእርሱ ሁሌም የሰማይ ደጅ የተከፈተ ነው፡፡ ከዓመት ተለይታ ጳግሜ ሦስት የሰማይ መስኮቶች፤ ወይም ደጆች በሙሉ ተከፍተው፣ የምዕመናን ጸሎት በተለየ ሁኔታ የሚያርግበት ጊዜ እንደ ሆነ ሊቃውንተ ቤተ-ክርስትያንም ይነግሩናል፡፡

ስለዚህ በዚህም ቀን ማለትም ጳግሜ ሦስት ያስለመድናቸውን ጸሎቶች፤ አንዳንዶቻችንም ያቋረጥናቸውን ጸሎቶች፤ በርትተን ብንጸል ቅድመ እግዚብሔር ይደርሳል፡፡

በዚህችም ቀን የጸለይነውን ጸሎቶች፤ ሊቀ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል እና ቅዱሳን መላእክት ቅድመ እግዚብአብሔር ያሳርጉልናል፡፡ በዚህችም እለት የእግዚአብሔር ምህረት እና ቸርነት ለሰው ልጆች የሚወርድበት ታላቅ እለት ነው፡፡

አባቶቻችን እንደሚነግሩን ከሆነ፤ ጳግሜ ሦስት ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ጀምሮ፤ ያስለመዱትንና ሌሎችንም ጸሎቶች ሲጸልዩ ያድራሉ፡፡ ስለዚህ እኛም እንደ እነሱ ማድረግ ባንችል፤ የበረታን ሌሊት ስድስት ሰዓት፤ የቻልን ሌሊት ዘጠኝ ሰዓት ተነስተን ጸሎት ልንጸልይ ይገባናል፡፡

#ጳግሜን_መጠመቅ_መተት_እና_ድግምትን_ይሽራል!

የወለላይቱ እመቤት ልጆች እንደምታውቁት ያለንበት ጊዜ አጋንንት ተፈቶ የተለቀቀበት፣ ሰው በክፋት ከአጋንንት ያልተናነሰበት አንዳንዴም የሚበልጥበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው፡፡ በተለይ ብዙ ምዕመናን በመተት በድግምት እድላቸው ተወስዶ፣ ሕይወታቸው ባዶ እየተደረገ ነው፡፡

አጋንንት ጎታቾች እና መተት መታቶች ጳግሜን በሰው ላይ የሚመትቱትን መተት የሚያድሱበት ስለሆነ ጸበል በርትተን ብንጠመቅ እድሳታቸው ይሽራል፣ መተታቸውም ይከሽፋል፡፡ ስለዚህ በዚህ በወርኃ ጳግሜ በመተት እና በድግምት የምትሰቃዩ ወገኖቼ በርትታችሁ ጸበል ተጠመቁ ጠጡ፡፡

ምክንያቱም ዓመቱን ሙሉ በእድላችን ሲመተት ወደ እና ሕይወት ሲጎተት የነበረው አጋንንት ጳግሜን በርትተን ከተጠመቅን አጋንንቱ አዲሱን አመት አይሻገርም፡፡

በተመተተብን መተት እና በበላነው ድግምት ውስጣችን በተለይ ሆዳችን፣ እንዲሁም መላ አካላታችን ላይ ደዌ ሆኖ የተቀመጠው አጋንንት ይለቀናል፣ ውስጣችን ያለው የደዌ መተት ይሻራል፡፡
እንዲሁም በአውደ ዓመት መስከረም አንድ ቀን በቅዱስ ዮሐንስ ስም አስታከው ዛር አንጋሾች፤ ለዛር ደም የሚያፈሱበት፣ የሚገብሩበት ጊዜ ነው፡፡

አዲሱን አመት ደም በማፍሰስ፣ ለዛር በመገበር ስለሚቀበሉ ጸበል መጠመቁ ከእዚህ ችግር እናመልጣለን፡፡ በተለይ ቤተሰባችሁ በቅዱስ ዮሐንስ የሽፋን ስም ‹‹ለዓውደ ዓመት ነው፣ ለአድባር ነው፣ አዲስን ዓመት ለመቀበት ነው፣ የእናት አባታችን የአያቶቻችን አምላክ እንዳይጣላን ነው፣

በአዲሱ ዓመት ጠላታችን ደሙ እንዲፈስ ነው፣ ደም የምናፈሰው የእኛን ጦስ ይዞ እንዲሄድ ነው›› በማለት ገብስማ፣ ወሰራ፣ ባለ ነጠላ ዶሮ፤ ነጭ፣ ቀይ በግ እያሉ ያረዱትን እንዳትበሉ፡፡

አውቃችሁ በዮሐንስ ስም ለዛር የተገበረለትን ብትበሉ በደም የገባውን ዛር፤ በጸበል ለማስወጣት ትቸገራላችሁ፡፡ በቤታችሁ፣ በአከባቢያችሁ እንደዚህ አይነት ክፉ ልማድ ካለ ተቃወሙ፣ ለማስተው ሞክሩ፡፡ የእነሱ እዳ ነው ነገ ለእናንተ የሚተርፈው፡፡

በተረፈ ይህችን ወርኃ ጳግሜን እንደ አባቶቻችን እንድንጠቀምባት አምላከ ቅዱስ ሩፋኤል ይርዳን፡፡

መንፈሳዊ ጉባኤ

06 Sep, 02:15


መንፈሳዊ ጉባኤ:
#ጷግሜን_ለምን_እንጾማለን?

#ጷግሜን_ለምን_እንጠመቃለን?

#በመጠመቃችን_የምናገኘው_ጥቅም_ምንድን_ነው?

#ጷግሜን_መጠመቅ_መተት_እና_ድግምትን_ይሽራል፡፡

#ጷግሜ_ሦስት_ርኅወተ_ሰማይ_ነው_ሰባቱ_ሰማያት_ይከፈታሉ ጸሎታችን በሙሉ ያርጋል፡፡

/ዩ ትዩብ ላይ የለቀኩትን ትምህርት በጽሑፍ ቃል በቃል አቅርቤላችኃለሁ/

የወለላይቱ እመቤት ልጆች እንደሚታወቀው ወርኃ ጳግሜ፤ ኢትዮጲያን ብቸኛዋ ባለ አሥራ ሦስት ወራት ሀገር ያደርገች ልዩ ወር ናት፡፡ ታዲያ ይህችህ በሦስቱ ወንጌላውያን አምስት ፣ በዘመነ ዮሐንስ በአራት ዓመት ስድስት ቀን የምትሆነው ጳግሜ፣ ብዙ ምስጢር እና ልዩ ጥቅም የላት ወር ናት፡፡

#ጳግሜን_ለምን_እንጾማለን?

