"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

@ewnetgen


@Dan12bot

ለአስተያየትዎ ይህን ይጠቀሙ እናመሠግናለን

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

20 Aug, 10:05


"መንፈሳዊ ጥበብን የምትወድ ነፍስ ዘወትር እግዚአብሔርን ታመሰግናለች፡፡ ሰው ሆይ! ሰዎች ክፉ ነገር ሲያደርሱብህ እግዚአብሔርን አመስግን፤ ያን ጊዜም ክፉው መልካም ይኾንልሃል፡፡

"እንዴት?" ብለህ የጠየቅኸኝ እንደኾነም፦ "በደል የሚፈፅመው ክፉ ነገር የሚቀበለው ሳይኾን ክፉ ነገር የሚያደርሰው ሰው ነውና" ብዬ በእውነት ያለ ሐሰት እመልስልሃለሁ፡፡

ስለዚህ ዘወትር እግዚአብሔርን አመስግን፡፡ ብትታመምም እግዚአብሔርን አመስግን፤ ሀብት ንብረት ብታጣም አመስግን፤ በሐሰት ቢከሱህም አመስግን፡፡ እንደ ነገርኩህ ተጎጂዎቹ ክፉ ተቀባዮች ሳይኾኑ ክፉ አድራሾች ናቸውና፡፡"

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

08 Aug, 10:01


እግዚአብሔር ለምን ይቆጣናል?

እግዚአብሔር የሚቆጣን ስለ ራሱ ክብር ብሎ አይደለም፡፡ ብንሰድበውም ብንክደውም እንኳን የሚቆጣን ስለ ሰደብነው ወይም ስለ ካድነው አይደለም፡፡ ምክንያቱም እኛ ስለ ካድነው እግዚአብሔር ምንም አይጎድልበትም፡፡ እኛ ስለ ሰደብነው እግዚአብሔር ምንም አይጎድልበትም፡፡ ይልቁንም እንዲህ በማድረጋችን የምንጎዳው እኛው ነን፡፡ በመኾኑም የሚቀጣን ለእኛ ካለው ጥልቅ ፍቅር የተነሣ ነው፡፡ የሚቆነጥጠን ለእኛ ካለው ወደርየለሽ ጠብቆቱ የተነሣ ነው፡፡ እርሱን እየናቅነውና እየራቅነው ስንሔድ በክፋት ላይ ክፋት እየጨመርን ስንሔድ እንዳንጎዳ ሽቶ ነው፡፡

ብርሃንን የሚጠላ ሰው ብርሃኑን ሊጎዳው አይችልም፤ በጨለማ ውስጥ በመቀመጡ ራሱን ይጎዳል እንጂ፤ በራሱ ላይ የጉዳት ዓይነትን ይከምራል እንጂ፡፡ እኛም እግዚአብሔርን ብንጠላው በእግዚአብሔር ባሕርይ ላይ ምንም ነገር አናጎድልም፤ ምረረ ገሃነምን በራሳችን ላይ እንፈርዳለን እንጂ፡፡

እግዚአብሔር በእኛ እይታ እጅግ ክፉ የሚመስሉ ነገሮች በእኛ ላይ ሲያመጣ እኛን ከመበቀል አንጻር አይደለም፤ ይበልጥ ወደ እርሱ እንድንቀርብ እንጂ፡፡ ሐኪሞች አእምሮአቸውን የሳቱ ሰዎች ቢሰድቡዋቸው አይከፋቸውም፡፡ በዚህ አኩርፈውም መድኃኒት ማድረጋቸውን አያቆሙም፡፡ ሕሙማኑ ለዚህ በሽታ የዳረጋቸውን በሽታ ይፈውሱላቸው ዘንድ ይተጋሉ እንጂ፡፡ የሕሙማኑን ችግር እንጂ የእነርሱ መሰደብ አያሳስባቸውም፡፡ እግዚአብሔር አምላካችንም የሚቆነጥጠን ስለ ሠራነው ኃጢአት አይደለም፤ ኃጢአት ሕመም ነውና ከሕመማችን እንድንፈወስ ሽቶ እንጂ፡፡
ቸር አባት ሆይ! ይህ ከአእምሮ የሚያልፍና የዚህ ዓለም ቋንቋ ሊገልፀው የማይችለው ፍቅርህና ጠብቆትህ ዘወትር እናስበው ዘንድ፣ አስበንም በተግባር እንኖረው ዘንድ አእምሮውን ማስተዋሉን ስጠን፡፡ ለዚህ ግሩም ፍቅርህ ያልተገባንና የዕውቀት ግምጃ ቤት ብቻ ኾነን እንዳንቀር ብርታቱን አድለን፡፡
አሜን!

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

07 Aug, 06:06


#ፍልሰታ_ለማርያም

ፍልሰታ ለማርያም ስንል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሚያልፈው ወደ ማያልፈው ዓለም ከመቃብር የወጣችበት ( የተነሣችበት ) ቀን ማለት ነው ወይም ደግሞ ከሥጋዊው ዓለም ወደ መንፈሳዊው ዓለም ከጨለማው ዓለም ወደ ብርሃናማው ዓለም የተሸጋገረችበት ማለት ነው ፡፡

‹‹ ፍልሰታ ለማርያም ›› የሚለው የግእዝ ቃል ሲኾን ‹ ፍልሰታ › ማለት ደግሞ ‹ ፈለሰ › ከሚል ግሥ የተገኘ ነው ፍልሰት ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መሔድን መሻገርን ( መፍለስን ) ያመለክታል ።

የእመቤታችንን ሥጋ ከገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር መፍለሱን ፤ አንድም ከጌቴሴማኒ ወደ መንግሥተ ሰማያት መነሣቱን ለማመልከት የሚነገር ነው ባሕረ ጥበባት ቅዱስ ያሬድ ‹‹ ማርያም በክብር በምስጋና ወደ ሰማያት ፈለሰች ( ተነሣች ዐረገች ) ሠራዊተ መላእክትና ሊቃነ መላእክት ሊቀበሏት ወረዱ የጌታዬ እናቱ እመቤቴ እልሻለሁ ! አባቷ ዳዊት መሰንቆው ይዞ ሙሴም መጎናጸፊያውን ተሸክሞ ወደ እርሷ መጡ ጴጥሮስና ጳውሎስ ሐዋርያት ሥጋዋን በወርቅ ማዕጠንት አጠኑ ፣ ሱራፌል ኪሩቤል ክንፎቻቸውን በእርሷ ላይ ዘረጉ ፤ ብርሃን ከሰማያት ፣ የክብር መብረቅም ( ክርስቶስ ) ከደመናት ወረደ ። ›› በማለት ሊቁ ዕርገቷን ያበሥረናል ::

እመቤታችን ካረፈች በኋላ የሥጋዋን መፍለስ አስመልክቶ ሐዋርያት የእመቤታችን ሥጋ የት እንደ ተቀመጠ አላወቁም ነበርና ፤ እግዚአብሔር የእመቤታችንን ሥጋ እንዲገልጥላቸው የጾሙት ጾም ነው ።

ይኸውም ሁለት ሱባዔ ጾመው የእመቤታችንን ሥጋዋን ሰጥቷቸው ትንሣኤዋንና ዕርገቷን በማየት በረከት ያገኙበት ጾም ነው ስለዚህ ጾመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት ፣ ትንሣኤና ዕርገት የሚዘከርበት ፤ ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ የኾነ ጾም ነው ፡፡

ምእመናንም በየዓመቱ ሕፃን አዋቂው ሳይቀር የእመቤታችን ፍቅር አድሮባቸው ጾሙን ይጾማሉ ፣ ያስቀድሳሉ ፤ ይቈርባሉ የፍልሰታን ጾም ከሌሎቹ አጽዋማት ልዩ የሚያደርገው ምንድን ነው ? ካልን

ኢትዮጵያ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የዐሥራት አገር በመኾኗና ሕዝበ ክርስቲያኑ ለእመቤታችን ልዩ ፍቅር ስላላቸው መሬት ላይ እየተኙ ፣ ጥሬ እየቆረጠሙ በሰላም በፍቅር ይጾሙታል ።

ስለሆነም ምእመናን ፍልሰታ ለማርያምን ከልጅ እስከ አዋቂው በጾም በጸሎትና በመቁረብ በጋራ በፍቅር ፣ በሰላም ያሳልፉታል ፡፡

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

06 Aug, 05:35


"ፍልሰታ መጣች"

"ሕጻኑም ወጣቱም ወንዱም ሴቱም ዕድሜው የገፋውም ሁሉም በፍቅር የሚጾሟት፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ረድዔትና በረከት የሚታፈስባት፡ ፍቅረ እግዚአብሔር በሰው ልቡና የሚሰለጥንባት ፈሪሃ እግዚአብሔር የሚያይልባት፡ የንሰሐና የምህረት ጾም ጾመ ፍልሰታ መጣች፡፡ በዓለም ያሉ ወደ ቤተክርስቲያን በቤተክርስቲያን ያሉ ወደ ገዳማት የሚገሰግሱባት ጾመ ፍልሰታ መጣች፡፡"

እንኳን አደረሰን አደረሳችሁ

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

26 Jul, 05:22


"ጌታ ሆይ እርሻውን አቃጥለህ ሰብሉን ብትባርክ ምን ይጠቅማል? ዛፉንስ ቆርጠህ ቅርንጫፉን ብትባርክ ምን ይረባል? እናቴ እርሻ ናት እኔ ሰብል ነኝ:: እናቴ ዛፍ ናት እኔ ቅርንጫፍ ነኝ:: እባክህን እናቴ ብትክድ እኔ ባምን ምን ይጠቅማል:: ጌታ ሆይ የእናቴን ልብ በሃይማኖት አጽናልኝ"

(ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ስለ እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ የጸለየው ጸሎት)

ቅዱስ ቂርቆስ ሆይ አንተ ሕፃን ሆነህ ትልቅ ነበርክ:: ትልቅ ሆነን ሕፃን የሆንን እኛን በምልጃህ አስበን!

