የትንቢት ድምፅ

@voiceofprophecy


እግዚአብሔር ምን አለ? እርሱ የሚናገረው እውነት ነው። ቃሉን በዚህ ገጽ ይከታተሉ። የኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል ሐዋርያት እንደሰበኩት እናቀርብላችኋለን።

የትንቢት ድምፅ

21 Oct, 19:04


ራሳችንን ብንመረምር ባልተፈረደብን ነበር

ክርስቲያን ንስሐ መግባት አያስፈልገውም ወይም ንስሐ አይገባም የሚል የተሳሳተ ትምህርት አለ።

ሰው አንዴ በክርስቶስ በማመን ከጸደቀ ወዲህ እንደገና ንስሐ ይገባል ማለት ጸድቆ የነበረውን መልሶ ኃጢአተኛ ማድረግ (እንደ ኃጢአተኛ መቁጠር) ነው የሚል ነው ምክንያታቸው።

ነገር ግን፣ ሁለት የንስሐ ዓይነቶች አሉ።

የመጀመሪያው ንስሐ፣ ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት የታረቅንበት (ሮሜ.5፥10)፥ ከሰይጣን አገዛዝ ወደ እግዚአብሔር የዞርንበት፥ ከእግዚአብሔርም ጋር በክርስቶስ ደም አማካኝነት ኪዳን ያደረግንበት ነው።

ጌታ ኢየሱስ ጳውሎስን ሐዋርያ አድርጎ ወደ አሕዛብ የሚልክበትን ምክንያት ሲገልፅለት “የኃጢአትን ስርየት በእኔም በማመን በተቀደሱት መካከል ርስትን ያገኙ ዘንድ፥ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሰይጣንም ሥልጣን ወደ እግዚአብሔር ዘወር እንዲሉ” አለው (ሐዋ.26፥17-18)።

ይህ የንስሐ ጥሪ ለሰዎች ሁሉ የቀረበ ነው።

“... እግዚአብሔር ያለማወቅን ወራት አሳልፎ አሁን በየቦታቸው ንስሐ ይገቡ ዘንድ ሰውን ሁሉ ያዛል፤ ቀን ቀጥሮአልና፥ በዚያም ቀን ባዘጋጀው ሰው እጅ በዓለሙ ላይ በጽድቅ ሊፈርድ አለው፤ ስለዚህም እርሱን ከሙታን በማስነሣቱ ሁሉን አረጋግጦአል።” (ሐዋ.17፥30-31)

ይኼኛው ንስሐ አንዴ ነው። ሰው አንዴ በክርስቶስ ከሆነ በኋላ በፈረቃ አንዴ በክርስቶስ አንዴ በዓለም መሆን አይችልም።

ነገር ግን፣ ሰው በክርስቶስ ሳለ ኃጢአትን ቢያደርግ ወይም ለክርስቲያን የማይገባ ኑሮ የሚኖር ከሆነ መታረም አለበት። ሁለተኛው የንስሐ ዓይነት እሱ ነው። ይኼኛው ንስሐ የሚደረገው አንድ ጊዜ ብቻ አይደለም። ስላደረግነው ነገር የእግዚአብሔር ቃልና መንፈስ ቅዱስ በሚገስጹን ሕሊናችንም በሚወቅሰን ነገር ሁሉ በማንኛውም ጊዜ ንስሐ መግባት ይኖርብናል።

እዚህ ላይ መረሳት የሌለበት፣ ንስሐ ጸሎት አይደለም። ንስሐ ከተሳሳተ አካሄድ መመለስ ስሕተትን ማረም ነው። “... ንስሐ ግቡ ኃጢአትም ዕንቅፋት እንዳይሆንባችሁ ከኃጢአታችሁ ሁሉ ተመለሱ” ነው የሚለው (ሕዝ.18፥30)።

ንስሐ፣ ሰው በሕሊናው ተወቅሶ ስሕተቱን አምኖ ክፉ ሥራውን ለመተው ሲወስን ነው እንጂ እንዲሁ “እኔ ኃጢአተኛ ነኝ፤ ማረኝ” እያሉ መጸለይን ልማድ ማድረግ አይደለም።

በእርግጥ የንስሐ ጸሎት አለ፤ ሰው ኃጢአቱን ለእግዚአብሔር የሚናዘዝበትና ምሕረትን የሚለምንበት። ነገር ግን፣ ከክፉ ሥራው መመለሱ እንጂ ጸሎቱ አይደለም ንስሐ።

ስለዚህ ንስሐ በግልፅ የሚታይ ተጨባጭ ፍሬ ያለው ነው፤ ምናባዊ አይደለም። ስለ ነነዌ ሰዎች ንስሐ ሲናገር “እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸው እንደተመለሱ ሥራቸውን አየ” ይላል (ዮና.3፥10)።

አንድ ክርስቲያን ንስሐ ያስፈልገዋል ማለት ክርስትናው ተሽሯል በክርስቶስ ያለውን ማንነት አጥቷል ማለት አይደለም። ነገር ግን፣ ዓላማውን ስቷል፥ ስለዚህ አካሄዱን ማስተካከል አለበት ማለት ነው።

እግዚአብሔር ያለ ሥራ በጸጋው አድኖናል ማለት ኃጢአት እንድንሠራ ተፈቅዶልናል ማለት አይደለም። ጸጋው ከኵነኔ ነው ነጻ ያወጣን፤ ጽድቅን ከማድረግ ግዴታ ነጻ አላደረገንም። ይልቁን ጽድቅን ማድረግ የተፈጠርንበት ዓላማ እና በምድር እንድንፈጽመው የተሰጠን ተልእኮአችን ነው። “እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን” ነው የሚለው (ኤፌ.2፥10)።

ደግሞም “ሰዎችን ሁሉ የሚያድን የእግዚአብሔር ጸጋ ተገልጦአል፤ ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል” ይላል (ቲቶ.2፥11-14)።

ክርስቲያን ከዚህ ዓላማ አንፃር ነው አካሄዱን መመርመርና መንገዱን ስቶ ሲገኝ መታረም ያለበት። ክርስቲያን ንስሐ አያስፈልገውም ከተባለ ግን ቢሳሳትም አይታረምም ማለት ነው። ይህ ትክክል እንዳልሆነ ግልጥ ነው።

በአዲስ ኪዳን በብዙ ስፍራ ለቤተክርስቲያንና ለምዕመናን ንስሐ እንዲገቡ የእግዚአብሔር ቃል ይናገራል። ይህም ንስሐ ላልዳኑ ሰዎች ብቻ እንዳልሆነ ነው የሚያሳየው።

ለምሳሌ፣ ሲሞን በፊት ጠንቋይ የነበረ ኋላ ግን በሐዋርያው ፊልጶስ ስብከት በጌታ አምኖ የተጠመቀ አዲስ ክርስቲያን ነበረ። ነገር ግን የእግዚአብሔርን ጸጋ ከሐዋርያት በገንዘብ ለመግዛት በፈለገ ጊዜ ሐዋርያው ጴጥሮስ “የእግዚአብሔርን ስጦታ በገንዘብ እንድታገኝ አስበሃልና ብርህ ከአንተ ጋር ይጥፋ። ልብህ በእግዚአብሔር ፊት የቀና አይደለምና ከዚህ ነገር ዕድል ወይም ፈንታ የለህም” አለውና ንስሐ እንዲገባ መከረው። “እንግዲህ ስለዚህ ክፋትህ ንስሐ ግባ፥ ምናልባትም የልብህን አሳብ ይቅር ይልህ እንደ ሆነ ወደ እግዚአብሔር ለምን፤ በመራራ መርዝና በዓመፅ እስራት እንዳለህ አይሃለሁና” አለው (ሐዋ.8፥20-23)። ይህ ለክርስቲያን የተነገረ ቃል መሆኑን እናስተውል።

በዮሐንስ ራእይ ደግሞ ከሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት አምስቱን ጌታ ንስሐ እንዲገቡ ሲያስጠነቅቃቸው እናያለን (ራእ.2-3)።

በመሆኑም ክርስቲያን ንስሐ መግባት አያስፈልገውም የሚለው ትምህርት ምዕመኑን ይጎዳዋል። ምክንያቱም፣ እግዚአብሔር ሥራችንን ሁሉ ወደ ፍርድ ማምጣቱ አይቀርም።

“አትሳቱ፤ እግዚአብሔር አይዘበትበትም። ሰው የሚዘራውን ሁሉ ያንኑ ደግሞ ያጭዳልና፤ በገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና፥ በመንፈስ ግን የሚዘራው ከመንፈስ የዘላለምን ሕይወት ያጭዳል።” (ገላ.6፥7-8)

ራስን መመርመርና ማረም ይጠቅማል፤ “እንደ ቆመ የሚመስለው እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ” (1ቆሮ.10፥12)፣ ደግሞም “ራሳችንን ብንመረምር ግን ባልተፈረደብን ነበር” ይላል (1ቆሮ.11፥31)።

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

10 Oct, 21:08


[10] ኢየሱስ ክርስቶስ በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ በይፋ ዳግመኛ ይመጣል።

የዘላለም ፍርድ ከክርስትና መሠረታዊ እምነቶች አንዱ ነው (ዕብ.6፥2)። ይህም እግዚአብሔር በሕይወት ዘመናችን የሠራነውን ሁሉ ወደ ፍርድ የሚያመጣው መሆኑና እያንዳንዳችን ላደረግነው ነገር ሁሉ ተጠያቂ መሆናችን ነው። “... እያንዳንዳችን ስለ ራሳችን ለእግዚአብሔር መልስ እንሰጣለን።” (ሮሜ.14፥12) ስለተናገርነው ነገር ጭምር እንጂ ስላደረግነው ነገር ብቻ አይደለም። ጌታ ኢየሱስ “... ሰዎች ስለሚናገሩት ስለ ከንቱ ነገር ሁሉ በፍርድ ቀን መልስ ይሰጡበታል” ይላል (ማቴ.12፥36)። ይህን ያወቀ አፉ እንዳመጣለት አይናገርም።

የሚፈርደው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ዳግመኛ ሲመጣ ሙታን ተነሥተው በሕይወት ካሉት ጋር ከእርሱ ፍርድን ይቀበላሉ። “የሰው ልጅ በአባቱ ክብር ከመላእክት ጋር ይመጣል፤ ለእያንዳንዱም ሰው እንደ ሥራው ዋጋውን ይከፍለዋል።” (ማቴ.16፥27/አ.መ.ት.)