የጳግሜ ወር በኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ሃይማኖት የዓለም ፍጻሜ መታሰብያ ወር ተደርጋ ትታሰባለች፡፡ ጳግሜ የዓመታት መሸጋገሪያ፤ ጨለማው የክረምት ወቅት፤ ወደ ማብቂያው እና የሚያልፍበት፤ እንደ ሆነ ሁሉ፤

ዳግም ምጽዓትም ከምድራዊ ወደ ሰማያዊ፤ ከጊዜያው ወደ ዘላለማዊ መሻጋገሪያ በመሆኑ ጳግሜ የእለተ ምጻት ምሳሌ የሆነችው፡፡ በዚህም ምክንያት የኦርቶዶክስ አማኞች የጳግሜን ወር በሱባኤ በጾም በጸሎት ያሳልፋሉ፡፡ በገዳም ያሉ አባቶች ጳግሜን በዝግ ሱባኤ ያሳልፋሉ፡፡

በእግርጥ ጳግሜ ከሰባቱ አጽዋማት ውስጥ ባትካተትም፤ ጳግሜን በግዴታ ሳይሆን በውዴታ ብንጾም የበረታን ሱባኤ ብንይዝባት፣ የቻልን በታቅቦ ብናሳልፋት ትልቅ ጥቅም አለው፡፡

አንደኛ በፈቃዳችን በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት፣ በሱባኤ ብናሳልፍ ጸጋና በረከት ያሰጠናል፡፡ ሁለተኛው ጳግሜ የአዲስ ዓመት መቀበያ የዋዜማ ቀናት በመሆኗ፤ አዲሱን ዓመት በጾም፣ በጸሎት በሱባኤ ብንቀበል አዲሱ ዓመት የበረከት፣ የረድኤት ይሆንልናል፡፡

አዲሱን ዓመት በተለይም በዋዜማው በመዝናናት፣ በመጨፈር፣ በመጠጣት እና በመዘሞት ከምንቀበል፤ በጸሎት ብንቀበል አዲሱ ዓመት የበረከት ዓመት፣ ያሰብነው ያቀድነው እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የሚሳካበት ይሆናል፡፡

ቅድም እንዳልኩት የገዳም አባቶቻችን የጳግሜን ወር፤ መንፈሳዊ ጥቅም ስለሚያውቁ፤ በፈቃዳቸው በታላቅ ሱባኤ ሆነው ስለ ሀገር፣ ስለ መጪው አዲስ ዓመት መልካምነት ፈጣሪን ይማጸኑበታል፡፡ እኛ የአባቶቻችን ልጆች ነን እና፣ እነሱ የሄዱበትን መንገድ ተከትለን፤ እንደ እነሱ ልንጠቀም ያስፈልጋልና፤ ወርኃ ጳግሜን በጾም በጸሎት እና በሱባኤ ብናሳልፍ እንጠቀማለን፡፡

በተለይ በአሁኑ ጊዜ እኛም፣ ሀገራችንም ቅድስት ቤተ-ክርስትያናችንም የገጠመን ፈተና፣ እጅጉን ከባድ ነውና እግዚአብሔር እንዲታረቀን፣ ገጸ ምህረቱን እንዲመልስልን፣ ወረርሽኙን እንዲያጠፋልን፣ ለቅድስት ቤተ-ክርስትያናችንና ለሀገራችን ጽኑ ሰላም እና አንድነት እንዲሰጥልን ወርኃ ጳግሜን እንደ በፊቱ በመብላት በመጠጣት ሳይሆን በጾም በጸሎት ብናሳልፍ ጥቅሙ ለእኛው ነው፡፡

#ጳግሜን_ለምን_እንጠመቃለን?

#በመጠመቃችን_ምን_ጥቅም_እናገኛለን?

እንደሚታወቀው ብዙዎቻችን ወርኃ ጳግሜን እንጠመቃለን፡፡ ጳግሜን የምንጠመቅበት ዋናው ምክንያት ከሊቀ መልአኩ ከቅዱስ ሩፋኤል ጋር የተያያዘ ነው፡፡  

በዚህ በጳግሜ ወር በዓለም ላይ ያሉ ውቅያኖሶች፣ ባህሮች፣ ወንዞች፣ ኩሬዎች ጸበሎች በአጠቃላይ ውሃዎች ሰማይ ተከፍቶ፣ በመላክእት የሚባረኩበት ስለሆነ፤ ጳግሜን የቻልን ጸበል ቦታ ሄደን፣ ወይም በአከባቢያችን ጸበል ካለ እዛም ሄደን፤ መሄድ ባይመቸን፣ ቤታችን ውስጥ ባለው ውኃ ብንጠመቅ እንባረክበታለን፣ ከበሽታችንም እንድንበታለን፡፡

በጳግሜ ጸበል፣ እንኳን የሰው በሽታ፤ በሽታ ያለው እህል፣ በሽታው ይለቀዋል፡፡  ገበሬው ከጳግሜ ወዲያ ነው የሚጠፋውንና የማይጠፋውን እህል የሚለየው፤ በተለይ ዘንጋዳ ጳግሜ ላይ ነው በደንብ የሚያስታውቀው፡፡

በአባባልም ‹‹ዘንጋዳ እና ቡዳ ከመስከረም ወዲያ›› ነው የሚያስታውቀው ይባላል፡፡ የሚገርመው አባቶቻችን ጳግሜ ሦስት ሌሊት ስድስት ሰዓት በተለይ ፏፏቴ ያለው ወንዝ፤ ውሃው ሲቆም ያዩታል፡፡