"የእግዚአብሔር ምስክር የታመነ ነው፤ ሕፃናትን ጠቢባን ያደርጋል" መዝ 19:7

(#ከዲያቆን_ሄኖክ_ኃይሌ_የተወሰደ)

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

25 Jul, 20:01


#ቅዱስ_ቂርቆስና_እናቱ_ቅድስት_ኢየሉጣ (#ሐምሌ_19)

ሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ ተቀበሉ። ይህም ሕፃን ዕድሜው ሦስት ዓመት ሲሆነው ከሮሜ አገር ወደሌላ ሀገር እናቱ ይዛው ሸሸች በዚያም የሸሸችውን መኰንን አገኘችው። 

ሰዎችም ነገር ሠሩባት ወደርሱ አስቀረባትና ስለ አምልኮ ጠየቃት እርሷም መኰንን ሆይ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነው ሕፃን አለ አማልክቶችህን ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ አለችው። 

ሕፃኑም ወደአለበት ጭፍራውን ልኮ ወደርሱ አስመጣው ሕፃኑንም ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየውና አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ እንዴት ነህ አለው። ሕፃኑም መልሶ አዎ ለእኔ ደስታ ተጠብቆልኛል ላንተ ግን ኀዘንና ልቅሶ ጥርስ ማፋጨትም ነው መጽሐፍ ለዝንጉዎች ተድላ ደስታ የላቸውም ብሏልና አለው እግዚአብሔር ኃይልና ንግግርን ሰጥቶታልና ብዙ ተናገረ በዚያም ያሉትን እስከ አስደነገጣቸው ድረስ ንጉሡን መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው ከብርታቱም የተነሣ አደነቁ። 

መኰንኑም በአፈረ ጊዜ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይ ታላላቆች የማይችሉትን ታላቅና አስጨናቂ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው እናቱንም ከርሱ ጋር እንደ እርሱ አሠቃያት እግዚአብሔርም ያለምንም ጉዳት ያነሣቸው ነበር። ብዙዎች አሕዛብም ይህን አይተው አደነቁ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበሉ። 

በሕፃኑ ላይም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት። ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችንም አደረገ ብዙዎች በሽተኞችንም አዳናቸው።

ከዚህም በኋላ መኰንኑ በታላቅ የናስ ጋን ውስጥ ውኃ ጨምረው በእሳት ያፈሉት ዘንድ አዘዘ የፍላቱም ድምጽ እንደ ክረምት ነጐድጓድ ሆነ ያን ጊዜም ፍርሀትና የሃይማኖት ጉድለት በእናቱ ላይ ደረሰባት ሕፃኑም ስለ እናቱ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። 

ያን ጊዜ ጌታችን ልቧን ወደ ሰማይ አሳርጎ ለቅዱሳን ሰማዕታት የተዘጋጁ የብርሃን ማደሪያዎችን አየች ከዚህም በኋላ ጸናች እግዚአብሔርንም አመሰገነችው ልጅዋንም ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አንተ አባቴ ነህ እኔም ልጅህ ነኝ አለችው። 

ያቺ ከኔ የተወለድክባትም ቀን የተባረከች ናት አለች ወደዚያ ወደ ጋኑ ውስጥ በገቡ ጊዜም የውኃው ፍልሐት እንደ ንጋት ጊዜ ውርጭ ቀዘቀዘ ከእግዚአብሔር የታዘዘ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወርዶ የእሳቱን ኃይል አቀዝቅዞታልና። 

ከዚህም በኋላ መኰንኑ ሥጋቸው ተቆራርጦ እስከሚወድቅ ድረስ በመቃጥን ውስጥ አድርገው እንዲጐትቷቸው አዘዘ ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ አዳናቸው መኰንኑም በታላቅ ሥቃይ ያሠቃያቸው ዘንድ አስቦ እስኪመክር ድረስ በወህኒ ቤት ዘጋባቸው። 

ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሕፃኑ ቂርቆስ ወርዶ አጽናናው አረጋጋውም። ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ሰማዕታት በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሐምሌ)

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

15 Jul, 17:57


#ትንሿ_ቤተክርስቲያን_በኦርቶዶክሳዊ_ቤተሰብ

[ባለትዳሮች] በቤታቸው ውስጥ ማድረግ ያለባቸው ቤተ ክርስቲያን መጥተው ያዩትን ነው፡፡ ለምሳሌ፦

👉 ቤተክርስቲያን ውስጥ የጠዋትና የሰርክ ጸሎት እንዳለ ኹሉ እነዚህ ባለ ትዳሮችም የጠዋትና የሰርክ ጸሎት በቤታቸው ውስጥ ሊኖራቸው ይገባል፡፡

👉 በቤተክርስቲያን ያለው የኅብረትና የአንድነት ጸሎት እንደ ኾነ ኹሉ፥ ባልና ሚስት ልጆችም ሳይለያዩ አብረው መጸለይ አለባቸው፡፡

👉 በቤተክርስቲያን ውስጥ ከቅዳሴ በኋላ ትምህርተ ወንጌል እንዳለ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም እራት ከበሉ በኋላ ቃለ እግዚአብሔር ሊማማሩ ይገባቸዋል፡፡

👉 በቤተክርስቲያን ውስጥ ራሳቸውን ገዝተው የሚኖሩ ትጉሃን መነኰሳት እንዳሉ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም ይህን ትግሃትና ምስጋና ወደ ቤታቸው ይዘዉት ሊኼዱ ይገባቸዋል፡፡

👉 ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማታ ላይ ኅብስቱን አበርክቶ ሕዝቡን ከመገባቸው በኋላ ወዲያው ወደ መኝታ እንዲኼዱ እንዳላደረገ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም ወደ መኝታቸው ከመኼዳቸው በፊት የቀን ውሎአቸውን መገምገም አለባቸው፡፡

👉 ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሌሊት ሌሊት ሲጸልይ ያድር እንደ ነበረ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም ሌሊት ላይ ነቅተው መጸለይ ይገባቸዋል፡፡ ሕፃናት ካሉም አብረዋቸው እንዲነሡ ማድረግ ይገባቸዋል፡፡

👉 በቤተክርስቲያን ጾም እንደሚታወጅ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም በቤተ ክርስቲያን ከሚታወጀው ጾም በተጨማሪ ከንስሐ አባቶቻቸው ጋር ተመካክረው በፈቃዳቸው ሊጾሙ ይገባቸዋል፡፡

👉 በቤተክርስቲያን ውስጥ እንዳለው፥ ባልና ሚስትም የቤታቸውን ግድግዳ፣ መስኮትና በር በመስቀል ሊያስጌጡት ይገባቸዋል፡፡ ማማተብ በማይችሉ ልጆቻቸው ግንባርም አድገው ራሳቸው ማማተብ እስኪችሉ ድረስ እነርሱ ያማትቡላቸው፡፡ ቅዱሳት ሥዕላትም በቤታቸው ውስጥ ሊኖሩ ይገባል፡፡

ቤታቸው ትንሿ ቤተ ክርስቲያን የምትኾነው በዚህ መንገድ ነው፡፡

#ኦርቶዶክሳዊ_ቤተሰብ
#በቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ መጽሐፍ፥ ገጽ 60 - 61
ትርጉም፦ #በገብረ_እግዚአብሔር_ኪደ

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

11 Jul, 08:40


ሚስት ያፈቅራታል፤ እንደ ልጅ ይወዳታል፤ እንደ አገልጋዩ ያሳድራታል (ይመግባታል)፤ እንደ ድንግል ልጁ ይጠብቃታል፤ እንደ አትክልት ሥፍራው ይከልላታል፤ እንደ አካሉም ይንከባከባታል።  እንደ ራስ ኾኖ ይመግባታል፤ እንደ ሥር ኾኖ ያሳድጋታል፤ እንደ እረኛ በለመለመ መስክ ያሰማራታል፤ እንደ ሙሽሪት ያገባታል፤ እንደ ታራቂ ይቅር ይላታል፤ እንደ በግ ይሠዋላታል፤ እንደ ሙሽራ በውበቷ ይማረካል፤ እንደ ባልም ደግሞ ረዳት ይኾንላታል።"

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
©ገብረ እግዚአብሔር ኪደ

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

09 Jul, 11:11


"ነገር ኹሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን ! !!