ክርስቶስ ዳግመኛ የሚመጣው በይፋ መሆኑ ይሰመርበት። ዳግመኛ መምጣቱ እንደ ልደቱ አይሆንም። ክርስቶስ መወለዱ ለጥቂቶች ማለትም ከምሥራቅ ለመጡት ጠቢባን፣ ለእረኞችና ለተመረጡ ቅዱሳን ብቻ ነበር የተገለጠላቸው። ለሕዝብ ሲገለጥም እርሱ ክርስቶስ መሆኑን ያወቁና ያመኑ ውሱን ነበሩ።

ዳግመኛ ሲመጣ ግን ፀሐይ በሰማይ ላይ ስታበራ ለዓለም ሁሉ እንደምትታይ ሰዎች ሁሉ ያዩታል። በመላእክት አጀብ በብዙ ክብር ስለሚመጣ ጌትነቱን የማያይ አይኖርም፤ ተቃዋሚዎቹ ሳይቀሩ። “እነሆ፥ ከደመና ጋር ይመጣል፤ ዓይንም ሁሉ የወጉትም ያዩታል፥ የምድርም ወገኖች ሁሉ ስለ እርሱ ዋይ ዋይ ይላሉ ...” ይላል (ራእ.1፥7)። በዚህም ምክንያት ዳግም ምጽአቱ “የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ክብር መገለጥ” ተብሏል (ቲቶ.2፥13)።

ክርስቶስ በማይታይ ሁኔታ ከዚህ በፊት ዳግመኛ መጥቷል የሚሉ ሐሰተኛ ትምህርቶችና ሃይማኖቶች ስላሉ ዳግመኛ መምጣቱ በይፋ እንደሚሆን ማወቅ ምዕመኑን ከስሕተት ይጠብቀዋል።

[11] ሰው ሁሉ ኃጢአተኛና ራሱን ማዳን የማይችል ነው።

ሰው አስቀድሞ ኃጢአተኛና ከእግዚአብሔር ፍርድ በታች የሚገኝ፥ ከዚያም ፍርድ በክርስቶስ ቤዛነት አማካኝነት ነጻ መውጣት የሚያስፈልገው ነው። “ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል።” (ሮሜ.3፥23)

ሰው ኃጢአተኛና ራሱን ማዳን የማይችል በመሆኑ ነው ክርስቶስ እንዲቤዠው ግድ የሆነው። ሰው ኃጢአት ባይኖርበት ወይም ደግሞ በነፍሱ ምትክ ሊከፍለው የሚችለው ዋጋ ቢኖረው ኖሮ ክርስቶስ መሠዋቱ ባላስፈለገ ነበር።

ሰው ኃጢአተኛ መሆኑን የማይቀበል ትምህርት ሁሉ የክርስቶስን መሠዋት ርካሽና አላስፈላጊ እንደሆነ አድርጎ ይቆጥራል። “... ጽድቅ በሕግ በኩል ከሆነ እንኪያስ ክርስቶስ በከንቱ ሞተ” ይላል (ገላ.2፥21)።

[12] ድነት የእግዚአብሔር ጸጋ ነው።

“ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል” ካለ በኋላ መፍትሔውን ሲያስቀምጥ “በኢየሱስ ክርስቶስም በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ” ይላል (ሮሜ.3፥23-24)።

ለሰው ያልተቻለውን ጽድቅ እግዚአብሔር በክርስቶስ አማካኝነት ፈጽሞታል። “ከሥጋ የተነሣ ስለ ደከመ ለሕግ ያልተቻለውን፥ እግዚአብሔር የገዛ ልጁን በኃጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ በኃጢአትም ምክንያት ልኮ አድርጎአል” (ሮሜ.8፥3)።

“ጸጋ” ማለት ስጦታ ነው። ድነትን በሥራችን እንዳላገኘነው ያመለክታል። “ጸጋው በእምነት አድኖአችኋል፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም” ይላል (ኤፌ.2፥8-9)።

[13] መዳን በእምነት ነው።

ሰው ይህን ድነት ወይም የእግዚአብሔርን የዘላለም ሕይወት ስጦታ የሚቀበለው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ነው።

“እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።” (ዮሐ.6፥47)

ቃሉን ሰምቶ በክርስቶስ የማያምን ግን ይፈረድበታል።

“በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል።” (ዮሐ.3፥18)

“ያመነ የተጠመቀም ይድናል፥ ያላመነ ግን ይፈረድበታል።” (ማር.16፥16)

[14] የኃጢአት ስርየት የሚገኘው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ነው።

“በእርሱ የሚያምን ሁሉ በስሙ የኃጢአቱን ስርየት እንዲቀበል ነቢያት ሁሉ ይመሰክሩለታል።” (ሐዋ.10፥43)

[15] አማኞች ዓለማዊነትን ክደው በጽድቅ በቅድናና እግዚአብሔርን በመፍራት ሊኖሩ ይገባል።

[16] ጋብቻ ወንድ ከሴት ጋር ብቻ ነው። የተመሣሣይ ጾታ የሥጋ ግንኙነት ዝሙት ነው።

[17] መጽሐፍ ቅዱስ፣ በእግዚአብሔር መንፈስ የተጻፈ፥ የእግዚአብሔር ቃል፥ የአስተምህሮና የልምምድ ሁሉ የበላይ ባለ ሥልጣንና መመዘኛ ነው።

በቀጣይ፣ ጌታ ቢፈቅድ፥ እዚህ ያልተብራሩትን ነጥቦች በዝርዝር እናያለን።

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

10 Oct, 21:06


የክርስትና መሠረታዊ እምነቶች

[1] እግዚአብሔር አንድ ነው። እውነተኛ አምላክ እግዚአብሔር ብቻ ነው።

ጌታ ኢየሱስ፦ “እኔና አብ አንድ ነን።” (ዮሐ.10፥30)

እንዲሁም፦ “እስራኤል ሆይ፥ ስማ፤ አምላካችን እግዚአብሔር አንድ እግዚአብሔር ነው።” (ዘዳ.6፥4)

አምላካችን እግዚአብሔር ብቻ ነው ማለት ነው። ይህም “... እግዚአብሔር አምላክህ እኔ ነኝ። ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ” ከሚለው ጋር ይስማማል (ዘጸ.20፥2-3)።

“አማልክት” ተብለው የሚጠሩ ብዙዎች በዓለም ቢኖሩም እውነተኛ አምላክ እግዚአብሔር ብቻ ነው።

“ብቻህን እውነተኛ አምላክ የሆንህ አንተን የላክኸውንም ኢየሱስ ክርስቶስን ያውቁ ዘንድ ይህች የዘላለም ሕይወት ናት።” (ዮሐ.17፥3)

[2] እግዚአብሔር በሦስት አካላት፥ ይኸውም በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ፥ ይኖራል።

[3] ኢየሱስ፥ ክርስቶስ እና የእግዚአብሔር ልጅ ነው፤ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ነው የተፀነሰው፤ በጾታዊ ግንኙነት አይደለም።

እግዚአብሔር ለአብርሃም “የምድር ሕዝቦች ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ” ብሎ የሰጠው ተስፋ (ዘፍ.22፥18) እና በቅዱሳን ነቢያቱ በኩል ለእስራኤልና ለዓለም የቀባውን መድኃኒት ሊልክላቸው የሰጠው ተስፋ ኢየሱስ ነው። “ክርስቶስ” የግሪክ ቃል ሲሆን ትርጉሙ “የተቀባው” ማለት ነው።

የወንጌል ዓላማ ይህን ለሰዎች መግለጥ ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ ወንጌሉን የጻፈበትን ዓላማ ሲገልጽ “... ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ ታምኑ ዘንድ፥ አምናችሁም በስሙ ሕይወት ይሆንላችሁ ዘንድ ይህ ተጽፎአል” ይላል (ዮሐ.20፥31)።

