ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው
መዝ 60፥4 ላይ ልበ አምላክ ዳዊት “ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው" በማለት የተናገረው በምሥጢር ክርስቶስ የሚሰጠንን የሐዲስ ኪዳን ልዩ ምልክት ሲያመላክት ነው። እግዚአብሔር የሚሰጠንን ልዩ ምልክት ገንዘብ ለማድረግ አስቀድመን ሊኖረን የሚገባው “ፈሪሐ እግዚአብሔር" ነው። ፈሪሐ እግዚአብሔር ወደ ጽድቅ መግቢያ በር ስለ ኾነ ልዩ ምልክትን ከእግዚአብሔር ለማግኘት የግድ የፈሪሐ እግዚአብሔርን ልብስ ውስጣችንን ማልበስ አለብን። ያ ልዩ ምልክት ቅዱስ መስቀሉ ነውና! መስቀል ዓለምን በሙሉ አምላካችን ክርስቶስ ወደ ራሱ የሳበበት የሰላም ዓርማ ነው። ይህ ምልክት ክርስቶሳውያን የመኾናችን ዋና መለያ ነው።
እግዚአብሔርን የማንፈራ በፊቱ ቆመን የምንተቻች፣ እርስ በእርሳችን የምንናናቅ እንዴት ምልክቱን ልናገኝ እንችላለን? በፈሪሐ እግዚአብሔር ውስጥ እስካልኖርን ድረስ ምልክቱን ማግኘት አንችልም። ለሚሳለቁበት፣ መቅደሱን የሳቅና የስላቅ ስፍራ ለማስመሰል ለሚጥሩ፣ ትሕትና ለሌላቸው፣ ቅዱሳን መላእክት በመንቀጥቀጥ የሚያመልኩትን አምላክ በመቅደሱ ተገኝተው የሚተኙበት ሰዎች ምልክቱን አያገኙትም። “ለሚፈሩት" ሲል ለሚያመልኩት ማለት ነው። እናመልክሃለን ብለው በተግባር ግን ፈጽሞ የራቁ ሳይኾን በእውነት የሚያምኑበት ናቸው ልዩ ምልክትን የሚያገኙት። ወደዚህ ምልክት ውስጥ በፍቅር እስካልገባን ድረስ ፍቅርንና ሰላምን ገንዘብ ማድረግ አንችልም። በተግባራዊ ሕይወታችን ውስጥ የቀበርነውን መስቀል በንጹሐን መምህራን በኩል ቆሻሻውን አስነሥተን መስቀሉን እስካላወጣነው ድረስ መስቀል የሕይወት ምልክት ነው ብለን የምንፈክር እንጂ በእርግጥም መኾኑን በሕይወት መግለጥ ያቃተን ግብዞች መኾናችንን እናረጋግጣለን።
ምልክት (Banner) የሚያመለክተው አምላካችን ክርስቶስ ዓለምን ለማዳን አንድ ጊዜ የገባበት መቅደስ የተባለውን ቅዱስ መስቀልን ነው። መስቀል ለክርስትናችን መለያ ምልክት ነው። ክርስትናን ከመስቀል ነጥሎ ለማየት መሞከር ማለት ቤተክርስቲያንን ከክርስቶስ ነጥሎ ለማየት እንደ መፈለግ ነው። መስቀል የቤተክርስቲያን ሙሽራ ክርስቶስ ቅድስት ቤተክርስቲያንን በደሙ ሲያጭ ፥መታጨቷን ለመግለጽ ያኖረላት ምልክት ነው። ቤተ ክርስቲያን ጉዞዋ በሙሉ ወደ ድኅነት የሚመራ ነው። በምድር ላይ በምእመናን ልብ ውስጥ መስቀል እየሳለች ሰማያዊቷን መንግሥት ታጓጓናለች።