ቀድሞ አባቶቻን ይህንን ተአምር ለማየት ጳግሜ ሦስት ሌሊት በተለይ ፏፏቴ ያለበት፣ ትልቅ ወንዝ ዳር ሄደው ያድሩ ነበር፡፡ ውሃው ቀጥ ብሎ ሲቆም ሰማይ ሲከፈት ያዩ ነበር፡፡ ጳግሜን በተለይም ጳግሜ ሦስት፣ የሊቀ መልአኩ የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በአሉ ስለሆነ፤

በዚህ ቀን ሊቀ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ውሆችን የሚባርክበት፤ እና ለሰው ልጆች በፈጣሪው ጸጋ፤ ድህነት እና ፈውስ የሚያሰጥበት ቀን ስለሆነ ብንጠመቅ ከበሽታችን እንድናለን፡፡

በመጸሐፍ ቅዱስ በዮሐንስ ወንጌል በምዕራ 5 ቁጥር 4 ላይ ‹‹አንዳንድ ጊዜ  የጌታ መልአክ ወደ መጠመቂያይቱ ወርዶ፣ ውኃውን ያናውጥ ነበርና፤ እንግዲህ ከውኃው መናወጥ በኃላ በመጀመሪያ የገባ ከማናቸውም ካለበት ደዌ ጤናማ ይሆን ነበር›› ይላል፡፡

የጌታ መልአክ ‹‹ውኃውን ያናውጥ ነበር›› የተባለው፤ ከሰማይ ወርዶ ውኃውን ይባርከው ነበር ለማለት ነው፡፡ ውኃውም የሚናወጠው የእግዚአብሔር መልአክ ውኃውን ሲባርከውና እና በመጠመቂያው፣ ለፈውስ ደጅ የሚጠኑት፣ ህሙማን ውሃው በመልአኩ መባረኩን የሚያውቁት ውኃው ሲናወጥ ነው፡፡

ዛሬም እንደ ቀድሞ ሊቀ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል፤ በዓለም ላይ ያሉትን ውሃዎች ሁሉ ስለሚባርካቸው፤ ብንጠመቅባቸው እንፈወሳለን፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል ብቻ ሳይሆን ሌሎች ቅዱሳን መላእክትም ውኃውን ይባርኩታል፡፡

ጳግሜ ሦስት ይህ ብቻ አይደለም ሊቀ መልአኩ ያስለመደን ነገር አለ፡፡ ይህም ሁል ጊዜ ጳግሜ ሦስት ሌሊት፣ ጠዋት፣ ከሰዓት አልያም ማምሻ ላይ ይዘንባል፡፡ ይህ ከሰማይ የሆነ የሊቀ መልአኩ የቅዱስ ሩፋኤል ጸበል ነው፡፡

በልጅነታችን ጳግሜ ሦስትን ‹‹ሩፋኤል አሳድገኝ›› እያልን እንጠመቃለን፡፡ ጳግሜ ሦስት በዘነበው ውኃ መጠመቅ ትልቅ መታደል እና ፈውስ ነው፡፡ በደዌ ይሰቃይ የነበረው ኢዮብም በዚህ ሳምንት ነው ተጠምቆ ነው የዳነው፡፡

የሚገርማችሁ በዚህ በከተማ ብዙም ስለማይታወቅ ነው እንጂ፤ በገጠር እና በክፍለ ሀገር የቅዱስ ሩፋኤል እለት የዘነው ዝናብ በእቃ ይቀዳና ይቀመጣል፡፡ በተቀዳው ጸበል ቦሃቃው ይረጭበታል፣ በውሃው እህሉ ይቦካበታል፣ ቤቱ ደጁ ይረጭበታል፡፡

ይህም የሚሆነው የቅዱስ ሩፋኤል እለት የዘነበው ውኃ የሰላቢ መንፈስን ስለሚያርቅ ነው፡፡ የሰላቢ መንፈስ ከቤታችን የእህል በረከት የሚያሳጣ፣ ለአንድ ወር ያሰብነውን ለሳምንት የማያዳርስ፣ ለዓመት ያልነው በሦስት ወር እንዲያልቅ የሚያደርግ፤ ክፉ መንፈስ ስላለ ይህን ያርቅልናል፣ በጸበሉ በረከት እህል አስቤዛውን ያበረክትልናል፡፡

እንደምታውቁት ቅዱስ ሩፋኤል ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት ሦስተኛው ነው፡፡ በመጀመሪያዋ እለተ ፍጥረት እግዚአብሔር መቶ ነገደ መላእክት ፈጥሮ በአሥር ከተማ ሲያኖራቸው

ቅዱስ ሩፋኤል ራማ ላይ ነው ከነ ሠራዊቱ ያረፈው ወይም የከተመው፡፡ በራማም መናብርት ተብለው ለሚጠሩት አሥሩ ነገድ አለቃ ወይም መሪ ሆኖ በእግዚአብሔር ተሹሟል፡፡ በኃላም መጋብያን በሚባሉ በሃያ ሦስቱ ነገድ ላይ ተሹሟል፡፡

ስለዚህ ጳግሜ ሦስት የሊቀ መልአኩ የቅዱስ ሩፋኤል በዓለ ሲመት ወይም የሹመት በዓሉ ነው፡፡

ይህንንም እራሱ ሊቀ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል በመጽሐፈ ጦቢት ምዕራፍ 12 ቁጥር 15 ላይ ‹‹ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ›› በማለት ተናግሯል፡፡

