ረቢዑል አወል የፍጥረታት ሁሉ አይነታ፣ የከውኑ ሞገስ፣ የሰው ዘር ኩራት፣ የሰላም ንጉስ፣ የስነ-ምግባር መለኪያ፣ የሰው ሁሉ አይነታ፣ የእዝነት ነቢይ የሆኑት ታላቅ ሰው ተወለዱ። ነቢዩ ሙሐመ(የአላህ ሰላምና እዝነት በርሳቸው ላይ ይሁን)።
የወደፊት ነቢይ መሆናቸውን የሰው ዘር ይረዳ ዘንድ በውልደታቸው እለት እጅግ ድንቅ ተዓምራት ታዩ።
ከእናታቸው ሆድ ተነስቶ የሻምን ቤተ-መንግስታት ያበራው ብርሃን አንዱ ነው፤ ብርሃናቸው ዓለምን ማዳረሱ የማይቀር መሆኑን አብሳሪ ነበር። የሻም መናገሻ ቤተ-መንግስታት 14 ጉልላቶች ተፈረካክሰው መውደቃቸው ነባሩን የግፍ ስልጣኔ አፈራርሰው በፍትህ ምድርን እንደሚሞሉ ገላጭ ነበር።
ወጣትነታቸው በመልካምነት ተምሳሌት የደመቀ ነበር። ጣኦታትን በገፍ በሚያመልክ ማህበረሰብ ውስጥ እየኖሩ አንድም ጊዜ ጣኦታትን እጅ ነስተው አያውቁም። ታማንነትና እውነተኝነት አይነተኛ ባህሪያቸው ነበሩ። “ሙሐመድ አል-አሚን” ከነቢይነት በፊት የተቸራቸው የማእረግ ስም ነበር።
ይህ ታማኝነታቸው አፋፍ ላይ የደረሰን የእርስ በርስ ጦርነት አምክነው ሰላም ማስፈን አስችሏቸዋል። “ምንኛ ያማረ ዳኛ አገኘን!”
40 አመታት ሃሰተኝነት እንዳልጎበኘው በሰዎች ሁሉ የተመሰከረለት ንፁህ ስብእና ከ40 ዓመት እድሜ በኋላ ለሰው ዘር በሙሉ እዝነት ተደርገው ተላኩ። በሩቅ ያያቸው የሚያከብራቸው፣ የቀረባቸው በፍቅራቸው የሚሸነፍላቸው ታላቅ ነቢይ የሰው ልጆችን ሁሉ ከጨለማዎች ሁሉ ሊያወጡና ወደ ብርሃን ሊመሩ ተላኩ።
ከእርሳቸው በፊት የነበሩ ነቢያትን የሰውን ልጅ የማቅናት ተልእኮ ለማሟላት የመጨረሻና የነቢያት መደምደሚያ ሆነው ተላኩ። የአደም፣ ኑህ፣ ዩኑስ፣ ኢብራሂም፣ ዩሱፍ፣ ሙሳ፣ ዘከሪያ፣ ኢሳ እና ሌሎች ነቢያቶች መልእክት በእርሳቸው ምሉእነቱ ተገለጠ።
በተሟላ ስብእናቸው ምሉእ አርአያ ይሆኑ ዘንድ በፈጣሪ ተመረጡ። ሁሉንም የሰው ልጅ ሚና በምሉእነት ኖረው አሳዩ።
የአባትነት እዝነት፣ የባልነት ደግነት፣ የሃገር መሪ ፍትሃዊነት፣ የጦር መሪ ብቃት፣ የኃይማኖት መሪ ጥበብ፣ የነጋዴ ታማኝነት፣… በአጠቃለይ በበርካታ ታላቅ ነቢያትና የለውጥ ኃዋሪያት ላይ ተበታትነው የምናገኛቸው ከፍ ያሉ ስብእናቸው እርሳቸው ላይ ሰፍረዋል።
“አንተም በታላቅ ጠባይ ላይ ነህ፡፡” (አል-ቀለም፡4) ሲል ያወደሳቸው ምስጢሩ ይኸው ነው፤ ምሉእ ስብእና።