እርሱም በጾታዊ ግንኙነት ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የተፀነሰ ነው።

መልአኩ ገብርኤል እናቱን ማርያምን ኢየሱስን እንደምትወልድ እንዲህ ሲል ነበር ያበሰራት፦ “መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፥ የልዑልም ኃይል ይጸልልሻል ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል።” (ሉቃ.1፥35)

[4] ኢየሱስ ክርስቶስ መለኮት (እግዚአብሔር) እና እውነተኛ ሰው ነው።

ክርስቶስ፥ ሕልውናው በእናቱ ማህፀን ሲፀነስ አልጀመረም። መፀነሱ፥ “ቃል ሥጋ ሆነ” እንደሚል ሰው የመሆኑ ጅማሬ ነው እንጂ የመኖሩ ጅማሬ አይደለም።

አይሁድ “ገና አምሳ ዓመት ያልሆነህ አብርሃምን አይተሃልን?” ባሉት ጊዜ ጌታ ኢየሱስ “አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ” አላቸው (ዮሐ.8፥57-58)፤ ምክንያቱም፥ ሰው ሆኖ ሳይወለድ በፊት፥ ዓለምም ሳይፈጠር፥ እርሱ ከእግዚአብሔር (ከአብ) ጋር መለኮት ነው። “በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር (በአብ) ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር (መለኮት) ነበረ።” (ዮሐ.1፥1)

ሲቀጥል “ሁሉ በእርሱ ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም” ይላል (ዮሐ.1፥3)። ከእግዚአብሔር (ከአብ) ጋር አብሮ ፈጣሪ መሆኑን ያሳያል። ስለ ኃጢአታችን ለመሞት በሥጋ የተገለጠው ይኸው ነው። “ቃልም ሥጋ (ሰው) ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን” ይላል (ዮሐ.1፥14)።

በሌላም ስፍራ እንዲህ ይላል፦

“እርሱ በባሕርዩ አምላክ ሆኖ ሳለ፣ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን ሊለቅቀው እንደማይገባ አድርጎ አልቈጠረውም፤ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ፣ በሰውም አምሳል ተገኝቶ፣ ራሱን ባዶ አደረገ፤ ሰው ሆኖ ተገልጦም፣ ራሱን ዝቅ አደረገ፤ እስከ ሞት፣ ያውም በመስቀል ላይ እስከ መሞት ድረስ ታዛዥ ሆነ።” (ፊልጲ.2፥6-8/አ.መ.ት.)

[5] ኢየሱስ ክርስቶስ ኃጢአት የለበትም።

“እርሱ ኃጢአትን ሊያስወግድ እንደ ተገለጠ ታውቃላችሁ፥ በእርሱም ኃጢአት የለም።” (1ዮሐ.3፥5)

[6] ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን ሞቷል፤ ከሞትም ተነሥቷል።

“... መጽሐፍ እንደሚል ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን ሞተ፥ ተቀበረም፥ መጽሐፍም እንደሚል በሦስተኛው ቀን ተነሣ።” (1ቆሮ.15፥3-4)

ይህ የክርስትና መሠረት ነው። ሐዋርያው እንዲህ ይላል፦

“ክርስቶስም ካልተነሣ እንግዲያስ ስብከታችን ከንቱ ነው እምነታችሁም ደግሞ ከንቱ ናት፤ ... ክርስቶስም ካልተነሣ እምነታችሁ ከንቱ ናት፤ እስከ አሁን ድረስ በኃጢአታችሁ አላችሁ።” (1ቆሮ.15፥14-17)

[7] በክርስቶስ ሞት የምትክነት አስተስርዮ (Substitutionary Atonement) ተደርጎልናል።

“ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን ሞተ” ማለት ምንም ግልጥ ቢሆን ትርጉሙን የሚያድበሰብሱ ትምህርቶች ስላሉ እውነቱን በአጽንዖት መናገር ያስፈልጋል።

አንዳንዶች እንደሚሉት ክርስቶስ የጽድቅን መንገድ ሊያሳየን በአርአያነት ብቻ አይደለም የሞተው።

ክርስቶስ ጻድቅ ሆኖ ሳለ በእግዚአብሔር ፈቃድ መከራን ሲቀበል በመታገሡ እኛም ያለ ጥፋታችን ስንገፋና መከራን ስንቀበል እንድንታገሥ ምሳሌ ትቶልን ማለፉ እውነት ቢሆንም የሞተው ምሳሌ ሊሆነን ብቻ ነው ማለት አይደለም።

ቃሉ በግልጥ እንደሚናገር ክርስቶስ ኃጢአታችንን ተሸክሞ በእኛ ፈንታ ሆኖ ነው የሞተው። ይህም “ደዌያችንን ተቀበለ”፣ “እግዚአብሔር የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ”፣ “ኃጢአታችንን ተሸከመ” ወዘተ. በሚሉ የማያሻሙ ቃሎች ተገልጾአል።

“በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ ሕመማችንንም ተሸክሞአል፤ ... ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ፤ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን። እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፤ እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ።” (ኢሳ.53፥4-6)

“ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ። በመገረፉ ቁስል ተፈወሳችሁ። ...” (1ጴጥ.2፥24-25)

እኛ ጽድቅ እንዲቆጠርልን፥ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኝ የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው (ሮሜ.3፥22)፥ ክርስቶስ በእኛ ምትክ እንደ ዓመፀኛ ተቆጥሯል ማለት ነው።

“... ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ሰጥቶአል፥ ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአል፤ እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ።” (ኢሳ.53፥12)

“እኛ በእርሱ ሆነን የእግዚአብሔር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ኃጢአት ያላወቀውን እርሱን ስለ እኛ ኃጢአት አደረገው።” (2ቆሮ.5፥21)

[8] ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሰማይ ዐርጓል።

[9] ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማያት ሊቀ ካህናት፣ የአዲስ ኪዳን መካከለኛ፣ አማላጅ፣ አስታራቂና ጠበቃችን ነው።

የትንቢት ድምፅ

26 Sep, 18:19


እግዚአብሔርን ያለመስማት አደጋ

መስማት የሚያስፈልገንን ሳይሆን መስማት የምንፈልገውን ብቻ እየመረጥን የምንሰማ ከሆንን፥ ስንስት እግዚአብሔር ሲገሥጸን አንሰማም፤ ከጥፋትም ራሳችንን አናድንም። ከእግዚአብሔር ቃል የሚጣል አንዳች የለም። “የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል።” (2ጢሞ.3፥16-17)

የእግዚአብሔር ቃል ሁልጊዜ የምሥራች ብቻ ይዞልን አይመጣም፤ ለደከመው እንዲበረታ ተስፋን፥ ላዘነው መጽናናትን፥ ለሳተው እንዲመለስ ተግሣጽን ይናገራል እንጂ።

በራእይ መጽሐፍ ውስጥ ጌታ ኢየሱስ ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያን ከሚናገረው ቃል ይህን እናያለን። የኤፌሶንን ቤተክርስቲያን “ከወዴት እንደ ወደቅህ አስብ ንስሐም ግባ የቀደመውንም ሥራህን አድርግ” ሲል (ራእ.2፥5) የፊልድልፍያን ቤተክርስቲያን ግን “እነሆ፥ በአንተ ፊት የተከፈተ በር ሰጥቼአለሁ ማንምም ሊዘጋው አይችልም፤ ኃይልህ ምንም ትንሽ ቢሆን ቃሌን ጠብቀሃልና፥ ስሜንም አልካድህምና” ይላል (ራእ.3፥8)።

እያንዳንዱን እንደ ሥራው የሚገባውን ይናገረዋል እንጂ ሁሉንም አያመሰግናቸውም ወይም ሁሉንም አይነቅፋቸውም። መነቀፍ ያለበትን ይነቅፈዋል፤ ምስጋና የሚገባውን ያመሰግነዋል። ለፊልድልፍያ ቤተክርስቲያን መጣላትን ቃል ብንወድም የሚያስፈልገን ለኤፌሶን ቤተክርስቲያን የተነገረው ቃል ሊሆን ይችላል፤ እንደ ሁኔታችን፤ እልል የሚያስብል ባይሆንም። ለፊልድልፍያ ቤተክርስቲያን መጣላት ቃል ያለ ምክንያት አልነበረም፤ “ኃይልህ ምንም ትንሽ ቢሆን ቃሌን ጠብቀሃልና፥ ስሜንም አልካድህምና” በሚል ምክንያት ነው።

እግዚአብሔር ሲገሥጸን እየተጣላን አይደለም። የሚወዳቸውን ነው ከጥፋት እንዲጠበቁ የሚገሥጻቸው። “እኔ የምወዳቸውን ሁሉ እገሥጻቸዋለሁ እቀጣቸውማለሁ፤ እንግዲህ ቅና ንስሐም ግባ” ነው የሚለው (ራእ.3፥19)። ንስሐንም የሚሰጥ እግዚአብሔር ራሱ ነው። “... እግዚአብሔር እውነትን ያውቁ ዘንድ ንስሐን ይሰጣቸዋልና ፈቃዱን ለማድረግ በዲያብሎስ ሕያዋን ሆነው ከተያዙበት ወጥመድ ወጥተው፥ ወደ አእምሮ ይመለሳሉ ...” ይላል (2ጢሞ.2፥25-26)።