መንፈሳዊ ጉባኤ

21 Aug, 19:03


መንፈሳዊ ጉባኤ:
❖ ❖ ❖ ኪዳነ ምህረት (የካቲት 16) ❖ ❖ ❖
               ❖ ❖ ❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖ ❖ ❖
   ኪዳነ ምህረት ማለት የምህረት መሐላ ማለት ነው፡፡ ከ33ቱ በዓላተ እግዝእትነ ድንግል ማርያም አንዱ ነው፡፡ እመቤታችንም ከጌታችን መቃብር እየሄደች በምትለምንበት ጊዜ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉምና ምን ልታመጣብን ነው በማለት ሊጣሏት ሲመጡ ጌታችንም ከዓይናቸው ሰውሯታል አይሁድም ጠባቂ ቢያቆሙ እመቤታችን ዕለት ዕለት መሄዷን አላቋረጠችም እመቤታችንም እንዲህ ብላ ስትጸልይ ልጄ ወዳጄዘንድ ሆይ ከስጋዬ ስጋ ከነፍሴ ነፍስ ነስተህ ሰው በመሆንህ ዘጠኝ ወር ከ5 ቀን በቻለችህ ማሕጸኔ ከአንተ ጋር ሀገር ለሀገር ስለ መሰደዴ መትተህ ልምናዬን ትሰማኝ  እለምንሃለሁ አለች በዚህ ጊዜ ንውጽውጽውታ ሆነ መቃብራት ተሰነጣጠቀ ጌታችንም እልፍ ከእልፍ መላዕክቱ ጋር መጥቶ ሰላም ለኪ ማርያም ምን እንዳደርግልሽ ትለሚኚኛለሽ አላት፡፡ እርሷም መታሰቢያዬን ያደረገውን ስለ ስሜ ለችግረኛ የሚራራውን በስሜ ቤተ ክርስቲያን ያነጸውን መባዕ የሰጠውን ከሃይማኖት ከፍቅር ጽናት ልጁን በስሜ የጠራውን ሁሉ ማርልኝ ከሞተ ስጋ ከሞተ ነፍስ አድንልኝ አለችው፡፡ ጌታችንም ይህን ሁለ እንዳደርግልሽ መሐልኩ ለኪ በርእስየ ወበ አቡየ ሕያው ወበመንፈስ ቅዱስ ብሎ ቃል ገብቶላት አርጓል፡፡
   ሌላው በላዔ ሰብ በአማርኛ ሰው በላ ማለት ነው፤ ትክክለኛ ስሙ ግን ስምዖን ይባላል ቅምር በሚባል አገር የሚኖር እጅግ ባለጸጋ ነበር፤ እንደ አብርሃም እንግዶችን እየተቀበለ ድሆችን እየመገበ የሚኖር ጻድቅ ነበር፤ ሰይጣን በዚህ ስራው ቀናበት ሊፈትነውም በሦስት አረጋዊ ሽማግሌዎች ሥላሴ ነን ብሎ ተገለጠለት ልክ እንደ አብርሃም፤ ሐዋርያው ጳውሎስ ሰይጣን የብርሃን መልአክ መስሎ ይመጣል እንዳለ፤ እርሱም ሥላሴ መስለውት ተቀበላቸው ተንከባከባቸውም፤ ምግብ አቀረበላቸው ምግብ አንበላም የምንጠይቅህን ግን ትፈጽምልን ዘንድ ቃል ግባልን አሉት ቃል ገባላቸው እንግዲያውስ የምትወደን ከሆነ አንድያ ልጅህን ሰዋልን አሉት፤ መጀመሪያ ደነገጠ ኃላ አብርሃም ልጁን ሊሰዋ አልነበረምን እኔንም ሊፈትኑኝ ይሆናል ብሎ ለማረድ ተዘጋጀ፤ ተው የሚለው ድምጽ አልሰማም፤ አረደው አወራረደው ይዞላቸው ቀረበ፤ መጀመሪያ ቅመስልን አሉት ቀመሰው ወዲያው እነዚያ ሰዎች ተሰወሩበት እርሱም አህምሮውን ሳተ ተቅበዘበዘ ከዚያ በኃላ ምግብ አላሰኘውም የሰው ስጋ እንጂ መጀመሪያ ቤተሰቦቹን በላ ከዚያም ጓደኞቹን ጦርና የውኃ መንቀል ይዞ ከቤቱ ወጣ ያገኘውን ሰው እየገደለ ይበላል የበላቸው ሰው ቁጥር 78 ደረሰ፤ በመንገድ ተቀምጦ የሚለምን በደዌ የተመታ አንድ ደሃ አገኘ ሊበላው ወደ እርሱ ተጠጋ ግን ቁስሉን አይቶ ተጸየፈው፤ ደሃውም “ስለ እግዚአብሔር ከያዝከው ውኃ አጠጣኝ” አለው “ዝም በል ደሃ” ብሎት አለፈ፤ “አረ በውኃ ጥም ልሞት ነው ስለ ጻድቃን ስለ ቅዱሳን” አለው አሁንም ዝም ብሎት ሄደ ለሦስተኛ ጊዜ “ስለ አዛኝቷ ስለ ድንግል ማርያም” አለው፤ ሰውነቱን አንዳች ነገር ወረረው “አሁን የጠራከውን ስም እስኪ ድገመው ስለ ማን አልከኝ” አለው፤ ስለ አዛኝቷ ስለ እመቤቴ ማርያም አለው፤ ይህቺስ ደግ እንደሆነች በምልጃዋም ከሲኦል እንደምታወጣ ህጻን እያለው እናትና አባቴ ይነግሩኝ ነበር፤ በል እንካ አለው እጁን ዘረጋለት ጥርኝ ውኃ ጠብ አደረገለት ወደ ጉሮሮው አልወረደም የተሰነጠቀ እጁ ውስጥ ገባ እንጂ፤ በለዔ ሰብ ከዚያች ደቂቃ በኃላ አዕምሮው ተመለሰለት እንዲህም