መስቀልን በአንገታችን ላይ ማድረጋችን የክርስቶስ ሙሽሪቶች መኾናችን ይታወቅ ዘንድ ነው። አንዲት ሴት ከታጨች በኋላ ሌላ ወንድ መፈለግ የለባትም፤ ሌላም ወንድ እንዲፈልጋት የሚያደርግ ሥራ መሥራት የለባትም። ቤተክርስቲያን መስቀሉን ከክርስቶስ በምልክትነት ከተቀበለች በኋላ ሌላ ነገር አትፈልግም። መስቀል የሕይወቷ ዓርማ አድርጋ ስትታወቅበት ትኖራለች እንጂ። መስቀል በምድር ያለችው ቤተ ክርስቲያን የሚደርስባትን መከራ የሚያመለክት ነው። መከራ ደግሞ የክርስትና ሕይወት መልክ ነው። ብዙዎቻችን የዚህ መሠረታዊ ሐሳብ ተቃራኒ የኾነ ሕይወት ነው ያለን። ከክርስቶስ መከራ ይልቅ የዘፋኞች ዘፈን ልባችንን የማረከብን፤ ከክርስቶስ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ይልቅ የዚህ ዓለም ተራ መብልና መጠጥ የሚያረካን ከክርስትናው እውነተኛ መንገድ እጅግ የራቅን ነን። ስለዚህ ምልክቱን ስንተው አጋንንትም መጥተው አደሩብንና ከሙሽራው ፈቃድ ለዩን።
ምልክት የተባለው በቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳርያ “የክርስቶስ ደም" ነው ይላል። በእርግጥ ይህን ደም ምልክት አድርገን የምንኖር ከኾነ ጠላት ድል ያደርገን ዘንድ አይችልም። መስቀል ደግሞ በዚህ ትርጒም የምልክት ምልክት ነው። የክርስቶስ ደም የፈሰሰበት የሕይወት ዕፀ ነውና። በመስቀል ላይ የተቆረሰውን የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋ የፈሰሰውን ክቡር ደም እናይበታለን። መስቀሉን ስንስም የምንስመው ዕፅነቱን ብቻ አይደለም ይልቅስ በዚያ ላይ ከሞት የሚያድነን ንጹሕ የክርስቶስን ደም ነው። ስለዚህ በመስቀል ዐይንነት ክርስቶስን እናየዋለን። በምልክቱ በኩል ምልክቱን የሰጠንን አምላክ ደሙን ሲያፈስልን ተመልክተን ፍቅሩን እናደንቃለን።
“ለሚፈሩት ምልክትን ሰጠሃቸው" የተባለውን ብዙ ሊቃውንት የእስራኤላውያን በኲር በግብጽ ምድር የተረፈበትን የፋሲካውን በግ ደም ነው ይላሉ። ያ ምንም የማያውቀው በግ ደሙ በቤቱ ጉበን ላይ በመቀባቱ ምክንያት የእስራኤል በኩራት ከዳኑ ሕያው በግ ክርስቶስ ቤት አድርጎ በቀራኒዮ በገባበት መስቀል ላይ ባፈሰሰው የሚናገር ደም'ማ እንዴት የበለጠ ድኅነት ይገኝ ይኾን? በኩራችን ክርስቶስን ከልባችን ውስጥ ለማጥፋት የሚተጉትን ክፉ አስተሳሰቦች በሙሉ እንዋጋቸው። ኹል ጊዜም ነገረ መስቀሉን ምልክት አድርገን የአጋንንትን ሐሳብ እናርቅ፤ በእግዚአብሔር ቃልም መሠረት ሳንሠቀቅ መከራ መስቀሉን ለመሸከም እንትጋ። የእውነት መኖር ከጀመርን ሕይወታችን በራሱ የመስቀል ሕይወት ይኾናል፤ ብዙ ግራ የተጋቡ ሰዎችንም የመሰቀል ሕይወትን ጣዕም አቅምሰን ከስሕተታቸው መመለስ እንችላለን። በመኾኑም ምልክታችንን ከጥልቅ ውስጣችን ሕያው አጥር አበጅተን መጠበቅ አለብን።
📝ዲ/ን ዮሐንስ ጌታቸው