ዓመፀኞች ግን ለስሕተት አልፈው ይሰጣሉ። “... በእውነት ያላመኑ ነገር ግን በዓመፅ ደስ ይላቸው የነበሩ ሁሉ ፍርድን እንዲቀበሉ፥ ሐሰትን ያምኑ ዘንድ እግዚአብሔር የስሕተትን አሠራር ይልክባቸዋል።” (2ተሰ.2፥11-12) ደግሞም “እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው” ይላል (ሮሜ.1፥28)። እግዚአብሔርን ያለመስማት አደጋ እሱ ነው።

የእስራኤል ንጉሥ አክዓብ እንዲህ ያደርግ ነበር። በእግዚአብሔር ፊት ክፉ እያደረገ መልካም የሚናገሩለትን ነቢያት ለራሱ ሰብስቦ ነበር። ይገሥጸውና የእግዚአብሔርን ቃል በግልጥ ይናገር ስለነበር ነቢዩን ሚክያስን ግን ይጠላው ነበር። “ክፉ እንጂ መልካም ትንቢት አይናገርልኝምና እጠላዋለሁ” አለ። ንጉሡ ሶርያውያንን ሊዋጋ ሲሄድ ነቢያቱ “እግዚአብሔር ድል ይሰጥሃል፤ ሂድ!” አሉት። ንጉሡ ግን በጦር ሜዳ ተወግቶ ሞተ። እውነትን ለመስማት ስላልፈለገ በሐሰተኛ ትንቢት ለሞት አልፎ እንዲሰጥ ተወስኖበት ነበር (1ነገ.22፥1-40)።

ጥበብ እንዲህ ትላለች፦ “እውቀትን ጠልተዋልና፥ እግዚአብሔርንም መፍራት አልመረጡምና፤ ምክሬን አልፈቀዱምና፥ ዘለፋዬንም ሁሉ ንቀዋልና፤ ስለዚህ የመንገዳቸውን ፍሬ ይበላሉ፥ ከራሳቸው ምክር ይጠግባሉ። አላዋቂዎችን ከጥበብ መራቅ ይገድላቸዋልና፥ ሰነፎችንም ቸልተኛ መሆን ያጠፋቸዋልና። የሚሰማኝ ግን በእርጋታ ይቀመጣል፥ ከመከራም ሥጋት ያርፋል።” (ምሳ.1፥29-33)

ደግሞም “ተግሣጽን ቸል የሚል የራሱን ነፍስ ይንቃል፤ ዘለፋን የሚሰማ ግን አእምሮ ያገኛል” ይላል (ምሳ.15፥32)።

እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ይናገራል እንጂ ሰውን ደስ ለማሰኘት አይደለም (ዮሐ.3፥34)። መምከርና መገሠጽም ሥራው ነው። “በእግዚአብሔር ፊት በሕያዋንና በሙታንም ሊፈርድ ባለው በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ፊት፥ በመገለጡና በመንግሥቱም እመክርሃለሁ፤ ቃሉን ስበክ፥ በጊዜውም አለጊዜውም ጽና፥ ፈጽመህ እየታገሥህና እያስተማርህ፥ ዝለፍና ገሥጽ ምከርም” ይላል (2ጢሞ.4፥1-2)።

ከዚያ ሲቀጥል ተግሣጽን ስለሚጠላ ትውልድ ነው የሚናገረው፦ “ሕይወት የሚገኝበትን ትምህርት የማይታገሡበት ዘመን ይመጣልና፤ ነገር ግን ጆሮቻቸውን የሚያሳክክ ስለ ሆነ፥ እንደ ገዛ ምኞታቸው ለራሳቸው አስተማሪዎችን ያከማቻሉ። እውነትንም ከመስማት ጆሮቻቸውን ይመልሳሉ፥ ወደ ተረትም ፈቀቅ ይላሉ።” (2ጢሞ.4፥3-4) ይህ አይሁንብን።

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

07 Sep, 20:04


... እንግዲህ ንቁ!

“የአሥሩ ቆነጃጅት ምሳሌ በታላቁ መከራ ውስጥ የሚያልፉትን እንጂ እኛን አይመለከትም፤ እኛ ከአስተዋዮቹም ከዝንጉዎቹም ውስጥ የለንበትም” የሚለው ትምህርት ትክክል አይደለም።

ምሳሌው፤ ጌታ የሚመጣበትን ጊዜ ስለማያውቁ ሁልጊዜ ተዘጋጅተው ሊኖሩ እንደሚገባ ሲያስተምራቸው ለደቀ መዛሙርቱ ከነገራቸው ሦስት ምሳሌዎች አንዱ ነው። የሦስቱም ምሳሌዎች መልእክት አንድ ሲሆን “ጌታችሁ በምን ሰዓት እንዲመጣ አታውቁምና እንግዲህ ንቁ። ያን ግን እወቁ፤ ባለቤት ከሌሊቱ በየትኛው ክፍል ሌባ እንዲመጣ ቢያውቅ ኖሮ፥ በነቃ ቤቱም ሊቈፈር ባልተወም ነበር። ስለዚህ እናንተ ደግሞ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፥ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና” የሚል ነው (ማቴ.24፥42-44)።

ከሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ጋር በማስተያየት ይህ ምክር በታላቁ መከራ ውስጥ ለሚያልፉ ለእስራኤልና ለአሕዛብ ብቻ የተሰጠ እንዳልሆነ መረዳት ይቻላል።

ድንገት የሚሆን ነገር ያልተዘጋጁበትና ያልጠበቁት ነገር ነው። እንዲሁም የጌታ መምጣት ድንገት የሚሆንባቸው ያልተዘጋጁት ናቸው፤ አማኞችም ቢሆኑ፤ ካልተዘጋጁ። ለምሳሌ፣ ጌታ ለሰርዴስ ቤተክርስቲያን እንደ ሌባ በድንገት እንደሚመጣ ሲናገር በራእይ መጽሐፍ ውስጥ እናያለን። በአጭሩ “... የነቃህ ሁን ... ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ” ነው የሚለው። እንዲህ ይላል፦

“ሥራህን በአምላኬ ፊት ፍጹም ሆኖ አላገኘሁትምና የነቃህ ሁን፥ ሊሞቱም ያላቸውን የቀሩትን ነገሮች አጽና። እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ። እንግዲያስ ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ በማናቸውም ሰዓት እንድመጣብህ ከቶ አታውቅም።” (ራእ.3፥2-3)

ታዲያ “ይህ እኛን አይመለከትም” እንዴት ይባላል? ቃሉ ጌታ ራሱ በቀጥታ ለቤተክርስቲያን የተናገረው እንደሆነ እያወቅን? ጸጋውን ብቻ ወደን ኃላፊነት ጠል እንዳንሆን። ጌታ እንድንሠራ ሥራ ሰጥቶን ከሆነ የሰጠንን ሥራ እንድንፈጽም ከእኛ ይጠብቃል።

“ቤቱን ትቶ ወደ ሌላ አገር እንደ ሄደ ሰው ነው፥ ለባሮቹም ሥልጣን ለእያንዳንዱም ሥራውን ሰጥቶ በረኛውን እንዲተጋ አዘዘ። እንግዲህ በማታ ቢሆን ወይም በእኩለ ሌሊት ወይም ዶሮ ሲጮኽ ወይም በማለዳ ቢሆን ባለቤቱ መቼ እንዲመጣ አታውቁምና ድንገት መጥቶ ተኝታችሁ እንዳያገኛችሁ ስለዚህ ትጉ። ለእናንተም የምነግራችሁ ለሁሉ እላለሁ፤ ትጉ።” (ማር.13፥34-37)

የእግዚአብሔርንና የእኛን ድርሻ ማወቅ ይኖርብናል። በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ የእኛን ትጋት የሚጠይቁ ኃላፊነት የምንወስድባቸውና በፍርድ ቀን ተጠያቂ የምንሆንባቸው ሥራዎች እንዳሉን መዘንጋት የለብንም። ጸጋን የሚሰጥ እግዚአብሔር ነው። በተሰጠን ጸጋ ማገልገል ደግሞ የእኛ ኃላፊነት ነው። “ከእግዚአብሔር ጋር አብረን የምንሠራ እንደ መሆናችን መጠን፣ የተቀበላችሁትን የእግዚአብሔርን ጸጋ ከንቱ እንዳታደርጉት አደራ እንላችኋለን” ይላል (2ቆሮ.6፥1)። ጌታ ሲመጣ ቆጥሮ የሰጠንን ሥራ ለመፈጸም ስንተጋ ሊያገኘን ይፈልጋል። እንዲህ ይላል፦

“እንኪያስ ምግባቸውን በጊዜው ይሰጣቸው ዘንድ ጌታው በቤተ ሰዎች ላይ የሾመው ታማኝና ልባም ባሪያ ማን ነው ጌታው መጥቶ እንዲህ ሲያደርግ የሚያገኘው ያ ባሪያ ብፁዕ ነው፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ባለው ሁሉ ላይ ይሾመዋል። ያ ክፉ ባሪያ ግን። ጌታዬ እስኪመጣ ይዘገያል ብሎ በልቡ ቢያስብ፥ ባልንጀሮቹን ባሮች ሊመታ ቢጀምር ከሰካሮችም ጋር ቢበላና ቢጠጣ፥ የዚያ ባሪያ ጌታ ባልጠበቃት ቀን ባላወቃትም ሰዓት ይመጣል፥ ከሁለትም ይሰነጥቀዋል፥ እድሉንም ከግብዞች ጋር ያደርግበታል፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል።” (ማቴ.24፥45-51)