መዲና ውስጥ የተከሰተ አንድ ክስተት ታወሰኝ። ጉዳዩ እንዲህ ነው፦
የአንድ የነቢዩ ባልደረባ የጦር ልብስ ይሰረቃል፤ የሰረቀው አንድ ከሙስሊሞች ወገን እንደሆነ የሚታወቅ ሰው ነው። የሰውዬውን ማንነት ነቢዩ እንዳወቁ የተረዳው ይህ ሰው ወንጀሉን በአንድ አይሁድ ለማላከክ የሚያስችለውን ሴራ ያሰኤራል። የተሰረቀውን ንብረት ወደ አይሁዱ ጓሮ ጣለ፤ ከርሱ ጎሳ የሆኑ አራት ሰዎችን ጠራ፤ ጉዳዩን አብራራ፤ የጎሳቸውን ስም ማዳን እንዳለባቸው አሳመናቸው፤ አሁኑኑ ሄደው ንብረቱን የሰረቀው አይሁዱ መሆኑን እንዲመሰክሩ ወተወታቸው፤ ሶስቱ ሃሳቡን ተቀብለው ነቢዩ ሙሐመድ ዘንድ መሰከሩ።
ነቢዩ ሙሐመድ የአይሁዱ ቤት እንዲበረበር አዘዙ። ንብረቱ ጓሮ ላይ ተገኘ። በተገኘው መረጃ መሰረት ወንጀለኛው አይሁዱ መሆኑንና ሙስሊሙ ነፃ መሆኑ ተገለፀ።
ይህ የሆነው ዒሻእ (የማታ) ሶላት ላይ ነው። ነቢዩ ሙሐመድ ለንጋት ሶላት ሲመጡ ሌላ ዜና ነበር። ፍትህ ከኃይማኖትም ከጎሳም በላይ በመሆኑ እነኛ በሃሰት የወነጀሉትን ሰዎች ድብቅ ሴራ የሚያጋልጥና የአይሁዱን ንፅህና የሚመሰክሩ የቁርአን አናቅፅ በነቢዩ ሙሐመድ ላይ ወርደው ነበር። አል-ኒሳእ፡105-115) ድረስ ይህንን ክስተት የሚያብራሩ አንቀፆች ናቸው።
የአይሁዱን ንፅህና የሚመሰክረው አንቀፅ እንዲህ ይነበባል፦
“ኀጢአትን ወይም አበሳን የሚሠራም ሰው ከዚያም በእርሱ ንጹሕን ሰው የሚሰድብ ቅጥፈትንና ግልጽ አበሳን በቁርጥ ተሸከመ፡፡” (አል-ኒሳእ፡ 112)
ዓለማችን ካለችበት ውጥንቅጥ ትድን ዘንድ የርሳቸውን አርአያነት በእጅጉ ትሻለች። ያን አርአያ ኖሮ ማሳየት ደግሞ የዘመኑ ሙስሊም ተልእኮ ነው።
“(ሙሐመድ ሆይ!) ለዓለማትም እዝነት አድርገን እንጅ አልላክንህም፡፡” (አል-አንቢያእ፡ 107)
የተባሉት ነቢይ ተከታዮች የርሳቸውን ተልእኮ አንግበው ለዓለም እዝነት ሊሆኑ ግድ ይላል። መዳኛውም ማዳኛውም መንገድ ይኸው ብቻ ነውና።
ጌታዬ ሆይ! በእኝህ ታላቅ ነቢይና በባልደረቦቻቸው እንዲሁም በቤተሰቦቻቸው ላይ ሰላምና እዝነትን አውርድላቸው።
https://www.facebook.com/100044378775683/posts/pfbid0o95F4zLmiafgwzQGgNt1B886FCoqi5Znr9dWXM2QWMfbY8Kef7Eah4BbJw1EwDSel/