አለ “በአንድ ዋሻ ውስጥ ገብቼ ስለ ኃጢያቴ አለቅሳለሁ ስጋዬ ከአጥንቴ እስኪጣበቅ እጾማለሁ ወዮሊኝ ወዮታም አለብኝ አለ፤ ወደ ዋሻ ገባ ምግብ ሳይበላ ውኃም ሳይጠጣ 21 ቀን ኖሮ በርሃብ ሞተ ይላል ተአምረ ማርያም። ጨለማ የለበሱ ሰይጣናት እያስፈራሩ እያስደነገጡ ነፍሱን ወደ ሲኦል ሊወስዷት መጡ፤ እመቤታችን ፈጥና በመካከላቸው ተገኘች፤ ልጄ ወዳጄ ይህችን ነፍስ ማርሊኝ አለችው እናቴ ሆይ 78 ነፍሳትን የበላ እንዴት ይማራል አላት፤ የካቲት 16 ቀን በጎልጎታ የገባህልኝ ቃል ኪዳን አስብ ስምሽን የጠራ መታሰቢያሽን ያደረገን እምርልሻለው ብለኸኝ የለምን አለችው፤ እርሱም እስኪ ይህቺን ነፍስ በሚዛን አስቀምጧት አለ ቢያስቀምጧት ጥርኝ ውኃው መዝኖ ተገኘ፤ ስላንቺ ስል ምሬታለው ሰባት ቀን ሲኦልን አስጎብኝታችሁ ወደ ገነት አግቧት አላቸው። ቦታሽ እዚህ ነበር እያሉ ሲኦልን አስጎብኝተው ወደ ገነት አገቧት። ልመናዋ ክብሯ የልጇም ቸርነት ከሁላችን ጋር ይሁን።
❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖
በዕለቱ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚቀርበውን የምስጋና ቃል እንደሚከተለው አቅርበናል መልካም በዓል፡፡
           ❖ ❖ ❖ ዋዜማ ❖ ❖ ❖
ሃሌ ሉያ (፬) ርግብየ ይቤላ በእንተ የዋሃታ፤
በሐኪ ማርያም ሐዳስዩ ጣዕዋ፤
እንዘ አመቱ እሞ ረሰያ ፤
ታዕካ ሰማይ ኮነ ማኅደራ፤
ዳዊት ይሴብሕ ወይዜምር ዕዝራ ፤
          ❖ ❖ ❖ ምልጣን ❖ ❖ ❖
እንዘ ዓመቱ እሞ ረሰያ ፤
ታዕካ ሰማይ ኮነ ማኅደራ፤
ዳዊት ይሴብሕ ወይዜምር ዕዝራ ፤
ዳዊት ይሴብሕ ወይዜምር ዕዝራ ፤
        እግዚአብሔር ነግሠ
        እንተ ክርስቶስ በግዕት እንተ ታስተርኢ እምርኁቅ ብሔር፤
        በቤተልሔም አስተብረከት ዕጓለ አንበሳ ግሩመ ወለደት፡፡
           ❖ ❖ ❖ ይትባረክ ❖ ❖ ❖
እግዝእትየ እብለኪ ወእሙ ለእግዚእየ እብለኪ፤
ቃል ቅዱስ ኀደረ ላዕሌኪ፡፡
           ❖ ❖ ❖ ሰላም ❖ ❖ ❖
ሃሌ ሉያ (3) ክነፈ ርግብ በብሩር ዘግቡር ወገበዋትሃኒ በሐመልማለ ወርቅ፤
የሐንፁ አሕዛብ አረፋተኪ በዕንቊ ክቡር፤
ወመሠረትኪ በወርቅ ንጹሕ ይሰግዱ ለኪ ውስተ ገጸ ምድር፤
በእንተ ዕበየ ክብርኪ አምላከ ፳ኤል ውእቱ ረዳኢኪ
ዘአድኀነኪ እምእደ ጸላዕትኪ፤
ወረሰየ ሰላመ ለበሐውርትኪ፡፡
         ❖ ❖ ❖ መልክአ ሥላሴ ❖ ❖ ❖
ሰላም ለኵልያቲክሙ እለ ዕሩያን በአካል፡
ዓለመክሙ ሥላሴ አመ ሐወፀ ለሣህል፡
እምኔክሙ አሐዱ እግዚአብሔር ቃል ፡
ተፈጸመ ተስፋ አበው በማርያም ድንግል
ወበቀራንዮ ተተክለ መድኃኒት መስቀል
          ❖ ❖ ❖ ዚቅ ❖ ❖ ❖
ወታስተሥርዪ ኃጢአተ ሕዝብኪ ተበውሐ ለኪ፤
እም አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፤
ከመ ትኩኒ ተንከተመ ለዉሉደ ሰብእ ለሕይወት ዘለዓለም፤
ለኪ ይደሉ ከመ ትኩኒ መድኀኒቶሙ ለመሐይምናን ሕዝብኪ፤
ኦ መድኀኒተ ኵሉ ዓለም ፤
ወልድኪ ሣህሎ ይክፍለነ ሰአሊ ለነ ቅድስት፡፡
         ❖ ❖ ❖ መልክአ ኪዳነ ምህረት ❖ ❖ ❖
ሰላም ለዝክረ ስምኪ ዘመንክር ጣዕሙ ;
ለወልድኪ አምሳለ ደሙ፤
መሠረተ ሕይወት ማርያም ወጥንተ መድኀኒት ዘእምቀዲሙ፤
ኪየኪ ሠናይተ ዘፈጠረ ለቤዛ ዓለሙ፤
እግዚአብሔር ይትባረክ ወይትአኰት ስሙ፡፡
         ❖ ❖ ❖ ዚቅ ❖ ❖ ❖
ቅንዑ ለእንተ ተዓቢ ጸጋ መድኀኒት ለነፍስ ወሥጋ፤
እስመ ርቱዓት ፍናዊሃ ጻድቃን የሐውርዎን ፤
ወኃጥአን ይስዕንዎን፤ ዘእንበለ ትብጻሕ ግብተ አሠንዩ ፍኖተ፤
ይፈኑ ለክሙ እመቅደሱ ረድኤተ መድኀኒተ መቤዛዊተ እሞ ቅድስተ፡፡