ምሳሌው አይመለከተንም የሚለው ሐሳብ ስለ ዝንጉዎቹ ዕጣ ፈንታ የተነገረውን ቃል በመፍራት የመነጨ ይመስላል፤ “የማይጠቅመውን ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል” የሚለውን (ማቴ.25፥30) እና ወደ ሰርግ እንዳይገቡ በሩን ዘግቶ ሰነፎቹን ቆነጃጅት “እውነት እላችኋለሁ፥ አላውቃችሁም” የሚለውን (ማቴ.25፥12)።

ነገር ግን የሚያስፈራ ነገር የለም። ምሳሌዎቹ ዝንጉዎች እንዳንሆን ለማሳሰብና ዝንጉ መሆን የሚያስከትለውን ጉዳት በአጽንዖት ለመግለጽ የተነገሩ ናቸው። ጉዳቱ ምን ድረስ እንደሚሆን በጅምላ እንዲህ ተብሎ ሊገለጽ አይችልም። እግዚአብሔር በእያንዳንዱ ላይ እንደ ሥራው ስለሚፈርድ (1ጴጥ.1፥17) ውጤቱ ከሰው ሰው ይለያያል። እንዲህ ነው የሚለው፦

“ከተመሠረተው በቀር ማንም ሌላ መሠረት ሊመሠርት አይችልም፥ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ማንም ግን በዚህ መሠረት ላይ በወርቅ ቢሆን በብርም በከበረ ድንጋይም በእንጨትም በሣርም ወይም በአገዳ ቢያንጽ፥ የእያንዳንዱ ሥራ ይገለጣል፤ በእሳት ስለሚገለጥ ያ ቀን ያሳያልና፥ የእያንዳንዱም ሥራ እንዴት መሆኑን እሳቱ ይፈትነዋል። ማንም በእርሱ ላይ ያነጸው ሥራ ቢጸናለት ደመወዙን ይቀበላል፤ የማንም ሥራ የተቃጠለበት ቢሆን ይጎዳበታል ...” (1ቆሮ.3፥11-15)

ስለዚህ፣ መልእክቱ ለሁሉም ነው፤ ጌታ ሲመጣ አማኙ በእምነቱ አገልጋዩም በአገልግሎቱ ሲተጋ እንዲገኝ የሚያሳስብ። “እንግዲህ በገደብ የለሽ ሕይወት፣ በመጠጥ ብዛትና ስለ ኑሮ በመጨነቅ ልባችሁ እንዳይዝልና ያ ቀን እንደ ወጥመድ ድንገት እንዳይደርስባችሁ ተጠንቀቁ፤ ይህ በመላው ምድር በሚኖሩት ሁሉ ላይ ይደርሳልና። ስለዚህ ከሚመጣው ሁሉ እንድታመልጡና በሰው ልጅ ፊት መቆም እንድትችሉ ሁልጊዜ ተግታችሁ ጸልዩ።” (ሉቃ.21፥34-36)

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

22 Aug, 21:45


እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን ...

“የእግዚአብሔርን መንግሥት መውረስ” ሲባል አንዳንዶቻችን ምድርን ለቅቆ በሰማይ መኖር ይሆናል የሚታየን። እሱ ስሕተት ባይሆንም ትልቁን ምስል አያሳየንም። የበለጠ ትክክለኛና ሙሉ የሆነ ትርጉም አለ።

የእግዚአብሔር መንግሥት እንደስሟ መንግሥት (አገዛዝ) ናት እንጂ ስፍራ (ሰማይም ሆነ ምድር) አይደለችም። ነገር ግን ሰማይንና ምድርን ትገዛለች። “እግዚአብሔር ዙፋኑን በሰማይ አዘጋጀ፥ መንግሥቱም ሁሉን ትገዛለች” ይላል (መዝ.103፥19)።

በኃጢአት ምክንያት የአሁኑ ዓለም ከእግዚአብሔር ቁጣ ወይም ፍርድ በታች ነው የሚገኘው። ይኸውም በሰይጣን እጅ ነው። ስለዚህም ሰይጣን “የዚህ ዓለም ገዥ” ተብሏል (ዮሐ.14፥30)። ደግሞም “ዓለም በሞላው በክፉው እንደ ተያዘ እናውቃለን” ይላል (1ዮሐ.5፥19)። ሰይጣን በዓመፀኞች ላይ የሚሠራው መንፈስ አለቃ ነው። እንዲህ ይላል፦

“በበደላችሁና በኃጢአታችሁ ሙታን ነበራችሁ፤ በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው።” (ኤፌ.2፥1-2)

የእግዚአብሔር መንግሥት እንድትመጣ የሚያስፈልገው ለዚህ ነው። የእግዚአብሔር መንግሥት ስትመጣለት ሰው ከዚያ ፍርድ ምሕረትን ያገኛል፤ ከሰይጣን ሥልጣን ነጻ ይወጣል። ጌታ ኢየሱስ አጋንንትን እያወጣ አይሁድን “በእግዚአብሔር መንፈስ አጋንንትን የማወጣ ከሆንሁ፥ እንግዲህ የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ ደርሳለች” አላቸው (ማቴ.12፥28)። ደግሞም “እርሱ መልካም እያደረገ ለዲያብሎስም የተገዙትን ሁሉ እየፈወሰ ዞረ” ይላል (ሐዋ.10፥38)።

ነገር ግን የሥጋን ፈውስ መቀበል ብቻውን በቂ አይደለም። ሰው ከሰይጣን አገዛዝ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የሚሻገረው በክርስቶስ በማመን የኃጢአትን ስርየት ሲያገኝ ነው። ለሰይጣን እንዲገዛ ያደረገው ኃጢአት እንደመሆኑ፥ ኃጢአቱ ሲወገድለት ሰው ከሰይጣን አገዛዝ አርነት ይወጣል። “እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን” ነው የሚለው (ቆላ.1፥13-14)። ወደ መንግሥቱ መፍለስ ከቁጣው ወደ ምሕረቱ መሻገር ነው። “በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቁጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።” (ዮሐ.3፥36)

ሰው ብቻ አይደለም ፍጥረት ሁሉ ምድርም ራሷ ፈውስን ይሻሉ። እግዚአብሔር አዳምን “ምድር ከአንተ የተነሣ የተረገመች ትሁን” ብሎ ስለፈረደ አሁን በምድር ላይ ልዩ ልዩ መከራ ሥቃይና ሐዘን አለ (ዘፍ.3፥17)። ፍጥረት ሁሉ ከዚህ መርገም ነጻ መውጣትን ይጠብቃል።

“የአሁኑ ዘመን ሥቃያችን ወደ ፊት ሊገለጥ ካለው፣ ለእኛ ከተጠበቀልን ክብር ጋር ሲነጻጸር ምንም እንዳይደለ እቈጥራለሁ። ፍጥረት ሁሉ የእግዚአብሔርን ልጆች መገለጥ በናፍቆት ይጠባበቃል። ፍጥረት ሁሉ ለከንቱነት ተዳርጓል፤ ይኸውም በራሱ ምርጫ ሳይሆን፣ ለተስፋ እንዲገዛ ካደረገው ከፈቃዱ የተነሣ ነው። ይህም ፍጥረት ራሱ ከመበስበስ ባርነት ነጻ ወጥቶ ለእግዚአብሔር ልጆች ወደ ሆነው ወደ ከበረው ነጻነት እንዲደርስ ነው። እስከ አሁን ድረስ ፍጥረት ሁሉ በምጥ ጊዜ እንዳለው ሥቃይ በመቃተት ላይ እንደሚገኝ እናውቃለን።” (ሮሜ.8፥18-22)

ይህ ፍጥረት በናፍቆት የሚጠባበቀው “የእግዚአብሔር ልጆች መገለጥ” የእግዚአብሔር መንግሥት ስትገለጥ የሚፈጸም ነው፤ “ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ፥ በዚያን ጊዜ እናንተ ደግሞ ከእርሱ ጋር በክብር ትገለጣላችሁ” እንደሚል (ቆላ.3፥4)።

በመሆኑም ምድር ለዓመፀኞች እንደተተወች አድርገን ልናስብ አይገባም። በሰማይ በእግዚአብሔር ዘንድ ያለው ጽድቅና ሰላም በምድርም ይሆናል፤ ጌታ እንዳስተማረን “መንግሥትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደ ሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን” ብለን እንደምንጸልይ (ማቴ.6፥10)። የእግዚአብሔር ፈቃድም እንዲህ ነው፦ “በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው።” (ኤፌ.1፥10)

ክርስቶስ ሲገለጥ የሰይጣን የዚህ ዓለም ገዥነቱ ያበቃል። “የዓለም መንግሥት ለጌታችንና ለእርሱ ለክርስቶስ ሆነች፥ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ይነግሣል” ይላል (ራእ.11፥15)።