አንድ አንዴ በሕይወታችን ምንም የማይጠቅሙ ነገሮችን ልንመርጥ እንችላለን ።የሚያስፈልገንና የማይጠቅመን ግን መንፈስ ቅዱስ ሲመርጥልን  ነው።"

አደጋና ስጋት ፡በሽታና ስቃይ ፡እጦትና ችግር ፡ራብና ጥማት ፡ኅዘንና ትካዜ ፡የሌለው ሕይወት እጅግ ጠቃሜ እንደ ኮነ አድርገን እናስባለን ነገር ግን ይህን የሌለው ሕይወት ኹሉ ጠቃሜ ላይኾን ይችላል ።

እንደ ራሳችን ሓሳብ ሳይኾን እንደ እግዚአብሔር ሓሳብ ስንጓዝ ግን ነገር ኹሉ ለበጎ ነው ። ነገር ኹሉ ሲባልም በእኛ እይታ በጎ ነው የምንለው ብቻ አይደለም ፡ ክፉ ነው የምንለውም ጭምር እንጂ።እንደ እግዚአብሔር ሓሳብ ስሆን ማግኘትም ማጣትም ፡ጤንነትም በሽታም ለበጎ ነው።

እግዚአብሔር ለእኛ መልካም የሚያደርግልን በጎ ነው ብለን በምናስበው ነገር ብቻ አይደለም። እጅግም ክፉና አስቸጋሪ መስለው ከሚታዩን ኹኔታዎችም ለእኛ ለልጆቹ እጅግ የሚደንቅና በጎ ነገርን ማድረግ ይችልበታል።

በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ 

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

08 Jul, 05:31


"አንተ ራስህ ለገዛ ወንድምህ ጨካኝና ይቅር የማትል ኾነህ ሳለስ እግዚአብሔር እንዲራራልህና እንዲምርህ እንዴት መለመን ይቻልሃል?

"ባልንጀራህ ምናልባት ንቆህ ሊኾን ይችላል፡፡ አዎ! አንተ ግን እግዚአብሔርን ኹልጊዜ እንደናቅኸው ነው፡፡ በባልንጀራና በእግዚአብሔር መካከልስ ምን ንጽጽር አለ? ባልንጀራህ ምናልባት ጉዳት ሲደርስበት ሰድቦህ ይኾናል፤ አንተም በዚህ ተበሳጭተህ ይኾናል፡፡ አንተ ግን ምንም ሳይጎዳህና በአንተ ላይ ክፉ ሳያስብ ይልቁንም ዕለት ዕለት በረከቱን እየተቀበልክ እያለ እግዚአብሔርን ሰድበኸዋል፡፡ እንግዲህ ተመልከት! ነቢዩ፡- “እመሰ ኃጢአተኑ ትትዐቀብ እግዚኦ መኑ ይቀውም - አቤቱ ኃጢአትንስ ብትጠባበቅ ማን ይቆማል?” ብሎ እንደ ተናገረ እግዚአብሔር በእርሱ ላይ የምንፈጽመውን በደል ቢመረምር ኖሮ አንዲት ቀንስ እንኳን በሕይወት መቆየት አንችልም ነበር (መዝ.129፡3)፡፡

እያንዳንዱ በደለኛ ሰው ለራሱ የሚያውቀውንና ሌላ ሰው የማይመሰክርበትን እግዚአብሔር ብቻዉን ግን የሚያውቀውንስ ይቅርና የተገለጠውና ሰው ኹሉ የሚያውቀው ኃጢአታችንን እንኳን እግዚአብሔር ቢቈጣጠር ኖሮ ከእነዚህ ኃጢአቶች በኋላ የምንጠብቀው ምንድን ነው? እግዚአብሔር ንዝህላልነታችንንና ጸሎት ስናደርስ የምናሳየው ግድየለሽነታችንን፣ ሠራተኞች ለአሠሪዎቻቸው ወታደሮችም ለአለቆቻቸው ጓደኛሞች ለጓደኞቻቸው የሚያሳዩትን ፍርሐትና ክብር ያህልስ እንኳን ለጸሎትና ለልመና በፊቱ በቆምን ጊዜ አለማሳየታችንን ቢቈጣጠር ኖሮ ምን ነበር የምንኾነው?

አንተ ከጓደኛህ ጋር ስትነጋገር ለምታደርገው ማንኛውም ነገር ትጠነቀቃለህ፡፡ ስለ በደሎችህ እግዚአብሔርን ስትጠብቀው፣ ለብዙ መተላለፎችህ ይቅርታን ስትጠይቀው፣ ሥርየትን ለማግኘት ስታሳስበው ግን [በፊቱ ላይ] ኹልጊዜ ግድየለሽ ትኾናለህ፡፡ ጉልበትህ በምድር ላይ ተንበርክኮ ሳለ ልቡናህ ግን እዚህም እዚያም፣ በገበያ ሥፍራም፣ በቤት ውስጥም ይዋልላል፤ ከንፈርህ በከንቱና እንዲሁ ያነበንባል፤ ይህን የምንፈጽመው ደግሞ አንዴ ወይም ኹለቴ ሳይኾን ኹልጊዜ ነው።

እንግዲህ እግዚአብሔር ይህን ብቻ እንኳን ቢመረምር ይቅርታን ወይም ምሕረትን እንደምናገኝ ታስባለህን? በእውነት አይመስለኝም!"

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ

#ትምህርት_በእንተ_ሐውልታት_መጽሐፍ
ገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተረጎመው

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

01 Jul, 13:38


#ሰኔ_24

#ኢትዮጵያዊው_ቅዱስ_አባ_ሙሴ_ጸሊም

ሰኔ ሃያ አራት በዚች ቀን አባ ሙሴ ጸሊም በሰማዕትነት ሞተ። ሰዎች ከገድሉ የተነሣ ይህን ቅዱስ ያደንቁታል እርሱ አስቀድሞ መንግሥተ ሰማያትን ገፍቷት ነበረና እርሱ በሥጋው ጠንካራ በሥራውም ኃይለኛ ነበር ይበላና ይጠጣ ይቀማና ያመነዝር ነበር ይገድልም ነበር ማንም ሊቋቋመው አይችልም ነበር። 

አንድ በግ በአንድ ጊዜ ጨርሶ እንደሚበላና አንድ ፊቀን ወይን ጠጅ እንደሚጠጣ ስለ እርሱ ተነግሮአል። እርሱም ፀሐይን ለሚያመልኩ ሰዎች አገልጋይ ነበረ ብዙ ጊዜም ወደ ፀሐይ እያንጋጠጠ ፀሐይ ሆይ አንተ አምላክ ከሆንክ አነጋግረኝ ይል ነበር ደግሞም በልቡ የማላውቅህ ሆይ ራስህን አሳውቀኝ ይል ነበር። 

ከዚህም በኋላ በአስቄጥስ ገዳም ያሉ መነኰሳት እግዚአብሔርን ያውቁታል ያዩታልም እያሉ ሲነጋገሩ ሰዎችን ሰማቸው። ያን ጊዜም ተነሣ ሰይፉንም ታጥቆ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደ በደረሰም ጊዜ አባ ኤስድሮስን አገኘው። አባ ኤስድሮስም ፈራው ሙሴ ጸሊምም እውነተኛውን አምላክ ታሳውቁኝና ታስረዱኝ ዘንድ ወደ እናንተ መጣሁ አለው። አባ ኤስድሮስም ወደ አባ መቃርስ ወስዶ አገናኘው። 

እርሱም ተቀብሎ ሃይማኖትን አስተማረው እንዲህም አለው ታግሠህ የማስተምርህን ከጠበቅህ እግዚአብሔርን ታየዋለህ። ከዚህም በኋላ የክርስትና ጥምቀትን አጥምቆ አመነኰሰው ከብዙዎች ገድለኞች ቅዱሳን ይልቅ ብዙና ጽኑዕ ገድልን መጋደል ጀመረ። 

ሰይጣንም ቀድሞ ሲሠራው በነበረ በመብሉና በመጠጡ በዝሙቱም ይዋጋው ነበረ እርሱም በራሱ ላይ የሚደርስበትን ሁሉ ለአባ ኤስድሮስ ይነግረው ነበር እርሱም አጽናንቶ ሊሠራው የሚገባውን ያስተምረው ነበር። 

ከገድሉ ብዛትም የተነሣ አረጋውያን መነኰሳት በሚተኙ ጊዜ ቤቶቻቸውን በመዞር ውኃ መቅጃዎችን ወስዶ ውኃ መልቶ በየቤታቸው ደጃፍ ያኖር ነበር። ውኃው ከእነርሱ ሩቅ ነበረና እንዲህም እያደረገ በመጋደል ለብዙ ዘመናት ኖረ። 

ሰይጣንም በእርሱ ቀንቶ በእግሩ ውስጥ አስጨናቂ የሆነ አመታትን መታው ተኝቶም እየተጨነቀ ብዙ ቀን ታመመ። ከዚህም በኋላ የመታውና የሚፈታተነው ሰይጣን እንደሆነ ዐውቆ ሥጋው በእሳት ተለብልቦ እንደ ደረቀ ዕንጨት እስቲሆን ድረስ ተጋድሎውንና አገልግሎቱን አበዛ። እግዚአብሔርም ትዕግስቱን አይቶ ከደዌው ፈወሰው የሰይጣንንም ጦር ከእርሱ አራቀለት የመንፈስ ቅዱስም ጸጋ አደረበት ወደርሱም አምስት መቶ ወንድሞች መነኰሳት ተሰበሰቡ በእነርሱም ላይ አበ ምኔት ሆነ። 

ከዚህ በኋላ ቅስና ሊሾሙት መረጡት በቤተ መቅደስም በሊቀ ጳጳሳቱ ዘንድ በአቆሙት ጊዜ ሊቀ ጳጳሳቱም አልፈቀደም ነበር አረጋውያኑንም ይህን ጠቋራ ለምን አመጣችሁት ከዚህ አውጡት አላቸው እርሱም መልክህ የከፋ ጠቋራ ሆይ መልካም አደረጉብህ በማለት ራሱን እየገሠጸ ወጣ ከዚህ በኋላ ዳግመኛ ሊቀ ጳጳሳቱ ጠራውና እጁን በላዩ ጭኖ ቅስና ሾመው እንዲህም አለው ሙሴ ሆይ እነሆ በውስጥም በውጭም ሁለመናህ ነጭ ሆነ። 