❖ ❖ ❖ መልክአ ኪዳነ ምህረት ❖ ❖ ❖
ሰላም ለዝክረ ስምኪ ዘአስተማልዎ በኮከብ፤
ሶበ ብርሃኖ ተከድኑ ጽልሙታነ ራእይ ሕዝብ፤
ኪዳነ አምላክ ማርያም ወተስፋ መድኀኒት ዘዐርብ፤
ተናዘዘ ብኪ አኮኑ ሕሊና ቀዳማይ አብ፤
አመ እምገነቱ ተሰደ በኃዘን ዕፁብ፡፡
         ❖ ❖ ❖ ዚቅ ❖ ❖ ❖
አንቲ ውእቱ ተስፋሁ ለአዳም ፤
አመ ይሰደድ እምገነት፡፡
          ❖ ❖ ❖ መልክአ ኪዳነ ምህረት በዓል ❖ ❖

መንፈሳዊ ጉባኤ

17 Aug, 20:06


✍️   ቅዱሱ ተራራ ✍️↲(፪ኛ ጴጥ፩÷፲፯-1፲፰ )

ደብረታቦር ማለት የታቦር ተራራ ማለት ነው፡፡
ከጌታችን ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ከ፱ኙ ዐበይት በዓላት መካከል የደብረታቦር በዓል አንዱ ነው፡፡
     በእስክንድርያ ግን ዐበይት በዓላቶቻቸው ፯ ናቸው፡: በዚህም ምክንያት ከዐበይት በዓላት ውስጥ አስገብተው ደብረታቦር አይቆጥሩትም ፡ይሁን እንጂ በበዓልነቱ አይከበርም ማለት ግን አይደለም።

      ደብረታቦር ወይም የታቦር ተራራ ጌታ በምድረ እስራኤል እየተዘዋወረ በማሰተማር ላይ በነበረበት ዘመን ነሐሴ ፲፫ ቀን ብርሃ መለኮቱንና ክብረ መንግስቱን የገለጠበት ታሪካዊ በዓል ነው፡፡ጌታችን በመዋዕለ ስብከቱ ብዙውን ጊዜ የሚስተምረውና ተአምራት የሚያደርገው በተራራ ላይ ነበር፡(ማቴ ፲፯÷፬) ይህን በዓል ከቅዱስ ዮሐንስ በቀር ፫ቱም ወንጌላውያን በየወንጌሎቻቸው መዝግበውታል(ማር፬÷፪ ፲፫ ፤ ሉቃ ፱÷28-36)
     ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስም “ ከገናናው ክብር ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው የሚል ድምፅ በመጣለት ጊዜ ከእግዚአብሔር አብ ክብርንና ከምስጋናን ተቀብሎአልና እኛም በቅዱሱ ተራራ ከእርሱ ጋር ሳለን ይህ ድምጽ ከሰማይ ሲወርድ ሰማን” በማለት የተገለጸውን ምስጢር ታላቅነት መስክሮአል(፪ኛ ጴጥ፪÷፲፯-፲፰፣በዓላት በዲ.ን ብርሃኑ አድማስ)
     ቅዱሳን ሐዋርያት ብርሃነ መለኮቱን ካዩ በኋላ የቃላቸው ትምህርት የእጃቸውም ተአምራት ብቻ ሳይሆን የልብሳቸውም ቁራጭ ጥላቸው ጋኔን ያወጣ ድወይ ይፈውስ ነበር( ሥርዓተ አምልኮ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ)
      ይህ ተራራ ከገሊላ ባሕር በምስራቅ ደቡባዊ በኩል ፲ ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን 572 ኪ.ሜ ከፍታ አለው፡፡የታቦር ተራራ በሐዲስ ኪዳን በግልጽ ባይጠቀስም በብሉይ ኪዳን ግን ተጠቅሶ እናገኘዋለን(መሳ ፬÷፮-፲፬) ቅዱስ ዳዊትም “ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ ወይሰብሑ ለስምከ መዝራዕትከ ምስለ ኃይል፤ ታቦርና አርሞንዔም በስምህ ደስ ይላቸዋል፡፡ ክንድህ ከኃይልህ ጋር ነው፡፡ እጅህ በረታች ቀኝህም ከፍ ከፍ አለች(መዝ 88÷12-13) ይላል፡፡ በደብረታቦር ዲቦራም ዘምራበታለች፡፡

      ጌታችን በቂሣርያ ሐዋርያትን “ሰዎች የሰው ልጅን ማን ብለው ይጠሩታል “ በማለት በጠቃቸው ቀን የቀሩት ደቀ መዛሙርት በተራራው ሥር ትቶ ሦስቱን ( ጴጥሮስን ያዕቆብንና ዮሐንስን ይዞ ወደ ታቦር ተራራ ወጣ፡፡ በተራራው ላይ ሳሉ የጌታችን መልክ ተለውጦ ፊቱ እንደ ፀሐይ አበራ፡ልብሱም እንደ በረዶ የነጻ ሆነ፡፡ በዚህ ጊዜ ብርሃነ መለኮቱንና ክብረ መንግስቱን ገለጠ(ሉቃ9÷29)
በደብረታቦር ተራራ ፭  ነገር ተከናውኗል፤
ሙሴና ኤልያስ ሲነጋገሩ ተሰምቷል፡፡
      -መልኩ ተለወጠ (ወተወለጠ አርአያሁ በቅድሜሆሙ) (ማቴ ፲፯÷፪) በዚህ ሰዓት በሐዋርያት ላይ ያደረ ሥጋዊ መንፈስ ራቀ፡ በውስጣቸው ያለው የጨለማ ፍርሃት አሰወገደላቸው( ጥርጥርን አለማመን እነዚህን ነገሮች ሀሉ ከልቡናቸው አስወገደላቸው፤ ፡የእግዚአብሔርን ክብር እንዲያስታውሉ አእምሮቸው ብሩህ ሆነ፡፡በደመና ውስጥ ሁኖ የምወልደው የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን የሚል ቃል ተሰማ ( ዝንቱ ወእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ወሎቱ ሰምዕዎ) ደመና የእግዚአብሔር የክብሩ ምሳሌ ነው፡፡

      ልብሱ እንደ በረዶ ነጻ ( ወአልባሲሁኒ ኮነ ከመ ፀዓዳ)
ጌታችን በደብረ ታቦር ተራራ የብሉይና የሐዲስ ኪዳ ሰዎችን ( ነቢያትና ሐዋርያትን ) አንድ አደረጋቸው፡፡ እሱ አምላካችን መጋቤ ብሉይ ወሐዲስ ነውና ፡፡ሌላው ምስጢር ሙሴና ኤልያስ የተጠሩበት ሙሴ ነህ ይላሉ ኤልያስ ነህ ይላሉ ሲሉት እርሱ አምላከ ሙሴ አምላከ ኤልያስ መሆኑን ሊያሳይ ነው፡፡
       ከነቢያቱ ለሊቀ ነቢያት ሙሴ “ጀርባዬን ታያለህ ፊቴን ግን አታይም ( ዘዳ 33÷28) በተባለው መሠረት “እባክህ ክብርህን ( ፊትህን) አሳየኝ ይህ ካልሆነማ ባለሟል መባሌ ምኑ ላይ ነው (ዘጸ33÷18-23) የሚለውን የባለሟልነት ጥያቄውን ሙሴን ከሙታን አስነስቶ ስለክብሩ የቀናውን ኤልያስንም ከብሔረ ሕያዋን አምጥቶ ክብሩን አሳይቷቸዋል የሙሴን ጸሎት ሳይረሳ ልመናውን ፈጸመለት፡፡
በጀርባ የተመሰለው ከ5500 በኋላ የተፈጸመው ምስጢረ ሥጋዌ ነው፡፡
          ሙሴና ኤልያስ መሆናቸው በምን ይታወቃል?

