ከኮንታ ዞን አስተዳደር የተላለፈ መልዕክት
ስለ አካባቢያችን በተሳሳተና ተገቢነት በሌለ አኳሃን በተለያዩ ሚዲያ አውታሮች የሚደረጉ አሉታዊ ድርጊቶች እንዲቆሙና እንዲታረሙ ከኮንታ ዞን አስተዳደር የተላለፈ መልዕክት
የኮንታ ዞን በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ውስጥ ከሚገኙ ዞኖች አንዱ ሲሆን ዞኑ ከአዲስ አበባ በጅማ በኩል 450 ኪ.ሜ ርቀት ሲኖረው በሰሜን በኩል ከኦሮሚያ ክልል ጅማ ዞን፣ በምስራቅ ከዳዉሮ ዞን፣ በምዕራብ ከከፋ ዞን እና በደቡብ በኩል ደግሞ ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጎፋ ዞን ጋር ይዋሰናል፡፡
ኮንታ ከሀገራችን ከሁሉም አካባቢዎች በተለያየ አጋጣሚ የመጡ ብሄር ብሄረሰቦች ያለአንዳች ልዩነት ለዘመናት በሰላምና በፍቅር ተከባብረው በጋራ የሚኖሩባትና ሰርተው ያተረፉባት፣ ኖረው ወልደው የከበሩባት የብዙኃን እናት ናት፡፡
የኮንታ ማህበረሰብ እንግዳ ተቀባይ የሆነ ቸር፣ደግና የዋህ ህዝብ መሆኑን እግር ጥሏቸው ለአንድ ቀን እንኳን ደርሰው የተመለሱ አካላት የሚመሰክሩት እውነታ ነው፡፡
ህዝቡ ሰላም ወዳድ የሆነ፣ከራሱ በላይ ለሌላው ሰላምና ደህንነት አብዝቶ የሚጨነቅ፣ ገራገር የመልካም እሴት ተምሳሌት የሆነ ህዝብ ነው፡፡
አካባቢያችን ኮንታ እንደ ሌሎቹ የሀገራችን አካባቢዎች ሁሉ የበርካታ ባህላዊ፣ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ ሀብቶች የሚገኙበትና በሀገር መሪ አንደበት ጭምር "ኮንታ በምድር ላይ ከስዕል ውጭ ገነት የሚታይበት ምድር"መሆኑ ተመስክሮ ከአካባቢው ተፈጥሮ ጋር የሚሄዱ ትላልቅ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች እየተገነባ ያለ አካባቢ ናት፡፡
ከማህበረሰባችን መልካም እሴትና ከአካባቢያችን ተፈጥሮ ሀብት ክምችት መነሻ የሀገር መሪዎች የትኩረት ማዕከል በመሆን የገበታ ለሀገር አካል የሆነው የኮይሻ ገበታ ለሀገር ፕሮጀክት፣ የጨበራ ዝሆን ዳና ሎጅ የሚገኝበት፣ የጨበራ ጩርጩራ ብሄራዊ ፓርክና በውስጡ የአፍሪካ ግዙፉ ዝሆን መገኛ፣ ከህዳሴ ግድብ ቀጥሎ ከፍተኛ የሆነና ሲጠናቀቅ 1,860 ሜጋ ዋት ማመንጨት የሚችል የኮይሻ ኃ/ኤ/ፓ/ ግድብ ያለበት አረንጓዴና ለምነት ከአመት አመት የማይለየው ውብ አካባቢ ነው፡፡
ኮንታ ስካይ ላይት የመሳሰሉ ትላልቅ የሆቴል ድርጅቶች የሚገኙበትና የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶች ዓመቱን ሙሉ የሚመላለሱበት የቱሪስት መዳረሻ የሆነ ከባቢ ነው፡፡
ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአንድ የአካባቢያችን አርሶ አደር በቃላት አገላለጽ ጉድለት መነሻ የተላለፈው መልዕክት በተሳሳተ መንገድ ማህበራዊ ሚዲያ ላይ ወጥቶ ብዙዎች ሲቀባበሉ መቆየቱ ይታወሳል፡፡