በአንዲትም ዕለት ቅዱሳን አረጋውያን ወደርሱ መጡ በእርሱም ዘንድ ውኃ አልነበረም እርሱም ከበዓቱ ብዙ ጊዜ ወጣ ገባ ይል ነበር ከዚህ በኋላም ብዙ ዝናም ዘንሞ ጕድጓዶችን ሁሉ ሞላ። አረጋውያንም ለምን ብዙ ጊዜ ወጣ ገባ ትል ነበር ብለው ጠየቁት እርሱም እግዚአብሔርን ውኃ ካልሰጠኸኝ ቅዱሳን አገልጋዮችህን ምን አጠጣቸዋለሁ እለው ነበር በቸርነቱም ዝናምን ልኮልን ውኃን አገኘን አላቸው። 

በአንዲትም ዕለት አባ ሙሴ ከአረጋውያን ጋራ ወደ አባ መቃርስ ሔደ አባ መቃርስም የሰማዕትነት አክሊል ያለው ከእናንተ ውስጥ አንዱን እነሆ አያለሁ አላቸው አባ ሙሴም አባቴ ሆይ ምናልባት እኔ እሆናለሁ በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይገደል ዘንድ አለው የሚል ጽሑፍ አለና ብሎ መለሰ። 

ከዚህም በኋላ የበርበር ሰዎች መጡ አባ ሙሴም ከእርሱ ጋራ ያሉትን መነኰሳት እነሆ የበርበር ሰዎች ደረሱ መሸሽ የሚፈልግ ይሽሽ አላቸው እነርሱም አባታችን አንተስ አትሸሽምን አሉት እርሱም በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይገደላል ስለሚለው የእግዚአብሔር ቃል እነሆ ያቺን ቀን ለብዙ ዘመናት ስጠብቃት ኖሬአለሁ አላቸው። 

ወዲያውኑም የበርበር ሰዎች ገብተው በሰይፍ ገደሉት መሸሽ ስለ አልፈለጉ ከእርሱ ጋራ ሰባት መነኰሳትም ተገደሉ አንዱ ግን ከምንጣፍ ውስጥ ተሠወረ የእግዚአብሔርንም መልአክ አየ በእጁም አክሊል ነበር እርሱም ቆሞ ይጠብቅ ነበር። ይህንንም በአየ ጊዜ ከተሠወረበት ወጣ የበርበር ሰዎችም ገደሉት የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ። 

ወንድሞች ሆይ ከሀዲና ነፍሰ ገዳይ ቀማኛና ዘማዊ የነበረውን ለውጣ ደግ አባት መምህርና የሚያጽናና ለመነኰሳትም ሥርዓትን የሠራ ካህን እንዳደረገችው በሁሉም አብያተ ክርስቲያን ስሙ እንዲጠራ እንዳደረገችው የንስሐን ኃይሏን ተመልከቱ። ሥጋውም በአስቄጥስ ገዳም ደርምስ በተባለ ቦታ ለዘላለም ይኖራል ከእርሱም ብዙዎች ድንቆችና ተአምራት ይታያሉ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሰኔ)

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

29 May, 06:46


#ግንቦት_21

#ደብረ_ምጥማቅ

ግንቦት ሃያ አንድ በዚች ዕለት አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በደብረ ምጥማቅ በስሟ በተሠራች ቤተ ክርስቲያን ጉልላት ላይ በብርሃን መርከብ ተቀምጣ ፊቷ በግልጥ ስለመታየቱ የክርስቲያን ወገኖች ሁሉም ታላቅ በዓልን ያደርጋሉ።

እርሷም በልጅዋ የመለኮት ብርሃን የተጐናጸፈች ናት በዙሪያዋም የመላእክት ሠራዊት የመላእክት አለቆችም በየማዕረጋቸው ክንፋቸውን ዘርግተው ይቆሙ ነበር ይጋርዷታልም። ሱራፌልም ማዕጠንታቸውን ይዘው ለንግሥዋ ገናናነት ይሰግዳሉ በየስግደታቸውም እንዲህ እያሉ ያመሰግኗታል። አብ በሰማይ ሁኖ ተመለከተ እንደ አንቺ ያለ አላገኘም አንድ ልጁንም ልኮ ከአንቺ ሰው ሆነ።

ሁለተኛ ሰማዕታትም በየማዕርጋቸው ረቂቃን በሆኑ ፈረሶቻቸው ተቀምጠው እየመጡ መጀመሪያ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአምባላይ ፈረሱ ወርዶ ይሰግድላታል እንዲሁም ባልንጀሮቹ ሰማዕታት መጥተው ይሰግዱላታል ።

ከእርሱ በኋላ የሚመጣው በዱሪ ፈረስ የሚቀመጥ ይህ መርቆሬዎስ ነው። ከዚህም በኋላ ሰማዕታት ሁሉ በመከታተል መጥተው ይሰግዱላታል ምስጋናም ያቀርቡላታል። ሁለተኛም ደግሞ የጻድቃን አንድነታቸው መጥተው በፊቷ ሰግደው ይመላለሳሉ።

ሄሮድስ የገደላቸው ሕፃናትም መጥተው ይሰግዱላታል በፊቷም እየዘለሉ አንዱ በአንዱ ላይ እየዘለለ በመተቃቀፍም ይጫወታሉ የተሰበሰቡትም በአዩ ጊዜ ደስታ ይመላባቸዋል በሰማይም ያሉ ይመስላቸው ነበር።

እናትና አባቱም የሞቱበት ቢኖር ወይም ከዘመዶቹ ወይም ባልንጀራዉ ቅድስት ድንግል እመቤቴ ሆይ ዕገሌን አሳዪኝ ብሎ በሚለምናት ጊዜ ቀድሞ በነበረበት መልኩ ያን ጊዜ ታመጣዋለች። ደግሞ መሀረባቸውን ወደላይ ይወረውሩላታል የወደደችውንም በእጇ ተቀብላ መልሳ ትጥልላቸዋለች ለበረከትም በየጥቂቱ ይካፈሉታል።

እንዲህም አምስት ቀን ሁሉ ክርስቲያንም እስላሞችም አረማውያንም ያይዋታል። ወደ ቤታቸውም ለመሔድ ሲሹ በፊቷ ሰግደው ይሰናበቷታል እርሷም ትባርካቸውና ይመለሳሉ።


ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን ለአባት እናቶቻችን የተገለጠች እመቤታችን ለእኛም በረድኤት ትገለጽልን:: ጣዕመ ስሟ በአንደበታችን: ጣዕመ ፍቅሯ በልባችን ይደርብን አሜን::

(#ስንክሳር_ዘተዋሕዶ)

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

29 May, 06:34


ቅዳሴ ቤታ ለማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም

ታላቋ ደብር ማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቅዳሴ ቤቷን ያከበረችው ከዛሬ ዘጠና ሁለት አመት በፊት በ1921 ዓ.ም ፣ በዘመነ ማቴዎስ ወንጌላዊ ፣ ግንቦት 21 ፣ ረቡዕ ቀን ነበር። ብፁእ አቡነ ሣዊሮስ ጳጳስ ዘደቡበ ኢትዮጵያ በ1918 ዓ.ም በመቃኞ ያሰሯት ይህች ደብር የብዙዎችን እንባ እያበሰች ፣ የለመኗትን ሁሉ እየሰጠች በምዕመናን ዙሪያውን ተከባ እንደ ኮከብ እያበራች ታላቅነቷን ይዛ ዛሬ ላይ ደርሳለች።

የደብራችን የቅኔ መምህር በሆኑት በታላቁ ሊቅ መምህር ዘካርያስ አምባው አማካኝነት መልክዕ የተደረሰላት ሲሆን ከዕለቱ ጋር የሚስማማውን እንዲህ አቅርበነዋል።

ሰላም ለበዓትኪ ውስተ ቤተ መቅደስ ሉዓላዊት
አመ ዕስራ ወአሚሩ ለወርኃ ግንቦት
ምዕራፈ ተድላ ሣዊሮስ ማኅደረ ስብሐት
እንበለ ዕረፍት ይዌድሱኪ ካሕናት
እለ ዕረፍቶሙ ይዕቲ አኮቴት

ተድላ የተባለ የሣዊሮስ ማደሪያ ማኅደረ ስብሐት ሆይ ከፍ ወዳለችው ቤተመቅደስ በግንቦት ሀያ አንድ ቀን ስለመግባትሽ ሰላም እላለው። ዕረፍታቸው ምስጋና የሆነላቸው ካሕናትም ያለ ዕረፍት ያመሰግኑሻል።

እንኳን ለቅዳሴ ቤቷ በሰላም በፍቅር አደረሰን አደረሳችሁ።
© መምህር ዮሐንስ እሸቱ

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

27 May, 06:46


✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞

❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖

❖ ግንቦት 19 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

++ አባ ዓቢየ እግዚእ ++

አባ ዓቢየ እግዚእ የተወለዱት በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን ትግራይ ተንቤን (መረታ) ውስጥ ነው:: የተባረኩ ወላጆቻቸው ያፍቅረነ እግዚእና ጽርሐ ቅድሳት ይባላሉ:: አጥምቀው 'ዓቢየ እግዚእ' ሲሉ ስም ያወጡላቸው የወቅቱ ዻዻስ ሰላማ መተርጉመ መጻሕፍት ናቸው:: ትርጉሙም "በጌታ ዘንድ ታላቅ ሰው" ማለት ነው::