   ሙሴ ብልቱትነቱ ኤልየስም በፀጉርነቱ አንድም በአነጋገራቸው ታውቋል፡፡ ሙሴም የእኔን የሙሴን ጌታ ማን ሙሴ ይልሃል እግዚአ ሙሴ ይበሉህ እንጂ ኤልየስም የእኔን የኤልያስን ጌታ ማን ኤልያስ ይልሃል እግዚአ  ኤልያስ ይበሉህ እንጂ ሲሉ ተሰምተዋል፡፡
       አንደድም ምውት ለሕያው ሕያው ለምውት ሲጸልዩ ተስምተዋል፡፡ አንድም ሙሴ እኔ ባሕር ብከፍል ጠላት ብገድል ደመና ብጋርድ መና ባወርድ እስራኤላውያንን ከክፋታቸው መመለስ አልተቻለኝም ላንተ ግን መልሶ ማደን ይቻልሃልና፡፡
    ኤልያስም እኔ ሰማይ ብለጉም እሳት ባዘንብ እስራኤላውያንን ከክፋታቸው መመለስ አልተቻለኝም ላንተ ግን መልሶ ማደን ይቻልሃልና ሲሉ ተስምተዋል ( አንድምታ ወንጌል ማቴ ምዕ.፲፯)
        ፍጻሜው ግን ደብረታቦር የመንግስተ ሰማያት ምሳሌ ናት፡፡ሕጋውያንም ደናግልም እንዲወርሷት ለማጠየቅ ከሕጋውያን ሙሴን ከደናግል ኤልያስን አመጣ፡፡
ይህ በዓል በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በተለይም በምእመናን ዘንድ የተለየ ስም አለው( ቡሄ ይባላል)፡፡
   ቡሄ ማለት መላጣ ( ገላጣ) ማለት ነው፡፡ በሀገራችን ክረምቱ አፈናው ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታየው በደብረታቦር በዓል አካባበር ስለሆነ “ቡሄ “ ያሉት ለዚህ ሳይሆን አይቀርም፡፡
ሊቃውንት "ቤሄ ከዋለ የለም ክረምት ደሮ ከጮኸ የለም ሌሊት”እንዲሉ(የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ገጽ- 127-128)
- ሕፃናት የሚያጮሁት ጅራፍ ጩኸት ድምፅ የድምፀ መለኮት ጅራፍ ሲጮህ ማስደንገጡን የሦስቱ ሐዋርያት ምሳሌ ሲሆን  መደንገጣቸው በድምፀ መለኮቱ መደንገጣቸውን መውደቃቸውን ያስታውሳል፡፡
   - በአንዳንድ ቦታዎች የቡሄ ዕለት ማታ ችቦ ያበራሉ በደብረታቦር ለታየው ብርሃነ መለኮት ምሳሌ ነው፡፡
- ምእመናን በድበረታቦር ክብሩን አየን ዛሬም ያ ክበሩ ለገለጥን ያስፈልጋል፡፡ እገዚአብሔር ክብሩን የገለጠበት ያ ተራራ ዛሬ የእኛ አካል ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ የእግዚአብሔር ክብሩና ጥበቡ የሚገለጥበት ማዳኑ የሚታይበት የተባረከ ሕይወት ሊኖረን ይገባል

- የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ ስለእኛ ጸልዩ
    እንኳን አደረሰን

መንፈሳዊ ጉባኤ

17 Aug, 19:59


#እንኳን_አደረሳቹ_አደረሰን_የተዋህዶ_ልጆች_በሙሉ😘🙏
✝️🌿👉 #ቡሄ_ጅራፍ_ማስጮህ
✝️🌿👉 #ችቦ_ማብራት
✝️🌿👉 #ሙልሙል_ዳቦ - ሐይማኖታዊ ምስጢራቸው ምንድነው⁉️
#ደብረ_ታቦር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያዕቆብን ፣ ዮሐንስንና ጴጥሮስን ይዞ ወደ ታቦር ተራራ ከወሰዳቸው በኋላ በዚያ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበትና ሙሴና ኤልያስን ጠርቶ የህያዋንና የሙታን አምላክነቱን ያሳየበት ከዘጠኙ የጌታ ዓበይት በዓለት ውስጥ አንዱ ነው።
✝️🌿💚💛
ቤተክርስቲያናችንም የተለያዩ ስርዓቶችን በመፈፀም አክብራው ታልፋለች፡፡ #በደብረ ታቦር በዓል የሚፈጸሙ ( #ቡሄ ፣ #ጅራፍ ማስጮህ ፣ #ችቦ ማብራትና #ሙልሙል_ዳቦ ) ትውፊታዊ የሃይማኖት ስርዓቶች ምሳሌዎች ምን እንደሆነ እናያለን፡፡
✝️🌿💚💛
#ቡሄ ቡሄ ማለት ብራ ፣ ብርሃን፣ ደማቅ ማለት ነው፡፡ ከስሙ ትርጉም እንደምንረዳው
ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት በዓል ስለሆነ ብራ፣  ብርሃን ደማቅ የሚል ፍቺ ያለው ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ አንድም ቡሄ ማለት ወቅቱ የክረምት ጨለማ አልፎ የብርሃን ወቅት ስለሚመጣ ሰማይም ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚለወጥበት የመሸጋገሪያ ወቀት ስለሆነ ብራ ተብሏል፡፡
✝️🌿💚💛
" ቡሄ ከዋለ የለም ክረም ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት እንዲሉ " አንድም ቡሄ…..ቡኮ "/ሊጥ" ማለት ነው፡፡ በዚህ በዓል ቡኮ ተቦክቶ ዳቦ/ ሙልሙል / ተጋርሮ የሚታደልበት በዓል ስለሆነ ይህ ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡
✝️🌿💚💛
✝️🌿👉 #ሙልሙል_ዳቦ
ሙልሙል ዳቦ አመጣጡ ጌታችን ብርሃናዊ መለኮቱን በገለጠበት በዚህ ዕለት በደብረታቦር አካባቢ የነበሩ ህፃናት እረኞች ቀኑ የመሸ ስላልመሰላቸው / ጌታችን በብርሃን አካባቢውን ሞልቶት ስለነበረ / በዛው ሆነው ከብትና በጎቻቸውን እየጠበቁ ሲቆዩባቸው የሰዓቱን መግፋት የተመለከቱ ወላጆች በችቦ ብርሃን ተጠቅመው ለልጆቻቸው የሚቀመስ ሙልሙል ዳቦ ይዘው
ወዳሉበት መምጣታቸውን ያሳያልና ታሪኩን እየዘከርን በዓሉን እናከብራለን፡፡
✝️🌿💚💛
#አንድም እንደ #ሐዋርያት_የምስራችሲነግሩን ወንጌል ሊሰብኩልን በየደጃፋችን መጥተው " ቢሄ በሉ " የሚሉትን ታዳጊዎችን ይበሉት ዘንድ ይሰጣቸዋል ይህም መጽሐፋዊ ነው ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን በደረሳችቡት ሁሉ ተመገቡ /ማቴ 10፥12/ ብሏልና ህፃናቱም የጌታን በዓል
ሊያበስሩ ሲመጡ ዳቦ መስጠት ልማዳዊ ብቻ ሳይሆን ህፃናቱም የደቀመዛሙርት ምሳሌ ናቸው፡፡
✝️🌿💚💛
#መዝሙራቸው ደግሞ የምስራች ወንጌል ይዘው የመምጣታቸው ምሳሌ ነው፡፡ ሐዋሪያት
በገቡበት ሀገር ሁሉ አስተምረው አጥምቀው የፀጋ ልጅነትን አሰጥተው እንደሚቆዩ ሁሉ ልጆችም ዘምረው አመስግነው መርቀው ውለዱ ክበዱ የመንግስተ ሰማያት ወራሾች ያድርጋችሁ ብለው አመስገነው ይሄዳሉና በሐዋሪያት ህፃናቱ ይመሰላሉ፡፡
✝️🌿💚💛
✝️🌿👉 #ችቦ_ማብራት
ችቦ የጌታችንን ብርሃነ መለኮት መገለጥን የሚያመለክት ነው፡፡ ጌታችን በደብረ ታቦር መለኮቱን ሲገልጥ ብርሃን አካባቢውን ሞልቶት ነበርና ያንን በዘመናችን ለመግለጥ የበዓሉ ዋዜማ ማታ ችቦ አብርተን አምላካችንን እናመሰግናለን፡፡ አንድም ደግሞ የችቦ ታሪክ ከላይ እንደገለፅነው የእረኞቹ ወላጆች ይዘውት የመጡት ብርሃን ነው፡፡
✝️🌿👉 #ጅራፍ
የጅራፍ ምሳሌነት በደብረ ታቦር በዓል በትውፊታዊ መልኩ የሚታየው ሚስጥር በእየሩሳሌም ስለሚሆነው የጌታችን ሞቱ ምሳሌ ነው፡፡ በዚህ በዓል ጅራፍ መገመዱ እና ማጮሁ ሁለት አይነት ምሳሌ አለው፡፡
✝️🌿💚💛
✝️🌿 #የመጀመሪያው_ምሳሌ - ጌታችን በዕለተ አርብ የደረሰበትን ግርፋትና ህማም እናስብበታለን፣
✝️🌿 #ሁለተኛው_ምሳሌ -  ደግሞ ድምፁን ስንሰማ የባህሪ አባቱን የአብን የምስክርነት ቃልና
በግርማው ሲገለጥ የተሰማውን ነጎድጓድ ያስታውሰናል፡፡
✝️🌿💚💛
የጅራፍን ትውፊታዊ ውርስ መጽሐፋዊ ትምህርቱንና ምስጢሩን ከትውልድ ጠብቆ ማስተላለፉ ተገቢ ነው፡፡
✝️🌿💚💛
በአጠቃላይ በዓለ ደብረ ታቦር ከነዚህ ሚስጢር ካላቸው ትምህርቶችና ትርጓሜያቱ ከትውልድ ወደ ትውልድ በቅብብል እንደመጣልን እኛም ሃይማኖታዊ ትውፊቱን ሳይለቅ ማስተላለፍ ይጠበቅብናል፡፡ የዚህ ነገር ባለ ድርሻ አካላት ደግሞ ወጣቶችና ወላጆች ናቸው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በቡሄ ጨዋታ የሚሰሙ ግጥሞች ስድብ ፊዝና ሳቅ ይታይባቸዋል ተጫዋቾቹም ከሰጡን እንመርቃለን ካልሰጡን እንራገማለን አይነት መልዕክት ያስተላልፋሉ። የሚብሰው አሳባቢ ነገሩ ደግሞ ኃይማኖታዊ ስርዓቱን ወደ ገንዘብ ማግኛ መቀየሩ ነው፡፡
✝️🌿💚💛
ስለሆነም ይህን ነገር በተለይ የነገ የሀገር ተረካቢና የቤተክርስቲያን ተተኪ የሆንን ወጣቶች ማስተካከል ይኖርብል፡፡ ወላጆችም ሕፃናት በየደጃፋችን ላይ በዓሉን ሊያበስሩ ሲመጡ አስደንግጦ ከማባረር በሚገባው መልኩ አስተምረን መርቀን ማስተናገድ ይጠበቅብናል ባህሉም እንዳይተው የበኩላችንን አደረግን ማለት ነው። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን

2,960

subscribers

1,717

photos

18

videos