በእርግጥ ጌታ ኢየሱስ ከሙታን በተነሣ ጊዜ “ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ” እንዳለው (ማቴ.28፥18) የሰይጣንን ሥልጣን አስቀድሞ ገፎታል። ነገር ግን መንግሥቱ በምድር ላይ ወዲያው አልተገለጠችም። ይህም የሆነው መንግሥቱ ስትገለጥ ዓመፀኞችን ከሰይጣንና ከመላእክቱ ጋር ስለሚቀጣቸው ሰዎች ከሚመጣው ፍርድ በንስሐ እንዲያመልጡ ዕድል ለመስጠት ነው። “ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፥ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል” ይላል (2ጴጥ.3፥9)።

እንዲያም ሆኖ ግን የአሁኑ ሰማይና ምድር ይጠፋሉ። “ጽድቅ የሚኖርባትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደ ተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን” (2ጴጥ.3፥13)። ሰማይና ምድር ቢለወጡም የክርስቶስ መንግሥት ግን ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል።

በመጀመሪያ፣ በራእይ መጽሐፍ በግልፅ እንተጻፈ ክርስቶስ ሲገለጥ ምድርን ለሺህ ዓመት ነው የሚገዛው (ራእ.20፥4)። ሺሁ ዓመት ሲፈጸም ታላቁና የመጨረሻው ፍርድ ይሆናል። ዓለም ከተፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ ያሉ ሙታን ተነሥተው በሕይወት ካሉት ጋር ፍርድን ይቀበሉና ፍጻሜ ይሆናል (ራእ.20፥11-15)። ከዚያም እግዚአብሔር አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርን ይፈጥራል። በአሁኑ ዓለም ያለው መርገም በዚያ ፈጽሞ አይሆንም። ባለራእዩ ዮሐንስ እንዲህ ይላል፦

“አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፥ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፥ ባሕርም ወደ ፊት የለም። ... ታላቅም ድምፅ ከሰማይ፤ ‘እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ነው፤ ከእነርሱም ጋር ያድራል፥ እነርሱም ሕዝቡ ይሆናሉ፤ እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል፤ እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና’ ብሎ ሲናገር ሰማሁ።” (ራእ.21፥1-4)

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

09 Aug, 14:03


ከሞት ወደ ሕይወት ተሻግሯል

በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፥ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻግሯል (ዮሐ.5፥24)።

ከጌታ ኢየሱስ ጋር የበሉና የጠጡ የሞቱና የትንሣኤውም የዓይን እማኞች የሆኑ ሐዋርያቱ ይህን ቃል ከአፉ ተቀብለው ለዓለም ሁሉ ሰበኩ።

“በክርስቶስ የሚያምን የዘላለም ሕይወት ካለው ታዲያ ሐዋርያቱ ራሳቸው ለምን ሞቱ? አሁንም ድረስ፥ በእርሱ ያመኑ ሁሉ እንደማንኛውም ሰው ይሞታሉ፤ ለምንድነው?” ያልተማረ ሰው ሊጠይቅ የሚችለው ጥያቄ ነው።

ጌታ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ይህን ምሳሌ ነገራቸው፦

“በአረጀ ልብስ አዲስ እራፊ የሚጥፍ የለም፤ ቢደረግ ግን፥ አዲሱ መጣፊያ አሮጌውን ይቦጭቀዋል፥ መቀደዱም የባሰ ይሆናል። በአረጀ አቁማዳም አዲስ የወይን ጠጅ የሚያኖር የለም፤ ቢደረግ ግን፥ የወይን ጠጁ አቁማዳውን ያፈነዳል የወይኑም ጠጅ ይፈሳል አቁማዳውም ይጠፋል፥ አዲሱን የወይን ጠጅ ግን በአዲስ አቁማዳ ያኖራሉ።” (ማር.2፥21-22)

የዘላለምን ሕይወትም እንደዚሁ በአሮጌው ፍጥረታዊው ሰውነታችን መኖር አይቻልም። ፍጥረታዊ ሰውነት የዘላለምን ሕይወት ማስተናገድ አይችልም። “ሥጋና ደም የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊወርሱ አይችሉም፥ የሚበሰብሰውም የማይበሰብሰውን አይወርስም። ... ይህ የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሊለብስ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ሊለብስ ይገባዋል።” (1ቆሮ.15፥50፤53)

“በሚሞት ሥጋችሁ ኃጢአት አይንገሥ” ሲል (ሮሜ.6፥12) አሁን በክርስቶስ አምነንም ለጊዜው በሚሞት አካላችን እንደምንኖር ያሳያል፤ የማይሞተውን እስንክንለብስ ድረስ። በክርስቶስ የሚያምን የዘላለም ሕይወት ካለው አሁን ለምን ይሞታል ለሚለው ጥያቄ መልሱ እሱ ነው።

“በዚህ ቋሚ ከተማ የለንም፤ ነገር ግን ወደ ፊት የምትመጣዋን ከተማ እንጠብቃለን” ነው የሚለው (ዕብ.13፥14)። ተጓዥ በመንገዱ ሳለ ድንኳን ይተክላል እንጂ ቋሚ ነዋሪ ባልሆነበት ስፍራ ሕንጻ አይገነባም። ከመድረሻው ሲደርስ ግን ቋሚ መኖሪያ ቤቱን ሊያንጽ ይችላል። አላፊ የሆነውን ምድራዊውን አካላችንን እንደዚሁ “ድንኳን” ብሎ ይጠራዋል። የማይሞተውንና ጸንቶ የሚኖረውን አካላችንን ደግሞ በሕንጻ ይመስለዋል። እንዲህ እያለ፦

“ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ፥ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘላለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንጻ እንዳለን እናውቃለን። በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፥ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና ለብሰን ራቁታችንን አንገኝም። በእውነትም የሚሞተው በሕይወት ይዋጥ ዘንድ ልንለብስ እንጂ ልንገፈፍ የማንወድ ስለ ሆነ፥ በድንኳኑ ያለን እኛ ከብዶን እንቃትታለን።” (2ቆሮ.5፥1-4)

በመሆኑም አሁን “የዘላለም ሕይወት አለን” ስንል የአሁኑ ሰውነታችን ሲጠፋ የማይሞተውን እንደምንለብስ እግዚአብሔር የሰጠን የድነት ተስፋ አለን ማለት ነው። “ልጅን (ክርስቶስን) አይቶ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወትን እንዲያገኝ የአባቴ ፈቃድ ይህ ነው፥ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ” ይላል (ዮሐ.6፥40)።

ድነት አሁን “ተስፋ” እንደሆነ ስንሰማ (ሮሜ.8፥24) አንዳንዶቻችን ሰው እንደሚሰጠው ተስፋ መስሎን አይቅለልብን። ሰው ተስፋ ሲሰጥ ለማድረግ ፈቃደኝነቱን፣ ተነሳሽነቱንና እቅዱን ብቻ ነው የሚያሳየው። ነገሩ ለመፈጸሙ ዋስትና የለም። ሰው ሙሉ ዋስትና መስጠትም አይችልም። ሰው አቅም ስላለውና ለማድረግ ፈቃደኛ ስለሆነ ብቻ አንድን ነገር ማድረግ አይችልም፤ ከቁጥጥሩ ውጪ የሆኑ ነገሮች ሊከሰቱ ስለሚችሉ። ስለዚህም መዝሙረኛው “ንጉሥ በሠራዊቱ ብዛት አይድንም ኃያልም በኃይሉ ብዛት አያመልጥም” ሲል (መዝ.33፥16)፥ ጥበበኛው ደግሞ “ፈረስ ለጦርነት ቀን ይዘጋጃል፤ ድል ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው” ይላል (ምሳ.21፥31)።

የእግዚአብሔር ሐሳብ ግን እንዳይፈጸም የሚከለክል የለም። ስለዚህ ተስፋው እርግጥ ነው። “የተስፋን ቃል የሰጠን ታማኝ ስለሆነ አምነን የምንናገርለትን ተስፋ አጥብቀን እንያዝ” ይላል (ዕብ.10፥23)። የዘላለም ሕይወት ተስፋችን እርግጠኛነት በእግዚአብሔር ማንነትና ባሕርይ ላይ የተመሠረተ እንደሆነ እናያለን።

ይህ ብቻም አይደለም። እግዚአብሔር ፈቃዱ እንደማይለወጥ ሊያሳየን የተስፋ ቃሉን በመሓላ አትሞታል። ይኸውም በክርስቶስ ደም ባደረገልን የድነት ኪዳን አማካኝነት ነው። እንዲህ ይላል፦

“ሰዎች ከእነርሱ በሚበልጠው ይምላሉና፥ ለማስረዳትም የሆነው መሐላ የሙግት ሁሉ ፍጻሜ ይሆናል፤ ስለዚህም እግዚአብሔር፥ የተስፋውን ቃል ለሚወርሱ ፈቃዱ እንደ ማይለወጥ አብልጦ ሊያሳያቸው ስለ ፈቀደ፥ እግዚአብሔር ሊዋሽ በማይቻል በሁለት በማይለወጥ ነገር፥ በፊታችን ያለውን ተስፋ ለመያዝ ለሸሸን ለእኛ ብርቱ መጽናናት ይሆንልን ዘንድ፥ በመሓላ በመካከል ገባ፤ ይህም ተስፋ እንደ ነፍስ መልሕቅ አለን እርሱም እርግጥና ጽኑ የሆነ ወደ መጋረጃውም ውስጥ የገባ ነው፤ በዚያም ኢየሱስ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ሊቀ ካህናት የሆነው፥ ስለ እኛ ቀዳሚ ሆኖ ገባ።” (ዕብ.6፥16-20)