+ዓቢየ እግዚእ በሕጻንነታቸው ሌሊት ሌሊት ባሕር ውስጥ ሰጥመው ሲጸልዩ አድረው ቀን ቀን እየተማሩ ብሉይ ከሐዲስ ጠነቀቁ:: ገና በወጣትነታቸው ወደ ታላቁ መነኮስ አቡነ መድኃኒነ እግዚእ ደብረ በንኮል ሔደው መንኩሰዋል:: በገዳሙ በጾም: በጸሎትና በስግደት ተወስነው ከኖሩ በኋላ ወደ ዋልድባ ሔደው የተሰወረች ቤተ ክርስቲያን አግኝተዋል:: በጊዜው በ40 ቀን አንዲት ቅጠል ብቻ ለቁመተ ሥጋ ይበሉ ነበር:: ከዚያም ወደ ሃገራቸው ተንቤን ተመልሰው ዛሬም ድረስ ድንቅ ሆኖ የሚታየውን ገዳም መሥርተው ብዙ መናንያንን አፍርተዋል:: ዓቢየ እግዚእ ገዳማዊና ጻድቅ ብቻ ሳይሆን ሐዋርያዊ
አባትም ነበሩ:: ከትግራይ እስከ ደንቢያ ደግሞ ሃገረ ስብከታቸው ነው::

+አንድ ጊዜ ደቀ መዛሙርትን አስከትለው ለስብከት ሲንቀሳቀሱ ተከዜ ወንዝ አካባቢ ደረሱ:: ቀኑ ነሐሴ 10 ነውና ተከዜ እስከ ገደፉ ሞልቶ ለ3 ቀናት ባለመጉደሉ ከ1,000 በላይ ሰዎች ሲያለቅሱ ደረሱ:: ጻድቁ ባካባቢው የነበሩት ኢ- አማንያን (አሕዛብ) ቢሆኑም ራርተዋልና "አምላከ ሙሴ" ብለው ጸልየው ወደ ጥልቁ ውስጥ ገቡ:: ቅዱስ ሚካኤል አብሯቸው ነበርና ተከዜ ግራና ቀኝ ተከፍሎ መሃሉ የብስ ሆነ:: ይሕን ድንቅ ያዩ ከ1,000 በላይ አሕዛብም አምነው በጻድቁ እጅ ተጠምቀዋል:: ይሕም ዘወትር ነሐሴ 10 ቀን በቤተ ክርስቲያናቸው (ጐንደር) ይከበራል:: ከዚያም እያስተማሩ ጐንደር ደረሱ:: ያኔ ጐንደር በቀሃና አንገረብ ወንዞች የታጠረች አንዲት መንደር ነበረች:: ጻድቁ
ቀን ቀን እየሰበኩ ማታ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናቸው የታነጸበት ሥፍራ ላይ ሲጸልዩ ያድሩ ነበር:: በዚያ ዘመን ጐንደር ውስጥ ጅብ: እባብና መሠል አራዊት ገብተው ሕዝቡን ጨረሱት:: ይሕንን የተመለከቱት አባ ዓቢየ እግዚእ ወደ እግዚአብሔር አለቀሱ:: በፍጹም ልባቸውም ስለ ሕዝቡ ለመኑ:: የለመኑትን የማይነሳ ጌታ ወደ ጻድቁ ቀርቦ "በስምሕ የተማጸኑ: በቃል ኪዳንህ ያመኑ: በምድር አራዊት አይሠለጥኑባቸውም:: በሰማይም እሳትን አያዩም:: ጐንደርንም አራዊት ገብተው ሰውን አይጐዱም::" ብሏቸው አርጓል::
ጻድቁም የወንጌል አገልግሎታቸውን ፈጽመው ወደ ገዳማቸው ተንቤን ተመልሰዋል:: ይሔው እኛ ምን ብንከፋ: ጻድቁንም ብንረሳቸው እግዚአብሔር ግን ዛሬም በጻድቁ ምልጃ ከተማዋን ጠብቆ ይኖራል:: ነገን ደግሞ እርሱ ያውቃል:: ዛሬ ቤተ ክርስቲያኑ የታነጸበት ቦታ (ጎንደር ቀበሌ 09 ኪዳነ ምሕረት) ጻድቁ የጸለዩበት ቦታ ነው:: እንኳን በወርሃዊ በዓላቸው (በ19) ይቅርና በዓመታዊ በዓላቸው (ግንቦት 19) ለንግስ የሚመጣው ሰው ቁጥር ያስተዛዝባል::

+አባ ዓቢየ እግዚእ በገዳማቸው ተንቤን ለብዙ ዘመናት በቅድስና ኑረው: 3 ሙታንን አስነስተው: ብዙ ድውያንን ፈውሰው: ብሔረ ብጹዓንን ጎብኝተው: የድኅነት ቃል ኪዳንም ተቀብለው: በ140 ዓመታቸው ግንቦት 19 ቀን አርፈዋል:: የጻድቁ ክብር ለሁሉ ነውና እባካችሁ እናስባቸው::

+<< ተአምሪሁ ለጻድቅ አቡነ ዓቢየ እግዚእ - - - ጸሎቱ ወበረከቱ የሃሉ ምስለ ኩልነ ሕዝበ ክርስቲያን ለዓለመ ዓለም:: አሜን:: >>+

+<< ከበዙ ተአምራቱ አንዱን >>+

=>ጻድቁ አባ ዓቢየ እግዚእ በገዳማቸው ተንቤን (መረታ) ሳሉ አንዲት መበለት መጥታ "አባቴ! የምጠጣውን ጸበል ባርከህ ስጠኝ?" አለቻቸው:: ጻድቁም በውሃው ላይ ጸሎትን አድርሰው : በመስቀላቸው ባርከው ሰጧት:: ወደ ባልንጀራዋ ስትደርስ ግን ሐሳቧን ቀየረችና "ልጠጣው" ብላ የተቀበለችውን ማይ (ጸበል) ልትጠመቅበት (ልትጸበልበት) ወሰነች:: ባልንጀራዋንም "በላዬ ላይ አፍሺልኝ" ስትል አዘዘቻት:: ባልንጀራዋም "እሺ" ብላ ልታፈስላት (ልትጸብላት) በፋጋ (ግማሽ ቅል) ያለውን ጸበል አነሳች:: ልታፈሰው ስትዘቀዝቀው ግን ከሆነው ነገር የተነሳ 2ቱም ደነገጡ:: ጸበሉ የረጋ ደም ወደ መሆን በቅጽበት ተለውጧልና:: ፍጹም ፍርሃት የወደቀባቸው ሴቶቹ እየተሯሯጡ ወደ አባ ዓቢየ እግዚእ በዓት ደረሱ:: ከውጭ ሆነውም "አባ! አባ የሰጠኸን ጸበልኮ የረጋ ደም ሆነ" አሏቸው:: ጻድቁም እንዳላዋቂ "ምን አጠፋችሁ?" ሲሉ ጠየቁ:: "አባታችን! ምንም አላጠፋንም:: ብቻ አፍሺልኝ ብየ ስሰጣት እንዲህ ሆነ" ስትል አንዷ መለሰች:: ጻድቁ ግን በየውሃት "ልጆቼ! ሁሌም : 'ምንም አላጠፋንም' አይባልም:: ሰው ሆኖ የማይበድል የለምና አንቺም ልጄ! እኔን ያልሺኝ 'የምጠጣው ጸበል ስጠኝ' ነበር:: ግን ልትጸበይበት ወደድሽ:: ስሕተትሽ ከዚህ ይጀምራል:: (የቅዳሴ ጸበል ለመጸበል አይሆንምና) በዚያ ላይ "አልቦ ዓቢይ ኃጢአት ከመ ወልጦ ቃል . ከውሸት በላይ ከባድ ኃጢአት የለም::" (ዮሐ. 8:44) በተጨማሪ ደግሞ ያለ ስልጣኗ እህትሽን 'አጥምቂኝ' አልሻት:: ስለነዚህ ነገሮች ጸበሉ ተለውጦባቹሃል" ብለው ወደ ጸበሉ በመስቀል አማተቡ:: "እፍ" ሲሉትም የረጋ ደም የነበረው ማይ ወደ ጸበልነቱ ተመለሰ:: ይህንን ያዩ ሴቶቹ በግንባራቸው ተደፍተው ለጻድቁ ሰገዱ::

=>ጸሎቱ ወበረከቱ የሃሉ ምስለ ኩልነ ሕዝበ ክርስቲያን ለዓለመ ዓለም:: አሜን::

❖አምላካችን በወዳጆቹ ምልጃ ሃገራችንን ከክፉው ሁሉ ይሠውርልን::

❖ግንቦት 19 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.አባ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ (ኢትዮዽያዊ)
2.አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም (የ12ቱ ሐዋርያት መቃብር
ከጌታ የተገለጠላቸው ኢትዮዽያዊ)
3.አቡነ ብስጣውሮስ ዘሐይቅ እስጢፋኖስ (ኢትዮዽያዊ)
4.ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት ታላቁ (7 ጊዜ ሙቶ የተነሳ)
5."805,007" ሰማዕታት (በአንድ ቀን ብቻ የተገደሉ)
6.አባ ይስሐቅ ገዳማዊ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

30 Apr, 07:33


1️⃣ በሕማማት የሚጸለዩ ፀሎቶች ምን ምን ናቸው?
2️⃣ በሕማማት ወቅት የሚሰሙ የምንላቸው ከሌላ ቋንቋ የተወሰዱ ቃላት ትርጉም
3️⃣ የ41 ስግደት ምን እየተባለ ነው የሚሰገድ?