ይህ ግለሰብ በጫካ ውስጥ ያገኛቸውን የሀገር ውስጥ ጎብኚዎችን መንገድ እንዳይጠፋባቸውና ዝሆንና ሌሎች የዱር እንስሳትን ማግኘት የሚችሉበትን ትክክለኛ አቅጣጫ ቃላት እያጠረው በየዋህነት "በዚህ ከሄዳችሁ ኮንታ ትገባላችሁ" ያለውን ንግግር ከአውድ ውጪ በመውሰድ ተገቢነት በሌለውና በተሳሳተ መንገድ በማሰራጨት የአካባቢያችንና የህዝባችን መልካም ስም እንዲጎድፍና አካባቢው በመጥፎ እንዲቀረጽ ምክንያት እየሆነ መሆኑን ታዝበናል፡፡
የዚህ ግለሰብ የዋህነት የተሞላው ንግግርና አገላለጽ በኢትዮጵያዊ ጨዋ ባህልና አስተሳሰብ በመልካምነትና በአውንታ ተወስዶ መገለጽ ሲገባው ስለአካባቢው በቂ መረጃ በሌላቸው አካላት ዘንድ ጥርጣሬን ፈጥሯል፡፡
አሁንም በተሳሳተ ትርክት የመጥፎ ነገር ምሳሌ ሆኖ በተለያየ ማህበራዊ ሚዲያ አውታሮች ሲገለጽ ይስተዋላል፡፡
ከሁሉ በላይ የሚያሳዝነው በመላው ዓለም ተደራሽነት ያላቸው እንደነ ኢ.ቢ.ኤስ(ebs) የመሳሰሉ ትላልቅ ሚዲያዎችና አንዳንድ ማስታወቂያ የሚሰሩ ድርጅቶች ጭምር ይህን የግለሰቡን አገላለጽ የሚዲያ ፕሮግራማቸውና የማስታወቂያቸው ማጣፈጫ አድርገው ሲጠቀሙ ማየት እጅግ ያሳዝናል፡፡
ኢ.ቢ.ኤስ ብዙ ሚሊዮን ተመልካች ያለውና ስሜ ጥር ሚዲያ ሆኖ ሲያበቃ እንዲህ አይነት የአንድን አካባቢና ህዝብ ስም የሚያጎድፍ ድርጊት መፈፀሙ ያሳዘነው የኮንታን ህዝብ ብቻ ሳይሆን ለተመልካቹም ሆነ ለኢትዮጵያ ህዝብ ክብር የሌለው መሆኑን ያሳያል፡፡
የትኛውም ሚዲያ ለሚዲያ ፍጆታ የሚጠቀማቸውንና ለህዝብ የሚያስተላልፈውን የድምጽም ሆነ የምስል መረጃ በይዘትም ሆነ በአገላለጽ ከማህበረሰቡ ባህል፣ታሪክ፣ቋንቋ፣ ሞራል፣ ስብዕናና እሴት ያላፈነገጠ መሆኑን ማረጋገጥ እንዳለበት በኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን የመገናኛ ብዙኃን አዋጅ ያስገድዳል፡፡
በመሆኑም በዚህም ሆነ በሌሎች መመዘኛዎች ለህዝብና ለሚዲያ በማይመጥን፤ የአንድን አካባቢ ስም በሚያጠለሽና ተገቢነት በሌለው አኳሃን በኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቪዥን በቀን 03/2/2017 ዓ/ም እሁድን በኢ.ቢ.ኤስ ፕሮግራም በጋዘጠኞች "በዚህ አትህዱ፤ በዚህ ከሄዳችሁ ኮንታ ትገባላችሁ" የሚል አሳፋር ድምጽ ተደጋግሞ ሲተላለፍ ተደምጧል፡፡
የትኛውም ጋዜጠኛም ሆነ የሚዲያ ባለሙያ ለአድማጭ ተመልካቹ ማድረስ ያለበትን ቃላትም ሆነ መልዕክት ጠንቅቆ ማወቅና መረዳት ግዴታ ሆኖ ሲያበቃ እንዲህ አይነት አንድን ህዝብ በሚያንቋሽሽና ለሌላውም የተሳሳተ መረጃና መልዕክት በሚያስተላልፍ አኳሃን የሚዲያ ፕሮግራም መስራት ህገ ወጥነት መሆኑን አበክረን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡
ስለዚህ የኢ.ቢ.ኤስ. ቴሌቪዥን ጣቢያ የተሳሳተ መልዕክት በማስተላለፍ የአካባቢውን ስም ከማጉደፍም ባለፈ ስለአካባቢያችን በቂ መረጃ በሌላቸው አካላት ዘንድ ብዥታ የፈጠረ በመሆኑ በራሱ ሚዲያ መልሶ የማረምና ህዝባችንንም በግልጽ ይቅርታ እንዲጠይቅ እያሳሰብን ይህ የማይሆን ከሆነ ጉዳዩ በህግ አግባብ እንዲታይ ለማድረግ የምንገደድ መሆኑን እየገለጽን ሌሎችም ተቋማትና ግለሰቦች ባለማወቅም ሆነ በቀልድ አልያም ለገንዘብ ማግኛ ተብሎ ስለአንድ አካባቢ የተሳሳተ መልዕክት ማስተላለፍ ከሞራልም ሆነ ከህግ አንፃር ተገቢ ባለመሆኑ እንዲቆም አጥብቀን እንገልፃለን፡፡