የዘላለም ሕይወት ተስፋ በእግዚአብሔር በኩል እርግጥ ሲሆን ተስፋውን ለማግኘት ከእኛ የሚጠበቀው እምነትና ትዕግሥት ነው፤ እንደ አብርሃም። “በእምነትና በትዕግሥትም የተስፋውን ቃል የሚወርሱትን እንድትመስሉ እንጂ ዳተኞች እንዳትሆኑ፥ ተስፋ እስኪሞላ ድረስ እያንዳንዳችሁ ያን ትጋት እስከ መጨረሻ እንድታሳዩ እንመኛለን። እግዚአብሔርም ለአብርሃም ተስፋ በሰጠው ጊዜ። ‘በእውነት እየባረክሁ እባርክሃለሁ፤ እያበዛሁም አበዛሃለሁ’ ብሎ፥ ከእርሱ በሚበልጥ በማንም ሊምል ስላልቻለ፥ በራሱ ማለ፤ እንዲሁም እርሱ ከታገሰ በኋላ ተስፋውን አገኘ።” (ዕብ.6፥11-15)

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

01 Aug, 14:22


ካመለጡ በኋላ ዳግመኛ ተጠላልፈው ...

እስቲ ይህን ቃል ደግሞ እንመልከት፦

“በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እውቀት ከዓለም ርኵሰት ካመለጡ በኋላ ዳግመኛ በእርስዋ ተጠላልፈው የተሸነፉ ቢሆኑ፥ ከፊተኛው ኑሮአቸው ይልቅ የኋለኛው የባሰ ሆኖባቸዋል። አውቀዋት ከተሰጣቸው ከቅድስት ትእዛዝ ከሚመለሱ የጽድቅን መንገድ ባላወቋት በተሻላቸው ነበርና።” (2ጴጥ.2፥20-21)

ታዲያ እነዚህ በጌታ አምነው የነበሩና በኋላ የካዱ አይደሉም? ሰው አንዴ በክርስቶስ ካመነ በኋላ ፈጽሞ ሊክድ አይችልም የምትሉ እነዚህንም በፊትም በጌታ ያላመኑ ነበሩ ትላላችሁ?

ሰዎቹ “ከዓለም ርኵሰት አምልጠው የነበሩ” መሆናቸው በግልጥ ተጠቅሷል (ቁ.20)። ያ ደግሞ በክርስቶስ በማመን የሚገኝ ከኃጢአት መንጻት (ስርየት) ካልሆነ ምንድነው?

ደግሞም፣ “እነርሱ የዋጃቸውን ጌታ እንኳ ክደው የሚፈጥንን ጥፋት በራሳቸው ላይ እየሳቡ የሚያጠፋ ኑፋቄን አሹልከው ያገባሉ” ይላል (2ጴጥ.2፥1)። በፊትም ያላመኑ ከነበሩ “የዋጃቸውን ጌታ ካዱ” እንዴት ይላቸዋል? አምነው እንደነበሩና በኋላ ግን እንደካዱ ነው የሚያሳየው።

በተጨማሪም፣ “ዳግመኛ” በዓለም እንደተጠላለፉ ያወራል (ቁ.20)። “ዳግመኛ” ማለት “መመለስ”ን ነው የሚያመለክተው። ነገር ግን አስቀድመው ያልተለዩትን እንዴት ይመለሱበታል፤ ቢለዩት ነው እንጂ። ዓለምን ከተለዩአት በኋላ ነው የተመለሱባት። “‘ውሻ ወደ ትፋቱ ይመለሳል’ እንዲሁም ‘ዐሣማ ቢታጠብም ተመልሶ በጭቃ ላይ ይንከባለላል’ የሚለው ምሳሌ እውን ይሆንባቸዋል” ይላል (2ጴጥ.2፥22)።

በመሆኑም ሰዎች እንዲድኑ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን እስከ መጨረሻው መጽናት አለባቸው።

ይህን ስንል አማኞች መዳናቸውን እንዲጠራጠሩ እያደረግን እንደሆነ ተደርጎ ሊቆጠር አይገባም። ይልቁን መዳናቸውን ለማረጋገጥ ይህን ማወቅና መተግበር ስለሚያስፈልግ አማኞችን በየጊዜው በአጽንዖት ማሳሰብ ይገባል።

በቤተክርስቲያን ታሪክ ክርስቶስን የሚያስክዱ ልዩ ልዩ የሐሰት ትምህርቶች በየጊዜው እየተፈበረኩ ጥቂት የማይባሉ ምዕመናንን እንዳሳቱ አውቀን ይህን አብዝተን ማድረግ ይኖርብናል። ሐዋርያትም በመልእክቶቻቸው አማኞች እንዲጸኑ እምነታቸውን እንዲጠብቁና እንዲጠነቀቁ ያሳስባሉ።

ቃሉ፥ “ድናችኋል”፣ “ዳግመኛ ተወልዳችኋል”፣ “ከእግዚአብሔር ጋር ታርቃችኋል” ወ.ዘ.ተ. ሲል አሁን በክርስቶስ ማመናችንን ብቻ ሳይሆን በዚያ እምነት እስከ መጨረሻ እንደምንጸና ታሳቢ አድርጎ ነው።

ለአብነት ያህል፣ ከእግዚአብሔር ጋር ስለመታረቃችን ሲናገር፥ “ከክፉ ባሕርያችሁ የተነሣ ቀድሞ ከእግዚአብሔር የተለያችሁ በአሳባችሁም ጠላቶች ነበራችሁ። አሁን ግን ነውርና ነቀፋ የሌለባችሁ ቅዱሳን አድርጎ በእርሱ ፊት ሊያቀርባችሁ፣ በክርስቶስ ሥጋ በሞቱ በኩል አስታረቃችሁ” ይልና ይህ የሚሆንበትን ሁኔታ ሲገልፅ “ይህም የሚሆነው በእምነታችሁ ተመሥርታችሁና ተደላድላችሁ በመቆም ከሰማችሁት የወንጌል ተስፋ ሳትናወጡ ጸንታችሁ ብትኖሩ ነው” ይላል (ቆላ.1፥21-23/አ.መ.ት.)።

በሌላም ስፍራ እንዲህ ይላል፦

“... ወንድሞች ሆይ፤ የሰበክሁላችሁንና የተቀበላችሁትን፣ ደግሞም ጸንታችሁ የቆማችሁበትን ወንጌል ላሳስባችሁ እወድዳለሁ፤ የሰበክሁላችሁን ቃል አጥብቃችሁ ብትይዙ፣ በዚህ ወንጌል ትድናላችሁ፤ አለዚያ ያመናችሁት በከንቱ ነው።” (1ቆሮ.15፥1-2/አ.መ.ት.)

በክርስቶስ አምነን በሥጋ በምንኖረው በቀሪው ዘመናችን ሁሉ እምነታችንን እንዳያስጥለን ከሰይጣን ጋር መጋደል አለብን። ይህ ተጋድሎ “የዲያብሎስን ሽንገላ (ማታለል) ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ” የተባለው ነው (ኤፌ.6፥11)። ዋነኞቹ ማታለያዎቹ የክርስቶስን ማንነትና ሥራ የሚያስክዱ የስሕተት ትምህርቶች ናቸው። ሐዋርያው በዚህ ቃል ምክሩን ይቋጫል፦

“እንግዲህ እናንተ፥ ወዳጆች ሆይ፥ ይህን አስቀድማችሁ ስለምታውቁ፥ በዓመፀኞቹ ስሕተት ተስባችሁ ከራሳችሁ ጽናት እንዳትወድቁ ተጠንቀቁ፤ ነገር ግን በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና እውቀት እደጉ።” (2ጴጥ.3፥17-18)

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

25 Jul, 16:24


ቃሉ በግልፅ የሚናገረውን ትተን በዚህ መልኩ እንደፈለግን እየተርጎምነው የምንሄድ ከሆነ በዚህ አካሄድ በመጽሐፍ ቅዱስ መመራት አንችልም።

“ከመንፈስ ቅዱስ ተካፋዮች ሆነው የነበሩ” ማለት ከመንፈስ ቅዱስ ተካፋዮች ሆነው የነበሩ ማለት ነው። ጉባኤ የታደሙ፣ አብረው ያጨበጨቡ ወ.ዘ.ተ. ማለት አይደለም።

የተጠቀሰው ቃል ራሱ በዝርዝር የተገለጸና የተብራራ ነው። ተጨማሪ ማብራሪያ አያስፈልገውም። በትርጉም እያሳበብን ቃሉን ለቲዮሎጂያችን እንዲስማማ አድርገን ብንጠመዝዘው የምንጎዳው እኛው ነን። እውነትን ከማወቅ ራሳችንን እንከለክላለን።

ለመዳናችን ዋስትና በእርግጥ አለን። ጌታ ቢፈቅድ ይህን በዝርዝር እናያለን። ነገር ግን፣ ዋስትናው፥ የአማኙን እስከ መጨረሻው በእምነቱ የመጽናት ግዴታ አያስቀረውም።

የትንቢት ድምፅ

20 Jul, 19:23


መጽናት ያስፈልጋችኋል!