      📚 የሕማማት ጸሎት 📚

በሕማማት የሚጸለየው በአብዛኛው ውዳሴ ማርያም እና መዝሙረ ዳዊት፤ የነቢያት ጸሎት ሲሆን የጌታን መከራ መስቀል የሚያነሱ መጻሕፍት ይጸለያሉ፡ ሕማማተ መስቀል፣ ድርሳነ ማሕየዊ የመሳሰሉ። መልክአ መልኮች፣ ድርሳናትና ገድላት የማይጸለዩት ዋናውን ጸሎት በጌታ ሕማማና መከራ መስቀል ለመስጠት ስለሆነ ነው። በአጠቃላይ በቤተክርስቲያን የሚነበበው ንባብ (ግብረ ሕማም) ዋናው የጸሎት ክፍል በመሆኑ ያንንም መሳተፍ ትልቁ ጸሎት ነው።

          🌿 ጥብጠባ 🌿

በሰሙነ ሕማማት እለተ ዓርብ ስቅለቱ መታሰቢያ ነው፡ ምእመናኑ በሰሙነ ሕማማት የሰሩትን ይናዘዛሉ  ካህናቱን በወይራ ቅጠል ትከሻቸውን እየጠበጠቡ  ስግደት ያዟቸዋል፡፡ ጥብጠባው የተግሳፅ ምሳሌ ነው፡፡

ይህ በስቅለተ ቀን የሚፈጸም ስነ ስርዓት ሲሆን ጥብጣቤ ማለት ቸብ ማድረግ ማለት ነው፡፡  ይህም የጌታን ግርፋት ያሳያል።፡ሕዝብ ክርስቲያኑ በእለተ ስቅለት ሲሰግድ ሲጸልይ ሲያነብ ከዋለ በኋላ ሰርሆተ ሕዝብ ይሆናል። አርብ ከ 11 ሰአት በኋላ ስግደት እንደሌለ ግብረ ሕማሙ "አልቦ ስግደት "ይላል።

📚 በሕማማት ወቅት የሚሰሙ የምንላቸው ከሌላ ቋንቋ የተወሰዱ ቃላት ትርጉም 📚

በግብረ ሕማማት ውስጥ ወደ ግእዝም ሆነ በኋላ ወደ አማርኛ ሳይተረጎሙ የተቀመጡ የዕብራይስጥ፣ የቅብጥ እና የግሪክ ቃላት ይገኛሉ፡፡ የእነዚህ ቃላት ትርጉም የሚከተለው ነው፡፡

        📌 "ኪርያላይሶን" 📌

ቃሉ የግሪክ ሲሆን አጠራሩ “ኪርዬ ኤሌይሶን” ነው፡፡ “ኪርያ” ማለት “እግዝእትነ” ማለት ሲሆን “ኪርዬ” ማለት ደግሞ “እግዚኦ”ማለት ነው፡፡ ሲጠራም “ኪርዬ ኤሌይሶን” መባል አለበት፡፡ ትርጉሙም “አቤቱ ማረን” ማለት ነው፡፡ “ኪርያላይሶን” የምንለው በተለምዶ ነው፡፡ ይኼውም ኪርዬ ከሚለው “ዬ”ኤላይሶን ከሚለው ደግሞ “ኤ” በመሳሳባቸው በአማርኛ "ያ"ን ፈጥረው ነው፡፡

            📌 "ናይናን" 📌

የቅብጥ(ጥንታዊው የግብጻውያን ) ቃል ሲሆን ትርጉሙ “መሐረነ፣ ማረን” ማለት ነው፡፡

             📌 "እብኖዲ"  📌

የቅብጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙ “አምላክ” ማለት ነው፡፡ “እብኖዲ ናይናን” ሲልም “አምላክ ሆይ ማረን” ማለቱ ነው

           📌 "ታኦስ" 📌

የግሪክ ቃል ሲሆን ትርጉሙ “ጌታ፣ አምላክማለት ነው፡፡ “ታኦስ ናይናንማለትም “ጌታ ሆይ ማረን” ማለት ነው፡፡

            📌 "ማስያስ" 📌

የዕብራይስጥ ቃል ሲሆነ ትርጉሙ “መሲሕ” ማለት ነው፡፡ “ማስያስ ናይናን” ሲልም “መሲሕ ሆይ ማረን” ማለት ነው

           📌 "ትስቡጣ" 📌

ደግ (ቸር) ገዥ ማለት ሲሆን "ትስቡጣ ናይናን" ማለት ቸር ገዥ ማረን ማለት ነው።

  📌 "አምንስቲቲ ሙኪርያቱ አንቲ ፋሲልያሱ" 📌

የቅብጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙም “ተዘከረነ እግዚኦ በውስተ መንግሥትከ- አቤቱ በመንግሥትህ አስበኝ” ማለት ነው፡፡

📌 "አምንስቲቲ መዓግያ አንቲ ፋሲልያሱ" 📌

የቅብጥ ቃል ሲሆን “ተዘከረነ ኦ ቅዱስ በውስተ መንግሥትከ  ቅዱስ ሆይ በመንግሥትህ አስበን” ማለት ነው

📌 "አምንስቲቲ ሙዳሱጣ አንቲ ፋሲልያሱ" 📌

የቅብጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙም “ተዘከረነ እግዚአ ኩሉ በውስተ መንግሥትከ፤የሁሉ የበላይ የሆንክ ወይ በመንግሥትህ አስበን” ማለት ነው፡፡

👉 የ41 ስግደት ምን እየተባለ ነው የሚሰገድ?

አንድ ክርስቲያን በፆም ጊዜ ከፀሎት በኋላ የጌታን መከራና ለእኛ ያሳየውን ፍቅር እያሰበ ከሐጢያቱ ብዛት ከአምላኩ ይቅርታ ያገኝ ዘንድ 41 ጊዜ እንዲህ እያለ ይስገድ

12 ጊዜ ---- #እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ
12 ጊዜ ---- #በእንተ እግዝዕትነ ማርያም መሐረነ
ክርስቶስ
12 ጊዜ ---- #ኪራላይሶን (አቤቱ ማረን)
5 ጊዜ ---- #ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ፣ ሮዳስ (አምስቱ የጌታ ችንካሮች)

✞ እንበለ ደዌ ወሕማም እንበለ ጻማ ወድካም ✞
✞ አመ ከመ ዮም ያብጽሐነ ያብጽሕክሙ ✞ 
✞ ለብርሃነ ትንሳኤሁ እግዚአብሔር ✞
     ✞ በፍስሐ ወበሰላም:: ✞
🪔🪔🪔🪔🪔🪔

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

30 Apr, 05:41


#የሰሙነ_ሕማማት_ማክሰኞ

#የጥያቄ_ቀን_ይባላል፦

ሰኞ ባደረገው አንጽሖተ ቤተመቅደስ ምክንያት፣ ሹመትን ወይም ሥልጣንን ለሰው ልጅ የሰጠ ጌታችን፣ ስለ ሥልጣኑ በጸሐፍት ፈሪሳውያን ተጠይቋልና፤ የጥያቄ ቀን ይባላል፡፡

ጥያቄውም ከምድራውያን ነገሥታት፣ ከሌዋውያን ካህናት ያይደለህ ትምህርት ማስተማር፣ ተዓምራት ማድረግ፣ ገበያ መፍታትን፣ በማን ሥልጣን ታደርጋለህ? ይህንንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ? የሚል ነበር፡፡ /ማቴ. 21፥23-27፣ ማር. 11፥ 7-35፣ ሉቃ.21፥23-27፣ ማር.11፥27-33፣ ሉቃ. 20፥1-8/፤ እርሱም ሲመልስ፤ «እኔም አንድ ነገር እጠይቃችኋለሁ፣ እናንተም ብትነግሩኝ በማን ሥልጣን እነዚህን እዳደርግ እነግራችኋለሁ፡፡ የዮሐንስ ጥምቀት ከወዴት ነበረ፣ ከሰማይ ነውን? ወይስ ከሰዉ? በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ ወይስ በሰው ፈቃድ?» አላቸው፡፡ እነርሱም ከሰማይ ብንል ለምን አልተቀበላችሁትም ይለናል፤ ከሰው ብንል ሕዝቡ ሁሉ ዮሐንስን እንደ አባት ያከብሩታል፣ እንደ መምህርነቱ ይፈሩታልና ሕዝቡን እንፈራለን፤ ተባብለው ከወዴት እንደሆነ አናውቅም ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንደማደርግ አልነግራችሁም አላቸው» ይህንንም መጠየቃቸው እርሱ የሚያደርጋቸውን ሁሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አጥተዉት አልነበረም፣ ልቡናቸው በክፋትና በጥርጥር ስለተሞላ እንጂ፡፡

#የትምህርት_ቀንም_ይባላል፡-

በማቴ. 21፥28፣ ማቴ. 25፥46፣ ማር.12፥2፣ ማር.13፥37፣ ሉቃ. 20፥9፣ ሉቃ. 21፥38 የሚገኙት ትምህርቶች ሁሉም የማክሰኞ ትምህርት ይባላሉ፡፡ በዚህ ዕለት በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረ፣ የትምህርት ቀን ይባላል፡፡ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ ከሥጋዊ ነገር ርቆ በዚህ ሰሞን የሃይማኖት ትምህርት ሲማር ሲጠይቅ መሰንበቱም መጽሐፋዊ ሥርዓት ነው፡፡

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

27 Apr, 20:31


#ሆሳዕና
(የዐቢይ ጾም ስምንተኛ ሳምንት)

ሆሣዕና ከስምንቱ የዐቢይ ጾም እሑዶች አንዱና የመጨረሻው ሳምንት ተብሎ የሚጠራ ከትንሣኤ ቀድሞ የሚገኝ የሕማማት መገቢያ ዋዜማ ነው።

ሆሣዕና አስቀድሞ ካለው ረቡዕ ጀምሮ የሚታሰብ ታላቅ የቤተክርስቲያን የበዓል ቀን እንደሆነ ይታወቃል። ይህን ስም በዚሁ ሰንበትና በዋዜማዎቹ ዕለታት የሚዘመረው ጾመ ድጓ ‘ሆሣዕና በአርያም’’ ‘ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት’’ ‘ዕለተ ሆሣዕናሁ አርዓየ… ‘ ወዘተ. በማለት ሆሣዕና የሚለውን ቃል ቅዱስ ያሬድና ሌሎችም አባቶች በየቦታው እየጠቀሱና እየተዘመረለት በአህያ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ኢየሩሳሌም የገባበትን ሁኔታ እየተረከ ስለሚዘምር ይህ ሰንበት በጌትነትና በክብር በውዳሴና ቅዳሴ ሆሣዕና በአርአያም እየተባለ በሽማግሌዎችና በሕፃናት አንደበት በድንጋዮችም ልሳን ሳይቀር እየተመሰገነ ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በከብር ሲገባ ለሰጣቸው ለተቀደሰ ሰላሙና ፍቅሩ መታሰቢያ ሆኖ የተሰጠ ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሌላ ቀን እንደ ተራ ሰው ሆኖ ወደ ኢየሩሳሌም ይገባ ነበር፡፡

በዚህ ቀን ግን የአይሁድ ንጉሥ ሆኖ በክብር ገባ፡፡ ከቢታንያ ተነሥቶ ደብረ ዘይት ሲደርስ ከሐዋርያቱ ሁለቱን በቤተፋጌ ሰው ተቀምጦባት የማያውቅ ውርንጭላ እንዲያመጡለት ላካቸው፡፡ “በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሒዱ በዚያን ጊዜም የታሰረችን አህያ ውርንጫም ከእርሷ ጋር ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁም አምጡልኝ፡፡ ማንም አንዳች ቢላችሁ ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ" አላቸው፡፡ ማቴ.21፡1-17 ወደ ቤተፋጌም ሄደው አህያዪቱን አገኙአት፡፡ ሲፈቱአትም ሳለ ባለቤቶቹ መጡባቸውና አስቆሟቸው፡፡ እነርሱም ኢየሱስ እንደፈለጋት ነገሩአቸው፡፡ ባለቤቶቹ ይህንን ሲያውቁ ተዋቸው፡፡ ሐዋርያትም የአህያዪቱን ውርንጭላ ፈትተው ወደ ኢየሱስ ወሰዱ፡፡ አጠገቡም ሲደርሱ ልብሳቸውን በአህያዪቱ ውርንጭላ ላይ አንጥፈው ኢየሱስን አስቀመጡት፡፡

#ለምን_ዘንባባ_ያዙ_ቢባል፡-
ዘንባባ እሾሃም ነው ፤አንተም የኃይል የድል ምልክት አለህ ሲሉ፤በሌላም በኩል ዘንባባ እሳት ለብልቦ ይተወዋል እንጂ አይበላውም አንተም ባህርይህ አይመረመርም ሲሉ፤አንድም ዘንባባ ረጅም /ልዑል/ ነው አንተም ባሕርይህ ልዑል ነው ሲሉ ዘንባባ ይዘው ተቀብለውታል፡፡

#የተምር_ዛፍ_ዝንጣፊ_ነው_ቢሉ፡-
ተምር ፍሬው አንድ ነው አንተም ባህርይህ አንድ ነው
ሲሉ፡፡አንድም፤ተምር ልዑል/ረጅም/ ነው አነተም ልዑለ ባህርይ ነህ ሲሉ፡፡ አንድም፤የተምር ፍሬው በእሾህ የተከበበ ነው በቀላሉ መለቀም አይቻልም ፤ የአንተም ምስጢር አነተ ካልገለጠከው አይመረመርም ሲሉ ነው፡፡

#የወይራ_ዛፍ_ዝንጣፊ_ነው_ቢሉ፡-
ወይራ ጽኑዕ/ ጠንካራ/ ነው አንተም ጽኑዓ ባህርይ ነህ ሲሉ፤አንድም ወይራ ለመስዋዕት ይሆናል፤ አንተም መስዋዕት ትሆናለህ ሲሉ፤አንድም ወይራ ዘይቱ ለመብራት ይሆናል አንተም የዓለም ብርሃን ነህ ሲሉ ይህንን ይዘው አያመሰገኑ ተቀበሉት፡፡

#ልብሳቸውንም_ማንጠፋቸው፡-
እንኳን አንተ የተቀመጥክባት አህያ እንኳን መሬት መርገጥ አይገባትም ሲሉ ልብሳቸውን አነጠፉለት፡፡ እነዚያ ያላመኑ አይሁድ ለተቀመጠባት አህያ ይህንን ያህል ክብር ከሰጡ፤ በድንግልና ጸንሳ ለወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምን ያህል ክብር ልናድረግለት ይገባን ይሆን?፡፡

#የዕለተ_ሰንበት_መዝሙር (ከጾመ ድጓ)
ወእንዘ ሰሙን በዓለ ፋሲካ ቀርቡ አርዳኢሁ ለአምላከ ጽድቅ ኀበ ደብረ ዘይት ሙራደ ዓቀብ ሀገረ እግዚአብሔር ወተቀበልዎ ሕዝብ ብዙኃን አዕሩግ ወሕፃናት ነሢኦሙ አዕፁቀ በቀልት እንዘ ይብሉ ሆሣዕና በአርያም ተፅዒኖ ዲበ ዕዋል ቦአ ሀገረ ኢየሩሳሌም በትፍሥሕት ወበሐሴት ይሁቦሙ ኃይለ ወሥልጣነ፡፡…..
ትርጉም: “በፋሲካ በዓል ሰሞን የእውነት አምላክ ደቀ መዛሙርት ወደ ደብረ ዘይት ቀረቡ፤ በሀገረ እግዚአብሔር (ኢየሩሳሌም) አቀበቱ ላይ ብዙ አረጋውያንና ሕፃናት የዘንባባ ቅጠል ይዘው ሆሣዕና በአርያም እያሉ ተቀበሉት፣ በአህያ ውርንጫ ላይ ተጭኖ በፍጹም ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ። ለእነዚህ ኃይልና ሥልጣንን ይሰጣቸዋል።

#መልዕክታት
ዕብ.8÷1-ፍጻ. ከተናገርነውም ዋናው ነገር ይህ ነው፤ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፡፡ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፤ እርስዋም በሰው ሳይሆን በእግዚአብሔር የተተከለች ናት፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ)

1ኛ ጴጥ.1÷13 ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና ነቅታችሁ ኑሩ፤ ኢየሱስ ክርስቶስም ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ፡፡  (ተጨማሪ ያንብቡ)

#ግብረ_ሐዋርያት
የሐዋ.8÷26-ፍጻ. የእግዚአብሔር መልአክም ፊልጶስን ተናገረው፤ እንዲህም አለው÷ “በቀትር ጊዜ ተነሣና በደቡብ በኩል ከኢየሩሳሌም ወደ ጋዛ በሚያወርደው በምድረ በዳው መንገድ ሂድ፡፡” ተነሥቶም ሄደ፡፡” እሆም÷   (ተጨማሪ ያንብቡ)

#ምስባክ
"ንፍሑ ቀርነ በዕለት ሠርቅ፡፡ በእምርት ዕለት በዓልነ፡፡ እስመ ሥርዓቱ ለእስራኤል ውእቱ" መዝ.80÷3
ትርጉም፦ በመባቻ ቀን በታወቀችው በዓላችን ቀን መለከትን ንፉ፤ ለእስራኤል ሥርዐቱ ነውና÷ የያዕቆብም አምላክ ፍርድ ነውና፡፡
ወይም
"እምአፈ ደቂቅ ወሕፃናት አስተዳሎከ ስብሓተ፡፡ በእንተ ጸላዒ፡፡ ከመ ትንሥቶ ለጸላዒ ወለገፋዒ፡፡" መዝ.80÷2
ትርጉም፦ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ፡፡ ስለ ጠላት÷ ጠላትንና ግፈኛን ታጠፋው ዘንድ፡፡

#ወንጌል
ዮሐ.12÷1-11 ፋሲካ ከሚውልበት ከስድስተኛው ቀን አስቀድሞ ጌታችን ኢየሱስ ከሙታን ያስነሣው አልዓዛር ወደ ነበረበት ወደ ቢታንያ መጣ፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ)

ቅዳሴ ፡- ቅዳሴ ዘጎርጎርዮስ፡፡

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

09 Apr, 07:01


#የሕያዋን_ሁሉ_እናት

አባታችን አዳም በኃጢአት ከወደቀ በኋላ ንስሐ በገባ ጊዜ አምላካችን ጌታ እግዚአብሔር የድህነት ቃል ኪዳን ገባለት ቃል ኪዳኑም ‹‹ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ›› የሚል ነበር ።

ስለሆነም አዳም ዐምስት ሺ ዐምስት መቶ ዘመን ሙሉ የሕይወት ምክንያት የሆነችውን የልጅ ልጁ እመቤታችን ድንግል ማርያም ከአብራኩ ከተከፈሉ ቅዱሳን ልጆቹ የምትወለድበትን ቀን ተስፋ እያደረገ ኖረ ።