ሰው አንዴ በክርስቶስ ካመነ በኋላ ሊክድ አይችልም የምትሉ ይህን ቃል እንዴት ታዩታላችሁ?

“አንድ ጊዜ ብርሃን የበራላቸውን ሰማያዊውንም ስጦታ የቀመሱትን ከመንፈስ ቅዱስም ተካፋዮች ሆነው የነበሩትን መልካሙንም የእግዚአብሔርን ቃልና ሊመጣ ያለውን የዓለም ኃይል የቀመሱትን በኋላም የካዱትን እንደገና ለንስሐ እነርሱን ማደስ የማይቻል ነው፤ ለራሳቸው የእግዚአብሔርን ልጅ ይሰቅሉታልና ያዋርዱትማልና።” (ዕብ.6፥4-6)

ይህ ቃል የሚመለከተው አይሁድን ወይም ዕብራውያንን ብቻ እንደሆነ አድርጎ ለማቅረብ ብዙ አስተማሪዎች ሲጥሩ ይስተዋላል። ነገር ግን ለአይሁድ ብቻ የሚሠራ መርህ የለም፤ አማኝ፥ አማኝ ነው። አይሁድ ይሁኑ ወይም አሕዛብ አምነው ስለነበሩና በኋላ ግን ስለ ካዱ ሰዎች ነው የሚያወራው።

መጀመሪያም አላመኑም ነበር የሚለው ሐሳብ አያስኬድም። ምክንያቱም፣ እነዚህ ሰዎች፥

1ኛ- ብርሃን የበራላቸው
2ኛ- ከመንፈስ ቅዱስ ተካፋዮች ሆነው የነበሩ
3ኛ- የእግዚአብሔርን መንግሥት ኃይል የተለማመዱ

መሆናቸው በማያሻማ ቃል ተገልጾአል። እነዚህ ነገሮች ደግሞ ያለ እምነት ፈጽሞ የሚሆኑ አይደሉም። ለምሳሌ፣ ያለ እምነት መንፈስ ቅዱስን መቀበል (መካፈል) አይቻልም። ስለዚህ፣ አምነው የነበሩና በግልጥ እንደተጠቀሰው “በኋላ የካዱ” ናቸው (ቁ.6)።

በመሆኑም የሚከተሉትን ነጥቦች ማወቅ ይኖርብናል።

1ኛ- አሁን የዳንን በተስፋ ነው። በተስፋ ከሆነ ገና አልተገለጠም ማለት ነው፤ ተስፋ የሚደረግ ነገር የማይታይ ነገር ነው። “በተስፋ ድነናልና፤ ነገር ግን ተስፋ የሚደረግበቱ ነገር ቢታይ ተስፋ አይደለም፤ የሚያየውንማ ማን ተስፋ ያደርገዋል? የማናየውን ግን ተስፋ ብናደርገው በትዕግሥት እንጠባበቃለን” ይላል (ሮሜ.8፥24-25)።

ስለዚህ፣ አሁን ሳናየው ያመንነው የሰውነታችን መዳን (ቤዛነት) ገና ወደፊት እንዲፈጸም የምንጠብቀው ነው። “... የመንፈስ በኵራት ያለን ራሳችን ደግሞ የሰውነታችን ቤዛ የሆነውን ልጅነት እየተጠባበቅን ራሳችን በውስጣችን እንቃትታለን” ይላል (ሮሜ.8፥23)።

ይህም የቤዛ ቀን ተብሎ በሚጠራው በጌታችን መምጣት ነው የሚፈጸመው። “እኛ አገራችን በሰማይ ነው፥ ከዚያም ደግሞ የሚመጣ መድኃኒትን እርሱንም ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን እንጠባበቃለን፤ እርሱም ሁሉን እንኳ ለራሱ ሊያስገዛ እንደሚችልበት አሠራር፥ ክቡር ሥጋውን እንዲመስል የተዋረደውን ሥጋችንን ይለውጣል” የተባለው ነው (ፊልጲ.3፥20-21)።

2ኛ- ተስፋ ያደረግነውን ለማግኘት በእምነት መጽናት የግድ ያስፈልገናል፤ እስክናገኘው ድረስ።

“እንግዲህ ታላቅ ብድራት (ዋጋ) ያለውን ድፍረታችሁን (መታመናችሁን) አትጣሉ። የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና።” (ዕብ.10፥35-36)

ከእምነት ወደ ኋላ ማፈግፈግ ለጥፋት ነው። “ገና በጣም ጥቂት ጊዜ ነው፥ ሊመጣ ያለውም ይመጣል አይዘገይምም፤ ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል ወደ ኋላም ቢያፈገፍግ፥ ነፍሴ በእርሱ ደስ አይላትም። እኛ ግን ነፍሳቸውን ሊያድኑ ከሚያምኑቱ ነን እንጂ ወደ ጥፋት ከሚያፈገፍጉ አይደለንም” ይላል (ዕብ.10፥37-39)።

የመዳን ዋስትና ትምህርት በዚህ መሠረት መቃኘት ይኖርበታል። ምን ትላላችሁ? አስተያየት መስጫው ላይ እስቲ ተወያዩበት።

* * * መጨረሻ * * *

የትንቢት ድምፅ

17 Jul, 22:56


አንዴ በክርስቶስ ያመነ ሰው በኋላ ቢክድ እንኳ ድነቱን አያጣም የሚሉ አሉ። ምክንያታቸው ደግሞ ድነት ስጦታ ስለሆነ አንዴ ከተሰጠ ወዲህ በምንም ሁኔታ አይወሰድም የሚል ነው።

ይህ እንዴት ይሆናል? “ልጁ ያለው ሕይወት አለው፤ የእግዚአብሔር ልጅ የሌለው ሕይወት የለውም” ነው ቃሉ የሚለው (1ዮሐ.1፥8-10)። ክርስቶስን ጥሎ ሕይወት የለም።

ደግሞም “የሙሴን ሕግ የናቀ ሰው ሁለት ወይም ሦስት ቢመሰክሩበት ያለ ርኅራኄ ይሞታል፤ የእግዚአብሔርን ልጅ የረገጠ ያንንም የተቀደሰበትን የኪዳኑን ደም እንደ ርኵስ ነገር የቆጠረ የጸጋውንም መንፈስ ያክፋፋ፥ እንዴት ይልቅ የሚብስ ቅጣት የሚገባው ይመስላችኋል?” ይላል (ዕብ.10፥28-29)። የሚያወራው ክርስቶስን ስለሚክድ ሰው መሆኑ ግልጥ ነው።

የዘላለም ሕይወት የእግዚአብሔር ስጦታ (በጸጋ) መሆኑን ቃሉ ሲናገር ከሰጪው እግዚአብሔር ተለይተን በራሳችን የሚኖረን ማለቱ ሳይሆን በሥራ እንዳላገኘነውና ደመወዛችን እንዳልሆነ ለመግለጽ ነው።

ክርስቲያን እንደ ዳነ ሰው የሆናቸውን ነገሮች ሁሉ የሆነው በክርስቶስ ውስጥ በመሆኑ ነው። የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችን የእግዚአብሔር ልጅ በሆነው በእርሱ ውስጥ በመሆናችን ነው። ከእርሱ ተነጥለን ልጆች አንሆንም።

የትንቢት ድምፅ

14 Jul, 06:42


የመስቀሉ ሥራ (የክርስቶስ ሞቱና ትንሣኤው) በአማኙ ላይ የሚተገበረው በጥምቀት አማካኝነት ነው!

“የሥጋንም ሰውነት በመገፈፍ፥ በክርስቶስ መገረዝ፥ በእጅ ባልተደረገ መገረዝ በእርሱ ሆናችሁ ደግሞ ተገረዛችሁ። በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀብራችሁ፥ በጥምቀት ደግሞ፥ ከሙታን ባስነሣው በእግዚአብሔር አሠራር በማመናችሁ፥ ከእርሱ ጋር ተነሣችሁ።” (ቆላ.2፥11-12)

ተቃራኒ ያልሆኑ ነገሮችን ተቃራኒ እንደሆኑ አድርገህ ነው የተናገርከው። እምነትና ጥምቀት የአንድ ሣንቲም ገጾች ናቸው።

“ከክርስቶስ ጋር ሞቻለሁ” “አዲስ ፍጥረት ሆኛለው” ወ.ዘ.ተ. ትላላችሁ። እነዚህ ኩነቶች የተከናወኑት በጥምቀት አማካኝነት መሆኑን በግልጽ የተጻፈውን ግን አትቀበሉም።

የትንቢት ድምፅ

14 Jul, 06:41


በውኃ ጥምቀት የኀጢአት ስርየት የሚገኝ ከሆነ የኢየሱስ የመስቀል ሥራ አያስፈልግም።

1,112

subscribers

66

photos

4

videos