የእመቤታችንን የድንግል ማርያምን የመወለዷን ዜና ተስፋ በማድረግ ‹‹ ሴት ›› ይላት የነበረውን ሚስቱን ሔዋንን በእመቤታችን ምሳሌነት ‹‹ ሔዋን ›› የሕያዋን ሁሉ እናት ብሎ ሠየማት ። ( ዘፍ 3 ፥ 20 )

ዳግማዊ አዳም ክርስቶስም የአዳምን ተስፋ በመስቀል ላይ በፈጸመ ጊዜ እውነተኛዋን ሔዋን ( ዳግሚት ሔዋንን ) ድንግል ማርያምን በዮሐንስ ወንጌላዊ በኩል ለሕያዋን ምዕመናን ሁሉ እናት አድርጎ ሰጠ ፡፡

ይህን የከበረ ምሥጢር የማይረዳ ‹‹ ሰው እንዴት ያሳዝናል ? ›› እኛ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ግን የቀዳማዊ አባታችንን የአዳምን እንዲሁም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሀለው ብሎ ያከበረንን ዳግማዊ አዳም የተባለውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ቃል ተቀብለን ‹‹ የሕያዋን ሁሉ እናት ›› ድንግል ማርያምን ልደቷን በፍጹም ደስታ እናከብራለን ከተወደደ ልጇ ምሕረትን ትለምንልን ዘንድም ወደ እርሷ እናንጋጥጣለን ፡፡

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

07 Apr, 07:12


#ደብረ_ዘይት
(የዐቢይ ጾም አምሥተኛ ሳምንት)

የዐቢይ ጾም የአምስተኛው ሳምንት ደብረ ዘይት ይባላል፡፡ ጌታ በደብረ ዘይት የዳግም ምጽአቱን ነገር ማስተማሩ ይነገርበታል፡፡ ደብረዘይት የስሙ ትርጓሜ የዘይት ተራራ ማለት ነው ስያሜ የተሰጠው በቦታው ብዙ ወይራ ተክል ይበቅልበት ስለ ነበር ነው፡፡
እርሱም በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ ደቀመዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድን ነው?›› አሉት (ማቴ. 24፥3፣  ዘካ. 14፥5 ፤ ሐዋ. 1፥11 ፤ 1ኛ ተሰ. 4፥16 ፤ ራዕ. 22፥7)

#አመጣጡስ_እንዴት_ነው?

ጌታ ይህንን ዓለም ለማሳለፍ ለሁሉም እንደ ሥራው ለመክፈል በግርማ መለኮቱ በክበብ ትስብዕቱ ይመጣል፡፡ ጊዜው ዘመነ ዮሐንስ ወርሃ መጋቢት ዕለት እሑድ መንፈቀ ሌሊት እንደሆነ ሊቃውንት ተናግረዋል፡፡ ምነው የሚያውቀው የለም ይባል የለምን? ቢሉ እውነት ነው የሚያውቀው የለም ብዙ የዮሐንስ ዘመን፤ ብዙ የመጋቢት ወር፤ ብዙ የእሑድ ዕለት አለና ለይቶ የሚያውቅ የለም፡፡ ሞት ለማን አይቀርምና ሁሉም ይሞታል፡፡ ዘፍ. 3፥19 በዕለተ ምጽአት ቅዱስ ገብርኤል ስምንቱን ነፋሳተ መዓት ከየመዛግብታቸው ያወጣቸዋል፡፡ ዛፏን ነቅለው ደንጊያውን ፈንቅለው ምድርን እንደ ብራና ይዳምጧታል፡፡ ቅዱስ ሚካኤል መለኸት ይነፋል፡፡ 1ኛ መቃ. 9፥8 ቅዱስ እግዚአብሔር ዘያነቅሖሙ ለሙታን ሲል በዱር በገደል በባሕር በየብስ በመቃብር ውስጥ ያሉት በአውሬ ሆድ ውስጥ ያሉ ሁሉ ይሰበሰባሉ፡፡ በሁለተኛው ነጋሪት ሲመታ አጥንትና ሥጋ አንድ ሆነው ፍጹም በድን ይሆናሉ፡፡ ሦስተኛው ነጋሪቱን መቶ (ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ህያው ዘኢይመውት) ንቃሕ መዋቲ ዘትነውም ባለ ጊዜ መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ደጉ ደጉነቱን ክፉውም ክፋቱን ይዞ ይነሳል፡፡    

ወንዱ የ30 ዓመት ሴቲቱ የ15 ዓመት ሆነው ጻድቃን ብርሃን ለብሰው ብርሃን ተጎናጽፈው ከፀሐይ 7 እጅ አብርተው ማቴ.13፥43 ኃጥአን ጨለማ ለብሰው ፍጹም ዲያቢሎስን መስለው ይነሳሉ፡፡ ጻድቃን ስለሠሩት መልካም ሥራ ኑ የአባቴ ቡሩካን ብሎ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሳቸዋል፡፡ ኃጥአንን ስለ ክፉ ሥራቸው (ከኔ ሂዱ) ገሃነም ይሰዳቸዋል፡፡ ጻድቃን ደስ ይላቸዋል ኃጥአን ግን ያዝናሉ፤ ዋይ ዋይ ይላሉ፤ ደረት ይደቃሉ እንባቸው ያፈሳሉ፡፡ የማይጠቅም ለቅሶ የማይጠቅም ሐዘን ሰቅለው የገደሉትም አይሁድ ክብሩን አይተው ላይጠቀሙ ይጸጸታሉ፡፡    

#ምልክቱስ_ምንድን_ነው? ብለው ጌታን ሲጠይቁ ‹‹ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው፡- ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፡፡ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ ይመጣሉና፤ ብዙዎችንም ያስታሉ፤ ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ አትደንግጡ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው፡፡ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥት በመንግሥት ላይ ይነሳል፤ ረሃብም ቸነፈርም መናወጥም በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል፤ እነዚህም ሁሉ የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው፡፡ በዚያን ጊዜ ለመከራ አሳልፈው ይሰጧችኋል ይገድሉአችሁማል፤ ስለ ስሜም በአሕዛብ ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ›› አላቸው፡፡ በዳግም ምጽአቱ ጊዜ ከቅዱሳኑና ከሰማዕታቱ ጋር ለመቆም ያብቃን፡፡

#የዕለተ_ሰንበት_መዝሙር_ከጾመ_ድጓ
እንዘ ይነብር እግዚእነ ውስተ ደብረ ዘይት ወይቤሎሙ ለአርዳኢሁ ዑቁኬ ኢያስሕቱክሙ ወንበሩ ድልዋኒክሙ ብዙኃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ ወዘአዝለፈ ትዕግሥቶ ውእቱ ይድኅን ወአመ ምጽአቱሰ....
(ጌታችን በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ተቀምጦ ሳለ ለደቀ መዛሙርቱ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፤ ተዘጋጅታችሁም ኑሩ፤ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ፤ እስከ መጨረሻው የጸና እርሱ ይድናል፡፡....)

#የዕለቱ_ምንባባት
1ኛ ተሰሎንቄ 4÷13-ፍጻ፡-
ወንድሞቻችን ሆይ÷ ስለ ሞቱ ሰዎች÷ ተስፋ እንደሌላቸው ሰዎች እንዳታዝኑ ልታውቁ እንወዳለን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሞቶ እንደ ተነሣ ካመንን እንዲሁ እግዚአብሔር ሙታንን በኢየሱስ ያስነሣቸዋል ከእርሱም ጋር ያመጣቸዋል፡፡.....

2ኛ ጴጥ.3÷7-14፡-
አሁንም ሰማይና ምድር በዚያ ቃል ለእሳት ተዘጋጅተዋል፤ ኃጥኣን ሰዎች እስከሚጠፉበት እስከ ፍርድ ቀንም ተጠብቀዋል፡፡ነገር ግን ወንድሞቻችን ሆይ÷ ይህን አትርሱ፤ በእግዚአብሔር ዘንድ አንዲት ቀን እንደ አንድ ሺህ ዓመት÷ ሺህ ዓመትም እንደ አንድ ቀን ነውና፡፡.....

ሐዋ. 24÷1-21፡-
በአምስተኛውም ቀን ሊቀ ካህናቱ ሐናንያ ከመምህራኑና ጠርጠሉስ ከሚባል አንድ ጠበቃ ጋር ወረደ፤ ጳውሎስንም በአገረ ገዢው ዘንድ ከሰሱት፡፡..... (ተጨማሪ ያንብቡ)

#የዕለቱ_ምስባክ
መዝ. 49÷2
እግዚአብሔርሰ ገሃደ ይመጽእ
ወአምላክነሂ ኢያረምም
እሳት ይነድድ ቅድሜሁ፡፡
ትርጉም፦
እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል፡፡
አምላካችንም ዝም እይልም፤
እሳት በፊቱ ይነድዳል በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ፡፡

#የዕለቱ_ወንጌል
ማቴ. 24÷1-25፡-
ጌታችን ኢየሱስም ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ሄደ፤ ደቀ መዛሙርቱም ወደ እርሱ ቀርበው የቤተ መቅደሱን የሕንጻ አሠራር አሳዩት፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው÷ “ይህን ሁሉ ታያላችሁን? እውነት እላችኋለሁ፤ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም፡፡.....” (ተጨማሪ ያንብቡ)

#የዕለቱ_ቅዳሴ፦ ቅዳሴ አትናቴዎስ

ምንጭ፡-
(የማቴዎስ ወንጌል 24፥1 ትርጓሜ፣ መዝገበ ታሪክ ቁጥር 2፣ ግጻዌ)